ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, July 30, 2026

ጴጥሮስ ያችን ሰዓት

 

“ጴጥሮስ ያችን ሰዓት” 
                                                    በሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድኅን


ታላቁ ባለቅኔና የተውኔት አዘጋጅ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ዘመን ተሻጋሪ የሆነችውን “ጴጥሮስ ያችን ሰዓት” የምትለዋን ግጥም የፃፈው፡ አንድ ቀን ምሽት ከማዘጋጃ ቤት ሲወጣ ባየው ትዕይንት ምክንያት ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡ ፀጋዬ ገ/መድህን ከማዘጋጃ ቤት እንደወጣ ቁልቁል ወደ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ሲያመራ አንድ ጀብራሬ (በሎሬቱ አነጋገር) ከአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ላይ ሸንቱን ሲሸና ተመለከተ፡፡ ፀጋዬም በደም ፍላት ወደ ጀብራሬው ተንደረደረ፡፡ ጀብራሬው ግን “አንተ ድንጋይ እሸናብሃለሁ፡፡ ድንጋይ ነህ …. ድንጋይ ነህ ….” እያለ በሐውልቱ ላይ ይሸናል፡፡ በዚህ ሰዓት ነበር ሎሬቱ “ጴጥሮስ ድንጋይ አይደለም” ብሎ ጀብራሬውን በደም ፍላት ዘሎ ያነቀው፡፡ ከዚያም አብረውት የነበሩት ሰዎች ገላገሉትና እየተብሰከሰከ አራት ኪሎን ተሻግሮ ቀበና ገባ፡፡
ማታውን አልተኛም፡ አነሆ “ጴጥሮስ ያችን ሰዓት” የምትለዋን ግጥምና ኑዛዜ ሲጭር አደረ፡፡
***************************************

አዬ! ምነው እመብርሃን? ኢትዮጵያን ጨከንሽባት?
ምነው ቀኝሽን ረሳሻት?
እስከመቼ ድረስ እንዲህ፣ መቀነትሽን ታጠብቂባት?
ልቦናሽን ታዞሪባት?
ፈተናዋን፣ ሰቀቀኗን፣ ጣሯን ይበቃል ሳትያት?
አላንቺ እኮ ማንም የላት….
አውሮጳ እንዲሁ ትናጋዋን፣ በፋሽስታዊ
ነቀርሳ
ታርሳ፣ ተምሳ፣ በስብሳ
ሂትለራዊ እባጭ ጫንቃዋን፣
እንደኮረብታ ተጭኗት
ቀና ብላ እውነት እንዳታይ፣ አንገቷን
ቁልቁል ጠምዝዟት
ነፍሷን ድጦ ያስበረከካት
ሥልጡን፣ ብኩን፣ መፃጉዕ ናት፤ ….
እና ፈርቼ እንዳልባክን፣ ሲርቀኝ
የኃይልሽ ውጋገን
አንቺ ካጠገቤ አትራቂ፣ በርታ በይኝ
እመ ብርሃን
ቃል ኪዳኔን እንዳልረሳት፣
እንዳልዘነጋት ኢትዮጵያን፡፡
አዎን፣ ብቻዬን ነኝ ፈራሁ
እሸሸግበት ጥግ አጣሁ
እምፀናበት ልብ አጣሁ
እማማ ኢትዮጵያን መንፈሴ፣ ተፈትቶ
እንዳይከዳት ሠጋሁ …
.
አዋጅ፣ የምሥራች ብዬ፣ የትብት
ምግቤን ገድፌ
ከእናቴ ማኅፀን አርፌ
ከአፈርዋ አጥንቴን ቀፍፌ
ደሜን ከደሟ አጠንፍፌ
ከወዟ ወዜን ቀፍፌ
በሕፃ እግሬ ድሄባት፣ በህልም አክናፌ
ከንፌ
እረኝነቴን በሰብሏ፣ በምድሯ ላብ
አሳልፌ
ከጫጩት እና ከጥጃ፣ ከግልገል ጋር
ተቃቅፌ፤
በጋው የእረኛ አደባባይ፣ ክረምት
እንደወንዙ ፍሳሽ
በገጠር የደመና ዳስ፣ በገደል ሸለቆ
አዳራሽ
ከቆቅ እና ከሚዳቋ፣ ከዥግራ ጠረን
ስተሸሽ
በወንዝ አፋፍ ሐረግ ዝላይ፣ መወርወር
መንጠልጠል ጢሎሽ
ከፍልፈል ጋር ሩጫ ስገጥም፣ ከቀበሮ
ድብብቆሽ
ከናዳ ጫፍ ሣር አጨዳ፣ ለግት ላሜ
ትንሽ ግጦሽ
ለጥጃዬ የሌት ግርዶሽ
ለጥማድ በሬዎች ራት፣ ለማታቸው
ትንሽ ድርቆሽ
ለግልገሌ ካውሬ ከለል
እማሳው ሥር ጎጆ መትከል
ለፀሐይ የሾላ ጠለል፣ ለዝናብ የገሳ
ጠለል
.
ውሎ የንብ ቀፎ ማሰስ፣ ያበባ
እምቡጥ ሲፈነዳ
የግጦሽ ሣር ሲለመልም፣ ሲሰማሩ
ሰደድ ሜዳ
አዝመራው ጣል ከንበል ሲል፣ ከብቱ
ለሆራ ሲነዳ
ፈረስ ግልቢያ ስሸመጥጥ፣ ከወፎች
ዜማ ስቀዳ
ልቤ በንፋስ ተንሳፎ፣ በዋሽንት ዋይታ
ሲከዳ …..
ያቺን ነው ኢትዮጵያ የምላት
እመ ብርሃን እረሳሻት?
ያቺን የልጅነት የምሥራች? የሕፃንነት
ብሥራት
የሣቅ የፍንደቃ ዘመን፣ የምኞት የተስፋ
ብፅአት
ያቺን የልጅነት እናት?
አዛኚቱ እንዴት ብለሽ፣ ጥርሶችሽን
ትነክሺባት?
.
ሥሜን በሥምሽ ሰይሜ፣
ባገልግሎትሽ ስዋትት
ከዜማ ቤት እቅኔ ቤት፣ ከድጓ ቤት
እመጻሕፍት
ካንቺ ተቆራኝታ ዕድሌ፣ ካንቺ ተቆራኝታ
ነፍሴ
ከቀፈፋ ደጀሰላም፣ ከቤተልሔም
ቅዳሴ
እኰ፣ ቀፎ ዳባ ለብሶ
ቅኔ ዘርፎ ግስ ገሦ
መቅደስ አጥኖ ማኅሌት ቆሞ
በልብስ ተክህኖ አጊጦ፣ በብር አክሊል
ተሸልሞ
እመ ብርሃን ያንች ጽላት፣ ነፍስ ላይ
በእሳት ታትሞ
የመናኒው ያባ ተድላ፣ ረድ ሆኜ፣
አብሮኝ ታድሞ
ሕይወቴ እምነትሽን ጸንሶ
ሥጋ ፈቃዴ ተድሶ
ለሕንፃሽ መዲና ቆሞ፣ ለክብርሽ
ድባብ ምሰሶ
.
ሥሜን በሥምሽ ሰይሜ፣ ሆነሺኝ
የእምነቴ ፋኖስ
ለዋዜማሽ ግሸን ማርያም፣ ለክብርሽ
ደብረ ሊባኖስ
ስሮጥ፣ በወንበሩ አኖርሺኝ፣
በአንበሳው በቅዱስ ማርቆስ
ታዲያ ዛሬ ኢትዮጵያ ስትወድቅ፣
ከምትሰጪኝ የፍርሃት ጦስ
ምነው በረኝነት እድሜ፣ ዓይኔን
በጓጎጣት የሎስ
የጋኔል ጥንብ አንሳ ከንፎ፣ ወርዶ
በጨለማ በርኖስ
.
ባክሽ እመ ብርሃን ይብቃሽ፣ ባክሽ
ምስለ ፍቁር ወልዳ
ጽናት ስጪኝ እንድካፈል፣ የእናቴን
የኢትዮጵያን ፍዳ፣
ከነከሳት መርዝ እንድቀምስ፣
ከነደደችበት እቶን
የሷን ሞት እኔ እንድሞታት፣ ገላዋ
ገላዬ እንዲሆን፡፡ …..
አዎን፣ ብቻዬን ነኝ ፈራሁ
እምፀናበት ልብ አጣሁ፡፡
.
ሕፃን ሆኘ የእርግብ ጫጩት
አንዳንዴ ርሃብ ሲያዳክማት
ችጋር ከጎጆዋ ገፍቶ እዛፍ ግርጌ ሲጥላት
እናቷ በርራ ደርሳላት
በአክናፏ ሙቀት ተታቅፋት
እፍ እያለች ግንባሯ ላይ ህይወት
ስትተነፍስባት
ወዲያው ነፍስ ትዘራለች
ሽር-ብር-ትር እያለች ።
ባክሽ አንችም አትራቂብኝ
እመብርሃን እናቴ ትንፋሽሽን እፍ በይብኝ
ፅናትሽን እፍ በይብኝ ፤
ወይም ይችን የሞት ጽዋ ፥
ጥላዋ ነፍሴን ካፈናት
እንዳልጠጣት አሳልፊያት
መራራ ክንፏን ገንጥለሽ ቀጠሮ ቃሏን
ግደፊያት
.
አለዚያም ፅናትሽን ስጭኝ ልጠጣው
ኪዳነ ውሉን
የኔ ፈቃድ እምነትሽ ነው ያንች ፍቃድ
ብቻ ይሁን ።
እንደጳውሎስ እንድፀና ፣በፍርሃት
ሳልታሰር
ለየዕለቱ ሞት እንዳልሰንፍ
የኪዳኔ ቃል እንዳይነጥፍ
ቃልሽ በሕሊናየ ዲብ ፣ ኃይልሽ
በሕዋሴ ይረፍ ።
ፍርሃት ቢያረብብኝም አንች ካለሽኝ
አልሰጋም
ኩርምት እችልበት ፣ እሸሸግበት
አይጠፋም
የግማደ መስቀሌን ጉጥ እታገስበት
አላጣም
አለዚያማ ብቻየን ነኝ ፣ ኢትዮጵያም
ያላንች የላት
አንች አፅኝኝ እንድፀናላት ።
አስርጭብኝ የእምነት ቀንጃ ፤
ለስጋቴ አጣማጅ አቻ
ለጭንቀቴ መቀነቻ ።…
.
አዎን ብቻየን ነኝ ፈራሁ
እሸሸግበት ጥግ አጣሁ
እምፀናበት ልብ አጣሁ …

ሎሬት ጸጋዬ ገብረ መድኅን ፲፱፻፷፩ ዓ.ም

---------



ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ፣ በፋሽስት ጣሊያን ሰማዕትነት የተቀበሉት በሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም ነበር፡፡
ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ፣ መስቀልና ወንጌል ብቻ ይዘው የወራሪውን የኢጣሊያ ፋሽስት ፣ ነውሩንና ግፉን ፊት ለፊት ታግለው፣ ለሃገራቸውና ለሃይማኖታቸው ሕይወታቸውን አሳልፈው የሰጡ ፣ በጳጳስ ናቸው፡፡
አባ ኃይለማርያም፣ ከመጀመሪያዎቹ አራት ኢትዮጵያውያን ጳጳሳት አንዱ ሆነው ሲመረጡ ስማቸው ብፅዕ አቡነ ጴጥሮስ ሆነ፡፡
በቅኔ ፣ በዜማ ፣ በመፃህፍት ትርጓሜ የተመረቁት አቡነ ጴጥሮስ፣ በ1921 ዓ.ም ጳጳስነት ከተሾሙ በኋላ፣ የኢጣሊያ ወረራ እስከገፋበት ድረስ ወሎንና ከሸዋ መንዝን እና ኤፍራታን፣ ግሺንና አንጾኪያን ሃገረ ስብከታቸው አድርገው ቆይተዋል፡፡
ከዚያ በፊትም በወላይታና በዝዋይ በመምህርነት አገልግለዋል፡፡
በማይጨው ዘመቻ ጊዜ ፣ ከንጉሰ ነገስቱ ጋር ሳይለዩ በማይጨው ተዋጊውን ሰራዊት እያበረታቱ አዋግተዋል፡፡
ኢትዮጵያዊያኑ ድል ሆነው ሲያፈገፈጉ በትውልድ አካባቢያቸው በሰላሌ ከተሰማሩት አርበኞች ከነዳጃዝማች አበራ ካሣ ጋር ተቀላቅለው ቆዩ፡፡
በ1928 ሐምሌ ወር አዲስ አበባን ከኢጣሊያኖች ለማስለቀቅ በተደረገው ከበባ በሰሜን በኩል ከዘመቱት አርበኞች ጋር አዲስ አበባ ደረሱ፡፡
አርበኞች አልቀናቸውም፡፡ ድል ሆነው ሲመለሱ ብፅዕ አቡነ ጴጥሮስ ግን ለመመለስ አልፈለጉም፡፡
ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ፀሎት አድርገው በቀጥታ ወደመሐል ከተማ ገብተው ተያዙ፡፡
የኢጣሊያ ሹማምንት ፣ አቡነ ጴጥሮስን አባበሉዋቸው፡፡
የኢጣሊያን ገዥነት ካመኑ በክብር እንደሚያዙ ነገሩዋቸው፡፡
ጳጳሱ ግን እምቢ አሉ፡፡ ገንዘብህ ለጥፋትህ ይሁን ብለው ረገሙ፡፡ እንኳንስ ሰው፣ ምድሩዋ እንዳትገዛ አወገዙ፡፡
በአቡነ ጴጥሮስ ድርጊት የተናደደው ጀኔራል ግራዚያኒ ፣ እንዲገደሉ ወሰነባቸው፡፡
ሐምሌ 22-1928 ዓ.ም ፣ ብፅዕ አቡነ ጴጥሮስ ፣ በሰንሰለት ታስረው ፣ ከአራዳ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በስተምዕራብ ባለው ቦታ ቆሙ፡፡
ከኋላቸው 8 ወታደሮች ጠመንጃቸውን ወድረው ተሰልፈዋል፡፡ በጊዜው በቦታው የነበረው ጋዜጠኛ እንደፃፈው ጥቁሩ ቀሚሳቸው ጭቃ ነክቶታል፡፡
ወንጌላቸውንና መስቀላቸውን ይዘዋል፡፡ ግድያቸውን እንዲመለከት በትዕዛዝ የተሰበሰበው ሕዝቡም ሆነ ምድሩዋ እንዳትገዛላት አወገዙ፡፡
ከረፋዱ 5፡30 ሆኖ ነበር፡- ይልና ጋዜጠኛው ስላሟሟታቸው እንዲህ ይላል፡፡ “አንድ መኮንን ውሳኔውን እየተንቀጠቀጠ ሲያነብ ፣ እሳቸው ግን ያለምንም ስጋት ያዳምጡት ነበር፡፡
“ወዲያው ዓይንዎ እንዲሸፈን ይፈልጋሉ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡ “እሱ የናንተ ተግባር ነው” አሉት፡፡
ትዕዛዝ ሲሰጣቸው ወታደሮቹ ተኮሱ፡፡
በስምንት ጥይትም መቷቸው፡፡ ግን አልሞቱም ነበርና ፣ ኮሎኔሉ በሶስት የሽጉጥ ጥይት፣ ራስ ቅላቸው ላይ ተኩሶ ገደላቸው፡፡
ሕዝቡም በሀዘን ተመታ” ይላል፡፡ ጋዜጠኛው ፣ ንብረታቸውን ወስደሁ ያለው ወታደር እንደነገረው ፣ ወንጌላቸውና መስቀላቸው በጥይት ተበሳስቷል፡፡
አቡነ ጴጥሮስ በ53 ፣ አመታቸው ፣አሁን ሐውልታቸው በቆመበት አካባቢ ተገድለው ባልታወቀ ቦታ ተቀብረዋል፡፡
ከነፃነት በኋላ በ1938 ለመታሰቢያ እንዲሆን ሐውልት ተቀርፆ ቆመላቸው፡፡
አሁን ያለው ሐውልት ለሁለተኛ ጊዜ ተሻሽሎ ተቀርፆ የቆመላቸው ነው፡፡ በፍቼም ለሶስተኛ ጊዜ ሐውልት ተቀርፆላቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በሙሉ ድምፅ በወሰነው መሰረት ፣ ሰማዕትነታቸውን አፅድቆ በስማቸው ቤተ ክርስቲያን ተሰርቶላቸዋል፡፡
ሰማዕተ ፅድቅ አቡነ ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን ፣ የታነፀው በትውልድ ቀያቸው በፍቼ ነው፡፡
የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሰማዕትነት የብዙ የጥበብ ሰዎችን ስሜት እየገዛ ገጣሚዎች ገጥመውላቸዋል፣ ቅኔ አዋቂዎች ቅኔ ዘርፈውላቸዋል ፣ ድራማ ተሰርቶላቸዋል፡፡



---------