ከደራሲያን ዓምባ

Friday, March 15, 2024

የዱባይ ከተማ ግዙፍ ፍሬም

 


አሮጌው ዱባይንና አዲሱን ዱባይ ለመለየት የተሰራው ግዙፍ ፍሬም ።

Wasihune Tesfaye

...
ይህ በአለም ተወዳዳሪ የሌለው ግዙፍ ፍሬም ፡ ከዋናው ( አዲሱ ) ዱባይ በ7 ኪ/ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው አል ኪፋፍ በተባለው የከተማዋ ክፍል ይገኛል ።
....
ዱባዮች ይህንን የ150 ሜትር ቁመትና ፡ ወደጎን 90 ሜትር ስፋት ያለው ፡ በውስጡ ዘመናዊ ሊፍቶች የተገጠሙለትን የአለማችን ግዙፍ ፍሬም ሲሰሩ ያለምክንያት አልነበረም ።
....................
ብልህና አርቆ አሳቢዎቹ የዱባይ መሪዎች ፡ ገንዘብ እንደጉድ ሲጎርፍላቸው ያችን በበረሀ ላይ የነበረች ከተማቸውን መለወጥ ፈልገው ተነሱ ።
ይህን ሲያደርጉ ግን ያችን የድሮዋን ከተማ ቅርሶች እና ታሪካዊ ነገሮቿን ባጠቃላይ አፍርሰው ሳይሆን ፡ በትንሽ ኪሎ ሜትሮች ራቅ ብለው ነበር ።
 

.........
እና ያሰቡት ተሳክቶ ፡ ማመን በሚያስቸግር መልኩ ዱባይ በግዙፍ ህንጻዎች ተሞላች ።
ከዛስ. ...
ከተማዋን ለሚጎበኙ ቱሪስቶች የድሮዋን ዱባይን እና የአሁኗን ዱባይ መመልከት እንዲችሉ ይህንን ግዙፍ ፍሬም ገነቡ ።
አሁን እዚህ ፍሬም ላይ ወጥቶ መጎብኘት የቻለ ሰው ፡ ከወዲህ ፡ ያችን ጥንታዊ መደብሮች ፡ የቅመማ ቅመም ሱቆች ፡ ጥንታዊ ሙዚየሟን እና የጥንታዊቷ ዱባይ ገፅታን የሚያሳዩ አሮጌ ቤቶች ያሉባትን የድሮዋን ዱባይ እና ከወዲያ በኩል ደግሞ ቡርጅ ኻሊፋን እና መሰል ህንጻዎች ያሉባትን አዲሷን ዱባይ መመልከት ይችላል ።
 
 
......
ስለዱባይ ካነሳን አይቀር ፡ በቡርጅ ኻሊፋ ህንጻ ውስጥ ስለሚገኘው Burj Al Arab's Royal Suite ጥቂት ነገር እንበል ።
ይህ በህንጻው 25 ኛ ፎቅ ላይ የሚገኘው ፡ በአለም የቅንጦት ተብለው ከሚመደቡ ሆቴሎች መሀከል አንዱ የሆነው ሆቴል ፡ ከቅንጡነቱ የተነሳ ፡ የክፍሉ ኮርኒስ እና ግድግዳዎቹ ፡ በ24 ካራት ወርቅ የተለበጡ ናቸው ።
ይህ ብቻ አይደለም ፡ በነዚህ የቅንጦች ክፍሎች ውስጥ የሚገኘው ቴሌቪዥን ራሱ በ24 ካራት ወርቅ የተለበጠ ነው ።
 

.....
ወደ ፅሁፋችን መነሻ ስንመለስ ፡ አንድን ከተማ ፡ ዘመናዊ የሚያስብለው ፡ የነበረውን የድሮ ገፅታ እና የከተማዋ ታዋቂ ስፍራዎች፡ አፍርሶ በአዲስ በመተካት አይደለም ፡ ዱባዮች ከላይ ለንፅፅር ያመች ዘንድ እንዳየነው አይነት ግድግዳና ኮርኒሱ ወርቅ የሆነ ቤት መስራት ቢችሉም ያንን የትናንቱን ትውስታና ታሪክ ያለበትን አሮጌውን የከተማ ገፅታ ግን አልነኩትም ።
 
 

......
። የድሮው ለታሪክ ፡ ለትውስታ ፡ እና ለጎብኚዎች ተትቶ ከተማን አሮጌውና አዲሱ በማለት ከፍሎ እንዲህ እንደዱባዮች ማስቀመጥ ይቻል ነበር ።
.....
" በአንድ ወቅት ፒያሳ የሚባል ቦታ ነበር " ልንል በተቃረብንበት ጊዜ ላይ ሆነን በቁጭት የተጻፈ ❤️
photo - old dubai and new dubai

 

Tuesday, February 20, 2024

የካቲት12 ቀን 1929 የሰማዕታት ቀን

 

ወራሪዋ ጣልያን በአዲስ አበባ የፈጸመችው ጭፍጨፋ 

አርብ የካቲት 12 ቀን 1929 ዓ.ም.

፨፨፨(የየካቲት 12) የሰማዕታት ሐውልት፨፨፨
መታሰቢያነቱ - ፋሽስት ጣሊያን በወገኖቻችን ላይ ላደረሰው መከራና በግፍ 
በየካቲት 12 ቀን 1929 ዓ.ም. ለተጨፈጨፉ ኢትዮጵያውያን
የሐውልቱ ቀራጮች - አጉበቲን ሲች አንቶንና ከርሰኔች ፋራን 
የተባሉ የዩጎዝላቪያ ዜጎች ናቸው፡፡
ሐውልቱ የቆመበት ቦታ ዲያሜትር - 26 ሜትር
የሐውልቱ ቁመት - 28 ሜትር
መገኛ ሥፍራ - 6 ኪሎ

(ምንጭ ፡- ኅብረ ኢትዮጵያ ፣ ቴዎድሮስ በየነ)


 

“--አየህ! የዚያን ዕለት ብዙ ጣሊያኖች ብዙ ሥራ ሠርተዋል፡፡ ወደ ማታ ገደማ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ስንገናኝ፣ ጓደኛዬ ቦምብ ስጥል የዋልሁበት እጄ ዝሏል ብሎ ነገረኝ። አንዱ ኢጣሊያዊ ሲያጫውተኝ፣ ባንዲት ትንሽ ጣሳ በያዝኳት ቤንዚን አስር ቤቶች አቃጠልኩበት አለኝ፤ በዋናው ጦርነት ጊዜ ጥይት ተኩሰው የማያውቁት ጣሊያኖች ሁሉ በዚያን ቀን ሲተኩሱ ዋሉ--”

           ይህ አንድ ስሙ እንዳይገለጽ የፈለገ ኢጣሊያዊ፣ ለጓደኛው ለሲኞር ዲሰማን የነገረውና  የታሪክ ጸሐፊው አንጄሎ ዲል ቦኮ የመዘገበው ሲሆን ደራሲ ጳውሎስ ኞኞም  “ኢትዮጵያና የኢጣሊያ ጦርነት; በተባለው መጽሐፉ ታሪኩን ለእኛ አድርሶታል። የካቲት 12 ቀን 1929 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ላይ፣ በጣሊያን ወታደሮች የተፈጸመው ጭፍጨፋ ታሪክ ቀርቧል፤ በመጽሐፉ፡፡ በዚህ ወቅት በመዲናዋ  ለሦስት ተከታታይ ቀናት በጣልያን ጨካኝ ወታደሮች በተካሄደው ጭፍጨፋ፣ 30 ሺህ ሰዎች መገደላቸው ተዘግቧል፡፡ አንዳንዶች ይህ ቁጥር የሚታመን ነውን? የሚል ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡ ጥያቄውን ለመመለስ ከላይ የተጠቀሰውን ምስክርነት ይዘን፣ በወቅቱ በአዲስ አበባ የከተመውን የጣሊያን የጦር ሰራዊት ክምችት መመልከት ተገቢ ይሆናል።
ጳውሎስ ኞኞ፣  በወቅቱ የነበረውን የጣሊያን የወታደር ኃይል በመጽሐፉ ሲገልጽ፤ “35ሺ የጣሊያን ሜትሮ ፖሊታንት (የከተማው ወታደሮች)፣ 40ሺ ባለ ጥቁር ሸሚዝ ሚሊሺያ፣ 3ሺ የሊቢያ ተወላጅ ወታደሮች፣ 5ሺ የኤርትራ ወታደሮች ነበሩ፡፡; ብሏል፡፡ በተጨማሪም #የኤርትራ ተወላጅ ወታደሮች፤ “እኛ ወታደሮች ነን፤ መሳሪያ በሌለውና በሴት ላይ አንተኩስም” በማለታቸው ብዙዎቹ በሰፈራቸው ውስጥ ተገደሉ” ሲልም አክሎ ጽፏል፡፡ ከዚህ አንጻር 78ሺ የሚሆነውን የጣሊያን ሠራዊት፣ በጭፍጨፋው ላይ ከማሰማራት የሚያግደው ነገር አልነበረም፡፡
የኒፒልስ ልዕልት መውለዷን ምክንያት በማድረግ ጀኔራል ግራዚያኒ፣ ለድሆች ምፅዋት ለመስጠት በገነት ልዑል ቤተ መንግሥት፣ በአሁኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ግቢ፣ ድሆች  እንዲሰበሰቡ ጥሪ አድርጎ ነበር።   እስከ እኩለ ቀን ባለው ጊዜም ሶስት ሺህ የሚሆኑ ድሆች ተሰበሰቡ፡፡ በዚህ ፕሮግራም ላይ ሰላሳ የሚሆኑ የጣሊያን ከፍተኛ ሹማምንቶች ተገኝተዋል፡፡ ይህን አጋጣሚ ራሳቸውን እያዘጋጁ ይጠብቁ የነበሩት አብርሃ ደቦጭና ሞገስ አስገዶም፣ ከነሱ ጀርባ የተሰለፉት ንጉሠ ነገሥቱ አፄ ኃይለ ሥላሴን ጨምሮ፣ ብዙዎች ጄኔራል ግራዚያኒን በመግደል፣ የጣሊያንን የወራሪነት ቅስም ለመስበር ቆርጠው ተነሱ፡፡ ጄኔራል  ግራዚያኒ፣ ለድሆችና በቦታው ለተገኙ ሰዎች ንግግር እያደረገ እያለ፣ እነ አብርሃም አከታትለው የእጅ ቦንብ ወረወሩ፡፡ ግራዚያኒ  ጀርባው ላይ ተመታ፡፡ የአዲስ አበባ ከንቲባ ጣሊያናዊው ጎይዶ ክርስቴና ሌሎች ሰላሳ ሰዎችም ቆሰሉ፡፡ ከሚወረወረው ቦምብ ለማምለጥ መሬት ላይ ተኝተው የነበሩት ከርቤጌሮች ከተኙበት ተነስተው ተኩስ ከፈቱ፡፡ ያገኙትን አበሻ ሁሉ እንዲገድሉ ከንቲባ ጐይዶ ክርስቴ ትእዛዝ ሰጠ፡፡ የጣሊያን ሹፌሮች ሳይቀሩ በአዲስ አበባ ከተማ እየተዟዟሩ ሕዝቡን ፈጁት፡፡ የቤተ መንግሥቱ ዙሪያ መንገዶች በሬሳ ተሞሉ። የመዲናዋ ቤቶች ከነዋሪዎቹ ጋር በእሳት ነደዱ፡፡ ነፍሳቸውን ለማትረፍ የሚሞክሩ ሰዎች እየተያዙ፣ ቤት እየተዘጋባቸው እንዲቃጠሉ ተደረገ፡፡ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በተካሄደው በዚህ ጭፍጨፋ፣ ሰላሳ ሺህ ሰዎች እንደተገደሉ ነው የተመዘገበው፡፡  
እኔ በዚህ ቁጥር አልስማማም፡፡ መግቢያው ላይ ያሰፈርኩትን ምስክርነት ይዞ ነገሩን የሚገመግም ሰውም ይስማማል ብዬ አልጠብቅም፡፡ ከጣሊያን ጦር ውስጥ ከ15ሺ እስከ 20ሺ  የሚሆነው ለሰፈር ጥበቃ እንዲቀር ቢደረግና  ቀሪው ሃምሳ ሺህ ወታደር እንኳን አንድ አንድ ሰው ቢገድል፣ ያለ ጥርጥር  የተጨፈጨፉት ኢትዮጵያዊያን ቁጥር ሃምሳ ሺህ ይደርሳል፡፡ 


አዲስ ዘመን ጋዜጣ በአንድ ወቅት አዲስ አበባ ውስጥ የነበሩ የዓይን ምስክርን አነጋግሮ፣ የሟቾቹ  ቁጥር ከሀምሳ ሺህ እስከ ሰማኒያ ሺህ ሊደርሱ እንደሚችሉ በመጠቆም መዘገቡን አስታውሳለሁ። እኒህ ሰው እንደተባለው ጭፍጨፋው በሦስት ቀናት ውስጥ አለመቆሙንና ለወር ያህል መዝለቁንም ተናግረዋል፡፡  ከዚህ አንጻር የየካቲት ሰማዕታት ቁጥር 30 ሺህ ነው ማለት ትክክል አይመስለኝም፡፡ የደብረ ሊባኖስ መነኮሳት እልቂትም ሊዘነጋ አይገባም፡፡ የየካቲት 12 አንድ ገጽታ ነውና፡፡
ከሃምሳ ሺህ ሰዎች በላይ የተጨፈጨፉበት፣ ከአስር ሺህ በላይ ደግሞ ደናኔ ተወስደው በእስርና በበሽታ እንዲያለቁ የተደረገበት የየካቲት 12 ቀን መስዋዕትነት በከንቱ አልቀረም፡፡ ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም ለኢጣሊያ መንግሥት አልገዛም በማለታቸው፣ በአደባባይ በጥይት ተደብድበው በተገደሉት በአቡነ ጴጥሮስ ሞት ያኮረፈውን የአዲስ አበባን ነዋሪ፣ በየካቲት 12 ጭፍጨፋ፣ ጨርሶ ልቡ እንዲቆርጥና እንዲነሳሳ አድርጎታል። እጅግ የሚበዛውም ፊቱን ወደ አርበኝነት አዞረ፡፡ በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ሳይቀር ለነፃነት በሚደረገው ትግል፣ የውስጥ አርበኛው እየተናበበ ሔደ፡፡
እንደ ሚያዚያ 27 የድል ቀን ሁሉ፣ በየዓመቱ ብሔራዊ በዓል ሆኖ ሲከበር የነበረው የየካቲት 12 ሰማዕታት ቀን፣ እየታሰበ መዋል ከጀመረ አርባ ስድስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት አንድም የመንግሥት ባለሥልጣንም ሆነ መንግሥት ወደ ቀድሞ ክብሩ ሊመልሰው አልቻለም፡፡  
“ኢትዮጵያ የቆመችው በልጆቿ መስዋዕትነት ነው; እያልን እንዴት  ዓመታዊ  የሰማዕታት ቀን አይኖረንም?
ከ1928 እስከ 1933 ዓ.ም ድረስ በዱር በገደሉ ደማቸውን አፍስሰው፣ አጥንታቸውን ከስክሰው ነፃነታችን ተከብሮ እንዲቆይ ያደረጉ የአምስት ዓመቱ አርበኞች፣ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊያን ሰማዕት ናቸው፡፡
ሁለት ጊዜ የተቃጣውን የሞቃዲሾ ወረራ የመከቱ፣ የተጣሰውን ድንበር ያስከበሩና የሀገር ታሪክ እንዳይደፈር የተሰዉ ወገኖቻችን ሰማዕቶቻችን ናቸው፡፡
የጦርነቱ ምክንያት በግልጽ ባይታወቅም፣ ከኤርትራ ጋር በተቀሰቀሰው ጦርነት፣ ከአካል እስከ ሕይወት መስዋዕትነት የከፈሉ ወገኖቻችን ለሀገራችን ሰማዕት ናቸው፡፡
 ሰማዕታት ትናንትም ዛሬም አሉን፤ነገም መስዋዕትነት የሚከፍሉና ሰማዕታት የሚሆኑ ወገኖቻችንን  የምንዘክርበት የሰማዕታት ቀን የሚኖረን መቼ ነው? ሺህ ጊዜ የሚነሳ ጥያቄ! 

                              ስድስት ኪሎ የሚገኘው የካቲት 12 የሰማዕታት ሃውልት ላይ

https://www.addisadmassnews.com/ 

Written by  አያሌው አስረስ Saturday, 20 February 2021

***********

የካቲት 12 እና የግራዚያኒ አዲስ አበባ

ህላዊ ሰውነት በሻህ (አርኪቴክት)
Helawi Sewnet Beshah (Architect) 
ጣሊያን ኢትዮጵያ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ወረራ አድርጎ ለአምስት አመት በተቆጣጠረበት ወቅት 1929 ዓ.ም. በየካቲት 12 እለተ አርብ ነበር። የአጼ ሀይለስላሴን ወደ እንግሊዝ መሰደድ ተከትሎ እና የሙሶሊኒን የቅኝ ግዛት ህልም እንዲያሳካ የኢትዮጵያ አስተዳዳሪ ሆኖ የተሾመው ግራዚያኒ፣ የኔፕልሱን ልዑል መወለድ አስመልክቶ ለችግርተኛ ቤተሰቦች ገንዘብ እሰጣለሁ ብሎ በገነተ ልዑል ቤተመንግስት (የዛሬው አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ስድስት ኪሎ ግቢ) በርካታ እንግዶች በተገኙበት በአዲስ አበባ ከተማ በድህነት ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች እንዲሰበሰቡ አዘዘ። ከተጋባዥ እንግዶቹም መካከል የጣልያን ሹማምንት የሜትሮፖሊታን ጳጳስ አቡነ ኪርል እና ሌሎች የኢትዮጵያ መኳንንቶች ተገኝተው ነበር።

ብራማ በነበረችው በዛች የወረሃ የካቲት አርብ የተገኙትም ኢትዮጵያውያን ከጠዋት ጀምረው አንድ በአንድ ቤተመንግስቱ ግቢ መሰብሰብ ጀመሩ። እስከረፋዱም ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ሶስት ሺህ ያህል ነዋሪዎች በተገኙበት የግራዚያኒ መረሃ ግብር ተጀመረ። የዕለቱ አጀማመር ሲታይ ሊመጣ ያለውን የሀዘን ድባብ የገመተ ሰው ይኖራል ብሎ ለማሰብ ያዳግታል። ጥቂት ቆይቶ እኩለ ቀን ገደማ ሊሆን አካባቢ በዋናው በር በኩል ቦንብ ፈነዳ፣ ሁለተኛም ፈነዳ። ገነተ ልዑል ቤተመንግስት ከየአቅጣጫው ጩኸት አስተጋባ። ሶስተኛ ቦብም ግራዚያኒ እና መኳንንቱ ከተቀመጡበት ጠረጴዛ አጠገብ ሲወረወር ግራዚያኒ ጠረጴዛ ስር ወደቀ። የተወሰኑ የጣልያኖቹን ሹማምንት መታ።

ቦምቡን የጣለው ከጣልያኖቹ ዘንድ በአስተርጉዋሚነት ይሰራ የነበረ አብርሃ ደቦጭ እና ጓደኛው ሞገስ አስገዶም የሚባሉ የኤርትራ ክፍለሀገር ተወላጅ ወጣቶች ነበሩ። በጥቅሉ ሰባት ቦምቦች ፈነዱ። ወዲያው ካርቴሲ ወደኢትዮጵያውያኑ መኩዋንንት ሽጉጡን አነጣጥሮ የመጀመሪያዋን አንድ ጥይት ተኮሰ። ካራ ቢኔሬዎችም (የጣሊያን የሲቪል ጠባቂዎች) ምሳሌውን ተከተሉ። በጥቂት ጊዜ ውስጥም ሶስት መቶ ሬሳዎች በዛ ግቢ ውስጥ ተከመሩ። ሀይለኛና ተገቢ ያልሆነ ጭፍጨፋ ነበር። ሽማግሌዎች፣ አይነስውራን፣ እግር የሌላቸው ለማኞች፣ ድሆች እናቶች እስከልጆቻቸው ነበሩበት። ሰላሳ ያህል ሰዎች ቆሰሉ። ለሶስት ሰአታት ያህል ያለቋረጥ በግቢው ውስጥ ተኩስ ተከፈተ። ከጥቂት ጊዜ በሁዋላ ባለጥቁር ሸሚዞች፣ የጣልያን ሾፌሮች የቅኝ ግዛቱ ወታደሮች በአዲስ አበባ ከተማ እየዞሩ ህዝቡን ይፈጁት ጀመር።

እዚህ ቀን ላይ እንዴት ተደረሰ የሚለውን ታሪካዊ ዳራ ወደኋላ መለስ ብለን እንመልከት። አውሮፓውያን በ1877 ዓ.ም. በጀርመን በርሊኑ ኮንፈረንስ ተገናኝተው አፍሪካን አንደቅርጫ ከተከፋፈሏት ከ11 ዓመታት በኋላ ጣልያን ኢትዮጵያን ቅኝ ለመግዛት ስትመጣ አድዋ ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ድል ትደረጋለች። አንድ ትውልድ አልፎ ከአርባ አመታት ቆይታ በኋላ በስልጣን ላይ የነበረው የጣልያኑ ፋሽስት ሙሶሎኒ የአድዋን ቁጭት ባለመርሳቱ ከበቀል ጋር ዘመናዊ የሆነ የአየርና የምድር ጦሩን ይዞ ኢትዮጵያ በድጋሚ መጣ። በዚህ ወቅት የጣሊያን ጦር ለኢትዮጵያ ሰራዊት ብርቱ ስለሆነበት አጼ ሃይለስላሴ በሚያዝያ (May 2, 1936) ጠዋት ከአገር ይሰደዳሉ። የጣሊያኑ ሙሶሊኒም ኢትዮጵያን በስተመጨረሻ በእጁ እንዳስገባ በሮማ ለተሰበሰበው ህዝቡ በደስታ አዋጁን አሰማ።

የኢትዮጵያን ጦር ማይጨው ላይ መሸነፍ እና እንዲሁም የንጉሱን ከአገር መውጣት ተከትሎ የጣሊያኑ አስተዳደር አዲስ አበባ እስኪገባ ድረስ በመሀል በተፈጠረው ክፍተት መዲናዋ ክፉኛ በተደራጁ ሌቦች ተዘረፈች፣ ጣሊያኖቹ እንዳይጠቀሙ በሚል ብዙ ህንጻዎችም በግለሰቦች ተቃጠሉ፣ ፈረሱ። ሙሶሊኒ ከጣሊያን በሰጠው ቀጥተኛ ትእዛዝ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የቅጣት እርምጃ አስወሰደ። ጉዳት የደረሰባት አዲስ አበባም ለወራሪዎቹ መልካም አቀባበል ያደረገች ምቹ ከተማ አልሆነችላቸውም። የጣሊያኑ ኮማንደር ባዶግሊዮ ወዲያውኑ ለሮም በላከው ቴሌግራም ላይ ሙሶሊኒ ወደኢትዮጵያ በስድስት ወራት ውስጥ ሊልካቸው ያሉትን የጣሊያናዊ ቤተሰቦች ዕቅድ ትንሽ እንዲቆጥበው መልዕክቱን አደረሰ። አዲስ አበባም የአዲሱ የፋሺስት ግዛት መዲና የመሆኗ የወደፊት ዕጣ ፈንታ አነጋጋሪ ሆነ።

የጣሊያንን መንግስት ከሚያማክሩት ባለሙያዎች ውስጥ አብዛኞቹ አዲስ አበባን መዲና አድርጎ ማስቀጠል ስህተት እንደሚሆን አስጠነቀቁ። በሸለቆዎች የተሰነጣጠቀው ተራራና ኮረብታማ የመልከአ ምድሯ አቀማመጥና ከፍታማነት አድካሚ እና ለጉልበት ስራ አዳጋች እንደሚሆንባቸው እንዲሁም ዘርዘር ያለው የከተማዋ አሰፋፈር ለትራንስፖርት ፈተና እንደሚሆን ቅሬታዎች ቀረቡ። የአፈሩ ባህሪ ተንሸራታችነት ለመሰረት ግንባታ የሚኖረው ተግዳሮት እንዲሁም የነበረው በርካታ የባህር ዛፍ ደን ለኢትዮጵያ ሽፍቶችና ታጋዮች ምሽግ እንደሚሆን ጣሊያኖቹ ሰጉ። ከሁሉም በላይ ግን በአዲስ አበባ የነበረው ብዝሃ ጥቁር አፍሪካዊና ኢትዮጵያዊ ህዝብን አፈናቅሎ ወደሌላ ቦታ ለማስፈርና የቅኝ ገዢዎቹን የመከፋፈል ፖሊሲ ለማራመድ ፈተና እንደሚሆንና እንደፋሺስቱ አመለካከት ከአገሬው ተወላጅ አሻራ የጸዳ አዲስ ከተማ መቆርቆር እንደሚያስፈልግ አመላከቱ። ለአዲስ መዲናነት ደሴ፣ ሞጆ፣ ነቀምት እና ሐረር እንደ አማራጭነት ቀረቡ። ነገር ግን በሙሶሊኒ እይታ ከአዲስ አበባ ውጪ የሆነ የዋና ከተማ ሀይሉን እና ክብሩን ለማሳየት በፍጹም አማራጭ እንደማይሆን ከለንደኑ ዴይሊ ቴሌግራፍ ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅ ይፋ ቢያደርግም ብዙ የቅኝ ግዛት ሹማምንቶቹ ሀሳቡን ይቀይራል የሚል ተስፋ ነበራቸው።

በመጀመሪያዎቹ ወራት የፋሽስቱ አስተዳደር የህዝብ የመንገድ ዳር ምልክቶች በጣልያንኛ ተተርጉመው እንዲጻፉ ተደረገ። የዋና ጎዳናዎች ስሞችም በሙሶሊኒ መንግስት ውስጥ በነበሩ አንዳንድ አመራሮች ስም ተሰየሙ። በየቦታውም ሆነ በየቤቱ የሙሶሊኒ ምስል እና በአንዳንድ ቦታዎች ለህዝቡ ፕሮፖጋንዳ የሚያስተላልፉ የድምጽ ማጉያዎች ተሰቀሉ። ከዚህ ጋር ተያይዞ ፋሺስቶቹ ከኢትዮጵያ ነጻነት ጋር የተያያዙ ምስሎች እና ሀውልቶችን ማስወገድ ላይ ተጠመዱ። ከነዚህም ውስጥ አራዳ ጊዮርጊስ አደባባይ ላይ የሚገኘው የምንሊክ ፈረስ ጋላቢ ሀውልት፣ ታላቁ ቤተመንግስት አጠገብ ያለው የባእታ ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገኘው የምኒሊክ መቃብር፣ ለገሀር ባቡር ጣቢያ ፊት ለፊት የቆመው የይሁዳ አንበሳ ሀውልት፣ በወቅቱ አዲስ አበባ ላይ የነበረ የአክሱም ሀውልት አምሳያ፣ የስላሴ ኮኮብ ሀውልት፣ እና በርካታ በወቅቱና ቀደምት የነበሩ መሪዎች ምስሎችን ያካትታል። ሙሶሊኒም በቴሌግራፍ በላከው መልዕክት “የምኒሊክ ሀውልትን መፈንዳት ይኖርበታል” ሲል አቅጣጫውን አስቀመጠ።

በወቅቱ የአገሪቱ ተጠባባቂ ገዢ ሆኖ ወደአዲስ አበባ የመጣውና በቅጽል ስሙ “የሊቢያ ጅብ” በመባል ይታወቅ የነበረው የቀድሞ ወታደሩ ግራዚያኒ ከሀውልቶቹ ጋር ተያይዞ የተሰጠውን ትዕዛዝ ለመፈጸም በማቅማማት ለጣልያኑ የቅኝ ግዛቶች ሚንስትር እንዲህ የሚል ቴሌግራፍ መልዕክት ላከ። “አዲስ አበባ እንደመጣሁ የምኒሊክ እና የይሁዳ አንበሳ ሐውልት አልተነሱም ነበር፤ ማንም የክቡርነትዎን ትዕዛዝም አላስተላለፈልኝም ነበር። ነገር ግን አሁን እንዲህ አይነቱ እርምጃ ማስተዋል ያለበት አይመስለኝም፣ በተለይ ተከትሎኝ ከመጣው መጥፎ ስሜ አንጻር። እናም ስኬታማ የሆነ ፖለቲካዊ ውጤት የማመጣ ከሆነ የበረደ አካሄድ መከተል ይኖርብኛል፤ በተለይ የዚህ አይነቱ እርምጃ ከሚነጥለን ከቤተክህነት ጋር፣” በማለት ስጋቱን ገለጸ።

በእንደዚህ አይነት ምክንያት ያልተደነቀው ሙሶሊኒ፣ ውሳኔው በአፋጣኝ እንዲፈጸምለት በድጋሚ ስላዘዘ በሀያ አራት ሰዐት ውስጥ የምኒሊክን እና የይሁዳ አንበሳን ሐውልት እንድታነሳ የሚል ትዕዛዝ ለግራዚያኒ በቴሌግራፍ ደረሰው። ከእንደዚህ አይነት ዱብ እዳ ጋር የተጋፈጠው ግራዚያኒ ትዕዛዙን እንደሚፈጽም ነገር ግን ጊዜ እንደሚያስፈልገው ጠቅሶ ለቅኝ ግዛት ሚንስትር ድኤታው ጻፈ። “እለምንዎታለሁ ክቡርነትዎ፤ የሚንስትሩን ትዕዛዝ እንደምፈጽም ያረጋግጡልኝ። ነገር ግን ሁለቱም ሀውልቶች በርካታ ቶን የሚመዝኑ እንደመሆናቸው፣ ከቆሙበት የማንሳቱ ስራ ባለሙያዎችን እና በርካታ ቀናት ይፈልጋል፣” ሲል በድጋሚ ተማጸነ። ከበርካታ ወራት በኋላ ስራው በጥቅምት 6 ሌሊት ላይ ተጠናቀቀ።

ኢትዮጵያውያኑ ከእንቅልፋቸው ተነስተው የምኒሊክን ሀውልት መነሳት ሲያዩ እጅግ ተቆጡ። በአደባባይ ላይ በርካቶች በእንባ ተራጩ። “ምኒሊክን አበቃ። በሌሊት ሰረቁት” ሲሉ አለቀሱ። ህዝቡ ሲሰበሰብ የጣሊያን ወታደሮች በሳንጃ ያባርሯቸው ጀመር። ይህም የሀውልቶቹን መነሳት ተከትሎ የተፈጠረው የኢትዮጵያውያኑ ፀረ ፋሽስት ተአማኒ ስሜት ዜና የጣሊያን መንግስት ጋር ደርሶ ብስጭት ፈጠረ። ግራዚያኒም ከሳምንታት በኋላ በእርምጃ እንደተቆጣጠረው አሳወቀ። በወቅቱ የነበረ አንድ ስዊድናዊ ከአመት በኋላ እንደተናገረው፣ ኢትዮጵያውያኑ እርስ በእርሳቸው ስለጣሊያኖቹ “መንፈሱን እራሱ ይፈሩታል። አድዋን እኛ እንደምናስታውሰው ነው የሚያስታውሱት፤” እያሉ እንደሚንሾካሾኩ ምልከታውን ገልጿል። የኢትዮጵያውያኑም ተቃውሞ እና ትግል በየቦታው ቀጠለ።

እናም በዚህ ሁኔታ ከወራት በኋላ አብርሃና ሞገስ በዳግማዊ ምንሊክ ትምህርት ቤት ትምህርታቸውን ለመከታተል የመጡት። አብርሃ በጽኑ የጣሊያኖቹን ዘረኛ ተግባራት ይቃወም ስለነበር ትግሉን ተቀላቅሎ ግራዚያኒን ከግብረአበሮቹ ጋር ለመግደል ሙከራ ያደረገው። በግራዚያኒም አጸፋ ሰላሳ ሺህ ያህል ንጹሀን ተገደሉ፤ ክስተቱም በኢትዮጵያ ታሪክ እጅግ አስከፊ የነበረ ጭፍጨፋ ሆነ።

ለማጠቃለል፣ አዲስ አበባ ከአድዋ ድል ማግስት ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎችና ከውጭ ሀገራት በመምጣት ሀብትና ንብረት አፍርቶ እየኖረ የነበረው እንዲሁም በከተማዋ እየተበራከተ በመጣውና በተለያዩ የንግድ እና የማህበራዊ አገልግሎት ስራ መስኮች ላይ በተሰማራው የከተማዋ ነዋሪ ቅሬታ አማካኝነት አጼ ምኒሊክ ወደ አዲስ አለም ከተማ ሄዶ አዲስ መዲና የመቆርቆር እቅዳቸውን ሊቀለበስ ችሎ ነበር። በተመሳሳይ ሁኔታም፣ ከአርባ አመት በኋላ የጣሊያን መንግስት ኢትዮጵያን በወረረበት ጊዜ፣ በርካታ የሙሶሊኒ መንግስት አማካሪዎች አዲስ አበባን ትተው አዲስ ከተማ እንዲቆረቆር ቢጎተጉቱትም ሙሶሊኒ አሻፈረኝ በማለቱ አዲስ አበባም አሁን ላለችበት ትሩፋትና ማንነት የካቲት 12 እና በወቅቱ የነበረው የግራዚያኒ አስተዳደር የራሱን አሻራ ጥሎ ሊሄድ ችሏል። ለዚህም ነው የከተማ ቅርስ ስላለፈው ታሪካችን፣ ባህላችን እና ስለማህበረሰባችን ዝግመተ ለውጥ ፍንጮች የሚሰጠን መስኮት ነው የምንለው። ቸር እንሰንብት!

https://ketemajournal.com/issue/

*******************************

ምላሹ የዘገየው የኢትዮጵያዊያን የካሳ እና ይቅርታ ጥያቄ ፣ወደ ቫቲካን ሰዎች

ከያኔው ገነተ-ልዑል ቤተመንግስት፣ከዛሬው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዝቅ ብሎ ኢትዮጵያ መቼም የማትዘነጋውን የእልቂት ቀን የሚዘክር ባለ 28 ሜትር ሃውልት አለ፡፡

በያመቱ ኢትዮጵያዊያን በዚህ ስፍራ የካቲት 12 ቀን ይሰበሰባሉ፡፡አባት እና እናት አርበኞች "እመ-ሰቆቃ" ግራዚያኒን በቀረርቶ ያወግዛሉ፣አምስት አመት ጣልያን ታግለው ለሀገሪቱ ዳግም ነጻነትን ያመጡትን ጀግኖች እያነሳሱ በፉከራ ያሞግሳሉ፡፡አንዳንዶቹ ደግሞ የዚህ ሁሉ በደል ፈጻሚ ሀገር መቼ ይሆን ይፋዊ ይቅርታ የምትጠይቀው? እጃቸው ያለበት አካላትስ የካሳ ከረጢታቸው መቼ ይሆን የሚፈታው ? ሲሉ ከንፈራቸውን ይነክሳሉ ::

የካሳ እና ይቅርታ ዘመቻ ወደ ቫቲካን ሰዎች

የሙዚቃ መሳሪያ እስከ አፍንጫው የታጠቀ የማርሽ ባንድ ሰራዊት፣ከተለያዩ ትምህርት ቤቶች የመጡ ብላቴናዎች ክያኔ፣ለዝክር የመጣው ሰው ስነ-ስርዓቱ ካለቀ በኋላ ቤቱ ገብቶ የሚያወራው አዲስ ነገር አሳጥተውት አያውቁም፡፡

የ2002 ዓመተ ምህረቱ የሰማዕታት ቀን ማግስት አዲስ ነገርን በተመለከተ በአያሌው ዕድለኛ ሳይሆን አልቀረም፡፡

አዲስ አበባ ጀግኖችን አሞግሳ ፤ለሰማዕታት የነፍስ ይማር ጸሎት አድርሳ በተመለሰች ማግስት፣ የካቲት 29-2002 ዓ.ም ፣ መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገው ‹ዓለማቀፍ ህብረት ለፍትህ -ለኢትዮጵያዊያን ጉዳይ› የተሰኘ ተቋም በመላው ዓለም የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና የኢትዮጵያ ወዳጆችን ትብብር የሚጠይቅ የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ ይፋ አደረገ።

የዘመቻውን ይዘት ከሚያብራራው ጥራዝ ላይ ትንሽ እንቆንጥር፣

"በ1935-41(እኤአ) ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ወርራ ባደረሰችው አሰቃቂ የጦር ወንጀል፣ የቫቲካን መንግስት እጅ ከጓንት ሆና ተባባሪ ስለነበረች፤የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ እንድትጠይቅ ተጽዕኖ እንዲደረግባት ፣ለዓለማቀፋዊው ህብረተሰብ ፣በዓለም ላሉ መንግስታት ሁሉ ፣ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ፤ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣….ለሌሎች ለሚመለከታቸው ድርጅቶችና ለእውነት ለቆሙ ህዝቦች ድጋፋቸውን እንዲያበረክቱ አቤቱታችንን በታላቅ ትህትና እናቀርባለን፡፡"

የዘመቻው ተጽዕኖ ውጤታማ ይሆን ዘንድ፣ 100ሺ ሰዎች ፊርማቸውን እንዲያኖሩ ተቋሙ በወቅቱ ጠይቋል።

ስምንት ዓመታት አለፉ፣ዘመቻውን የተቀላቀሉ ሰዎች ቁጥር 7ሺ አልሞላም፣ቫቲካንም ይቅርታ አልጠየቀችም።

የቫቲካን ዝምታ …የአረጋዊው ቁጭት

ዘመቻው ይፋ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በየአደባባዩ ብቅ እያሉ የዘመቻውን አስፈላጊነት ለማስረዳት ሲለፉ የሚታዩ አረጋዊ አሉ። እኝህ ሰው "ዓለማቀፍ ህብረት ለፍትህ -ለኢትዮጵያዊያን ጉዳይ" የተሰኘው ተቋም ሀላፊ ኪዳኔ ዓለማየሁ ናቸው ፡፡

የታለመው የፈራሚ ብዛት ካለመስመሩ ጎን ለጎን፣ ቫቲካን ካለወትዋች እስከአሁን ኢትጵያዊያንን ይቅርታ አለመጠየቋ አይወጥላቸውም ፣"ናዚዎች በአይሁዶች ላይ እልቂት ሲፈጽሙ ቫቲካን ዝም በማለቷ ብቻ በክርስቲያናዊ ትህትና አይሁዶችን ይቅርታ ጠይቃለች ፣" ሲሉ የሚያነሱት አቶ ኪዳኔ ፣« እንደ ክርስቲያን ድርጅት ለፈፀሙት የወንጀል ተባባሪነት ይቅርታ መጠየቅ አይበዛባቸውም። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሀገር ስለሆነች ይሆን ወደኃላ የሚሉት?ግራ የሚያጋባ ጉዳይ ነው፣›› ሲሉ ጥያቄ ይመዛሉ፡፡

የተቋማቸውን ስልክ የመታ ሰው ከሚነሳቸው ጥያቄዎች አንዱ ቫቲካን በኢትዮጵያዊያን እልቂት ውስጥ ያላት ተሳትፎ ምን ያህል ነው? የሚል ነው፡፡ ከሌላኛው ጫፍ ብዙ ጊዜ የማይጠፉት አቶ ኪዳኔ የቫቲካንን ተሳትፎ ፤ የይቅርታውን አስፈላጊነት ለማስረዳት አይታክቱም።

"ፋሽስት ኢጣልያ ኢትዮጵያን በወረረች ጊዜ ብዙ ወንጀሎች ተፈፅመዋል። አንድ ሚሊየን ኢትዮጵያዊያን ተጨፍጭፈዋል፣ከዚያ ውስጥ በአዲስ አበባ በሶስት ቀናት ብቻ 30ሺ ሰዎች ተጨፍጭፈዋል፣ ከ2ሺ በላይ ቤተ-ክርስቲያኖችና 525ሺ ቤቶች ወድመዋል። ፋሽስት ጣልያኖች ብዙ ዝርፊያ፣ስደት እና እንግልት በኢትዮጵያዊያን ላይ አድርሰዋል።እንዲያ በሚሆንበት ጊዜ ቫቲካኖች ፋሽስት ጣልያኖችን ደግፈዋል፣ባርከዋል ቀድሰዋል፣" ሲሉ በቁጭት ይናገራሉ።

አቶ ኪዳኔ ዓለማየሁ ከታሪክ አዋቂዎች፣ ከንጉሳዊያን ቤተሰቦች፣ ከሃይማኖት አባቶች እና ከሌሎች የኢትዮጵያ ወዳጆች ጋር በመሆን ያቋቋሙት ተቋም፣ ቫቲካን ይቅርታ ትጠይቅ ዘንድ የሚለፋው -ይቅርታው ለኢትዮጵያዊያን ስነልቦናዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ ካሳን ብሎም ዓለማቀፋዊ ዕውቅና እንደሚያመጣ በማመን እንደሆነ ያብራራሉ።

በተቀናጀ ዘመቻ አቤቱታቸውን ያሰሙ ህዝቦች ለተገቢ ካሳ መብቃታቸውንም ለአብነት ይዘረዝራሉ፣"ጣልያኖች 30ሺ ሊቢያዊያንን በመጨፍጨፋቸው ፣ለዚህ አድራጎታቸው 5 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ካሳ (በልማት ስራ መልኩ) ለመክፈል ተስማምተዋል፣" በማለት ካለመናገር ደጅ አዝማችነታችን እንዴት እንደተነፈገ ያሰምራሉ፡፡

ይሄ ዘመቻ እንደ ኢትዮጵያ መንግስት እና የጥንታዊ ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ያሉትን ተቋማት ድጋፍ ቢያገኝ ኖሮ ውጤቱ ይፈጥን እንደነበረ የሚያነሳሱት አቶ ኪዳኔ ፣ዘመቻው ከታለመው የፈራሚዎች ቁጥር እስከ አሁን ድረስ አንድ አስረኛውን አለማግኘቱ የፈጠረባቸውን ቅሬታ አይሸሸጉም፡፡

"ዲፕሎማሲን " የሚመክረው የአርበኞች ማህበር

"በደም እና አጥንት ግብር " ሀገራቸውን ያቆዩ እናትና አባት አርበኞች ያቋቋሙት "የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር" በስምንት ዓመታት ውስጥ የተለያዩ ለውጦችን አስተናግዷል፡፡

ጥቂት የማይባሉት አባላቱን በሞት ተለይተዋል፣ የአስተዳደር ሽግሽግም ተፈጽሟል፡፡ የዛሬ ስምንት ዓመት ማህበሩን ይመሩ የነበሩት ሊቀ-ትጉሃን አስታጥቄ አባተ -በልጅ ዳንኤል ጆቴ መስፍን ተተክተዋል፡፡እንደነበር ከቀጠሉት አንዱ ወኔ ይመስላል፣በማህበሩ መሪ ድምጸት ውስጥ እንደሚሰማው ያለ፣

"የኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር የኢትዮጵያ ንብረት የሆነ ሚስማር ጭምር ያለአግባብ ሄዶ እንደሆነ 'ወደ ሀገሩ መመለስ አለበት' የሚል ፅኑ የሆነ፣ የማያወላውል አቋም አለው ፣" ይላሉ ልጅ ዳንኤል ጆቴ መስፍን የቫቲካን እና የይቅርታው ጉዳይ ሲነሳ፣ የጋለ ድምጸታቸው መልሶ ይሰክንና በተጀመረው አይነት መንገድ ካሳ እና ይቅርታን የመጠየቅ ሂደት ውስጥ ማህበራቸው ሊሳተፍ እንደማይችል ይናገራሉ። ለዚህ የሚሰጡት ምክንያት ማህበሩ የተመሰረተበት ህግና ደንብ ከላይ የተጠቀሰውን ዓይነት ዘመቻ ለመከወን የማያስችል መሆኑ ነው።

ከሁሉም ከሁሉም ግን የማህበሩ ፕሬዚደንት በግለሰቦች አስተባባሪነት እዚህ የደረሰው የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ ውጤታማ ስለመሆኑ ጥርጣሬ አላቸው።በጋርዮሽ ተፅዕኖ የመፍጠር ሙከራ ይልቅ በመንግስታት መካከል የሚደረግ ንግግር ፍቱን መፍትሄ እንደሚያመጣ ለማሳየት ባቀደ መልኩ፣ "የአክሱምን ሀውልት የኢትዮጵያ መከላከያ ሃይል ሄዶ አላመጣውም … ዲፕሎማሲ እንጂ" ይላሉ፡፡

ቫቲካን 'አላት'የሚባለውን የግፍ ተሳትፎንም ልጅ ዳንኤል ጆቴ ይጠራጠሩታል፣ "እኛ እንደምንረዳው( የጣልያንን ጦር) ባርኮ የላከው ሚላኖ ላይ የነበረ ቄስ ነው። የአቶ ዘውዴ ረታን መፅሃፍ ላይ ራሱን የቻለ ታሪካዊ መግለጫ አለው(አቶ ዘውዴ ረታ አምባሳደር በነበሩበት ወቅት ተመራምረው እና ጥናት አድርገው የፃፉት መፅሃፍ ነው)። አንዳንድ ታሪኮችን በስሜታዊነት ተነስቶ ከማየት ርቀን፣ አንስተን እና አውርደን በደንብ ተዘጋጅተን የቀረብን ጊዜ ጣልያኖችም ሆነ እንግሊዞች ነገሮችን የማይመልሱበት ፣የተጠየቁትን የማያደርጉበት ምንም ምክንያት የለም፣"ሲሉ የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር በዘመቻው ላይ ያለውን የፍሬ ነገር ጥርጣሬ ያጋራሉ፡፡ 

"የኢትዮጵያ አምላክ፣ይረዳናል!"

በሰሜን አሜሪካ የሚገኘው ‹ዓለማቀፍ ህብረት ለፍትህ -ለኢትዮጵያዊያን ጉዳይ› ሃላፊ ኪዳኔ ዓለማየሁ ድምጽ ውስጥ ሀዘን ተጠልሏል፡፡በልጅ ዳንኤል ጆቴ በኩል የተሰጠው ምላሽ እንዳልተዋጠላቸው ያሳብቃል፡፡

"ለፍትህ ጉዳይ ሁላችንም ሃላፊነት አለብን።እንኳን እኛ ኢትዮጵያዊያኑ ይቅርና ጣልያኖች ሳይቀሩ እየደገፉት ያለ ጉዳይ ነው።በዚህ ጉዳይ ላይ ወደ ኋላ ማለት ለአገር የሚያኮራ ጉዳይ አይደለም፣" ሲሉ ይመክታሉ፡፡ የቫቲካን ተሳትፎ ላይ ጥያቄ መነሳቱም ቢሆን ለእሳቸው እንቆቅልሽ ነው፣ "ብዙሃኑ ጳጳሳት ወርቃቸውን ሳይቀር እያወጡ ለጦርነቱ አስተዋፅኦ ያደረጉ መሆኑን፣ አንደኛው ‹ካርዲናል› ይሄ ጦርነት ቅዱስ ጦርነት ነው ሲሉ የተናገሩት መረጃ አለን፣ የጣልያን ጦር አዲስ አበባ ሲገባ የደስታ መግለጫ ካወጡት መካከል የመጀመሪያው (የቫቲካኑ) ፖፕ ሃያስ ነበሩ፡፡ ይሄንና ሌላ ማስረጃዎችን ያየ ..እንዲህ ያለ የማይሆን ነገር ለመናገር አይችልም፣" ሲሉ ይሟገታሉ፡፡

አቶ ኪዳኔና አጋሮቻቸው ከእኒህ ሁሉ ዓመታት በኃላ "ይሄ ነገር አይሰምርም" ብለው መዝገባቸውን ለማጠፍ ዝግጁ አይደሉም፡፡ ከዚህ ቀደም በቫቲካን ተባባሪነት ለደረሰ በደል፣ የነዋይ ካሳን እና ይፋዊ ይቅርታን ማግኘት እንዲሁም በወቅቱ የተዘረፉ ቁሳቁሶች እና ቅርሶች ወደሀገራቸው ተመላሽ እንዲሆኑ ለማድረግ ጥረታቸው እንደሚቀጥል ይናገራሉ።

በእነ አቶ ኪዳኔ አለማየሁ መንደር የተስፋ ጀምበር አልጠለቀችም ፡፡በዚህ ዓመት ህዳር ወር ላይ ከ81 ዓመት በፊት የካቲት 12 ለተፈጠረው እልቂት ሰበብ የሆነው ሩዶልፎ ግራዚያኒ መታሰቢያ ሃውልት 'አፊል' ከተሰኘችው የሮማ ጎረቤት ከተማ እንዲነሳ ተወስኗል፡፡

ሃውልቱ እንዲሰራ የገንዘብ ፈሰሱን ያጸደቁት የከተማዋ ከንቲባ እና ሁለት የአስተዳደር አባላት ‹‹ፋሽስት ይቅርተኝነት›› Apologia del Fascismo የሚሰኘው ህግ ተጠቅሶ በስምንት እና ስድስት ወራት እስር እንዲቀጡ ተወስኗል፡፡

ሃውልቱ መወገድ እንዳለበት ለመጠየቅ በተደጋጋሚ ሲጎተጉቱ ከነበሩ ተቋማት አንዱ ለሆነው 'ዓለማቀፍ ህብረት ለፍትህ -ለኢትዮጵያዊያን ጉዳይ'፣ውሳኔው የሌሎች ዘመቻዎች ተስፋም ፈጽሞ እንዳልከሰመ የሚያሳይ ምልክት ይመስላል፡፡

ሃላፊው የ ቫቲካን ይቅርታ መዘግየት የሚያብከነክናቸውን ያክል አንድ ቀን ይቅርታው እንደሚሰማ ያላቸውን ዕምነትም ከፍተኛ ነው፡፡ ይሄን የሚደግፈው የሚደጋግሙት ሀረግ ነው ''የፍትህ አምላክ፣የኢትዮጵያ አምላክ፣ይረዳናል!'' የሚለው፡፡

https://www.bbc.com/amharic/news-44198353

**********************************************

https://www.gudayachn.com/2014/02/12.html

 

 https://www.facebook.com/1845896815651636/photos/%E1%8B%A8%E1%8A%AB%E1%89%B2%E1%89%B5-121929-%E1%8B%93%E1%88%9D-%E1%8A%A0%E1%8B%B2%E1%88%B5-%E1%8A%A0%E1%89%A0%E1%89%A3-%E1%8A%A8-%E1%88%B0%E1%88%8B%E1%88%B3-%E1%88%BA%E1%88%85-%E1%89%A0%E1%88%8B%E1%8B%AD-%E1%8A%90%E1%8B%8B%E1%88%AA%E1%8B%8E%E1%89%BD%E1%8B%8B-%E1%89%A0%E1%8A%A0%E1%8A%95%E1%8B%B2%E1%89%B5-%E1%8C%80%E1%8A%95%E1%89%A0%E1%88%AD-%E1%88%B0%E1%88%9B%E1%8A%A0%E1%89%B5%E1%8A%90%E1%89%B5-%E1%8B%A8%E1%89%B0%E1%89%80%E1%89%A0%E1%88%89%E1%89%A3%E1%89%B5-%E1%89%80%E1%8A%95-%E1%8A%90%E1%89%A0%E1%88%A8%E1%89%BD-%E1%8B%A8%E1%8B%9B%E1%88%AC/1846383585602959/?paipv=0&eav=AfZREjMYFPEAQaC2VRnSiLcsQAmnYg9Hb5p8A9BfqGm_g6GUJluev1DD_RYna2cmipU&_rdr

 

 

 

 

 

 

Monday, February 19, 2024

በአፄ ኃይለሥላሴ ዘመን የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሚኒስትሩ አቶ ከተማ ይፍሩ

 አቶ ከተማ ይፍሩ 

የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር 


ከተማ ይፍሩ፡ ያልተነገረላቸው የአፍሪካ አንድነት ባለ ራዕይ

በፊውዳሉ ስርዓት ሹመት በደም ትስስር፤ በዘርና አጥንት ተቆጥሮ በሚሰጥበት ወቅት ስሟ ብዙ ከማትታወቀው የሐረርጌ ግዛቷ ጋራ ሙለታ ከደሃ ገበሬዎች ቤተሰብ የተገኘውና በ30ዎቹ ዕድሜ የነበረው ወጣት ከተማ ይፍሩ የአገሪቷ የውጭ ጉዳይ ግንኙት አድራጊ፣ ፈጣሪ እንዲሁም የአፄ ኃይለሥላሴ ዋና ልዩ አማካሪ (ቺፍ ኦፍ ስታፍ) ይሆናል ብሎ ያለመ አልነበረም።

ነገር ግን የማይታሰበው እውን ሆኖ ከተማ ከዚህም አልፎ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ ላይ አሻራውን መጣል ችሏል።

የታሪክ መዛግብትም ሆነ በቅርብ የሚያውቋቸው ተራማጅ ብለው የሚጠሯቸው ከተማ ኢትዮጵያ ቅኝ ባለመገዛቷ ከአህጉሩ የተለየችና ኢትዮጵያውያንም ልዩ ነን የሚል እሳቤ በአብዛኛው ዘንድ ቢንሸራሸርም ለሳቸው ግን የኢትዮጵያ እጣ ፈንታ ከሌሎች አፍሪካውያን የተለየ አይደለም ፤ መተባበር ካለባትም ከአፍሪካውያን ጋር ነው የሚል ቁርጠኛ አቋም ነበራቸው። 

ገና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እያሉ ሊግ ኦፍ ኔሽን ኢትዮጵያን አንቅሮ የተፋበት ሁኔታ ቁጭት እንደፈጠረባቸው በአሁኑ ሰዓት የህይወት ታሪካቸውን እየፃፈ ያለው ልጃቸው መኮንን ከተማ ይናገራል።

የጥቁር ህዝቦች ነፃነት ተምሳሌት የሆነችው ኢትዮጵያ በጣልያን ስትወረር አባል የሆነችበት የሊግ ኦፍ ኔሽን ይተባበረኛል የሚል እምነት ነበራት ። ነገር ግን ያልተጠበቀው ሆኖ አፄ ኃይለሥላሴ ንግግር በሚያደርጉበት ወቅት በመዘባበት፣ በጩኸትና በፉጨት ንግግራቸው ተቋረጠ።

ይህም ሁኔታ ታዳጊው ከተማን ከማስከፋት አልፎ ለተጨቆኑ ህዝቦች እንዲቆም ፤ ለፍትህና ለእኩልነት እንዲታገል መሰረት እንደሆነው የቅርብ ጓደኞቻቸው ምስክር ናቸው።

በአንድ ወቅት የቀድሞው የጣልያንና ጂቡቲ አምባሳደር ዶ/ር ፍትጉ ታደሰ ስለ ከተማ ተጠይቀው ሲመልሱ በቅኝ ግዛት ስር የነበሩ የአፍሪካውያን ሁኔታ ስለሚያሳስባቸውም "እኛ ነፃነት አግኝተን፤ እነርሱ በባርነት ቀንበር እንዴት ይሰቃያሉ" የሚል አስተሳሰብ ነበራቸው ብለዋል።

ለዚያም ነበር ኢትዮጵያ ከጣልያን ጋር በነበራት ትግል የረዳቻት እንግሊዝን እንኳ ለመተቸት ቅንጣት ወደ ኋላ ያላሉት። እንግሊዝ በአፓርታይድ ጭቆና ስር ለነበረችው ደቡብ አፍሪካ የጦር መሳሪያ መሸጧንም በከፍተኛ ሁኔታ ተችተዋል።

ከመተቸት ባለፈም ነፃ ያልወጡ የአፍሪካ ሀገራት ነፃ እንዲወጡ ከፍተኛ ርብርብና ለነፃ አውጭዎቿም ድጋፍ አድርገዋል። ከዚህም ውስጥ የሚጠቀሰው ለማንዴላ በኢትዮጵያ ፓስፖርት እንዲዘዋወሩ ማድረጋቸው ነው።

ማንዴላ በአፓርታይድ መንግሥት በቁጥጥር ስር ሲውሉ የከተማ ፎቶ በኪሳቸው ውስጥ እንደተገኘ የከተማ ልጅ መኮንን ይናገራል።

ፎቶው ላይ ለነፃነት ታጋዩ የሚል ፅሁፍ የነበረበት ሲሆን ፎቶው በማንዴላ እስር ወቅት እንደ ማስረጃ ሰነድ ቀርቦ እንደነበር በደቡብ አፍሪካ ጆሀንስበርግ ቪትዝ ዩኒቨርስቲ ሙዝየም ማስረጃ ተቀምጧል።

 

                                የተከበሩ ከተማ ይፍሩ ከዊኒ እና ኔልሰን ማዴላ ጋር

ከተማና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ

1950ዎቹ ለአፍሪካውያን የተለየ ተስፋ ይዞ የመጣ ጊዜ ነበር። የነበሩበት የቅኝ ግዛት፣ ጭቆና፣ ባርነትን በመሰባበር ነፃነት የተፈነጠቀበት ጊዜ ነበር።

በዛን ጊዜም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከዚህ ቀደም ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ ወጣቱ ፓን አፍሪካኒስት ከተማ የአፍሪካ አህጉራዊ ድርጅት መፈጠር አለበት የሚል ንግግር ተናገሩ።

ነፃ በወጡት አፍሪካ ሀገራት መካከል የአህጉሯ ህብረት ቢፈለግም ድርጅትን ሳይሆን ሀገራቱ ተዋህደው አፍሪካ አንድ ልትሆን ይገባል የሚል እሳቤዎች የጎሉበት ጊዜ ነበር።

በአንድ ወገን ዋናና ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ሀገራቱ በፍጥነት ተዋህደው አፍሪካ አንድ ልትሆን ይገባል የሚለው የካዛብላንካ ቡድን፤እንዲሁም አንድ ከመሆን በፊት ሌሎች ትብብሮች ሊቀድሙ ይገባል የሚለው የሞኖሮቪያ ቡድኖች ነበሩ።

ኢትዮጵያም በወቅቱ የሞኖሮቪያን ቡድን ተቀላቅላ ነበር። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከተማ ኢትዮጵያ ሁለቱን አንጃዎች የማስማማት ስራ መስራት እንዳለባት ለንጉሱ አጥብቆ ተናገሩ።

ምንም እንኳን በወቅቱ ወግ አጥባቂ የነበሩት ሹማምንቱና መኳንንቱ "እንምከርበት" የሚል ኃሳብ ቢያነሱም አፄ ኃይለሥላሴ ግን "ታምንበታለህ" የሚል ጥያቄ ብቻ እንዳቀረቡላቸውና ሂደቱን ብቻ እንዲያሳውቃቸው እንደነገራቸው መኮንን ይናገራል።

ሁለቱም ቡድኖች ስብሰባቸው ላይ እንዲገኙ ጥሪ ሲያቀርቡ ለኢትዮጵያ መልካም አጋጣሚ እንደሆነ በማሰብ አጀንዳቸውን ይዘው ሄዱ።

የሚኒስትሩ ዋነኛ አጀንዳ የነበረው ከ20 በላይ አባላት የነበሩትን የሞኖሮቪያን ቡድንና ስድስት ብቻ አባላት የነበሩትን የካዛብላንካን አንጃ አሳምኖ አዲስ አበባ ጉባኤ ማካሄድ ነበር።


                      ማንዴላ በቁጥጥር ስር በዋሉበት ወቅት ከኪሳቸው የከተማ ፎቶ ተገኝቶ ነበር

ኢትዮጵያ ሁለቱን ቡድኖች አንድ ላይ ለማምጣት የመሪነት ቦታውን በመያዝ የሞኖሮቪያን ቡድን ስብሰባ ለመሳተፍ አቶ ከተማ ወደ ሌጎስ አመሩ።

አመራሮቹን አዲስ አበባ በሚካሄደው ጉባኤ እንዲመጡ ፤ በኋላም ንጉሱንም አሳምነው ለመሪዎቹ ምስጋና እንዲያቀርቡ ያደረጉ ሲሆን ንጉሱም " እኛ ከሞኖሮቪያም ሆነ ከካዛብላንካ አይደለንም። ከአፍሪካ ጋር ነን የሚል" ታሪካዊ ንግግራቸውን አደረጉ።

በተለይም በወቅቱ የሀሳቡ አመንጪና ከረር ያለ አቋም የነበራቸውን የ ጋናውን መሪ የነንክሩማህን ቡድን ማምጣት ቀላል እንዳልነበር ከተማ ይናገሩ እንደነበር መኮንን ይገልፃል ።

በተለይም ጉዳዩን አወዛጋቢ ያደረገው በወቅቱ የሞኖሮቪያ አባል የነበሩት የቶጎው መሪ መገደል ያኛውን ቡድን መወንጀልና ሁኔታዎችም መካረር ጀመረ። ነገሮችንም ለማለሳለስ ብዙ ጥረት ተደረገ።

ከዚህም ውስጥ ሌላኛውን የካዛብላንካ ቡድን አባል የነበሩትንም የጊኒውን መሪ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬንም ወደ አስመራ በመጋበዝ ከንጉሱ ጋር እንዲነጋገሩ ተደረገ። ኢትዮጵያና ጊኒ በመከፋፈል አያምኑም የሚል መግለጫም በጋራ አወጡ።

መሪዎቹን አስማምቶ ማምጣት በጣም የከበደ ስራ እንደነበር የሚናገረው መኮንን በብዙ አጋጣሚዎችም አባቱ ከተማ የዲፕሎማሲ ክህሎታቸውን በመጠቀም ነገሮችን እንዳሳኩ ይናገራል።

 

ከተማ በየሃገራቱ ሲዞሩ "ሀገር አልለቅም፤ ንጉሱ አያስገቡኝም" የሚሉ ማባበያዎችን ይጠቀሙ እንደነበር የሚናገረው መኮንን ከተማ የቱኒዝያውን ፕሬዚዳንት ያግባቡበትን መንገድ ለይቶ ይጠቅሳል። ፕሬዚዳንቱ የሁለቱ ቡድኖች የጋራ አቋም ሳይኖር እንዴት አንድ ላይ እንሰበሰባለን የሚል የእምቢታ ምላሽ ሲሰጧቸው በምላሹም "አፄ ኃይለሥላሴ ያለርሰዎ ይህ ስብሰባ አይካሄድም" እንዳሏቸው መኮንን ይናገራል።

በወቅቱ አፄ ኃይለሥላሴ የነበራቸው ቦታ ከፍተኛ ስለነበርም የቱኒዚያው ፕሬዝዳንት እሺ ብለው መጡ። ያ ታሪካዊ ስብሰባ ሊደረግም በቃ፤ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትም ተበሰረ።

ነገር ግን ሁሉ ቀላል አልነበረም። ሁለት የተለያዩ እሳቤዎችን ይዘው የመጡ ቡድኖችን አንድ ላይ መምጣት ቀላል አልነበረም፤ የተወሰኑ ግጭቶች ቢፈጠሩም የነበረው የስሜት ድባብ በጣም የተለየ እንደነበር አቶ ከተማ ለልጃቸው ለመኮንን ነግረውታል።

"እንዲህ አይነት ስሜት አፍሪካ ውስጥ ተፈጥሮ አያውቅም" ብለው አባቱ አጋጣሚውን ገልፀውለታል።

አዲስ አበባን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ፅህፈት ቤት የማድረግ ትግል

በመቀጠልም የአፍሪካ ፖሊሲዎችን ማርቀቅ፣ የድርጅቱ ፀሐፊ እንዲሁም ዋና ፅህፈት ቤት የት ይሁኑ የሚሉ አንገብጋቢ ጥያቄዎች ነበሩ።

በከተማ አመራርነት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሁለቱን አንጃዎች ፖሊሲና ሌሎች ሀሳቦችን ጨምረው አቀረቡ፤ ፖሊሲዎቹ ላይ አንዳንድ አለመስማማቶች ቢፈጠሩም ሰነዱ ተፈረመ።

ከተማ ስራቸው አላለቀም ለኢትዮጵያ የነበረው ጥሩ ስሜት እያለ ኢትዮጵያ የድርጅቱ ፅህፈት ቤት መቀመጫ ትሁን የሚል ሀሳብ አቀረቡ። በፍጥነት ከአመራሩ "አይቻልም" የሚል ምላሽ ተሰጣቸው። ምክንያቱ ደግሞ "ከተማ የራሱን ስም ለማበልፀግ" እየሰራ ነው ብለው ንጉሱን የሚመክሩ ስለነበሩ እንደሆነ መኮንን ይናገራል።

የተፈራው አልቀረም ትንሽ ቆይቶም ፈረንሳይኛ ተናጋሪ ሀገራት የድርጅቱ መቀመጫ ዳካር እንድትሆን መስማማታቸው ተሰማ። ኢትዮጵያ ድርጅቱን ለመመስረት ይህንን ያህል ለፍታ አመድ አፋሽ መሆኗ ንጉሱን አስደነገጣቸው።

ከሴኔጋል ሌላም ናይጀሪያ ያላትን ትልቅነት ተጠቅማ እዚህ መሆን አለበት የሚል ክርክርም ጀምራ ነበር። የሃገራቱ እሰጣገባ ብቻ ሳይሆን "ኢትዮጵያን አትምረጡ" የሚል ቴሌግራም እንደተሰራጨም እንደነበር የሶማሊያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ለከተማ አሳዩዋቸው።

"ኢትዮጵያና ሶማሊያ መካከል ግጭት እያለ ሚኒስትሩ ያንን ማድረጋቸው ለአባቴ በህይወቱ ሙሉ የሚያስደንቀው ጉዳይ ነበር። ቢጋጩም የሶማሊያ ድጋፏ ለኢትዮጵያ ነበር" ይላል መኮንን

በመቀጠልም ኢትዮጵያ እንድትመረጥ የማግባባቱ ስራ/ ዘመቻ/ ተጀመረ። በተለይም ለጊኒ እናንተ ኢትዮጵያን መቀመጫ ካደረጋችሁ የፀሀፊውን ቦታ እንሰጣችኋለን የሚል ሃሳብን እንዳቀረበ መኮንን ይናገራል።

በመጨረሻም ከናይጀሪያ በስተቀር ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋና ፅህፈት ቤት መቀመጫ እንድትሆን አገራቱ ድምፃቸውን ሰጡ።

"ብዙዎች እንደሚሉት አፄ ኃይለሥላሴ ስለነበሩ አዲስ አበባ ተመረጠች የሚለው ሳይሆን ከብዙ ማግባባት፣ ክርክርና ፍጭቶች በኋላ ነው የድርጅቱ ፅህፈት ቤት አዲስ አበባ ሊሆን የቻለችው።" በማለት መኮንን ያስረዳል።


 

ከጋራ ሙለታ ቦስተን ዩኒቨርስቲ

ለዘመናት በተለያዩ መድረኮች ላይ ኢትዮጵያን የወከሉት አቶ ከተማ የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ፤ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከመሆናቸው በፊት በተለያዩ ኃላፊነት አገልግለዋል።

የትምህርት ጉዟቸው ሀ ብሎ የተጀመረው ኬንያ ነበር። ምክንያቱም ጣልያን ኢትዮጵያን ሲቆጣጣር በሰባት አመታቸው ወደ ጂቡቲ ለመሰደድ ተገደዱ።

ትንሽ ጊዜ ጅቡቲ ቆይተውም ጉዟቸውን ከአጎታቸው ጋር ወደ ኬንያ አደረጉ። በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ስር በነበረችው ኬንያም ስደተኞች ከአገሬው ተማሪ ጋር አብሮ መማር ስለማይቻል ለኢትዮጵያውያን ስደተኞች ተብሎ በተከፈተውና በቢትወደድ ዘውዴ ገብረ ህይወት ኃላፊነት በሚመራው ትምህርት ቤት ጀመሩ።

ኢትዮጵያ ነፃነቷን ስትቀዳጅ ደግሞ ወደ ጋራ ሙለታ ተመለሱ። ያኔም ትምህርታቸውን የመቀጠል ፅኑ ፍላጎት እንደነበራቸው መኮንን ይናገራል። ለዚህ ደግሞ የአጋጣሚ በር ተከፈተላቸው።

ንጉሱ የተለያዩ አካባቢዎችን በሚጎበኙበት ወቅት ጋራ ሙለታን ሲጎበኙ በአካባቤው ዕድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ልጆች አሉ ምን ይደረግ? ብለው ሲጠየቁ አዲስ አበባ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምጣት እንደሚችሉ ምላሽ ተሰጣቸው።

መኮንን እንደሚናገረው አዲስ አበባ ሄደው ወዲያው ትምህርት ቤት የሚገቡ መስሏቸው የነበረ ቢሆንም ሲደርሱ አናስገባም የሚል ምላሽ ተሰጣቸው። የሚያድሩበትም ሆነ የሚበሉት አልነበራቸውም፤ በጊዜው "ሰው ለሰው አዛኝ በመሆኑ" ይላል በአካባቢው የነበሩ ወታደሮች መጠጊያ ሆኗቸው። ስራም እየሰሩ ትንሽ ከቆዩ በኋላ ነገሩ በወቅቱ የጦር ሰራዊት ኃላፊ ለነበሩት ጄኔራል መርዕድ መንገሻ በመነገሩ በሳቸው ምክንያት ትምህርታቸውን ሊጀምር እንደቻሉ ይናገራል።

የትምህርት ቤቱ ተማሪዎች የመኳንንትና የሹማምንት ልጆች በመሆናቸው ከፍተኛ ልዩነት ይታይበት የነበረ ሲሆን አባቱ የነገሩትንም መኮንን እንዲህ ያስታውሰዋል።

"ንጉሱ በየጊዜው እየመጡ ተማሪዎቹን ይጎበኛሉ። መምህሩም ስም በሚጠራበት ወቅት ከስማቸው ፊት ደጃዝማች፣ ልዑል እንዲሁም ሌሎች ሹመቶች ነበሩ። ጃንሆይም ልጆቹ በእኩልነትና ያለምንም ተፅእኖ ትምህርታቸውን እንዲማሩ ቅጥያው እንዲሰረዝ አዘዙ" ይላል።

በመቀጠልም ለከፍተኛ ትምህርት ወደ አሜሪካ ሚቺጋን ሆፕ ኮሌጅ ፖለቲካል ሳይንስና አለም አቀፍ ግንኙነት ለማጥናት ያቀኑ ሲሆን፤ የማስተርስ ዲግሪያቸውንም በቦስተን ዩኒቨርስቲ በተመሳሳይ ትምህርት ተመርቀዋል።

አሜሪካ ሲደርሱ ከፍተኛ ዘረኝነት ያጋጠማቸው ሲሆን፤ "ውሾችና ጥቁሮች አይፈቀድም" የሚሉ መልእክቶች እንዲሁም የነበረው የዘረኝነት ሁኔታ አፍሪካዊነታቸውን ብቻ ሳይሆን የፓን አፍሪካዊነት ፅንሰ ሀሳባቸውንም በከፍተኛ ሁኔታ ያሳደገው ነገር እንደሆነ መኮንን ይናገራል።

ምንም እንኳን የፒኤችዲ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ቢጠየቁም ቤተሰቤን እረዳለሁ ብለው ተመለሱ። ትልቅ ህልም የነበራቸው አቶ ከተማ በውጭ ጉዳይ በተለያዩ ዘርፎች በኃላፊነት ቢያገለግሉም ከደሃ ቤተሰብ ከመምጣታቸው ጋር ተያይዞ ሹመቶች ያመለጧቸው ነበር።

የሹማምንት ልጆች በተለያዩ መስሪያ ቤቶች ሲቀመጡ እሳቸው ዝም ተባሉ። ይህንንም ጉዳይ በጊዜው ውጭ ጉዳይ ለነበሩት ለፀሀፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተወልድ አጫወቷቸው ነበር።

ሚኒስትሩም ጉዳያቸውን ለንጉሱ እንዲያቀርብ መከሯቸው። "ደፋርና በግልፅ ተናጋሪ ነበር" የሚለው መኮንን ለንጉሱ የጠየቀበትን መንገድ ይገልፃል " እኔ ወደ ኋላ የቀረሁት በማንነቴ ነው" ብሎ በመናገሩ ንጉሱ ተቆጥተው ውጣ አሉት። 

ቢሆንም የደመወዝ ጭማሪ ተደረገላቸው፤ ከጥቂት ጊዜ በኋላም ቢሆን ደግሞ ሹመቱ ተሰጣቸው። ለሹመቱም ጄኔራል መርዕድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረጉ ሲሆን ብዙ ተቃውሞም ገጥሟቸዋል። የውጭ ጉዳይ ኃላፊ መሆን ግን አልጋ ባልጋ አልሆነላቸውም።

"ይህ ሁኔታ በጣም አስደንጋጭ ነበር። ብዙዎች በመቃወም ተከራክረዋል። ምንም እንኳን ሹመቱ ጥሩ ቢሆንም። ብዙ ጠላቶችንም ማፍራት ቻለ" በማለት መኮንን ይናገራል።

ንጉሱን በድፍረት በመናገር ታሪክ የሚያስታውሳቸው ከተማ የንጉሱም ዋና ልዩ ፀሀፊም ለመሆን ችለው ነበር።

ምንም እንኳን ከአፍሪካውያን ጋር ህብረት መመስረትና ሌሎች አማራጮችን በድፍረት መናገሩ ብዙዎችን ቢያስደንቅም ለመኮንን "ንጉሱ እሱን መስማታቸውና የሚመክራቸውንም ጉዳይ ተግባራዊ ማድረጋቸውን ያደንቃል" ሌላው ሰው የማይጠይቃቸውን ነገሮች ከተማ በድፍረት ይጠይቁ እንደነበርም መኮንን ይናገራል።

ለምሳሌ አባቱ ካጨወቱት መካከል አፄ ኃይለስላሴን ንጉስ ባይሆኑ ምን ይሆኑ ነበር? ብለው ጠይቀው ነበር። እርሳቸውም በምላሹ "ዶክተር" ብለው መልሰውለታል።

ተራማጁ በንጉሳዊ አገዛዝ ስርአት ውስጥ

ብዙ እሳቤዎቻቸው ከጊዜው የቀደመ ነው የሚባልላቸው ከተማ አፍሪካ አንድነት ድርጅትን መሰረት ከማስያዝ በተጨማሪ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ገለልተኛ አቋም እንዲኖረው ብዙ ጥረዋል።

ከዚያም በተጨማሪ ንጉሱን ስልጣን ለልጃቸው እንዲያጋሩ፤ ህገ መንግሥታዊ የዘውዳዊ ስርዓት እንዲመሰረት የሚሉና ሌሎች ኃሳቦችን አካተው ምክር አዘል ደብዳቤም ፅፈውላቸው ነበር።

"በዚች አነስተኛ ማስታወሻ ላሳስብ የምወደው ግርማዊነትዎ ከፈለጉ የመሸጋገሪያውን ድልድይ ለመዘርጋትና የኢትዮጵያ ህዝብ ወደፊት ከሞግዚትነት ወጥቶ የራሱን እድል በራሱ ለመወሰን የሚያስችለውን ለማድረግ ስለሚችሉ ሳይውል ሳያድር አስበውበት አንድ የተፋጠነና የተወሰነ እርምጃ እንዲወስዱ ነው" ከደብዳቤው የተቀነጨበ

በድፍረት የመናገሩ ጉዳይ ገደብ እንዳለው ያልተረዱት አቶ ከተማ በተለይም በስልጣናቸው ላይ መምጣቱ በንጉሱ ዘንድ ቅሬታን አሳደረ።

ደብዳቤውን በፃፉ በማግስቱ ከውጭ ጉዳይ አውጥተው ወደ ንግድ፣ ኢንዱስትሪና ቱሪዝም ሚኒስትር ቀየሯቸው። አባቱ በሁኔታው ብዙ ደስተኛ እንዳልነበሩና እንደከፋቸውም መኮንን ይናገራል።

ከሶስት አመታት በኋላም ከተማ የተነበዩት አልቀረም ንጉሱ ከስልጣን ወረዱ። "ምክሩን ሰምተው ቢሆን ኖሮ ያ መጥፎ ስርአት ላይመጣ ይችል ነበር፤ ይስተካከልም ነበር" ይላል መኮንን

የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ፅንሰ ሃሳብ ከመመስረት ጀምሮ፣ የአፍሪካ ፖሊሲዎችን ማርቀቅ፣ ካዛብላንካንና ሞኖሮቪያን አስማምቶ አንድ ላይ ማምጣትና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ፅህፈት ቤት አዲስ አበባ እንዲሆን ማድረግ ከሚጠቀሱ ስራዎቻቸው የተወሰኑት ቢሆንም ታሪክም ሆነ ታሪክ ፀሀፊዎች ዘንግተዋቸዋል። በስማቸውም የተቀመጠ ሀውልት ወይም ሌላ ማስታወሻ የላቸውም። ለምን? መኮንን መልስ አለው

"አንድ ህዝብ ታሪኩን ሳያውቅ ሲቀር ይህ ነው የሚሆነው፤ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዴት ተመሰረተ የሚለውን በአንድ አረፍተ ነገር መናገር እንችላለን፤ ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ሁለቱን ቡድኖች አስታረቁ ማለት እንችላለን። ዝርዝሩን ግን ምን ያህል እናውቃለን፥ መንግሥት በተለወጠ ቁጥር ታሪክ የሚጀምረው በኔ ነው ይልና ያኛውን ያፈርሰዋል። የሚያውቁት ደግሞ እኔ ለሳቸው ተገዢ ነኝ የሚል አስተሳሰብ አለ። የአቶ ከተማ ይፍሩ ስም ከተነሳ ድንገት የሳቸውን ሊሸፍነው ይችላል የሚልም ነገር ይኖራል። አይሸፍንም እሳቸው መሪ ናቸው ተገቢውን ክብር ማግኘት አለባቸው። ነገር ግን ገና ለገና የሳቸውን ስም ይሸፍናል በሚል የግለሰቦች አስተዋፅኦ ሊደበቅ አይገባም። በዛ ላይ ከእንደዚህ አይነት ደሃ ቤተሰብ ከመጣ ሰው ይህንን ሁሉ ታሪክ ከሰራ በኋላ፤ ላገሩ ካበረተ በኋላ ለሌሎች ምሳሌ ይሆናል እንጂ ይሄንንማ መደበቅ አንችልም"

ያ ተስፋን የሰነቀ ድርጅት ብዙም አልቀጠለም በአባላቱ ሃገራት መፈንቅለ መንግሥቶች፣ ግድያዎች ቀጠሉ። በተለይም ከተማ በደርግ ጊዜ ከዘጠኝ አመት የእስር ቆይታ በኋላ ምሬታቸውና ኃዘናቸው ከፍተኛ እንደነበር መኮንን ይናገራል። 

 

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በተመሰረተበት በመጀመሪያዎቹ ሶስት አመታት ችግሮቻቸውን በአህጉራዊ ድርጅቱ ይፈቱ ነበር እንደ ምሳሌም የሚነሱት አልጀሪያና ሞሮኮ ሲዋጉ ኢትዮጵያ አንዷ አሸማጋይ ነበረች።

እሳቸውም በአንድ ወቅት በአሜሪካ ድምፅ ተጠይቀው እንደተናገሩት "ሀገራቱ ስልጣን የሚተካኩበት ስርዓት ማምጣት ስላልቻሉ መፈንቅለ መንግሥቶች መከታተል ጀመሩ" ብለዋል።

አፍሪካውያን በአንድነት አህጉሯ በአለም አቀፍ ደረጃ የመደራደር አቅምን እንዲሁም ተሰሚነት እንድታገኝ የተጀመረው ጉዞ ወደ ኋሊት ሆኖ ወታደሮች በተለያዩ ቦታዎች ስልጣንን መያዝ ጀመሩ። ይህም ሁኔታ በጣም ያሳዝናቸው ነበር ቢልም እሳቸው ካበረከቱት አንፃር ከአንድ ሰው ከሚጠበቀው በላይ እንዳደረጉ የሰሯቸው ስራዎች ምስክር ናቸው ይላል።

ከባለቤታቸው ራሔል ስነ ጊዮርጊስ አራት ልጆች አፍርተዋል። ከእስር ሲፈቱ የአስራ አምስት አመት ልጅ የነበረው መኮንን ደግ፣ ቀላልና የሰው ሃሳብ የሚሰሙ ሰው እንደነበሩ ይናገራል። አቶ ከተማ ራሳቸውንስ እንዴት ይገልፁ ይሆን መኮንን እንደሚለው ወጣ ያለ አስተሳሰብ (ሬብል) ነኝ ይሉ ነበር ብሏል። 

https://www.bbc.com/amharic/news-47169409

 

ያልተነገረላቸዉ የአፍሪቃ አንድነት መስራችና ዲፕሎማት

ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ኢትዮጵያ ካፈራቻቸዉ ብርቅዬ ልጆች አንዱ ናቸዉ። አፍሪቃዉያን ወንድምና እህቶቻችን ናቸዉ፤ የኛ የብቻ ነጻነት ዋጋ የለዉም ይሉ ነበር። ለአህጉር አፍሪቃ የሚያስቡ ፓን አፍሪካኒስት ነበሩ። እንደ ኔልሰን ማንዴላ፤ ኬኔት ካዉንዳ ያሉ የአፍሪቃ ታጋዮችን ኢትዮጵያ እንድትረዳ ያደረጉ ናቸዉ። እነሱም መጨረሻ ከልብ አመስግነዋል። 
«ስለአፍሪቃ አንድነት ድርጅት መቋቋም ታሪኩን ከኔ በላይ የሚያዉቅ ሰዉ የለም ብል አልተሳሳትኩም። ዋናዉ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ከተቋቋመ ጀምሮ የአፍሪቃ ሃገራት ነጻ መዉጣትን በጣም ነዉ ያፋጠነዉ። ምክንያቱም በስድሳዎቹ መጀመርያ የተባበሩት መንግስታት ጉባዔ ላይ የአፍሪቃ ሃገራት አንድነት እና ህብረት ጠንካራ እንደነበር ትዝ ይለኛል። በጣም በጣም የተጠናከረ ቡድን ነበር። ለአንድ አላማም የቁሙ ነበሩ። ይህ አላማ አፍሪቃዉያን ነጻ መዉጣት አለባቸዉ የሚል ነበር። ያን ግዜ አንድ ላይ ስለሆንን እኛን መከፋፈልም አልተቻለም ነበር። ስለዚህ አንድነታችን እና ድርጅቱ አስተዋጽኦ አድርጓል። ሌላዉ ደሞ፤ የአፍሪቃ መሪዎች ሌላዉ ቢቀር በዓመት አንድ ጊዜ በጋራ ተሰባስበዉ የአህጉርዋን ችግሮች፤መወያያ መድረክ ማግኘታቸዉ ትልቅ ስኬት ነዉ። ህብረቱ ችግሩ ላይ ዉሳኔ አገኘንም አላገኘም፤ መፍትሄ ማግኘቱ ግን ያጠራጠራል፤ ቢሆንም ግን በዓመት አንድ ጊዜ የአህጉሪቱ መሪዎቹ ተሰባስበዉ መወያየታቸዉ አንድ ትልቅ ስኬት ነዉ። የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት የተቋቋመዉ ብዙ ሃገራት ነጻ በወጡ በሦስተኛዉ ዓመት ነዉ »
ከ 1953 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮጵያ የዉጭ  ጉዳይ ሚኒስቴር፤ ተጠባባቂ ሚኒስትርነት በኋላም የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነዉ ለአስር ዓመት ያገለገሉት የተከበሩ ከተማ ይፍሩ ከተናገሩት ከማህደር የተወሰደ ቃል ነዉ። በንጉሱ ዘመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነዉ ያገለገሉት አቶ ከተማ ይፍሩ፤ ባገለገሉባቸዉ ዘመናት ሁሉ ኢትዮጵያ በሁሉም አቅጣጫ የዉጭ ተቀባይነት ያገኘችበት እና ንቁ ተሳታፊ የነበረችበት ዘመን እንደነበር ይነገራል። ከዚህ ሌላ የተከበሩ ከተማ ይፍሩ የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነዉ ሲያገለግሉ የአፍሪቃ የኢኮኖሚ ኮሚሽን ብሎም የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት እንዲመሰረት እና ሁለቱም ተቋማት ዋና መቀመጫቸዉ ኢትዮጵያ መዲና አዲስ አበባ ላይ እንዲሆን ቀዳሚዉን እና ጠንካራዉን ሚና የተጫወቱ ዲፕሎማት ነበሩ። ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ በዚህ ተግባራቸዉ የኢትዮጵያ የዲፕሎማቲክ ጀግና ሲሉ ብዙዎች ያወድሷቸዋል። ትናንት ረቡዕ አዲስ አበባ ላይ  « ከተማ ይፍሩ፤ የሰላም የዕድገት እና የፓን አፍሪካኒዝም አቀንቃኝ » በሚል ርዕስ የክቡር ከተማ ይፍሩን የህይወት ታሪክ ብሎም፤ በአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ምስረታ የነበራቸዉን ጉልህ ሚና የሚያሳይ መጽሐፍ ተመርቆ ለአንባቢያን ቀርቧል። የኢትዮጵያ የዲፕሎማቲክ ጀግና የክቡር ከተማ ይፍሩን የጽሑፍ እና የድምፅ ማስታወሻዎችን፤ የሥራ ሰነዶችን፤ የተለያዩ የቀድሞ የአፍሪቃ መንግሥታት የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችን እና ባለሥልጣናትን በማነጋገር በመጽሐፍ መልክ ለአንባብያን ያቀረቡት የከተማ ይፍሩ የመጨረሻ ልጅ አቶ መኮንን ከተማ ናቸዉ። አቶ መኮንን በመረጃ ላይ የተመሰረት ሰነዶችን በማሰባሰብ ይህን መጽሐፍ ለአንባብያን ለማቅረብ 23 ዓመታት  ወስዶባቸዋል።

«መጽሐፉ ያዉ የአባቴ ታሪክ ነዉ። የጻፍኩበት ምክንያቶች ብዙ ናቸዉ። ዋናዉ ግን አባቴ የሰራዉ ስራና ታሪክ ለቤተሰቡ፤ ለእናቴ ወይም ለወንድሞቼ ሳይሆን ለሃገሩ ብሎም ለአህጉር አፍሪቃ ነዉ። ይህን ትልቅ ታሪክ ይዘን መቀመጥ አንችልም። የዛሬ 23 ዓመት አፍሪቃ አንድነት ምስረታ ታሪክ ላይ ሰርቻለሁ፤ ይህን ታሪክ በመጽሐፍ ለማዉጣት ስሰራም  23 ዓመታት ፈጅቶብኛል። የታሪክ ምሁራን ስለአቶ ከተማ ይፍሩ መጥተዉ ይጠይቁኛል፤ መጽሐፍም ይጻፋሉ ብዬ ጠብቄ ነበር። ግን ማንም ባለመምጣቱና ባለመጠየቁ ራሴ መጻፍ ነበረብኝ። የአፍሪቃ ህብረትም የምስረታዉን በዓል ሲያከብር አባቴን አላስታወሰም፤ እናቴም አልተጋበዘችም። ሌላዉ አባቴ ከደሐ ገበሪ ተወልዶ እራሱን አሻሽሎ፤ ይህን ሁሉ ስራ መስራት ከቻለ ወጣቱን ትዉልድ ያበረታታል በሚል አስቤ ነዉ።»

የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ህብረት ተቋቁሞ ዋና ጽ/ቤቱ የት ይሁን የሚለዉ ጥያቄ በህብረቱ አባል ሃገራት መካከል ከፍተኛ ክርክር እና ዉዝግብ ያስነሳ ሂደት እንደነበር አቶ አቶ መኮንን ከተማ አጫዉተዉናል። በዚህም የዝያን ጊዜዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከተማ ይፍሩ፤ ወደ ተለያዩ አፍሪቃ ሃገራት ድርጅቱ በመጓዝ ዋና መቀመጫዉ ኢትዮጵያ ላይ እንዲሆን ብዙ ዉይይቶችን እና የማሳመን ሥራዎችን ሰርተዋል። ከዝያም የአፍሪቃ ሃገራት የድርጅቱ ዋና ጽ/ቤት አዲስ አበባ ላይ እንዲሆን ተስማሙ፤ አቶ ከተማ ይፍሩ ቆየት ብሎ የድርጅቱን ዋና ጽ/ ቤት ወደ አዲስ አበባ ለማምጣት ያደረጉትን ጥረት በተመለከተ ሲናገሩ፣  «ከዝያ እንቅስቃሴ ብዙ የተረዳሁት ነገር አለ። የሃገራችንን ፤ መጠናከር የሚፈልጉ እንዳሉ ሁሉ፤ ደካማ ሃገር እንድትሆን የሚሹ ብዙ መሆናቸዉንም አይቻለሁ፤ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት አዲስ አበባ ላይ መሆን ምን ጥቅም እንዳስገኘ ደግሞ የዛሬዋ ኢትዮጵያ የያዘቸዉን ስፍራ የሚመለከት ሁሉ የሚፈርድ ይሆናል፤ ይህ ያለፈዉ የድካም ዉጤት ነዉ። በጎዉን ነገር አጠንክሮ መቀጠል ያለበት ደግሞ የዛሬዉ ትዉልድ ይመስለኛል» ሲሉ የተከበሩ አቶ ከተማ ይፍሩ መናገራቸዉ ተዘግቧል።

አቶ መኮንን ከተማ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ላይ እንዲሆን ስለመወሰኑ ሂደት በጥቂቱ አጫዉተዉናል።

«መጀመርያ ልክ ድርጅቱ እንደተመሰረተ፤ ዋና ጽ/ቤቱ አዲስ አበባ እንዲሆን ጠይቆ ነበር። የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ሲመሰረት በቻርተሩ ጉዳይ እና ጽ/ ቤቱ የት ይሁን በሚለው ጥያቄ ላይ የናይጀርያዉ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ጃጃ ዋቹኩ እና አቶ ከተማ አልተስማሙም ነበር።

የድርጅቱ ቻርተር እሳቸው አባል በሆኑበት የሞንሮቪያ ቡድን ቻርተር ጋር አንድ መሆን አለበት ብለው ተከራክረው ነበር። ኢትዮጵያ ያቀረበችው ቻርተር ግን ፀደቀ። በኋላ ደግሞ ጽ/ ቤቱ የት ይሁን ሲባል የሴኔጋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዱዱ ቲያም ሴኔጋልን፤ የኮንጎ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ኮንጎን፤ ናይጄሪያም እንዲሁ፤ አቶ ከተማ ደግሞ ኢትዮጵያን አቀረቡ። በመጨረሻ በጎርጎረሳዉያኑ 1964 ዓ.ም ላይ ዳካር ሴኔጋል ላይ የተሰበሰቡት የውጭ ጉዳይ ሚንስትሮች ከብዙ ልፋት በኋላ ኢትዮጵያን እንዲመርጡ ተደረገ። በሚቀጥለውም ግብፅ በተደረገው የመሪዎች ጉባዬ መሪዎቹ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቹን ውሳኔ አፀደቁ። ይህ ዉዝግብ መንግሥቱን በተለይም ንጉሱን በጣም አስጨነቋቸዉ ነበር።  የኢትዮጵያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማለትም አባቴ አቶ ከተማ ፤ ሁሉንም ለማሳመን ከፍተኛ ስራን ሰርቷል። ጥሩ ወዳጆችም ነበሩት። ለምሳሌ የአልጀርያዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኋላ የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት የሆኑት አብደል አዚዝ ቡቲፍሊካ ፤ የሴራሌዮን እና የጊኒ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች፤ በተለይ የድርጅቱ ዋና ፀሐፊ የነበሩት የጊኒዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲያሎ ቴሊን ሁሉን አሳምኖ ነዉ ከብዙ ትግል በኋላ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ጽ/ቤት አዲስ አበባ ላይ ለመሆን የበቃዉ። የአፍሪቃ ህብረት እስከዛሬ መቀመጫዉ አዲስ አበባ ላይ በመሆኑ እስከዛሬም ኢትዮጵያ እየተጠቀመች ነዉ።»  

አቶ መኮንን ፤ የተከበሩ ከተማ ይፍሩ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሉ ኢትዮጵያ በቅኝ ግዛት ስር የነበሩ የአፍሪቃ ሃገሮች ከቅን ግዛት እንዲላቀቁ ከፍተኛ ሚና መጫወታቸዉም ይነገራል?

«እዚህ ጉዳይ ላይ አባቴን የኢትዮጵያ ሬድዮ ጠይቆት አንድ የተናገረዉ ነገር አለ። አፍሪቃዉያን ወንድምና እንህቶቻችን ናቸዉ፤ የኛ የብቻ ነጻነት ዋጋ የለዉም ብሏል። አባቴ ለሃገሩ ብቻ ሳይሆን ለአህጉር አፍሪቃ የሚያስብ ፓን አፍሪካኒስት ነበር። የአፍሪቃን አንድነት ነበር ይዞ የሚጓዘዉ። አፍሪቃ ዉስጥ የሚታየዉ የዘር መድሎ ያበሳጫዉ ነበር። ያንን ነጻ ለማዉጣት ከፍተኛ ፍላጎት ስለነበረዉ ይህን ተፈጻሚ ለማድረግ ይሰራበት ነበር። ንጉሱም የአባቴን ሥራ አይተዉ ተቀየሩ። በኋላም አባቴን ይከተሉ ጀመር። እነ ኔልሰን ማንዴላ እንደ ኬኔት ካዉንዳ ያሉ የአፍሪቃ ታጋዮች እና ነፃ አዉጭዎችን ኢትዮጵያ እንድትረዳ ያደረገም አባቴ ነዉ። እነሱም መጨረሻ ላይ ከልብ አመስግነዋል።»  

የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት መመስረት በቅኝ ግዛት ስር ለነበሩ ሃገሮች ነጻነት በአፋጣኝ እንዲመጣ እና እንዲቀዳጁ ረድቷል ሲሉ የተከበሩ ከተማ ይፍሩ ቀደም ብለዉ ተናግረዉ ነበር። 

«የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት ከተመሰረተ ጀምሮ የአፍሪቃ ሃገሮች ነጻ መዉጣትን በጣም ነዉ ያፋጠነዉ። ትዝ ይለኛል በ 60ዎቹ መጀመርያ ላይ በተባበሩት መንግስታት ጉባዔ ላይ፤ የአፍሪቃ ሃገራት አንድነት በጣም የተጠናከረ ነበር። ለአንድ አላማ ቆመን ነበር። ይህ አላማችን የነበረዉ አፍሪቃዉያን በሙሉ ነጻ መዉጣት አለባቸዉ የሚል ነበር። አንድ ላይ ስንሆን ሊከፋፍሉ የፈለጉ ሃገሮች መከፋፈል አልተቻለም ነበር። ስለዚህ ያ አንድ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል።»  

(ከተማ ይፍሩ፤ የሰላም የዕድገት እና የፓን አፍሪካኒዝም አቀንቃኝ) ሲሉ አቶ መኮንን ላንባቢ ያቀረቡት መጽሐፍ ረቡዕ ግንቦት 23 ቀን 2015 ዓ.ም ሲመረቅ፤ ፕሮፌሰር ብሩክ ኃይሉ በሻህ ከተጋባዥ እንግዶች መካከል አንዱ ነበሩ። ስለ አቶ ከተማ ይፍሩ የሚተርከዉንም መጽሐፍ አንብበዉታል።


«አዎ መጽሐፉን አንብቤያለሁ። ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ኢትዮጵያ ካፈራቻቸዉ ብርቅዬ ልጆች አንዱ ናቸዉ። በዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስርያ ቤት ለአስር ዓመታት ነዉ ያገለገሉት። የከተማ ይፍሩ የመጨረሻ ልጅ አቶ መኮንን፤ « ከተማ ይፍሩ፤ የሰላም የዕድገት እና የፓን አፍሪካኒዝም አቀንቃኝ » በሚል ርዕስ በቁጭት ግሩም መጽሐፍ ጽፏል። ሰነዶችን አገላብጦ ይህን መጽሐፍ ለአንባቢ ለማቅረብ 23 ዓመታት ፈጅቶበታል። 

ፕሮፌሰር ብሩክ መጽሐፉን እንዴት አገኙትት? በመጽሐፉ የተከበሩ ከተማ ይፍሩን የህይወት ታሪክ ብሎም ያራመዱትን ፓን አፍሪካኒዝምን አገኙበት?

«አዎ አግንቼበታለሁ፤ ታሪኩ የሚጀምረዉ የከተማ ይፍሩን ትዉለድ እድገት እና የትምህርት ደረጃን በመተረክ ነዉ። . . . »

************

 ዶቼ ቬለ

 

 

 


ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ተመሰረተ።


 የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (አ.አ.ድ)

The Organization of African Unity(OAU)

 ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም) የ32 ነፃ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች በተገኙበት የያኔው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ያሁኑ የአፍሪካ ህብረት (AU) ምስረታ በግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሤና በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከተማ ይፍሩ ያላሠለሠ ጥረት በአዲስ አበባ ከተማ እውን ሆነ ።

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ

በመሰብሰቢያው አዳራሽ የሚገኘው በአሰፋና ሠረቀ 
የማነብርሃን የተሣለ የ፴፪ቱ መሥራች መሪዎች ምስል።

ለብዙ ሺ ዓመታት ኢትዮጵያ ብቻዋን በአኅጉሩ ውስጥ ከአውሮፓውያኖች የቅኝ ግዛት ቀንበር ውጪ ቆይታ የሙሶሊኒ ፋሺስት ኢጣልያ፲፱፻፳፰ ዓ/ም ወርራት በነበረ ጊዜ አርበኞች ልጆቿ ውድ አገራቸውንና ነጻነታቸውን አሳልፈው ላለመስጠት አምስት ዓመታት ሙሉ ተዋጉ። ንጉሠ ነገሥታቸውም የእዚህን የግፍ ወረራ ለማጋፈጥ በዓለም መንግሥታት ማኅበር መድረክ ላይ ሲቀርቡ፣ ከአፍሪቃ አኅጉር ብቸኛዋ አባል ኢትዮጵያ ማንም አጋዥ አገር አልነበራትም።

ለአኅጉሩ ነጻነት በቅኝ ግዛት ሥርም የነበሩት ሕዝቦች፤ በነጻነትም ላይ የነበሩት አገራት የአውሮፓውያንን መዥገራዊ ልጥፍነት ለማላቀቅ ብዙ ከታገሉ በኋላ በሰሐራዊ አፍሪቃ የካቲት ፳፯ ቀን ፲፱፻፵፱ ዓ/ም ጋና ነጻ ሆነች። ከዚያ አስከትሎ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት እስከተመሠረተ ድረስ በ፲፱፻፶፩ ዓ/ም ጊኒ ነጻ ስትሆን በ ፲፱፻፶፪ ዓ/ም አሥራ አምስት አገራት፤ በ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ሦሥት አገራት፤ በ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ደግሞ አራት አገራት ነጻነታቸውን ተቀዳጁ።

የአኅጉሩ መሪዎች በዓለም መድረክ ላይ ለበለጠ ተሰሚነት የትብብርን ግንባር ማሳየት እንደነበረባቸው በመገንዘብና ገና ነጻ ላልወጡትም ወንድም አገሮች ሉዐላዊነት መታገል ስለነበረባቸው ዓላማቸውን ግብ ለማድረስ በሁለት ቡድን ተከፍለው ፣ ባንድ በኩል እራሱን “የዘመናዊ ተራማጅ” ብሎ የሚጠራው፣ በጋናው ፕሬዚደንት ክዋሜ ንክሩማ የሚመራው የ “ካዛብላንካ ቡድን” በ ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ተመሠረተ። ይሄ ቡድን የአኅጉሩን መንግሥታት በኅብረት ለማዋሃድ ዓላማ የያዘ ሲሆን አባላቱ ጋናአልጄሪያጊኒሞሮኮግብጽማሊ እና ሊቢያ ነበሩ።

ሁለተኛው ቡድን የ”ሞንሮቪያ ቡድን” ሲሆን የተመራው በ ሴኔጋል ፕሬዚደንት ሊዮፖልድ ሴዳር ሴንግሆር ነበር። አባላቱ ሴኔጋልናይጄሪያላይቤሪያ እና ኢትዮጵያ ሲሆኑ የነሱ የኅብረት አስተያየት ደግሞ የዱኛ ኅብረት ሳይሆን ፍላጎታቸው ረጋ ባለ ሁኔታ የዱኛኪን ኅብረት አንድነትን ያስከትላል የሚል ነበር።

መጨረሻ ላይ በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ከተማ ይፍሩ ታላቅ ጥረትና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ ሁለቱም ወገኖች አዲስ አበባ ላይ እንዲገናኙ በተደረገው ጥሪ መሠረት ተሰባስበው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን የስምምነት ውል ፴፪ ነጻ ሀገሮች ሲፈርሙ ድርጅቱ ተመሠረተ።

************************************

ግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ዘኢትዮጵያ የአፍሪካ አባት

Haile Selassie I of Ethiopia: Father of the O.A.U.’’ (የናይጄሪያው ሳንዴይ ኦብዘርቨር፤ ጁላይ 23፣ 1972)

ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖች ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል…፡፡’’ (የጊኒው ፕ/ት የነበሩት ሴኮቱሬ)

የትናንቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ህብረት የተመሰረተው ከ59 ዓመታት ግንቦት 16 ቀን 1955 ዓ.ም ነበር፡፡ ወቅቱ የአፍሪካ አገራት በሁለት የተከፈሉበት ነበር፡፡ በአንድ ወገን ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ሀገራቱ በፍጥነት ተዋሕደው አፍሪካ አንድ ልትሆን ይገባል የሚለው የካዛብላንካ ቡድን፤ እንዲሁም አንድ ከመሆን በፊት ሌሎች ትብብሮች ሊቀድሙ ይገባል የሚለው የሞኖሮቪያ ቡድኖች ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያም በወቅቱ የሞኖሮቪያን ቡድን ተቀላቅላ ነበር፡፡ በኋላ ኢትዮጵያ ባደረገችው ከፍተኛ ጥረት ሁለቱ ቡድኖች የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ለመመስረት ባስቻለው ስብሰባ ላይ ለመታደም አዲስ አበባ ከተሙ፡፡

ቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ በጉባኤው ላይ ለተገኙት የአፍሪካ መሪዎች ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው እንዲህ አሉ፡-

“በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል፡፡ ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው፡፡ ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው…፡፡’’

ዕለታዊው የአዲስ ዘመን የወርኻ ግንቦት 15 ቀን 1955 ዓ.ም. ዕትሙ በፊት ለፊት ገጽ ላይ፣ ‘‘ሠላሳ የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ጉባኤ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፈተ፤ ግርማዊ ጃንሆይም የጉባኤው የክብር ሊቀመንበር እንዲሆኑ ተመረጡ፡፡’’ በሚል ዐቢይ ርዕስ ስር እንዲህ ይላል፡-

“ቁጥራቸው ከ250 ሚሊየን በላይ በሆኑ አፍሪካውያን እጅግ በጋለ ስሜት ይጠበቅ የነበረውና መላው ዓለም ሁኔታውን በቅርብ ይከታተለው የነበረው የ30ዎቹ የአፍሪካ ነጻ መንግሥታት መሪዎች ጉባዔ ግንቦት 14 ቀን ትናንት ከእኩለ ቀን በኋላ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፍቷል፡፡ ጉባኤውን የከፈቱት ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጉባኤው ሥራውን ከመጀመሩ በፊት የአንድ ደቂቃ የኅሊና ጸሎት እንዲደረግ አሳስበው ጸሎት ተደረገ፡፡’’ 

ቀጥሎም የሊቀመንበር ምርጫ እንዲደረግ አሳስበው የጊኒው ፕሬዚደንት ሴኩቱሬ የመጀመሪያውን ምርጫ እንዲያደርጉ ተጠየቁ፡፡ እርሳቸውም የኢትዮጵው ንጉሥ ኃ/ሥላሴ የጉባኤው ሊቀመንበር እንዲኾኑ ጠቆሙ፤ የፕሬዚደንት ሴኩቱሬ ሐሳብ በጉባኤው አባሎች በሙሉ በመደገፉ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ የአፍሪካ አንድነት ደርጅት የመጀመሪያው ፕሬዚደንት ኾነው ተመረጡ፡፡ ከዚህ በኋላ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ለዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ሥራ ታላቅ መመሪያ የሚሰጥ የሚከተለውን ንግግር አደረጉ፡፡

“ዛሬ የገጠመን ዕድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ መቼም ያልተገኘ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ በፊታችን የተደቀኑት ችግሮች ያንኑ ያህል ከፍ ያሉና ከባድ ናቸው፡፡ ታሪክና ጊዜ የጣሉብን ከፍተኛ ኃላፊነት ሁላችንም ረጋ ብለን እንድናስብና እንድናመዛዝን ያስገድደናል፡፡ የተነሳንበትን ከፍተኛ ተግባር በመልካም አከናውነን ብንገኝ ስማችንና ተግባራችን በታሪክ መልካም ስም ይኖረዋል፡፡ ተግባራችንን ሳንፈጽም ብንቀር ግን ይታዘንብናል፡፡ ስለዚህ እምነታቸውን የጣሉብንን ሕዝቦቻችን በሚመጡት ጊዜያቶች ውስጥ ከእኛ የሚጠብቁትን ሁሉ ለመፈጸም እንዲያበቃን ሁሉን የሚችለውን ፈጣሪያችን ጥበብንና አስተዋይነትን እንዲሰጠን እናምነዋለን፣ እንለምንዋለንም፡፡’’

በወቅቱ በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ የተገኙት የናይጄሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር ታፌዋ ባሌዋ ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ኢትዮጵያና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽዖ ሲገልጹ ተከታዩን ብለው ነበር፤

“መላው የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎችና የመንግሥታት ባለ ሥልጣኖች በአዲስ አበባ ላይ ሊገኙ ለመቻላቸው በግርማዊነትዎ ጥረት ስለሆነ በተለይ ለግርማዊነትዎ እጅግ ከፍ ያለ ክብር የሚያሰጥ ነው፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ አንድነት እንዲገኝ የምናደርገው ጥረት ወደፊት የኢትዮጵያን መናገሻ ከተማ የአዲስ አበባ ስም ደጋግሞ የሚያወሳ ስለሆነ የአዲሲቱ አፍሪካ ታሪክ የግርማዊነትዎን ስም በተቀዳሚው ገጹ ላይ አሳምሮ የሚያኖረው ለመሆኑ ጥርጥር የለበትም፡፡’’

የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮቱሬም በአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያ ያደረገችውን ታላቅ አስተዋጽዖ እንዲህ ገልጸውታል፡-

“… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖች ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል…፡፡’’

ድርጅቱን በመመስረት ረገድ አፄ ኃይለ ሥላሴ የነበራቸውን ሚና አስመልከቶ፣ ኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካ ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ባቀረበው አጠር ያለ ጽሑፍ ‘‘Haile Selassie played a very important role in the establishment of the Organization of African Unity in 1963’’ ብሏል፡፡

‘‘ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ (ቀኃሥ) የአአድ መሥራች እና አባቱም የሆኑለት ከድርጅቱ ዋናዎቹ አንቀሳቃሾች አንዱ እንደነበሩ የጋናው ዘጋኔያን ታይምስ በጁላይ 24፣ 1972 ዕትሙ የፊት ገጽ ላይ ጽፎአል፡፡

የናይጄሪያው ሳንዴይ ኦብዘርቨር ቀኃሥ 80ኛ ዓመታቸውን ባከበሩበት ሐምሌ 16 ቀን 1964 ዓ.ም. (ጁላይ 23፣ 1972) ባወጣው ዕትሙ ‹‹የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አባት ኢትዮጵያዊው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ›› (Haile Selassie I of Ethiopia: Father of the O.A.U.) በሚል ርዕስ ስለግርማዊነታቸው ሰፊ ሐተታ አውጥቶ ነበር፡፡

እንደ ሰንዴይ ኦብዘርቨር አገላለጽ፣ ቀኃሥ ስለ አፍሪካ ያላቸው ውጥን እጅግ በጣም የተዋጣና የተቃና መሆኑን ጠቅሶ፣ አዲስ አበባ ‹‹የፓን አፍሪካን መዲና›› (የአፍሪካ አንድነት ከተማ) ለመባል የበቃችበትን ምክንያት አስታውሶ ነበር፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ኢትዮጵያ ስለአፍሪካ ሕዝብ የፖለቲካ ደኅንነት ላላት ተቆርቋሪነት ጉልህ ምልክት ነው፡፡ ድርጅቱ የተቋቋመውም በድንገት ከተፈጠረ ስሜት አልነበረም፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ በእርጋታና አንዳንድ ጊዜም በግላቸው የአፍሪካ አገሮች ገና ነፃነታቸውን ሳይጎናጸፉ የወደፊት መሪዎች ለሚሆኑት ሰዎች የትምህርትን ዕድል በመስጠት ረድተዋል፡፡ ግርማዊነታቸው በአፍሪካ አህጉር ያላቸው ተሰሚነት አገራቸው ከድንበሮቿ ውጭ ካላት ተሰሚነት የተገኘ ሳይሆን ንጉሠ ነገሥቱ ካተረፉት የመከበር ዕድል ነው፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅትም የአፍሪካ ኃይሎች ራሳቸውን ለመከላከል ይተባበሩ ዘንድ ግርማዊ ጃንሆይ ባላቸው እምነት መሠረት ፈቃዳቸውን ከግቡ ማድረሳቸው የሚያስደንቅ ነው፡፡ በዚህም መሠረት፣ በየትኛም የአህጉሩ ክፍል አምባጓሮ ቢነሳ ተገቢው ስምምነት እንዲፈጸም ግርማዊነታቸው ዓይነተኛ መድኅን ሆነዋል፡፡ በዚህም መሠረት የናይጄሪያ ችግር በተፈጠረበት ጊዜ የአስታራቂነት ዕርምጃ የወሰዱ ሲሆን ይህም ፍጻሜ እንዳገኘ በችግሩ ምክንያት አለመግባባት የተፈጠረባቸውን አፍሪካውያን መሪዎችን ፈጥነው ለማስማማት ችለዋል፡፡ ጃንሆይ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ድርጅት ጋር በመተባበር የወጠኑት 16 ዓመታት የፈጀውን የሱዳንን ችግር በማስወገድ ታሪካዊ ስምምነት እንዲፈጸም አስችሏል፡፡

ግርማዊነታቸው ሴኔጋልና ጊኒ አለመግባባታቸውን ለማስወገድ በተስማሙበት ይኸውም በላይቤሪያ ዋና ከተማ በሞንሮቪያ ውስጥ በተደረገው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ስብሰባ ሊቀ መንበር ሆነው መርተዋል፡፡ በዚህ መሠረት ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ቀደም ሲል ጀምሮ የታሪክ ሥፍራቸውን መያዛቸው ጉልህ ነው፡፡

በውጩም ዓለም ቢሆን አፍሪካ ግንባራቸው ሳይታጠፍ ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካና ከእስያ መሪዎች ጋር ለመቋቋም የሚችሉ ከፍተኛ መሪዎች ያላት መሆኑን ግርማዊ ጃንሆይ በሚገባ አስመስክረዋል፡፡

ኢትዮጵያ በዓለም ጋዜጦች በሚል ርዕስ በእንግሊዝኛ፣ ፈረንሣይኛና ጣሊያንኛ በግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ልዩ ካቢኔ ፕሬስ ክፍል ከ1957 እስከ 1966 ዓ.ም. ይታተም የነበረው መጽሔት የቀኃሥን ተግባሮች መዘከሩ ይታወቃል፡፡ አንዱ የጠቀሰው ለንደን ታይምስ (The Times London) በጁላይ 22፣ 1972 (ሐምሌ 15 ቀን 1965 ዓ.ም.) ዕትሙ፣ ‹‹የንጉሠ ነገሥቱ ጽኑ ሥልጣን በአፍሪካ መሪዎች ዘንድ ታፋሪነትን አትርፎላቸዋል›› (Emperor’s firm authority earns respect among the Leaders of Africa) በሚል ርዕስ ሐተታውን አስፍሮ ነበር፡፡

በመጭረሻም፤ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሰረት ዋነኛ አላማው በቅኝ አገዛዝ ስር የነበሩ አገሮችን ነጻ ማውጣት ነበር፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረት 32 ነጻ ሀገራት ብቻ የነበሩት፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በወቅቱ በቅኝ አገዛዝ ለሚማቅቁ አገሮች ተገቢውን ወታደራዊ ድጋፍና ስልጠና ሰጥቷል፡፡ የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረንስ /ANC/ አፓርታይድን እንዲዋጋና ZANU እና ZAPU የተባሉ የፖለተካ ድርጅቶች ዚምባብዌን ነጻ እንዲያወጡ ድርጅቱ መሳሪያና ወታደራዊ ስልጠና አበርክቷል፡፡

አፓርታይድን ለማውገዝ የደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ በአህጉሪቱ እንዳይበር ማዕቀብ መጣሉና የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን በማሳመን የተመድ አካል የሆነው የዓለም የጤና ድርጅት ከደቡብ አፍሪካ እንዲወጣ ማድረጉ ታሪክ ከመዘገባቸው የድርጅቱ ስኬቶች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ 

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በተመሰረተ በ39 ዓመቱ በ1994 ዓ.ም. ስሙን ለውጦ፣ ዛሬ 55ቱም የአፍሪካ አገራት አባል በሆኑበት የአፍሪካ ኅብረት ተተክቷል፡፡

https://ethioreference.com/archives/31356

***************************************

አፄ ኃይለ ሥላሴ፣ ኢትዮጵያና የአፍሪካ አንድነት/ኅብረት – በፍቅር ለይኩን
 
en-haile-selassie‹‹ኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካ›› ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ባቀረበው አጠር ያለ ጽሑፍ እንዲህ ብሏል፡- ‹‹Haile Selassie played a very important role in the establishment of the Organization of African Unity in 1963.›› ዕለታዊው የአዲስ ዘመን የወርኻ ግንቦት 15 ቀን 1955 ዓ.ም ዕትሙ በፊት ለፊት ገጽ ላይ፣ ‹‹ሠላሳ የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ጉባኤ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፈተ፡፡ ግርማዊ ጃንሆይም የጉባኤው የክብር ሊቀመንበር እንዲሆኑ ተመረጡ፡፡›› በሚል ዐቢይ ርዕስ ዜናና ሰፊ ሐተታን ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡
የሰኞ ማለዳው የግንቦት 19 ቀን 1955 ዓ.ም የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ደግሞ በርእሰ አንቀጹ፣ ‹‹የካዛብላንካና የሞኖሮቪያ የሌሎችንም ብሎኮችና ቻርተሮች ሠርዞ የአፍሪካ አንድነትን የሚመሠርተው ‹የአፍሪካና የማላጋሲ አገሮች ድርጅት ቻርተር› ግንቦት 17 ቀን ለግንቦት 18 ቀን አጥቢያ 1955 ዓ.ም. ከሌሊቱ 7 ሰዓት ከ45 ደቂቃ ላይ በአፍሪካ አዳራሽ ውስጥ ተፈርሟል፡፡ በአራቱ ቀን ጉባኤ ፍጻሜ አዲስ የአፍሪካ ታሪክ፣ አዲስ የዓለም ታሪክ ተጽፏል፣ ተመዝግቧል፡፡›› ሲል የምስራቹን ዜና አስነብቧል፡፡ የትላንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬው የአፍሪካ ኅብረት የ50ኛ ዓመቱን የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓሉን በተለያዩ አገር አቀፍና አኅጉር አቀፍ ዝግጅቶች ለማክበር ዝግጅቱን ከጀመረ ወራት ተቆጥረዋል፡፡ በተለይም ደግሞ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት መመሥረት ግንባር ቀደም ሚና ባላትና ታላቅ አስተዋጽኦ ባደረገችው፣ የኅብረቱም ዋና መቀመጫ በሆነችው በአገራችን ኢትዮጵያ የበዓሉን ዝግጅት የደመቀና ልዩ ለማድረግ ሽር ጉድ እየተባለ ነው፡፡
ይህን በዓልም ባማረና በደመቀ ሁኔታ ለማክበር ራሱን የቻለ የበዓል ዝግጅት ሴክረታሪያት ቢሮ ተቋቁሞ፣ የአፍሪካ ኅብረት የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት በዓሉን ዓመቱን ሙሉ ለማክበር፣ የተለያዩ ዝግጅቶችን ቀርጾ በእንቅስቃሴ ላይ እንደሆነ አይተናል፣ ሰምተናል፣ አውቀናልም፡፡
ከወራት በፊትም በመዲናችን በአዲስ አበባ ዋና ዋና ቦታዎችና አደባባዮች ላይ ‹‹I am African. I am the African Union›› የሚሉ የአፍሪካ ሕዝቦችን ማንነት፣ ታሪክ፣ ቅርስና ባህል የሚያንጸባርቁ፣ የአፍሪካዊነትን ስሜት፣ ኩራትና ወኔ የሚቀሰቅሱ ፖስተሮችን አይተናል፡፡ ከዑራኤል ወደ እስጢፋኖስ በሚወስደውም መንገድ ላይም የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ያቋቋሙ የፓን አፍሪካ አቀንቃኝ የሆኑ አባቶች ምስልም በትልቁ ተሰቅሎ አይቻለሁ፡፡ ይህ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መልካም ሊባል የሚችል ነው፡፡ ለወደፊቱም በዓሉ በተለያዩ መጠን ሰፊ በሆኑ ዝግጅቶች እንደሚከበርና በበዓሉም ላይም የአፍሪካ አገራት ርዕሳነ ብሔራት፣ ተወካዮችና ባለ ሥልጣናት፣ ዓለም አቀፍ መሪዎች፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለ ሙያዎች፣ ፖለቲከኞች፣ ደራሲያን፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች … ወዘተ በሚሳተፉበት በደመቀ ሁኔታ በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር የበዓሉ ዝግጅት ኮሚቴ በተደጋጋሚ አሳውቋል፡፡
በዚህ ጽሑፌ ከሰሞኑ መላው አፍሪካና አፍሪካውያን፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና እንዲሁም በአጠቃላይ የአፍሪካ ወዳጆች፣ የመንግሥታቱ ድርጅት፣ የተለያዩ አኅጉራዊና ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ታዋቂ ሰዎች አብርውን በደስታ ሊያከብሩት እየተዘጋጁ ስላለው የአፍሪካ ኅብረት የ50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ስናወራ ልብ ልንለው የሚገባ አንድ ትልቅ ቁም ነገር አለ፡፡
ይኸውም በዚህ በዓል ላይ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ለአፍሪካ ኅብረት እውን መሆን ትልቅ መሥዋዕትነት የከፈሉትንና ስማቸውን በወርቅ ቀለም በታሪክ ማሕደር የጻፉትን አፍሪካውያን አባቶቻችንን ማስታወስ የሚገባን ይመስለኛል፡፡ ይህ ጽሑፍም ለትላንትናው አፍሪካ አንድነት ድርጅት ለዛሬው የአፍሪካ ኅብረት እውን መሆን የታገሉትን የፓን አፍሪካ አቀንቃኝ አባቶቻችንን ታሪክ በተከታታይ በአጭሩ ለማቅረብ ይሞክራል፡፡
ይህ ጹሑፍ የአፍሪካ ኅብረትን የ50ኛ ዓመት ወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ምክንያት በማድረግ በቅድሚያ የአፍሪካ አባት፣ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማትና የጥቁር ሕዝብ የነጻነት ዓርማ፣ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት መቋቋምና በሂደትም ለኅብረቱ እውን መሆን ትልቁን የመሠረት ድንጋይ ስላስቀመጡት ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ታሪክ፣ ፖለቲካዊ ሰብእና፣ በአፍሪካውያንም ሆነ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ስለነበራቸው መወደድ፣ ተቀባይነትና ታላቅ ክብር በአጭሩ በማዘከር የታሪክ ማስታወሻውን አሐዱ ብሎ ይጀምራል፡፡ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ መንግሥት ታሪክ በእሳቸው ዘመን ከነበሩ ከተራው የኅብረተስብ ክፍል ጀምሮ እስከ ታላላቅ ባለ ሥልጣናትና የሃይማኖት አባቶች፣ ዲፕሎማቶች፣ የውጭ አገር መሪዎች፣ ታላላቅ ሰዎችና ፖለቲከኞች በቃል ከተናገሩት፣ በጽሑፍ ካስቀመጡት፣ በግል ማስታወሻዎቻቸው ከተዉልን፣ እንዲሁም የአጼ ኃ/ሥላሴንና የኢትዮጵያን ታሪክ በተመለከተ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ጸሐፍት በመጻሕፍቶቻቸው ካሰፈሯቸው መረጃዎች በመነሣት ነው ይህን አጠር ያለ የታሪክ ማስታወሻ ጽሑፍ ያዘጋጀሁት፡፡
በአጭር ቃል የዚህ ተከታታይ ታሪክ አቅራቢ የአፄ ኃ/ሥላሴ ዘመን ጣእሙንም ሽታውንም አልደረስበትም፡፡ በእሳርቸው ዘመንም አልታሰበም፣ አልተፈጠረምም፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ታሪክ ተማሪነቴና ባለሙያነቴ የኢትዮጵያን ታሪክ በሰፊውና በሚገባ ማጥናት ከጀመርኩበት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አንስቶ አሁን እስካለሁበት የትምህርት ሕይወቴና የሥራ ልምዴ እንዳስተዋልኩት፣ በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ አፄ ኃ/ሥላሴ በአብዛኛው በአዎንታዊ መልኩ የሚገለጹበት ታሪክ፣ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ ዘንድም አንቱታን ያተረፉበትን ዝናና ክብር እንዲጎናጸፉ ያደረጋቸው በሳል የሆነ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ሰብእና እንዳላቸው ነው የተረዳሁትና ያስተዋልኩት፡፡ በስድስት ዓመታት ውስጥ ለሁለት ጊዜ ‹‹Man of the Year›› የዓመቱ ምርጥ ሰው በማለት የለንዶኑ ታይምስ መጽሔት የመረጣቸው አፄ ኃይለ ሥላሴ ከፍ ያለ ሰብእና የነበራቸውና በዓለም አቀፍ ደረጃ እንደ ታላቅ መሪና አባት የሚታዩ የተዋጣላቸው ዲፕሎማቲክ፣ እንዲሁም በዓለማችን ከሚገኙ ታላላቅ መሪዎችና ፖለቲከኞች ዘንድ ትልቅ ከበሬታ የነበራቸው ኢትዮጵያዊ ንጉሥ እንደነበሩ የታሪክ ድርሳናትና ብዙዎች ሰዎች ይመሰክራሉ፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ኃ/ሥላሴ ከሀያ በየሚበልጡ የክብር ዶክትሬት ድግሪዎችን ከተለያዩ አገራት መሪዎችና ዩኒቨርስቲዎች ተቀብለዋል፡፡ ምናልባትም አገራችን ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከምትታወቀበት ድርቅ፣ ራብና የእርስ በርስ ጦርነት ባሻገር በአንጻራዊ መልኩም ቢሆን በአዎንታዊነት ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የአገራችንን ስም በመልካም እንዲነሣ ምክንያት ከሆኑ የኢትዮጵያ መሪዎች መካከል አፄ ኃ/ሥላሴ አንዱ፣ ብቸኛውና ዋንኛው ናቸው ብል፣ ብዙም ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡ ይህን ኢትዮጵያን አዎንታዊ በሆነ መልኩ እንድትነሳ በማድረግ ረገድና ዓለም አቀፉ የፖለቲካ መድረክ የነበራቸውን ተቀባይነት፣ ክብርና ዝና እንዲሁም ለባለ ቃል ኪዳን አገሮችና በኋላም ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መመሥረት፣ ለ50ኛ ዓመቱ የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓሉ ዋዜማ ላይ ለሚገኘው ለአፍሪካ ኅብረት እውን መሆን፣ ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ የነበራቸውን ትልቅ ሚና የሚያስታውስ አንድ ያጋጠመኘኝን ታሪክ እዚህ ጋር ማንሳቱ ተገቢ ይመስለኛል፡፡
እውቁ የነጻነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላና በርካታ አፍሪካውያን የነጻነት ታጋዮች ለ27 ዓመታት በተጋዙበትና በመንግሥታቱ ድርጅት፣ ዩኔስኮ ዓለም አቀፍ ቅርስ አድርጎ በመዘገበው በሮቢን ደሴት ሙዚየምና በደቡብ አፍሪካ የአርትና ካልቸር ደፓርትመንት የሚሰጠውን የስኮላር ሺፕ አሸንፌ፣ በተማርኩበት በኬፕታውኑ የዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርስቲ የድኅረ ምረቃ ትምህርት ቆይታዬ ከኢትዮጵያዊነት የነጻነት መንፈስና ከአፄ ኃ/ሥላሴ ጋር በተገናኘ አንድ በእጅጉ ያስደነቀኝ ነገር ገጥሞኝ ነበር፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ በዋነኝነት በዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርስቲና በኬፕ ታውን ዩኒቨርስቲ በሚገኙ ደቡብ አፍሪካውያንና የሌሎች አፍሪካ አገሮች የተቋቋመ የግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ (የራስ ተፈሪያን) የተማሪዎች እንቅስቃሴ ኅብረት በሚል መጠሪያ የሚታወቅ በዩኒቨርስቲው ግቢ ቢሮ ተሰጥቶት የሚንቀሰቀስ ማኅበር ነበር፡፡ በነገራችን ላይ በደቡብ አፍሪካ አንዳንድ ዩኒቨርስቲዎች እንደታዘብኩት በፖለቲካና በሃይማኖት፣ እንዲሁም ኪነ ጥበብን፣ ባህልንና ታሪክን መሠረት አድርጎ የተቋቋሙና በነጻነት በዩኒቨርስቲው ግቢ ቢሮ ተሰጥቷቸው የሚንቀሳቀሱ በተማሪዎች የተቋቋሙ የተለያዩ ድርጅቶችና ፓርቲዎች ይገኛሉ፡፡
ታዲያ እኔ በተማርኩበት በዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርስቲ በሚገኘው የግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ የተማሪዎች ኅብረት እንቅስቃሴ ቢሮ ውስጥ የእንቅስቃሴው ደጋፊዎችና አባላት የሆኑት ተማሪዎች ለኢትዮጵውያን የስኮላር ሺፕ ተማሪዎች ባቀረቡላቸው ጥያቄ መሠረት የአማርኛ ቋንቋን የሚያስተምሯቸው ሁለት ሴቶችና አንድ ወንድ ተማሪዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ከእኔ ቀደምው ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ያሉ ተማሪዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ለምርምር ሥራ፣ ለልምድ ልውውጥና ለተጨማሪ ጥናት ወደ አውሮፓ በሄዱበት አጋጣሚ ለእነዚህ አፍሪካውያን ወንድሞቻችን ከአንተ በተሻለ ስለ ኢትዮጵያችን የሺህ ዘመናት ታሪክ፣ ሥልጣኔ፣ የነጻነት ተጋድሎና ቋንቋችንን ሊያስተምራቸው የሚችል የለም በማለት ከራስ ተፈራውያኑ የዩኒቨርስቲው ማኅበረሰብ ጋር አስተዋወቁኝ፡፡
ከዚሁ ማኅበር አባላት ተማሪዎቹ ጋር በተዋወኩበት በአጭር ጊዜ ውስጥ በሚገባ ለመግባባት ቻልን፡፡ ለጥቂት ወራት እነዚህ ወጣት ተማሪዎች የአማርኛ ቋንቋ ማስተማር ቆይታዬ እንዲሁም በተለያዩ አጋጣሚዎች ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ፣ ባህል፣ ቅርስ፣ ሃይማኖት … ወዘተ ባደርግናቸው ውይይቶች በርካታ ቁም ነገሮችን አንስተን እንነጋገር ነበር፡፡ በአብዛኛው የውይይታችን ማእክል ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ለፓን አፍሪካ እንቅስቃሴ፣ ለአፍሪካ የፀረ-ባርነትና የፀረ-ቅኝ ግዛት የነፃነት ትግል፣ በደቡብ አፍሪካ ፀረ-አፓርታይድ ትግል ውስጥ ስለነበራቸው ጉልህ ሚናን በተመለከተ ነበር፡፡ በዚህ ውይይታችን ውስጥ ደግሞ ደጋግመው ከሚነሱት መካከል አፄ ኃ/ሥላሴ አንዱና ዋናው መሆናቸውን ልብ ይሏል፡፡
እኔ እንደ ኢትዮጵያዊነቴና የታሪክ ባለሙያነቴ ስለ አገሬ ኢትዮጵያ ታሪክና ስለ መሪዎቻችን ካለኝ ግንዛቤና እውቀት ይልቅ እነዚህ አፍሪካውያን ተማሪዎች ስለ አኅጉራችን አፍሪካና ስለ አገሬ ታሪክ ያካፈሉኝ እውቀታቸውና ያላቸው መረዳት በጊዜው በእጅጉ ግርምትን አጭሮብኝ ነበር፡፡ እነዚህ ተማሪዎች ኢትዮጵያና ሕዝቦቿ በጥቁር ሕዝቦች ታሪክ፣ ቅርስ፣ ባህልና የነጻነት ተጋድሎ ውስጥ ያላቸውን ማእከላዊ ስፍራን በተመለከተ የሚያስረዱ በቢሮአቸው ያሰባሰቧቸው መጻሕፍቶችና መዛግብቶቻቸው፣ የምስልና የድምፅ መረጃ ክምችቶቻቸው በእጅጉ ነበር ያሰደነቀኝ፡፡
ከዚህም በላይ ደግሞ ሌላው በእጅጉ ያስደመመኝ ነገር ቢኖር በዩኒቨርስቲው ግቢ ውስጥ በሚገኘው የራስ ተፈሪያኑ ተከታዮች ማኅበር ቢሮ ግድግዳ አንድ ጎን በሁለት የታሪክ መስመር ተከፍሎ በተለያዩ ሰዎች ምስሎችና መረጃዎች አሸብርቆ ያየሁት Wall of Fame እና Wall of Shame የሚለው የቢሮው ግድግዳ ክፍል ነው፡፡ በዚሁ Wall of Fame እና Wall of Shame ወይም ‹‹የታሪክ ዕንቁዎችና የታሪክ አተላዎች›› ተብሎ በተከፈለው ግድግዳ ላይ ‹‹በዎል ኦፍ ፌም›› ምስላቸውና ስማቸው በግንባር ቀደምትነት ከተለጠፉት መካከል የአፄ ኃ/ሥላሴና የባለቤታቸው የእቴጌ መነን በመጀመሪያው ረድፍ ይገኛል፡፡ በተጨማሪም በዓድዋው ዘመቻ የኢጣሊያንን ወራሪ ኃይል አሸንፈው አዲስ የጥቁር ሕዝቦችን አዲስ ታሪክ የጻፉት የአፄ ምኒልክ፣ እንዲሁም ከእንግሊዞች ጋር ተዋግተው ራሳቸውን የሠዉት የአፄ ቴዎድሮስ ምስሎችና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
በዚህ ‹‹የታሪክ ዕንቁዎች›› የክብር ግድግዳ ላይ አፄ ኃ/ሥላሴ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በገፍ በወረረች ጊዜ በሊግ ኦፍ ኔሽን፣ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ያቀረቡት አቤቱታና ንግግራቸው በልዩ ንድፍና በአገራችን ሰንደቀ ዐላማ አሸብርቆ በግድግዳው ላይ ይታያል፡፡ ‹‹የዎል ኦፍ ፌምን›› ግድግዳ ካስዋቡ የታሪክ ሰዎች ፎቶግራፎች በአብዛኛው ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ የሚሸቱት በዓይነትም በብዛትም እጅግ ልቀው ይገኛሉ፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በዚሁ ‹‹በዎል ኦፈ ፌም›› የታሪክ መስመር ውስጥ ለጥቁር ሕዝቦች ነጻነት ትልቅ ተጋድሎ ያደረጉ እንደ እነ ማርከስ ጋርቬይ፣ አፍሪካ አሜሪካዊው ማርቲን ሉተር፣ የፓን አፍሪካ አባቶች የጋናው ንኩርማ፣ የኬንያው ጆሞ ኬንያታ፣ ሴኔጋላዊው ሴዳር ሴንጎርና ሌሎችም የአፍሪካ የነጻነት ታጋዮችና መሪዎች በኢትዮጵያ ሰንደቀ ዓላማና በኃ/ሥላሴ ግንባር ቀደም አዝማችነት የክብር ግርግዳውን ተጋርተውታል፡፡
ሌላው አስገራሚው ነገር የንጉሡን የአፄ ኃ/ሥላሴን ልደትና የነገሡበትን ዕለት የራስ ተፈራውያኑ ማኅበር ተከታይ ተማሪዎች እንግዶችን ከውጭ ሁሉ ሣይቀር በመጋበዝ ጭምር የዩኒቨርስቲውን የተማሪዎች ማእክልንና የግቢውን ሜዳ በኢትዮጵያ ሰንደቀ ዓላማ፣ በኃ/ሥላሴና በባለቤታቸው እቴጌ መነን ፎቶ ግራፍ አሸብርቀውና በአፍሪካ የሬጌ ሙዚቃ ስልት አጅበው በታላቅ በሆነ የኢትዮጵያዊነት የነጻነት መንፈስ ቀናቱን ያከበሩ እንደነበረ ትዝ ይለኛል፡፡
የማስታውሰው በዩኒቨርስቲው የምንገኘው በጣት የምንቆጠር ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች በአፍሪካም ሆነ በተቀረው ዓለም በድርቅ፣ በራብና በእርስ በርስ ጦርነት ስማችን እየተነሳ የምንሳቀቅበትን ምስላችንን፣ እነዚህ የዩኒቨርስቲው የራስ ተፈራውያን ተከታይ ተማሪዎች በተለያዩ ጊዜያት በግቢው ውስጥ የአገራችንን አረንዴ፣ ብጫና ቀይ ሰንደቀ ዓላማ ሰቅለው ሲያከብሩ ስናይ በአገር ፍቅር ናፍቆትና ትዝታ፣ በኢትዮጵያዊነት ብሔራዊ ስሜትና ኩራት ውስጣችን የተናጠበትን አጋጣሚ አልረሳውም፡፡ በእርግጥ የእነዚህ ተማሪዎች እንቅስቃሴና አካሄድ በአብዛኛው ሃይማኖታዊ መልክ ያለውና ኃ/ሥላሴን መለኮታዊ ሰብእና እንዳላቸው አድርጎ የሚያቀርብ ቢሆንም የተማሪዎቹ እንቅስቃሴ ከሃይማኖታዊ መልኩ ይልቅ አፍሪካዊነቱና ፖለቲካዊ አንድምታው በእጅጉ የጎላ ነው፡፡ እነዚህ ደቡብ አፍሪካውያንም ሆነ የሌሎች የአፍሪካ አገሮች ተማሪዎች ልብም ሆነ በአብዛኛው ጥቁር ሕዝቦች ልብ ውስጥ ኢትዮጵያ የጥቁር ህዝቦች ታሪክ፣ ባህል፣ ቅርስ፣ ሃይማኖት፣ ነጻነት ትልቅ ተምሳሌትና ማእክል ተደርጋ የምትወሰድ አገር ናት፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ ባላት የሺህ ዘመናት የረጅም ዘመን ሥልጣኔ፣ ታሪክና ቅርስ የተነሣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ የሆነ የታሪክ እሴት ያላት አገር ለመሆን በቅታለች፡፡ በተለይም ደግሞ መላው አፍሪካንና የጥቁር ዘርን ሁሉ ከጫፍ እስከ ጫፍ ያነቃነቀው ኢትጵያውያን በዓድዋ ጦርነት ያስመዘገቡት አንጸባራቂ ድል ኢትዮጵያን ከጥቁር ሕዝቦች ታሪክ ማማ ላይ እንድትወጣ አስችሏታል፡፡
ለአፍሪካ፣ ለአፍሪካ አሜሪካውያንና በጃማይካና በካረቢያ ላሉ የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ትግል መለኮስ ይኸው የአድዋው ድል ትልቅ አስተዋጽኦ ነበረው፡፡ የእነ ማርከስ ጋርቬይና የትግል አጋሮቹ የጥቁር ሕዝቦች የነፃነትና የመብት ጥያቄ ውሉ የሚመዘዘው ከኢትዮጵያዊነት የነጻነት መንፈስ፣ የአባቶቻችን የአይበገሬነትና ቆራጥ የተጋድሎ ታሪክ ውስጥ ነው፡፡ የአፍሪካውያኑ የፓን አፍሪካ አቀንቃኞችና የፀረ ቅኝ ግዛት ታጋዮች የእነ ንኩርማ፣ የእነ ጆሞ ኬንያታ የአፍሪካዊነት ስሜትና ቆራጥ መንፈስ መፍለቂያ ምንጩም ይኸው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ከተሸከሙት ክቡር የነጻነት ተጋድሎ አኩሪ ታሪክና ቅርስ የሚመዘዝ ነው፡፡
ከአፄ ምኒልክ የዓድዋው ድል በኋላ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከኃያላኑ አገሮች እኩል የተሠለፈችው ብቸኛው የጥቁር ሕዝብ አገር ኢትዮጵያ ይህ ገናና የነጻነት ተጋድሎ ታሪኳ ከአፍሪካ እስከ አሜሪካ፣ ከአውሮፓ እስከ ኤዥያ፣ ከመካከለኛው ምስራቅ እስከ ቻይና፣ ሩሲያ፣ ጃማይካና ካረቢያን ምድር ድረስ ዘልቆ ተሰምቶ ነበር፡፡ ይህ የኢትጵያዊነት የነጻነት መንፈስ ውሉ ሳይቋረጥ በአፍሪካውያንና በጥቁር ሕዝቦች ደም ውስጥ በሚገባ ተዋህዶ፣ በተባበረ ክንድ የጸናችና አንድ የሆነች አፍሪካ በዓለም መድረክ ከፍ ብላ እንድትታይ ደግሞ ትልቁን ሚና በመጫወት ረገድ አፄ ኃ/ሥላሴ የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡
ይህን ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ኢትዮጵያና አፄ ኃ/ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦና ተደናቂ ሥራ በተመለከተ በወቅቱ በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ የተገኙት የናይጄሪያው ጠቅላይ ሚኒስቴር የሆኑት፣ ክቡር ሰር አል ሃጂ አቡበከር ታፌዋ ባሌዋ እንደሚከተለው ነበር ያሉት፡- መላው የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎችና የመንግሥታት ባለ ሥልጣኖች በአዲስ አበባ ላይ ሊገኙ ለመቻላቸው በግርማዊነትዎ ጥረት ስለሆነ በተለይ ለግርማዊነትዎ እጅግ ከፍ ያለ ክብር የሚያሰጥ ነው፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ አንድነት እንዲገኝ የምናደርገው ጥረት ወደፊት የኢትዮጵያን መናገሻ ከተማ የአዲስ አበባ ስም ደጋግሞ የሚያወሳ ስለሆነ የአዲሲቱ አፍሪካ ታሪክ የግርማዊነትዎን ስም በተቀዳሚው ገጹ ላይ አሳምሮ የሚያኖረው ለመሆኑ ጥርጥር የለበትም፡፡ አፄ ኃ/ሥላሴ በ1930ዎቹም ኢትዮጵያ የሊግ ኦፍ ኔሽን አባል እንድትሆን በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ኢትዮጵያንም ብቸኛዋ አፍሪካዊትና የጥቁር አገር ሊግ ኦፍ ኔሽን አባል በማድረግ ጥረታቸውን በሚገባ አሳክተዋል፡፡
በኋላም በተባበሩት መንግሥታት ምሥረታ ስብሰባ ወቅትም ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ፍራንክሊን ዴላኖ ሩዜቬልት፣ ከብሪታንያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዊንስተን ቸርችልና ከቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ስታሊን ጋር በያልታ ጥቁር ባሕር ልዩ ስብሳባ ላይ ተሣትፈዋል፡፡ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጋራ ስምምነት መሠረትም በኮሪያ ልሣነ ምድር የኢትዮጵያን የሰላም አስከባሪ ኃይል በማሰማራት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡ በዚህም አፄ ኃ/ሥላሴ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በዓለም አቀፍ መድረክ እንዲታወቁ ትልቁን ሚና ተጫውተው አልፈዋል፡፡
ፍቅር፣ ወንድማማችነት፣ ሰላም፣ አንድነትና ኅብረት ለአፍሪካና ለአፍሪካውያንን ወሳኝና ተቀዳሚ ነገር መሆኑ የተረዱት አፄ ኃ/ሥላሴ አፍሪካውያን አባቶችን፣ ፖለቲከኞችንና መሪዎችን በማስተባበር የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲቋቋም የላቀ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
በወቅቱ ድርጅቱ ሲቋቋም የነበሩ ሰዎች እንደመሠከሩት አፄ ኃ/ሥላሴ እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ የአፍሪካ መሪዎችን ጉባኤ ስብሰባ በመምራት፣ ይህ የአፍሪካውያን የወንድማማችነት፣ የአንድነትና የፍቅር ሰነድ ሳይፈረም ማንኛችንም ብንሆን ከዚህ ስብሰባ አዳራሽ ውስጥ በጭራሽ አንወጣም በማለት የተኮራረፉና የተለያዩ ፖለቲካዊ ቁርሾ ውስጥ የገቡትን የአፍሪካ አገራት መሪዎችን በማግባባትና በማሸማገል ንጉሡ ኅብረቱ እውን እንዲሆን ታላቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡
የትላንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ኅብረት በሁለት እግሩ እንዲቆም በማስቻል የኢትዮጵያ የሺህ ዘመናት ታሪክ፣ ሥልጣኔና ቅርስ፣ የቀደሙ አባቶቻችን ጽኑና አይበገሬ የሆነው የኢትዮጵያዊነት ብሔራዊ ኩራትና መንፈስ እንዲሁም ጥቁር ሕዝቦችን ሁሉ ያኮራውና አንገቱን ቀና አድርጎ እንዲራመድ ያስቻለው የኢትዮጵያውያኑ የነፃነት ተጋድሎ፣ በባርነትና በቅኝ ግዛት ስር ይማቅቁ ለነበሩ ለአፍሪካ አገሮች ነፃነትና አንድነት እውን መሆን ትልቁን መሠረት ጥሏል፡፡
ይህን የኢትዮጵያንና የኢትጵያውያንን ታላቅ ታሪክ፣ ሥልጣኔ፣ ብሔራዊ ኩራትና የአባቶቻችንን አኩሪ የነፃነት ገድል ለዘመናዊው ዓለም በማስተዋወቅና ረገድ የኢትዮጵያ መሪ የነበሩት ኃ/ሥላሴ በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ ክቡር ስምና ዝናና የፈተረላቸውን በርካታ አኩሪ ስራዎችን ሠርተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ዛሬ የ50ኛ ዓመቱን የወርቅ ኢዮቤልዩ ልደቱን ለማክበር ዋዜማ ላይ ያለውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/ኅብረት እንዲቋቋም ከሐሳብ ወይም ከጽንሱ አንስቶ እስከ ተግባራዊነቱ ድረስ የላቀ ተሣትፎ ነበራቸው ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ፡፡
ንጉሡ ቀዳማቂ አፄ ኃ/ሥላሴ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ ጉባኤ ስብሰባ ላይ ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው እንዲህ ነበር ያሉት፡- በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል፡፡ ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው፡፡ ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው … ፡፡ የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮ ቱሬም በአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያና ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦና ሥራ በተመለከተ ሲናገሩ እንዲህ ነበር ያሉት፡-
… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሠ በአፄ ኃ/ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖችም ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል … ፡፡ ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ከአገራችን ኢትዮጵያና ከአፄ ኃ/ሥላሴ ጋር አብሮ ስማቸው የሚነሡ ኢትዮጵያውያን ምሁራንና ድርጅቱንም በጸሐፊነት ያገለገሉ ባለ ታሪክ የሆኑ ሰዎች አሉ፡፡ እነርሱም የውጭ ጉዳይ ሚኒስተሩ አቶ ከተማ ይፍሩና የድርጅቱ የመጀመሪያ ዋና ጸሐፊ ሆነው የተመረጡት አቶ ክፍሌ ወዳጆ ናቸው፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ አቶ ከተማ ይፍሩ በመላው አፍሪካ አገራት በመዞርና መሪዎቹን ወደ ጉባኤው እንዲመጡ በመጋበዝና በማግባባት ታላቅ የሆነ ሚና ተጫውተዋል፡፡ አንዳንድ ጸሐፊዎችና ታሪክ አዋቂዎች እንደሚሉትም አቶ ከተማ ይፍሩ ከመሪዎቹ ማረጋገጫ እስከሚያገኙ ድረስ ወደ አገራቸው መሄድ እንደማይችሉ በመግለጽ አፍሪካውያን መሪዎች በስብሰባው ላይ እንዲገኙ በማድረግ ትልቅ ጥረት ማድረጋቸውን ብዙዎች ይመሰክሩላቸዋል፡፡
የዛሬውን መጣጥፌን ከማጠናቀቄ በፊት በቀጣይ ጽሑፌ ስለ ፓን አፍሪካ አመሠራረትና፣ በፓን አፍሪካ እንቅስቃሴ ውስጥ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውን ድርሻ ምን እንደነበር ከታሪክ ማሕደር በማጣቀስ ለመጻፍ እሞክራለሁ፡፡ በጽሑፌም ቀንደኛ ፓን አፍሪካኒስት ስለነበረው የጋናው ዶ/ር ንኩርማ በጥቂቱ ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡ የዛሬውን አጭር መጣጥፌን ኢትዮጵያ፣ ጀግና ልጆቿና ንጉሠ ነገሥቷ የነበሩት አፄ ኃ/ሥላሴ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅትና መመሥረትና በኋላም ለኅብረቱ እውን መሆን ያበረከቱትን ትልቅ አስተዋጽኦ ያዘከርኩበትን አጭር የታሪክ ማስታወሻ፣ አፄ ኃ/ሥላሴ በአዲስ አበባ ላይ በተደረገው የግንቦት 15ቀን 1955 ዓ.ም. የአፍሪካ መሪዎች መክፈቻ ጉባኤ ላይ ባሰሙት ታሪካዊ ንግግራቸው ጽሑፌን ልቋጭ፡፡
ዛሬ የገጠመን ዕድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ መቼም ያልተገኘ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ በፊታችን የተደቀኑት ችግሮች ያንኑ ያህል ከፍ ያሉና ከባድ ናቸው፡፡ ታሪክና ጊዜ የጣሉብን ከፍተኛ ኃላፊነት ሁላችንም ረጋ ብለን እንድናስብና እንድናመዛዝን ያስገድደናል፡፡ የተነሳንበትን ከፍተኛ ተግባር በመልካም አከናውነን ብንገኝ ስማችንና ተግባራችን በታሪክ መልካም ስም ይኖረዋል፡፡ ተግባራችንን ሳንፈጽም ብንቀር ግን ይታዘንብናል፡፡ ስለዚህ እምነታቸውን የጣሉብንን ሕዝቦቻችን በሚመጡት ጊዜያቶች ውስጥ ከእኛ የሚጠብቁትን ሁሉ ለመፈጸም እንዲያበቃን ሁሉን የሚችለውን ፈጣሪያችን ጥበብንና አስተዋይነትን እንዲሰጠን እናምነዋለን፣ እንለምንዋለን፡፡
ክብር ለአፍሪካ አንድነት ለደከሙ አፍሪካውያን አባቶቻችንና ጀግኖቻችን ሁሉ! ሰላም! ሻሎም!

 

 

***********************************

የዛሬው አፍሪካ ሕብረት የትላንቱ የአፍሪካ አንድነት ምስረታ

 
የትናንቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ህብረት የተመሰረተው ከ57 አመታት በፊት በዚህ ሳምንት ግንቦት 16 ቀን 1955 ዓ.ም ነበር::
ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ በጉባኤው ላይ ለተገኙት የአፍሪካ መሪዎች ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው እንዲህ አሉ፡-
"በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል:: ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም:: የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው:: ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው … ::"
ዕለታዊው የአዲስ ዘመን የወርሀ ግንቦት 15 ቀን 1955 ዓ.ም ዕትሙ በፊት ለፊት ገጽ ላይ፣ ‹‹ሠላሳ የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ጉባኤ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፈተ:: ግርማዊ ጃንሆይም የጉባኤው የክብር ሊቀመንበር እንዲሆኑ ተመረጡ::›› በሚል ዐቢይ ርዕስ ስር እንዲህ ይላል፡-
"ቁጥራቸው ከ250 ሚሊየን በላይ በሆኑ አፍሪካውያን እጅግ በጋለ ስሜት ይጠበቅ የነበረውና መላው ዓላም ህዝብ ሁኔታውን በቅርብ ይከታተለው የነበረው የ30ዎቹ የአፍሪካ ነጻ መንግስታት መሪዎች ጉባዔ ግንቦት 14 ቀን ትናንት ከእኩለ ቀን በኋላ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፍቷል:: … ጉባኤውን የከፈቱት ግርማዊ ንጉሠ ነገስት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጉባኤው ስራውን ከመጀመሩ በፊት የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት እንዲደረግ አሳስበው ጸሎት ተደረገ:: ቀጥሎም የሊቀ መንበር ምርጫ እንዲደረግ አሳስበው የጊኒው ፕሬዚደንት ሴኩቱሬ የመጀመሪያውን ምርጫ እንዲያደርጉ ጠየቁ:: ክቡር ፕሬዚደንት ሴኩቱሬ ቀደም ብሎ ተደርጎ የነበረው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጉባዔ ጠቅላላ ውሳኔ ያልሰጠ መሆኑን በመግለጽ ከተናገሩ በኋላ፣ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት የጉባዔው ፕሬዚደንት የላይቤሪያው ፕሬዚደንት ተብማን፤ የተባበረው የአረብ አንድነት ሪፐብሊክ ፕሬዚደንት ናስርና የጋናው ፕሬዚደንት ንኩሩማህ፤ የአይቮሪኮስቱ ፕሬዚደንት ቧኜ፤ የናይጄሪያው ታፌዋ ባሌዋ የሴኔጋሉ ሊዎፖልድ ሴንጎር፤ የኮንጎ ብራዛቪሉ ኦቦ ፋልቤር ዩሉና የታንጋኒካው ጁሊየስ ኔሬሬ የጉባኤው ተከታታይ ፕሬዚደንቶች እንዲሆኑ ሐሳብ አቀረቡ::
ይህ ሐሳብ በጉባኤው አባሎች በሙሉ በመደገፉ በፕሬዚደንት ሴኮቱሬ የቀረበው ምርጫ ጸደቀ:: ከዚህ በኋላ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ለዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ሥራ ታላቅ መመሪያ የሚሰጥ ንግግር አደረጉ::"
አፄ ኃይለ ሥላሴ በወቅቱ ባደረጉት ታሪካዊ ንግግራቸው እንዲህ ብለው ነበር::
"ዛሬ የገጠመን ዕድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ መቼም ያልተገኘ ትልቅ ዕድል ነው:: በፊታችን የተደቀኑት ችግሮች ያንኑ ያህል ከፍ ያሉና ከባድ ናቸው:: ታሪክና ጊዜ የጣሉብን ከፍተኛ ኃላፊነት ሁላችንም ረጋ ብለን እንድናስብና እንድናመዛዝን ያስገድደናል:: የተነሳንበትን ከፍተኛ ተግባር በመልካም አከናውነን ብንገኝ ስማችንና ተግባራችን በታሪክ መልካም ስም ይኖረዋል:: ተግባራችንን ሳንፈጽም ብንቀር ግን ይታዘንብናል:: ስለዚህ እምነታቸውን የጣሉብንን ሕዝቦቻችን በሚመጡት ጊዜያቶች ውስጥ ከእኛ የሚጠብቁትን ሁሉ ለመፈጸም እንዲያበቃን ሁሉን የሚችለውን ፈጣሪያችን ጥበብንና አስተዋይነትን እንዲሰጠን እናምነዋለን፣ እንለምንዋለን::"
ግንቦት 17 ቀን ማታ ከምሽቱ ሁለት ሰኣት ጀምሮ በታላቁ ቤተመንግስት ስለአፍሪካ መሪዎች እንግድነት ክብር ታላቅ የእራት ግብዣ አድርገው ነበር::
ሰኞ ግንቦት 19 ቀን 1955 ዓ.ም የወጣው የአዲስ ዘመን ጋዜጣ "ካዛብላንካና ሞኖሮቪያ ተሰርዞ አንድ ቻርተር ተፈረመ" በሚል ርዕስ ባወጣው ዜና ‹‹የካዛብላንካና የሞኖሮቪያ የሌሎችንም ብሎኮችና ቻርተሮች ሠርዞ የአፍሪካ አንድነትን የሚመሠርተው ‹የአፍሪካና የማላጋሲ አገሮች ድርጅት ቻርተር› ግንቦት 17 ቀን ለግንቦት 18 ቀን አጥቢያ 1955 ዓ.ም ከሌሊቱ 7 ሰዓት ከ45 ደቂቃ ላይ በአፍሪካ አዳራሽ ውስጥ ተፈርሟል::"
ተደናቂ ሥራ በወቅቱ በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ የተገኙት የናይጄሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር ታፌዋ ባሌዋ ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ኢትዮጵያና አፄ ኃይለ ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦ ሲገልጹ ተከታዩን ብለው ነበር::
"መላው የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎችና የመንግሥታት ባለ ሥልጣኖች በአዲስ አበባ ላይ ሊገኙ ለመቻላቸው በግርማዊነትዎ ጥረት ስለሆነ በተለይ ለግርማዊነትዎ እጅግ ከፍ ያለ ክብር የሚያሰጥ ነው:: በዚህ ጉባኤ ላይ አንድነት እንዲገኝ የምናደርገው ጥረት ወደፊት የኢትዮጵያን መናገሻ ከተማ የአዲስ አበባ ስም ደጋግሞ የሚያወሳ ስለሆነ የአዲሲቱ አፍሪካ ታሪክ የግርማዊነትዎን ስም በተቀዳሚው ገጹ ላይ አሳምሮ የሚያኖረው ለመሆኑ ጥርጥር የለበትም::"
የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮቱሬም በአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያ ያደረገችውን ታላቅ አስተዋጽዎ እንዲህ ገልጸውታል፡-
"… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው:: ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው:: ይህ በንጉሡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖች ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል:: ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል …::"
በፍቅር ለይኩን የተባሉ የታሪክ ባለሙያ የአፍሪካ ኅብረት የ50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓልን አስመልክተው ባሰናዱት ጽሑፍ ድርጅቱን በመመስረት ረገድ አፄ ኃይለ ሥላሴ የነበራቸውን ሚና እንደገለጹት ፣ "‹ኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካ› ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ባቀረበው አጠር ያለ ጽሑፍ ‹Haile Selassie played a very important role in the establishment of the Organization of African Unity in 1963›› ብሏል:: …
ፍቅር፣ ወንድማማችነት፣ ሰላም፣ አንድነትና ኅብረት ለአፍሪካና ለአፍሪካውያንን ወሳኝና ተቀዳሚ ነገር መሆኑ የተረዱት አፄ ኃይለ ሥላሴ አፍሪካውያን አባቶችን፣ ፖለቲከኞችንና መሪዎችን በማስተባበር የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲቋቋም የላቀ አስተዋጽኦ አድርገዋል::
በወቅቱ ድርጅቱ ሲቋቋም የነበሩ ሰዎች እንደመሠከሩት አፄ ኃይለ ሥላሴ እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ የአፍሪካ መሪዎችን ጉባኤ ስብሰባ በመምራት፣ ይህ የአፍሪካውያን የወንድማማችነት፣ የአንድነትና የፍቅር ሰነድ ሳይፈረም ማንኛችንም ብንሆን ከዚህ ስብሰባ አዳራሽ ውስጥ በጭራሽ አንወጣም በማለት የተኮራረፉና የተለያዩ ፖለቲካዊ ቁርሾ ውስጥ የገቡትን የአፍሪካ አገራት መሪዎችን በማግባባትና በማሸማገል ኅብረቱ እውን እንዲሆን ታላቅ ሚና ተጫውተዋል::

***********************************

ታሪክ በዛሬው ዕለት
ግንቦት 17 ቀን ከተፈፀሙ የታሪክ ክስተቶች መካከል
•1955 ዓ/ም - የ22 ነጻ የአፍሪቃ አገራት መሪዎች አዲስ አበባ ላይ ተሰብስበው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን መሠረቱ።
•1963 ዓ/ም - በአዲስ አበባ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሰላማዊ ሰልፍ፤ በከተማው ወጥቶ-እብሶች እና ንብረት ላይ ጉዳት አደረሱ። በዚህም ምክንያት አሥር ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤቶች ተዘጉ።
•1977 ዓ/ም - በባንግላዴሽ ታላቅ አውሎ ነፋስ ተነስቶ ያስከተለው የዝናብ ጎርፍ ፲ ሺ የሚጠጉ ሰዎችን ገደለ።
•1989 ዓ/ም - በሲዬራ ሌዎን፣ በሻምበል ጆኒ ፖል ኮሮማ የተመራ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ፕሬዚደንት አህመድ ቴጃን ካባህን ከሥልጣን አወረደ።
.......................................................
#የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ምስረታ - 57ኛ ዓመት
የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (የአሁኑ "የአፍሪካ ኅብረት - AU") የተመሰረተው ከዛሬ 57 ዓመታት በፊት (ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም) ነበር፡፡
እ.አ.አ በ1884/85 ከተካሄደው የበርሊን ጉባዔ (Berlin Conference) በኋላ ኃያላኑ የአውሮፓ አገራት የአፍሪካ አገራትን በመቀራመት የቅኝ ግዛት አደረጓቸው፡፡ አውሮፓውያኑ አገራትም በቀጥተኛ አስተዳደር እንዲሁም በከፋፍሎ መግዛት መርሆች በመታገዝ አፍሪካውያኑን ለባርነት ዳረጓቸው፡፡ የአፍሪካን የተፈጥሮ ሀብት ለኢንዱስትሪዎቻቸው ግብዓት ወደ አገራቸው አጋዙት፡፡
የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም አውሮፓዊው ወራሪ የኢጣሊያ ጦር በታላቁ ንጉሰ ነገሥት ዳግማዊ አጤ ምኒልክ በተመራው የኢትዮጵያ ጦር ሲሸነፍ በቅኝ ግዛት ቀንበር ስር ያሉ አፍሪካውያን ስለነፃነት በርትተው ማለም ጀመሩ፡፡ ታላቁ የዓድዋ ድል የማንቂያ ደወል ሆነላቸው፡፡ ከዚህ ጊዜ በኋላ አፍሪካውያን በአንድም ይን በሌላ መንገድ ለነፃነታቸው መዋጋት ጀመሩ፡፡ ጋና የጀመረችው የነፃነት ችቦ በሌሎቹም አገራት አበራ፡፡
የአኅጉሩ መሪዎች በዓለም መድረክ ላይ ለበለጠ ተሰሚነትና የትብብርን ግንባር ማሳየት እንደነበረባቸው በመገንዘብና ገና ነጻ ላልወጡትም ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ሉዐላዊነት መታገል ስለነበረባቸው ዓላማቸውን ግብ ለማድረስ የሚያስችል ኅብረት/ማኅበር ለመመስረት አሰቡ፡፡ ማኅበሩን በመመስረት ሂደት ላይም ኢትዮጵያና ከቅኝ ግዛት ነፃ የወጡት አገራት በሁለት የተለያዩ ጎራዎች ተከፈሉ፡፡
አንደኛው ቡድን ራሱን ‹‹የዘመናዊ ተራማጅ›› ብሎ የሚጠራው ‹‹የካዛብላንካ ቡድን›› ሲሆን የቡድኑ አባላት በፖለቲካና በኢኮኖሚ የተዋሃደች የአፍሪካ ፌደሬሽንን የመመስረት ዓላማና የግራ ዘመም ፖለቲካ አቀንቃኝ በሆኑ መሪዎች የተዋቀረ ነበር፡፡ በዚህ ጎራ የተሰለፉት አገራት ጋና፣ አልጄሪያ️፣ ጊኒ🇬🇳️፣ ሞሮኮ🇲🇦️፣ ግብጽ🇪🇬️፣ ማሊ🇲🇱️ እና ሊቢያ 🇱🇾️ሲሆኑ የቡድኑ መሪም የወቅቱ የጋናው ፕሬዝደንት ክዋሜ ንክሩማህ ነበሩ፡፡
ሁለተኛው ቡድን ደግሞ ‹‹የሞንሮቪያ ቡድን›› ሲሆን የአፍሪካ አገራት ያለፖለቲካዊ ውህደት በኢኮኖሚያዊና በሕዝብ ለሕዝብ ትስስሮች ተባብረው መዝለቅ እንዳለባቸው ያምናል፡፡ በዚህ ጎራ የነበሩት አገራት ሴኔጋል🇸🇳️፣ ናይጄሪያ🇳🇬️፣ ላይቤሪያ🇱🇷️ እና ኢትዮጵያ 💚💛🧡 ነበሩ።
በመጨረሻም በወቅቱ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ታላቅ ጥረትና በንጉሰ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ ሁለቱም ወገኖች አዲስ አበባ ላይ እንዲገናኙ በተደረገው ጥሪ መሠረት ግንቦት 14 ቀን 1955 ዓ.ም የ32 ነጻ አገራት ተወካዮች አዲስ አበባ ላይ ለስብሰባ ተቀመጡ፡፡ ከሦስት ቀናት ውይይት በኋላም፣ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም አገራቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን የስምምነት ውል (OAU Charter) ሲፈርሙ የድርጅቱ ምስረታ እውን ሆነ።
በወቅቱም የአገራቱ መሪዎች ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ንጉሰ ነገሥት ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ፣ ጸሐፌትዕዛዝ ክቡር አቶ አክሊሉ ሀብተወልድና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ያበረከቱት አስተዋፅኦ ላቅ ያለ ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ በርካታ ወገኖች ለቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ‹‹የአፍሪካ አባት›› የሚል ስም ሰጥተዋቸዋል፡፡
ጃንሆይ - የአፍሪካ አባት! 
 
ምንጭ:- ልዑል ዓምደጽዮን ሠርፀድንግል እና ልዩ ልዩ


**********************************

የአፍሪካ ኅብረት (አንድነት ድርጅት) ምሥረታ የዓይን እማኝ የነበሩት ፊታውራሪ ምን ይላሉ?

መንግሥቱ አበበ__Saturday, 01 June 2013 

 *************************************

እንግዶች በመሳፍንትና በመኳንንት ቤቶች አርፈዋል ሁፌት ቧኜ አውሮፕላን ስለማይወዱ በመርከብና በባቡር ነበር የመጡት

የኋላ ማርሽ አስገብተን ወደ ዛሬ 51 ዓመት እንጓዝ፡፡ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት ከቅኝ አገዛዝ ነፃ የወጡበት ጊዜ ነበር፡፡ ነፃ ያልወጡም አገራት ነበሩ፡፡ አፍሪካ ተባብራ ችግሮቿን እንድትፈታ፣ ነፃነቷንም እንድታስከብርና ነፃ ያልወጡ አገራትን እንድትደግፍ፣ በአንድነት የምንትቀሳቀስበት ኅብረት ያስፈልጋታል በማለት የፓን አፍሪካኒዝም የሚቀነቀንበት ወቅት ነበር፡፡ ከብዙ ጥረት በኋላ ሐሳቡ ተቀባይነት አገኘና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲመሠረት ነፃ የአፍሪካ መንግሥታት ተስማሙ፡፡

ነገር ግን ማን አስተባባሮ ድርጅቱ ይመሥረት? ቻርተሩንስ ማን ያዘጋጀው? የድርጅቱ መቀመጫስ የት ይሁን? … የሚሉት ምላሽ የሚሹ ጥያቄዎች ነበሩ።

በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያ እኔ ኃላፊነቱን እወጣለሁ አለች፡፡ ይኼኔ ከየአካባቢው ተቃውሞ ተነሳ፡፡ “ኢትዮጵያ መሰብሰቢያ አዳራሽ፣ ሆቴል፤ መንገድ፤ ንፅህና፣ … የላትም፡፡ ካይሮ፣ ሌጐስ፣ ናይሮቢ፣ … እያሉ እንዴት አዲስ አበባ መቀመጫ ትሆናለች? በማለት የተቃወሙ ፖለቲከኞች ብዙ ናቸው፡፡ ነገር ግን ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ በነበራቸው ብልህ ፖለቲካዊ ብስለት፣ ከፍተኛ ጥረትና የማሳመን ችሎታ፣ አዲስ አበባ ከ51 ዓመት በፊት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የአፍሪካን አንድነት ድርጅት ምሥረታ ጉባኤ እንድታዘጋጅ ተወሰነ፡፡ ከውሳኔው በኋላ ጃንሆይ የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸውን ሰብስበው፣ ጉዳዩን ካስረዱ በኋላ “ጊዜ የለንም፤ ያሉን 12 ወራት ብቻ ናቸው። የአውሮፕላን ማረፊያ ሜዳ፣ መሪዎች ሲመጡ የሚያርፉበትና የሚሰበሰቡበት አዳራሽ የለም። ጎበዝ! እንዴት ይህን ኃላፊነት እንወጣ? በማለት ጠየቁ፡፡ ለዝግጅት የተሰጠው ጊዜ በጣም አጭር ነው፡፡

ለምን ስብሰባው ለሌላ ጊዜ አይተላለፍም? በማለት ሐሳብ ያቀረቡ ሚኒስትሮች ነበሩ፡፡ ልዑል ራስ መንገሻ ስዩም (በወቅቱ ደጃዝማች) “ዕድሉ ሊያመልጠን አይገባም፡፡ ገንዘቡ ከተፈቀደልኝ በተባለው ጊዜ ውስጥ (እንዲያውም ከዚያ ቀደም ብዬ በዘጠኝና በአስር ወር) ሥራውን አጠናቅቄ አስረክባለሁ” በማለት ቃል ገቡ፡፡ ንጉሡም፣ ልዑል ራስ መንገሻ የተግባር ሰው መሆናቸውን ስለሚያውቁ “መንገሻ አደርገዋለሁ ካለ ያደርገዋል” በማለት በሐሳባቸው ተስማሙ፡፡ “ሥራው ወዲያውኑ ተጀምሮ ሌት ተቀን እየተሠራ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ፣ የአፍሪካ አዳራሽና የግዮን ሆቴል ተሠርተው ስላለቁ፣ ጉድ ተባለ፡፡ ልዑል ራስ መንገሻም “ልጄ ተባረክ” በመባል በንጉሡ ተመሰገኑ ያሉት በወቅቱ የፓርላማ አባል የነበሩት ፊታውራሪ አበበ ሥዩም ደስታ ናቸው፡፡

ፊታውራሪ አበበ ሥዩም የዛሬ 50 ዓመት የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሠረት በፓርላማ ሕግ መምሪያ ም/ቤት የተንቤን ሕዝብ እንደራሴና የበጀት ኮሚቴ ሊቀመንበር ነበሩ፡፡ ስለ አፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ፣ ስለ እንግዶቹ አቀባበልና ዝግጅት፣ … የሚናገሩት አላቸው። ዛሬ ፊታውራሪ አበበ የ83 ዓመት አዛውንት ናቸው። በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ በዝርዝር ሲናገሩ የማስታወስ ችሎታቸው ይደንቃል፡፡ ከ50 ዓመት በፊት የነበረውን ነገር ከዓመትና ከሁለት ዓመት በፊት እንደተፈፀመ ታሪክ ነው የሚያንበለብሉት፡፡ የሕይወት ታሪካቸውንም ጽፈው “ዝክረ ሕይወት” በሚል ርዕስ አሳትመዋል፡፡

ፊታውራሪ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተመሠረተው እንዴት እንደነበር ያጫውቱናል፤ እንከታተላቸው፡፡ በዚያን ጊዜ አፄ ኃይለ ሥላሴ አፍሪካን አንድ የማድረግ ሕልም ነበራቸውና ሕልማቸው ተሳካ። በንጉሡ ዙሪያ የተሰባሰቡት ሚኒስትሮች በሳል ዲፕሎማቶች ነበሩ፡፡ ካቢኔው የሚመራው በጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀ/ወልድ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ክቡር ከተማ ይፍሩ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር፣ ክቡር ዶ/ር ተስፋዬ ገ/እግዚ የማስታወቂያ ሚ/ር፣ ክቡር ዶ/ር ምናሴ ኃይሌ፤ ክቡር አቶ ሰይፉ ማኅተመ ሥላሴ፣ እንዲሁም አፈ-ንጉሥ ተሾመ … የሚባሉ ሚኒስትሮች ወደ ተለያዩ የአፍሪካ አገሮች እየሄዱ ሲያስተባብሩና ሲያግባቡ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ብዙ ተደማጭነት የነበራቸው የግብፁ መሪ ጋማል አብዱልናስር ነበሩ፡፡ እሳቸውን ለማግባባት ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡ ይኼው የማግባባት ጥረት ተሳክቶ ስብሰባው በአዲስ አበባ እንዲካሄድ ሲወሰን እንግዶቹ መጥተው የሚሰበሰቡበት አዳራሽ፣ የሚያርፉበት ሆቴል፣ የለም፡፡ የተሰጠን ጊዜ ደግሞ አንድ ዓመት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ካላዘጋጀን ዕድሉ ለሌላ ይተላለፋልና ምን ይደረግ? ተባለ።

የሲዳሞ ጠቅላይ ገዥ የነበሩት ክቡር ደጃዝማች መንገሻ ሥዩም የሥራና መገናኛ ሚኒስትር ሆነው ስለተሾሙ፣ “ገንዘብ ከተሰጠኝ በአንድ ዓመት ውስጥ አይደለም፤ በዘጠኝ ወር ግፋ ቢል በአስር ወር ጨርሼ አስረክባለሁ” በማለት ለጃንሆይ ቃል ገቡ፡፡ “መንገሻ አያደርግም አይባልም፤ ይሠራል” ተባለ፡፡ የገንዘብ ሚ/ር የነበሩት እነ ክቡር አቶ ይልማ ዴሬሳና አንዳንድ ሚኒስትሮች “ይኼ እንዴት ይሆናል?” በማለት ጥያቄ አንስተው ነበር፡፡ ሥራው ተጀምሮ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፍያና የአፍሪካ አዳራሽ የተሠራው ያኔ ነው፡፡ 24 ሰዓት ሌት ተቀን በሦስት ፈረቃ ሲሠራ 11 ሰዎች ሞተውበታል፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ጽ/ቤት የድሮው ረዥሙ ሕንፃ ለአባዲና ፖሊስ ኮሌጅ የተሰጠ ሕንፃ ነበር፡፡ ጽ/ቤቱ የት ይሁን ተብሎ ሲፈለግ የድሮው ዓለም በቃኝ (ወህኒ ቤት) የነበረበት አጠገብ ያለው ሕንፃ ተመረጠ፡፡ ሌሎች ዙሪያውን ያሉት ከዚያ በኋላ የተሠሩ ናቸው፡፡


 

በዚያን ጊዜ የነበሩት ግዮን፣ ኢትዮጵያ፣ ራስ፣ ጣይቱ፣ ሒልተንና ገነት ሆቴሎች ብቻ ነበሩ፡፡ መሪዎቹ ሲመጡ የት ይረፉ ሲባል፣ በግዮን ሆቴል 32 መሪዎች የሚይዝ ቅጥያ ሁለት ፎቅ የተሠራው ያኔ ነው፡፡ ስብሰባው የተካሄደው አሁን ብሔራዊ ቤተመንግስት (ያኔ ኢዮቤልዩ ቤተ-መንግሥት) ተብሎ በሚጠራው ነበር፡፡ አዲስ አበባ አሸብርቃለች፡፡ በተለይ ከፒያሳ ማዘጋጃ ቤት እስከ ለገሃር ባቡር ጣቢያ ያለው ቸርችል ጐዳና፣ ከመስቀል አደባባይ እስከ ስድስት ኪሎ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ (ያኔ ገነተ - ልዑል ቤተመንግሥት) ድረስ በኢትዮጵያና በተለያዩ አገራት ባንዲራና መብራት አጊጦ ነበር፡፡ ዝግጅቱ ከተጠናቀቀ በኋላ መሪዎቹ የሚመጡበት ቀን ተቆረጠና ግንቦት 1955 ዓ.ም እንዲሆን ተወሰነ፡፡ የዝግጅቱ ዋና ተዋናይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ነበሩ።

በወቅቱ ኃይለኛ ዝናብ ስለነበር ጃንሆይ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ እየተገኙ ሁሉንም መሪዎች የተቀበሉት በዣንጥላ ነው - ዝናብ እየዘነበባቸው፡፡ ቀይ ምንጣፍ ተነጥፎና ፖሊስ ባንድ ማርሽ እያሰማ፣ ለእያንዳንዱ መሪ 21 ጊዜ መድፍ እየተተኮሰ ነበር የተቀበሏቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ትዝ የሚለኝ፣ የኮትዲቫር (ያኔ አይቮሪኮስት) መሪ የነበሩት ሁፌት ቧኜ በፍፁም በአውሮፕላን መጓዝ አይወዱም፡፡ ስለዚህ በመርከብ እስከ ጅቡቲ መጥተው ከዚያ ደግሞ በልዩ ባቡር ግንቦት 16 ቀን አዲስ አበባ ሲገቡ ደማቅ አቀባበል ተደርጐላቸዋል፡፡ በተወካይ የተሳተፉ አገሮች ቢኖሩም ኢትዮጵያን ጨምሮ 32 አገራት በመሪዎቻቸው አማካኝነት በስብሰባው ላይ ተሳትፈዋል፡፡ መሪዎቹና የልዑካን ቡድኑ አባላት አዲስ አበባ መግባት የጀመሩት ከግንቦት 13 ቀን ጀምሮ ሲሆን ተጠቃለው የገቡት ግንቦት 15 ቀን ነበር፡፡ ግንቦት 16 ቀን ምሽት ጃንሆይ በታላቁ ቤተመንግሥት በአፄ ምኒልክ አዳራሽ ለመሪዎቹ ክብር፤ ለልዑካን ቡድን አባላት፣ ለዲፕሎማቶች፣ ለጋዜጠኞች፣ በሀገር ውስጥ ላሉ መሳፍንት፣ ጳጳሳት፣ ሚኒስትሮች፣ መኮንኖች፣ ለታዋቂ ነጋዴዎችና ግለሰቦች በአጠቃላይ ከሦስት ሺም አምስት መቶ በላይ ለሚሆኑ እንግዶች ታላቅ የራት ግብዣ አደረጉ፡፡

ተጋባዦቹ ወደ አዳራሹ ከመግባታቸው በፊት በቤተመንግሥቱ ፊት ለፊት ባለው ሜዳ ላይ የተለያዩ ቀለማት ያላቸው ሪችት ተተኩሷል። አዳራሹ በአገር ባህል ቁሳቁሶች፣ የኢትዮጵያን ጥንታዊ ሥልጣኔ በሚያሳዩና በታዋቂ አርቲስቶች በተሣሉ ሥዕሎችና በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓለማ አሸብርቋል፡፡ የክብር ዘበኛ፣ የጦር ሠራዊትና የፖሊስ ሠራዊት የሙዚቃ ቦንቦችም ልዩ ልዩ ጥዑመ ዜማዎችን በማቅረብ እንግዶቹን ሲያስደስቱ አምሽተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካዊቷ ማሪያ ማኬባ “የጥንቱ ትዝ አለኝ” የሚለውን የዶ/ር ጥላሁን ገሠሠን ዜማ ስታንቆረቁር ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ ወደ አዳራሹ የተገባው ሁለት ለሁለት እጅ ተያይዞ ነበር፡፡ በመጀመሪያ የገቡት የኢትዮጵያ ንጉሥ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና የግብፁ ፕሬዚዳንት ጋማል አብዱልናስር ነበሩ፡፡ ጃንሆይ አጭር እንደ መሆናቸው መጠን፣ እጅ ለእጅ ተያይዘው ሲገቡ ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ በጣም ረዥም ከሚባሉት ጋማል አብድልናስር ሌሎችም በፊደል ተራቸው መሠረት ሁሉም መሪዎች እንዲገቡ ተደረገ፡፡

እራት ከተበላና ከተጠጣ በኋላ ክቡር ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ ከፈረንሳዊት ሚስታቸው ጋር ወደ መድረክ በመውጣት ዳንስ አስጀምረዋል። በማግሥቱ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም 32ቱ መሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካን አንድነት ድርጅት ቻርተር በፊርማቸው አፀደቁ፡፡ ቻርተሩ ለም/ቤቱ ቀርቦ በሙሉ ድምፅ አፀደቅነው። ቻርተሩ ለፓርላማ የቀረበው፣ ዓለም አቀፍ ውሎችንና ስምምነቶችን ም/ቤቱ ማወቅ ስላለበትና በቻርተሩ አንቀጽ 23 መሠረት አባል አገሮች ለድርጅቱ በየዓመቱ የሚከፍሉትን መዋጮ በበጀት ተይዞ መፅጸቅ ስላለበት ነው፡፡ ክቡር ፊታውራሪ አበበ ሥዩም ግን ጥቂት ቅሬታ አላቸው፡፡

“ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እንግሊዝኛ ፈረንሳይኛ ተናጋሪ በመጋል የተከፋፈሉትን የአፍሪካ መንግሥታት አስተባብረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ቻርተር እንዲፈረም ያደረጉ ታላቅ መሪ ነበሩ፡፡ አሁን በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ ፊትለፊት የጋናው መሪ የክዋሜ ንኩሩማ ሐውልት ብቻ እንዲቆም በመደረጉ ቅሬታ አለኝ፡፡ ወደፊትም ቢሆን ለጃንሆይና ለመሥራች መሪዎች መታሰሲያ ሐውልት ይቆምላቸዋል የሚል እምነት አለኝ” ብለዋል፡፡ ሌላው ቅሬታቸው ደግሞ የአፍሪካ አንድነት ሲመሠረት የነበሩ ጥቂት የዓይን እማኞች ስላሉ እነሱ በአፍሪካ ኅብረት ምሥረታ 50ኛ ኢዮቤልዩ በዓል ላይ እንዲገኙ ያለመጋበዛቸው አሳዝኖአቸዋል፡፡