ከደራሲያን ዓምባ

Monday, February 19, 2024

ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ተመሰረተ።


 የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (አ.አ.ድ)

The Organization of African Unity(OAU)

 ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም) የ32 ነፃ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች በተገኙበት የያኔው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ያሁኑ የአፍሪካ ህብረት (AU) ምስረታ በግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሤና በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከተማ ይፍሩ ያላሠለሠ ጥረት በአዲስ አበባ ከተማ እውን ሆነ ።

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ

በመሰብሰቢያው አዳራሽ የሚገኘው በአሰፋና ሠረቀ 
የማነብርሃን የተሣለ የ፴፪ቱ መሥራች መሪዎች ምስል።

ለብዙ ሺ ዓመታት ኢትዮጵያ ብቻዋን በአኅጉሩ ውስጥ ከአውሮፓውያኖች የቅኝ ግዛት ቀንበር ውጪ ቆይታ የሙሶሊኒ ፋሺስት ኢጣልያ፲፱፻፳፰ ዓ/ም ወርራት በነበረ ጊዜ አርበኞች ልጆቿ ውድ አገራቸውንና ነጻነታቸውን አሳልፈው ላለመስጠት አምስት ዓመታት ሙሉ ተዋጉ። ንጉሠ ነገሥታቸውም የእዚህን የግፍ ወረራ ለማጋፈጥ በዓለም መንግሥታት ማኅበር መድረክ ላይ ሲቀርቡ፣ ከአፍሪቃ አኅጉር ብቸኛዋ አባል ኢትዮጵያ ማንም አጋዥ አገር አልነበራትም።

ለአኅጉሩ ነጻነት በቅኝ ግዛት ሥርም የነበሩት ሕዝቦች፤ በነጻነትም ላይ የነበሩት አገራት የአውሮፓውያንን መዥገራዊ ልጥፍነት ለማላቀቅ ብዙ ከታገሉ በኋላ በሰሐራዊ አፍሪቃ የካቲት ፳፯ ቀን ፲፱፻፵፱ ዓ/ም ጋና ነጻ ሆነች። ከዚያ አስከትሎ የአፍሪቃ አንድነት ድርጅት እስከተመሠረተ ድረስ በ፲፱፻፶፩ ዓ/ም ጊኒ ነጻ ስትሆን በ ፲፱፻፶፪ ዓ/ም አሥራ አምስት አገራት፤ በ፲፱፻፶፫ ዓ/ም ሦሥት አገራት፤ በ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ደግሞ አራት አገራት ነጻነታቸውን ተቀዳጁ።

የአኅጉሩ መሪዎች በዓለም መድረክ ላይ ለበለጠ ተሰሚነት የትብብርን ግንባር ማሳየት እንደነበረባቸው በመገንዘብና ገና ነጻ ላልወጡትም ወንድም አገሮች ሉዐላዊነት መታገል ስለነበረባቸው ዓላማቸውን ግብ ለማድረስ በሁለት ቡድን ተከፍለው ፣ ባንድ በኩል እራሱን “የዘመናዊ ተራማጅ” ብሎ የሚጠራው፣ በጋናው ፕሬዚደንት ክዋሜ ንክሩማ የሚመራው የ “ካዛብላንካ ቡድን” በ ፲፱፻፶፬ ዓ/ም ተመሠረተ። ይሄ ቡድን የአኅጉሩን መንግሥታት በኅብረት ለማዋሃድ ዓላማ የያዘ ሲሆን አባላቱ ጋናአልጄሪያጊኒሞሮኮግብጽማሊ እና ሊቢያ ነበሩ።

ሁለተኛው ቡድን የ”ሞንሮቪያ ቡድን” ሲሆን የተመራው በ ሴኔጋል ፕሬዚደንት ሊዮፖልድ ሴዳር ሴንግሆር ነበር። አባላቱ ሴኔጋልናይጄሪያላይቤሪያ እና ኢትዮጵያ ሲሆኑ የነሱ የኅብረት አስተያየት ደግሞ የዱኛ ኅብረት ሳይሆን ፍላጎታቸው ረጋ ባለ ሁኔታ የዱኛኪን ኅብረት አንድነትን ያስከትላል የሚል ነበር።

መጨረሻ ላይ በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ከተማ ይፍሩ ታላቅ ጥረትና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ ሁለቱም ወገኖች አዲስ አበባ ላይ እንዲገናኙ በተደረገው ጥሪ መሠረት ተሰባስበው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን የስምምነት ውል ፴፪ ነጻ ሀገሮች ሲፈርሙ ድርጅቱ ተመሠረተ።

************************************

ግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ዘኢትዮጵያ የአፍሪካ አባት

Haile Selassie I of Ethiopia: Father of the O.A.U.’’ (የናይጄሪያው ሳንዴይ ኦብዘርቨር፤ ጁላይ 23፣ 1972)

ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖች ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል…፡፡’’ (የጊኒው ፕ/ት የነበሩት ሴኮቱሬ)

የትናንቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ህብረት የተመሰረተው ከ59 ዓመታት ግንቦት 16 ቀን 1955 ዓ.ም ነበር፡፡ ወቅቱ የአፍሪካ አገራት በሁለት የተከፈሉበት ነበር፡፡ በአንድ ወገን ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ሀገራቱ በፍጥነት ተዋሕደው አፍሪካ አንድ ልትሆን ይገባል የሚለው የካዛብላንካ ቡድን፤ እንዲሁም አንድ ከመሆን በፊት ሌሎች ትብብሮች ሊቀድሙ ይገባል የሚለው የሞኖሮቪያ ቡድኖች ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያም በወቅቱ የሞኖሮቪያን ቡድን ተቀላቅላ ነበር፡፡ በኋላ ኢትዮጵያ ባደረገችው ከፍተኛ ጥረት ሁለቱ ቡድኖች የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ለመመስረት ባስቻለው ስብሰባ ላይ ለመታደም አዲስ አበባ ከተሙ፡፡

ቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ በጉባኤው ላይ ለተገኙት የአፍሪካ መሪዎች ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው እንዲህ አሉ፡-

“በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል፡፡ ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው፡፡ ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው…፡፡’’

ዕለታዊው የአዲስ ዘመን የወርኻ ግንቦት 15 ቀን 1955 ዓ.ም. ዕትሙ በፊት ለፊት ገጽ ላይ፣ ‘‘ሠላሳ የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ጉባኤ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፈተ፤ ግርማዊ ጃንሆይም የጉባኤው የክብር ሊቀመንበር እንዲሆኑ ተመረጡ፡፡’’ በሚል ዐቢይ ርዕስ ስር እንዲህ ይላል፡-

“ቁጥራቸው ከ250 ሚሊየን በላይ በሆኑ አፍሪካውያን እጅግ በጋለ ስሜት ይጠበቅ የነበረውና መላው ዓለም ሁኔታውን በቅርብ ይከታተለው የነበረው የ30ዎቹ የአፍሪካ ነጻ መንግሥታት መሪዎች ጉባዔ ግንቦት 14 ቀን ትናንት ከእኩለ ቀን በኋላ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፍቷል፡፡ ጉባኤውን የከፈቱት ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጉባኤው ሥራውን ከመጀመሩ በፊት የአንድ ደቂቃ የኅሊና ጸሎት እንዲደረግ አሳስበው ጸሎት ተደረገ፡፡’’ 

ቀጥሎም የሊቀመንበር ምርጫ እንዲደረግ አሳስበው የጊኒው ፕሬዚደንት ሴኩቱሬ የመጀመሪያውን ምርጫ እንዲያደርጉ ተጠየቁ፡፡ እርሳቸውም የኢትዮጵው ንጉሥ ኃ/ሥላሴ የጉባኤው ሊቀመንበር እንዲኾኑ ጠቆሙ፤ የፕሬዚደንት ሴኩቱሬ ሐሳብ በጉባኤው አባሎች በሙሉ በመደገፉ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ የአፍሪካ አንድነት ደርጅት የመጀመሪያው ፕሬዚደንት ኾነው ተመረጡ፡፡ ከዚህ በኋላ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ለዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ሥራ ታላቅ መመሪያ የሚሰጥ የሚከተለውን ንግግር አደረጉ፡፡

“ዛሬ የገጠመን ዕድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ መቼም ያልተገኘ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ በፊታችን የተደቀኑት ችግሮች ያንኑ ያህል ከፍ ያሉና ከባድ ናቸው፡፡ ታሪክና ጊዜ የጣሉብን ከፍተኛ ኃላፊነት ሁላችንም ረጋ ብለን እንድናስብና እንድናመዛዝን ያስገድደናል፡፡ የተነሳንበትን ከፍተኛ ተግባር በመልካም አከናውነን ብንገኝ ስማችንና ተግባራችን በታሪክ መልካም ስም ይኖረዋል፡፡ ተግባራችንን ሳንፈጽም ብንቀር ግን ይታዘንብናል፡፡ ስለዚህ እምነታቸውን የጣሉብንን ሕዝቦቻችን በሚመጡት ጊዜያቶች ውስጥ ከእኛ የሚጠብቁትን ሁሉ ለመፈጸም እንዲያበቃን ሁሉን የሚችለውን ፈጣሪያችን ጥበብንና አስተዋይነትን እንዲሰጠን እናምነዋለን፣ እንለምንዋለንም፡፡’’

በወቅቱ በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ የተገኙት የናይጄሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር ታፌዋ ባሌዋ ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ኢትዮጵያና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽዖ ሲገልጹ ተከታዩን ብለው ነበር፤

“መላው የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎችና የመንግሥታት ባለ ሥልጣኖች በአዲስ አበባ ላይ ሊገኙ ለመቻላቸው በግርማዊነትዎ ጥረት ስለሆነ በተለይ ለግርማዊነትዎ እጅግ ከፍ ያለ ክብር የሚያሰጥ ነው፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ አንድነት እንዲገኝ የምናደርገው ጥረት ወደፊት የኢትዮጵያን መናገሻ ከተማ የአዲስ አበባ ስም ደጋግሞ የሚያወሳ ስለሆነ የአዲሲቱ አፍሪካ ታሪክ የግርማዊነትዎን ስም በተቀዳሚው ገጹ ላይ አሳምሮ የሚያኖረው ለመሆኑ ጥርጥር የለበትም፡፡’’

የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮቱሬም በአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያ ያደረገችውን ታላቅ አስተዋጽዖ እንዲህ ገልጸውታል፡-

“… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖች ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል…፡፡’’

ድርጅቱን በመመስረት ረገድ አፄ ኃይለ ሥላሴ የነበራቸውን ሚና አስመልከቶ፣ ኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካ ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ባቀረበው አጠር ያለ ጽሑፍ ‘‘Haile Selassie played a very important role in the establishment of the Organization of African Unity in 1963’’ ብሏል፡፡

‘‘ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ (ቀኃሥ) የአአድ መሥራች እና አባቱም የሆኑለት ከድርጅቱ ዋናዎቹ አንቀሳቃሾች አንዱ እንደነበሩ የጋናው ዘጋኔያን ታይምስ በጁላይ 24፣ 1972 ዕትሙ የፊት ገጽ ላይ ጽፎአል፡፡

የናይጄሪያው ሳንዴይ ኦብዘርቨር ቀኃሥ 80ኛ ዓመታቸውን ባከበሩበት ሐምሌ 16 ቀን 1964 ዓ.ም. (ጁላይ 23፣ 1972) ባወጣው ዕትሙ ‹‹የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አባት ኢትዮጵያዊው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ›› (Haile Selassie I of Ethiopia: Father of the O.A.U.) በሚል ርዕስ ስለግርማዊነታቸው ሰፊ ሐተታ አውጥቶ ነበር፡፡

እንደ ሰንዴይ ኦብዘርቨር አገላለጽ፣ ቀኃሥ ስለ አፍሪካ ያላቸው ውጥን እጅግ በጣም የተዋጣና የተቃና መሆኑን ጠቅሶ፣ አዲስ አበባ ‹‹የፓን አፍሪካን መዲና›› (የአፍሪካ አንድነት ከተማ) ለመባል የበቃችበትን ምክንያት አስታውሶ ነበር፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ኢትዮጵያ ስለአፍሪካ ሕዝብ የፖለቲካ ደኅንነት ላላት ተቆርቋሪነት ጉልህ ምልክት ነው፡፡ ድርጅቱ የተቋቋመውም በድንገት ከተፈጠረ ስሜት አልነበረም፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ በእርጋታና አንዳንድ ጊዜም በግላቸው የአፍሪካ አገሮች ገና ነፃነታቸውን ሳይጎናጸፉ የወደፊት መሪዎች ለሚሆኑት ሰዎች የትምህርትን ዕድል በመስጠት ረድተዋል፡፡ ግርማዊነታቸው በአፍሪካ አህጉር ያላቸው ተሰሚነት አገራቸው ከድንበሮቿ ውጭ ካላት ተሰሚነት የተገኘ ሳይሆን ንጉሠ ነገሥቱ ካተረፉት የመከበር ዕድል ነው፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅትም የአፍሪካ ኃይሎች ራሳቸውን ለመከላከል ይተባበሩ ዘንድ ግርማዊ ጃንሆይ ባላቸው እምነት መሠረት ፈቃዳቸውን ከግቡ ማድረሳቸው የሚያስደንቅ ነው፡፡ በዚህም መሠረት፣ በየትኛም የአህጉሩ ክፍል አምባጓሮ ቢነሳ ተገቢው ስምምነት እንዲፈጸም ግርማዊነታቸው ዓይነተኛ መድኅን ሆነዋል፡፡ በዚህም መሠረት የናይጄሪያ ችግር በተፈጠረበት ጊዜ የአስታራቂነት ዕርምጃ የወሰዱ ሲሆን ይህም ፍጻሜ እንዳገኘ በችግሩ ምክንያት አለመግባባት የተፈጠረባቸውን አፍሪካውያን መሪዎችን ፈጥነው ለማስማማት ችለዋል፡፡ ጃንሆይ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ድርጅት ጋር በመተባበር የወጠኑት 16 ዓመታት የፈጀውን የሱዳንን ችግር በማስወገድ ታሪካዊ ስምምነት እንዲፈጸም አስችሏል፡፡

ግርማዊነታቸው ሴኔጋልና ጊኒ አለመግባባታቸውን ለማስወገድ በተስማሙበት ይኸውም በላይቤሪያ ዋና ከተማ በሞንሮቪያ ውስጥ በተደረገው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ስብሰባ ሊቀ መንበር ሆነው መርተዋል፡፡ በዚህ መሠረት ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ቀደም ሲል ጀምሮ የታሪክ ሥፍራቸውን መያዛቸው ጉልህ ነው፡፡

በውጩም ዓለም ቢሆን አፍሪካ ግንባራቸው ሳይታጠፍ ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካና ከእስያ መሪዎች ጋር ለመቋቋም የሚችሉ ከፍተኛ መሪዎች ያላት መሆኑን ግርማዊ ጃንሆይ በሚገባ አስመስክረዋል፡፡

ኢትዮጵያ በዓለም ጋዜጦች በሚል ርዕስ በእንግሊዝኛ፣ ፈረንሣይኛና ጣሊያንኛ በግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ልዩ ካቢኔ ፕሬስ ክፍል ከ1957 እስከ 1966 ዓ.ም. ይታተም የነበረው መጽሔት የቀኃሥን ተግባሮች መዘከሩ ይታወቃል፡፡ አንዱ የጠቀሰው ለንደን ታይምስ (The Times London) በጁላይ 22፣ 1972 (ሐምሌ 15 ቀን 1965 ዓ.ም.) ዕትሙ፣ ‹‹የንጉሠ ነገሥቱ ጽኑ ሥልጣን በአፍሪካ መሪዎች ዘንድ ታፋሪነትን አትርፎላቸዋል›› (Emperor’s firm authority earns respect among the Leaders of Africa) በሚል ርዕስ ሐተታውን አስፍሮ ነበር፡፡

በመጭረሻም፤ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሰረት ዋነኛ አላማው በቅኝ አገዛዝ ስር የነበሩ አገሮችን ነጻ ማውጣት ነበር፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረት 32 ነጻ ሀገራት ብቻ የነበሩት፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በወቅቱ በቅኝ አገዛዝ ለሚማቅቁ አገሮች ተገቢውን ወታደራዊ ድጋፍና ስልጠና ሰጥቷል፡፡ የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረንስ /ANC/ አፓርታይድን እንዲዋጋና ZANU እና ZAPU የተባሉ የፖለተካ ድርጅቶች ዚምባብዌን ነጻ እንዲያወጡ ድርጅቱ መሳሪያና ወታደራዊ ስልጠና አበርክቷል፡፡

አፓርታይድን ለማውገዝ የደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ በአህጉሪቱ እንዳይበር ማዕቀብ መጣሉና የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን በማሳመን የተመድ አካል የሆነው የዓለም የጤና ድርጅት ከደቡብ አፍሪካ እንዲወጣ ማድረጉ ታሪክ ከመዘገባቸው የድርጅቱ ስኬቶች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ 

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት በተመሰረተ በ39 ዓመቱ በ1994 ዓ.ም. ስሙን ለውጦ፣ ዛሬ 55ቱም የአፍሪካ አገራት አባል በሆኑበት የአፍሪካ ኅብረት ተተክቷል፡፡

https://ethioreference.com/archives/31356

***************************************

አፄ ኃይለ ሥላሴ፣ ኢትዮጵያና የአፍሪካ አንድነት/ኅብረት – በፍቅር ለይኩን
 
en-haile-selassie‹‹ኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካ›› ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ባቀረበው አጠር ያለ ጽሑፍ እንዲህ ብሏል፡- ‹‹Haile Selassie played a very important role in the establishment of the Organization of African Unity in 1963.›› ዕለታዊው የአዲስ ዘመን የወርኻ ግንቦት 15 ቀን 1955 ዓ.ም ዕትሙ በፊት ለፊት ገጽ ላይ፣ ‹‹ሠላሳ የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ጉባኤ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፈተ፡፡ ግርማዊ ጃንሆይም የጉባኤው የክብር ሊቀመንበር እንዲሆኑ ተመረጡ፡፡›› በሚል ዐቢይ ርዕስ ዜናና ሰፊ ሐተታን ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡
የሰኞ ማለዳው የግንቦት 19 ቀን 1955 ዓ.ም የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ደግሞ በርእሰ አንቀጹ፣ ‹‹የካዛብላንካና የሞኖሮቪያ የሌሎችንም ብሎኮችና ቻርተሮች ሠርዞ የአፍሪካ አንድነትን የሚመሠርተው ‹የአፍሪካና የማላጋሲ አገሮች ድርጅት ቻርተር› ግንቦት 17 ቀን ለግንቦት 18 ቀን አጥቢያ 1955 ዓ.ም. ከሌሊቱ 7 ሰዓት ከ45 ደቂቃ ላይ በአፍሪካ አዳራሽ ውስጥ ተፈርሟል፡፡ በአራቱ ቀን ጉባኤ ፍጻሜ አዲስ የአፍሪካ ታሪክ፣ አዲስ የዓለም ታሪክ ተጽፏል፣ ተመዝግቧል፡፡›› ሲል የምስራቹን ዜና አስነብቧል፡፡ የትላንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬው የአፍሪካ ኅብረት የ50ኛ ዓመቱን የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓሉን በተለያዩ አገር አቀፍና አኅጉር አቀፍ ዝግጅቶች ለማክበር ዝግጅቱን ከጀመረ ወራት ተቆጥረዋል፡፡ በተለይም ደግሞ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት መመሥረት ግንባር ቀደም ሚና ባላትና ታላቅ አስተዋጽኦ ባደረገችው፣ የኅብረቱም ዋና መቀመጫ በሆነችው በአገራችን ኢትዮጵያ የበዓሉን ዝግጅት የደመቀና ልዩ ለማድረግ ሽር ጉድ እየተባለ ነው፡፡
ይህን በዓልም ባማረና በደመቀ ሁኔታ ለማክበር ራሱን የቻለ የበዓል ዝግጅት ሴክረታሪያት ቢሮ ተቋቁሞ፣ የአፍሪካ ኅብረት የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት በዓሉን ዓመቱን ሙሉ ለማክበር፣ የተለያዩ ዝግጅቶችን ቀርጾ በእንቅስቃሴ ላይ እንደሆነ አይተናል፣ ሰምተናል፣ አውቀናልም፡፡
ከወራት በፊትም በመዲናችን በአዲስ አበባ ዋና ዋና ቦታዎችና አደባባዮች ላይ ‹‹I am African. I am the African Union›› የሚሉ የአፍሪካ ሕዝቦችን ማንነት፣ ታሪክ፣ ቅርስና ባህል የሚያንጸባርቁ፣ የአፍሪካዊነትን ስሜት፣ ኩራትና ወኔ የሚቀሰቅሱ ፖስተሮችን አይተናል፡፡ ከዑራኤል ወደ እስጢፋኖስ በሚወስደውም መንገድ ላይም የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ያቋቋሙ የፓን አፍሪካ አቀንቃኝ የሆኑ አባቶች ምስልም በትልቁ ተሰቅሎ አይቻለሁ፡፡ ይህ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መልካም ሊባል የሚችል ነው፡፡ ለወደፊቱም በዓሉ በተለያዩ መጠን ሰፊ በሆኑ ዝግጅቶች እንደሚከበርና በበዓሉም ላይም የአፍሪካ አገራት ርዕሳነ ብሔራት፣ ተወካዮችና ባለ ሥልጣናት፣ ዓለም አቀፍ መሪዎች፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለ ሙያዎች፣ ፖለቲከኞች፣ ደራሲያን፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች … ወዘተ በሚሳተፉበት በደመቀ ሁኔታ በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር የበዓሉ ዝግጅት ኮሚቴ በተደጋጋሚ አሳውቋል፡፡
በዚህ ጽሑፌ ከሰሞኑ መላው አፍሪካና አፍሪካውያን፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና እንዲሁም በአጠቃላይ የአፍሪካ ወዳጆች፣ የመንግሥታቱ ድርጅት፣ የተለያዩ አኅጉራዊና ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና ታዋቂ ሰዎች አብርውን በደስታ ሊያከብሩት እየተዘጋጁ ስላለው የአፍሪካ ኅብረት የ50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ስናወራ ልብ ልንለው የሚገባ አንድ ትልቅ ቁም ነገር አለ፡፡
ይኸውም በዚህ በዓል ላይ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ለአፍሪካ ኅብረት እውን መሆን ትልቅ መሥዋዕትነት የከፈሉትንና ስማቸውን በወርቅ ቀለም በታሪክ ማሕደር የጻፉትን አፍሪካውያን አባቶቻችንን ማስታወስ የሚገባን ይመስለኛል፡፡ ይህ ጽሑፍም ለትላንትናው አፍሪካ አንድነት ድርጅት ለዛሬው የአፍሪካ ኅብረት እውን መሆን የታገሉትን የፓን አፍሪካ አቀንቃኝ አባቶቻችንን ታሪክ በተከታታይ በአጭሩ ለማቅረብ ይሞክራል፡፡
ይህ ጹሑፍ የአፍሪካ ኅብረትን የ50ኛ ዓመት ወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ምክንያት በማድረግ በቅድሚያ የአፍሪካ አባት፣ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማትና የጥቁር ሕዝብ የነጻነት ዓርማ፣ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅት መቋቋምና በሂደትም ለኅብረቱ እውን መሆን ትልቁን የመሠረት ድንጋይ ስላስቀመጡት ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ታሪክ፣ ፖለቲካዊ ሰብእና፣ በአፍሪካውያንም ሆነ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ስለነበራቸው መወደድ፣ ተቀባይነትና ታላቅ ክብር በአጭሩ በማዘከር የታሪክ ማስታወሻውን አሐዱ ብሎ ይጀምራል፡፡ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ መንግሥት ታሪክ በእሳቸው ዘመን ከነበሩ ከተራው የኅብረተስብ ክፍል ጀምሮ እስከ ታላላቅ ባለ ሥልጣናትና የሃይማኖት አባቶች፣ ዲፕሎማቶች፣ የውጭ አገር መሪዎች፣ ታላላቅ ሰዎችና ፖለቲከኞች በቃል ከተናገሩት፣ በጽሑፍ ካስቀመጡት፣ በግል ማስታወሻዎቻቸው ከተዉልን፣ እንዲሁም የአጼ ኃ/ሥላሴንና የኢትዮጵያን ታሪክ በተመለከተ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ጸሐፍት በመጻሕፍቶቻቸው ካሰፈሯቸው መረጃዎች በመነሣት ነው ይህን አጠር ያለ የታሪክ ማስታወሻ ጽሑፍ ያዘጋጀሁት፡፡
በአጭር ቃል የዚህ ተከታታይ ታሪክ አቅራቢ የአፄ ኃ/ሥላሴ ዘመን ጣእሙንም ሽታውንም አልደረስበትም፡፡ በእሳርቸው ዘመንም አልታሰበም፣ አልተፈጠረምም፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ታሪክ ተማሪነቴና ባለሙያነቴ የኢትዮጵያን ታሪክ በሰፊውና በሚገባ ማጥናት ከጀመርኩበት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አንስቶ አሁን እስካለሁበት የትምህርት ሕይወቴና የሥራ ልምዴ እንዳስተዋልኩት፣ በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ አፄ ኃ/ሥላሴ በአብዛኛው በአዎንታዊ መልኩ የሚገለጹበት ታሪክ፣ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ ዘንድም አንቱታን ያተረፉበትን ዝናና ክብር እንዲጎናጸፉ ያደረጋቸው በሳል የሆነ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ሰብእና እንዳላቸው ነው የተረዳሁትና ያስተዋልኩት፡፡ በስድስት ዓመታት ውስጥ ለሁለት ጊዜ ‹‹Man of the Year›› የዓመቱ ምርጥ ሰው በማለት የለንዶኑ ታይምስ መጽሔት የመረጣቸው አፄ ኃይለ ሥላሴ ከፍ ያለ ሰብእና የነበራቸውና በዓለም አቀፍ ደረጃ እንደ ታላቅ መሪና አባት የሚታዩ የተዋጣላቸው ዲፕሎማቲክ፣ እንዲሁም በዓለማችን ከሚገኙ ታላላቅ መሪዎችና ፖለቲከኞች ዘንድ ትልቅ ከበሬታ የነበራቸው ኢትዮጵያዊ ንጉሥ እንደነበሩ የታሪክ ድርሳናትና ብዙዎች ሰዎች ይመሰክራሉ፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ኃ/ሥላሴ ከሀያ በየሚበልጡ የክብር ዶክትሬት ድግሪዎችን ከተለያዩ አገራት መሪዎችና ዩኒቨርስቲዎች ተቀብለዋል፡፡ ምናልባትም አገራችን ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከምትታወቀበት ድርቅ፣ ራብና የእርስ በርስ ጦርነት ባሻገር በአንጻራዊ መልኩም ቢሆን በአዎንታዊነት ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የአገራችንን ስም በመልካም እንዲነሣ ምክንያት ከሆኑ የኢትዮጵያ መሪዎች መካከል አፄ ኃ/ሥላሴ አንዱ፣ ብቸኛውና ዋንኛው ናቸው ብል፣ ብዙም ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡ ይህን ኢትዮጵያን አዎንታዊ በሆነ መልኩ እንድትነሳ በማድረግ ረገድና ዓለም አቀፉ የፖለቲካ መድረክ የነበራቸውን ተቀባይነት፣ ክብርና ዝና እንዲሁም ለባለ ቃል ኪዳን አገሮችና በኋላም ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መመሥረት፣ ለ50ኛ ዓመቱ የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓሉ ዋዜማ ላይ ለሚገኘው ለአፍሪካ ኅብረት እውን መሆን፣ ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ የነበራቸውን ትልቅ ሚና የሚያስታውስ አንድ ያጋጠመኘኝን ታሪክ እዚህ ጋር ማንሳቱ ተገቢ ይመስለኛል፡፡
እውቁ የነጻነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላና በርካታ አፍሪካውያን የነጻነት ታጋዮች ለ27 ዓመታት በተጋዙበትና በመንግሥታቱ ድርጅት፣ ዩኔስኮ ዓለም አቀፍ ቅርስ አድርጎ በመዘገበው በሮቢን ደሴት ሙዚየምና በደቡብ አፍሪካ የአርትና ካልቸር ደፓርትመንት የሚሰጠውን የስኮላር ሺፕ አሸንፌ፣ በተማርኩበት በኬፕታውኑ የዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርስቲ የድኅረ ምረቃ ትምህርት ቆይታዬ ከኢትዮጵያዊነት የነጻነት መንፈስና ከአፄ ኃ/ሥላሴ ጋር በተገናኘ አንድ በእጅጉ ያስደነቀኝ ነገር ገጥሞኝ ነበር፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ በዋነኝነት በዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርስቲና በኬፕ ታውን ዩኒቨርስቲ በሚገኙ ደቡብ አፍሪካውያንና የሌሎች አፍሪካ አገሮች የተቋቋመ የግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ (የራስ ተፈሪያን) የተማሪዎች እንቅስቃሴ ኅብረት በሚል መጠሪያ የሚታወቅ በዩኒቨርስቲው ግቢ ቢሮ ተሰጥቶት የሚንቀሰቀስ ማኅበር ነበር፡፡ በነገራችን ላይ በደቡብ አፍሪካ አንዳንድ ዩኒቨርስቲዎች እንደታዘብኩት በፖለቲካና በሃይማኖት፣ እንዲሁም ኪነ ጥበብን፣ ባህልንና ታሪክን መሠረት አድርጎ የተቋቋሙና በነጻነት በዩኒቨርስቲው ግቢ ቢሮ ተሰጥቷቸው የሚንቀሳቀሱ በተማሪዎች የተቋቋሙ የተለያዩ ድርጅቶችና ፓርቲዎች ይገኛሉ፡፡
ታዲያ እኔ በተማርኩበት በዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርስቲ በሚገኘው የግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ የተማሪዎች ኅብረት እንቅስቃሴ ቢሮ ውስጥ የእንቅስቃሴው ደጋፊዎችና አባላት የሆኑት ተማሪዎች ለኢትዮጵውያን የስኮላር ሺፕ ተማሪዎች ባቀረቡላቸው ጥያቄ መሠረት የአማርኛ ቋንቋን የሚያስተምሯቸው ሁለት ሴቶችና አንድ ወንድ ተማሪዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ከእኔ ቀደምው ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ያሉ ተማሪዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ለምርምር ሥራ፣ ለልምድ ልውውጥና ለተጨማሪ ጥናት ወደ አውሮፓ በሄዱበት አጋጣሚ ለእነዚህ አፍሪካውያን ወንድሞቻችን ከአንተ በተሻለ ስለ ኢትዮጵያችን የሺህ ዘመናት ታሪክ፣ ሥልጣኔ፣ የነጻነት ተጋድሎና ቋንቋችንን ሊያስተምራቸው የሚችል የለም በማለት ከራስ ተፈራውያኑ የዩኒቨርስቲው ማኅበረሰብ ጋር አስተዋወቁኝ፡፡
ከዚሁ ማኅበር አባላት ተማሪዎቹ ጋር በተዋወኩበት በአጭር ጊዜ ውስጥ በሚገባ ለመግባባት ቻልን፡፡ ለጥቂት ወራት እነዚህ ወጣት ተማሪዎች የአማርኛ ቋንቋ ማስተማር ቆይታዬ እንዲሁም በተለያዩ አጋጣሚዎች ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ፣ ባህል፣ ቅርስ፣ ሃይማኖት … ወዘተ ባደርግናቸው ውይይቶች በርካታ ቁም ነገሮችን አንስተን እንነጋገር ነበር፡፡ በአብዛኛው የውይይታችን ማእክል ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ለፓን አፍሪካ እንቅስቃሴ፣ ለአፍሪካ የፀረ-ባርነትና የፀረ-ቅኝ ግዛት የነፃነት ትግል፣ በደቡብ አፍሪካ ፀረ-አፓርታይድ ትግል ውስጥ ስለነበራቸው ጉልህ ሚናን በተመለከተ ነበር፡፡ በዚህ ውይይታችን ውስጥ ደግሞ ደጋግመው ከሚነሱት መካከል አፄ ኃ/ሥላሴ አንዱና ዋናው መሆናቸውን ልብ ይሏል፡፡
እኔ እንደ ኢትዮጵያዊነቴና የታሪክ ባለሙያነቴ ስለ አገሬ ኢትዮጵያ ታሪክና ስለ መሪዎቻችን ካለኝ ግንዛቤና እውቀት ይልቅ እነዚህ አፍሪካውያን ተማሪዎች ስለ አኅጉራችን አፍሪካና ስለ አገሬ ታሪክ ያካፈሉኝ እውቀታቸውና ያላቸው መረዳት በጊዜው በእጅጉ ግርምትን አጭሮብኝ ነበር፡፡ እነዚህ ተማሪዎች ኢትዮጵያና ሕዝቦቿ በጥቁር ሕዝቦች ታሪክ፣ ቅርስ፣ ባህልና የነጻነት ተጋድሎ ውስጥ ያላቸውን ማእከላዊ ስፍራን በተመለከተ የሚያስረዱ በቢሮአቸው ያሰባሰቧቸው መጻሕፍቶችና መዛግብቶቻቸው፣ የምስልና የድምፅ መረጃ ክምችቶቻቸው በእጅጉ ነበር ያሰደነቀኝ፡፡
ከዚህም በላይ ደግሞ ሌላው በእጅጉ ያስደመመኝ ነገር ቢኖር በዩኒቨርስቲው ግቢ ውስጥ በሚገኘው የራስ ተፈሪያኑ ተከታዮች ማኅበር ቢሮ ግድግዳ አንድ ጎን በሁለት የታሪክ መስመር ተከፍሎ በተለያዩ ሰዎች ምስሎችና መረጃዎች አሸብርቆ ያየሁት Wall of Fame እና Wall of Shame የሚለው የቢሮው ግድግዳ ክፍል ነው፡፡ በዚሁ Wall of Fame እና Wall of Shame ወይም ‹‹የታሪክ ዕንቁዎችና የታሪክ አተላዎች›› ተብሎ በተከፈለው ግድግዳ ላይ ‹‹በዎል ኦፍ ፌም›› ምስላቸውና ስማቸው በግንባር ቀደምትነት ከተለጠፉት መካከል የአፄ ኃ/ሥላሴና የባለቤታቸው የእቴጌ መነን በመጀመሪያው ረድፍ ይገኛል፡፡ በተጨማሪም በዓድዋው ዘመቻ የኢጣሊያንን ወራሪ ኃይል አሸንፈው አዲስ የጥቁር ሕዝቦችን አዲስ ታሪክ የጻፉት የአፄ ምኒልክ፣ እንዲሁም ከእንግሊዞች ጋር ተዋግተው ራሳቸውን የሠዉት የአፄ ቴዎድሮስ ምስሎችና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
በዚህ ‹‹የታሪክ ዕንቁዎች›› የክብር ግድግዳ ላይ አፄ ኃ/ሥላሴ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በገፍ በወረረች ጊዜ በሊግ ኦፍ ኔሽን፣ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ያቀረቡት አቤቱታና ንግግራቸው በልዩ ንድፍና በአገራችን ሰንደቀ ዐላማ አሸብርቆ በግድግዳው ላይ ይታያል፡፡ ‹‹የዎል ኦፍ ፌምን›› ግድግዳ ካስዋቡ የታሪክ ሰዎች ፎቶግራፎች በአብዛኛው ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ የሚሸቱት በዓይነትም በብዛትም እጅግ ልቀው ይገኛሉ፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በዚሁ ‹‹በዎል ኦፈ ፌም›› የታሪክ መስመር ውስጥ ለጥቁር ሕዝቦች ነጻነት ትልቅ ተጋድሎ ያደረጉ እንደ እነ ማርከስ ጋርቬይ፣ አፍሪካ አሜሪካዊው ማርቲን ሉተር፣ የፓን አፍሪካ አባቶች የጋናው ንኩርማ፣ የኬንያው ጆሞ ኬንያታ፣ ሴኔጋላዊው ሴዳር ሴንጎርና ሌሎችም የአፍሪካ የነጻነት ታጋዮችና መሪዎች በኢትዮጵያ ሰንደቀ ዓላማና በኃ/ሥላሴ ግንባር ቀደም አዝማችነት የክብር ግርግዳውን ተጋርተውታል፡፡
ሌላው አስገራሚው ነገር የንጉሡን የአፄ ኃ/ሥላሴን ልደትና የነገሡበትን ዕለት የራስ ተፈራውያኑ ማኅበር ተከታይ ተማሪዎች እንግዶችን ከውጭ ሁሉ ሣይቀር በመጋበዝ ጭምር የዩኒቨርስቲውን የተማሪዎች ማእክልንና የግቢውን ሜዳ በኢትዮጵያ ሰንደቀ ዓላማ፣ በኃ/ሥላሴና በባለቤታቸው እቴጌ መነን ፎቶ ግራፍ አሸብርቀውና በአፍሪካ የሬጌ ሙዚቃ ስልት አጅበው በታላቅ በሆነ የኢትዮጵያዊነት የነጻነት መንፈስ ቀናቱን ያከበሩ እንደነበረ ትዝ ይለኛል፡፡
የማስታውሰው በዩኒቨርስቲው የምንገኘው በጣት የምንቆጠር ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች በአፍሪካም ሆነ በተቀረው ዓለም በድርቅ፣ በራብና በእርስ በርስ ጦርነት ስማችን እየተነሳ የምንሳቀቅበትን ምስላችንን፣ እነዚህ የዩኒቨርስቲው የራስ ተፈራውያን ተከታይ ተማሪዎች በተለያዩ ጊዜያት በግቢው ውስጥ የአገራችንን አረንዴ፣ ብጫና ቀይ ሰንደቀ ዓላማ ሰቅለው ሲያከብሩ ስናይ በአገር ፍቅር ናፍቆትና ትዝታ፣ በኢትዮጵያዊነት ብሔራዊ ስሜትና ኩራት ውስጣችን የተናጠበትን አጋጣሚ አልረሳውም፡፡ በእርግጥ የእነዚህ ተማሪዎች እንቅስቃሴና አካሄድ በአብዛኛው ሃይማኖታዊ መልክ ያለውና ኃ/ሥላሴን መለኮታዊ ሰብእና እንዳላቸው አድርጎ የሚያቀርብ ቢሆንም የተማሪዎቹ እንቅስቃሴ ከሃይማኖታዊ መልኩ ይልቅ አፍሪካዊነቱና ፖለቲካዊ አንድምታው በእጅጉ የጎላ ነው፡፡ እነዚህ ደቡብ አፍሪካውያንም ሆነ የሌሎች የአፍሪካ አገሮች ተማሪዎች ልብም ሆነ በአብዛኛው ጥቁር ሕዝቦች ልብ ውስጥ ኢትዮጵያ የጥቁር ህዝቦች ታሪክ፣ ባህል፣ ቅርስ፣ ሃይማኖት፣ ነጻነት ትልቅ ተምሳሌትና ማእክል ተደርጋ የምትወሰድ አገር ናት፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ ባላት የሺህ ዘመናት የረጅም ዘመን ሥልጣኔ፣ ታሪክና ቅርስ የተነሣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ የሆነ የታሪክ እሴት ያላት አገር ለመሆን በቅታለች፡፡ በተለይም ደግሞ መላው አፍሪካንና የጥቁር ዘርን ሁሉ ከጫፍ እስከ ጫፍ ያነቃነቀው ኢትጵያውያን በዓድዋ ጦርነት ያስመዘገቡት አንጸባራቂ ድል ኢትዮጵያን ከጥቁር ሕዝቦች ታሪክ ማማ ላይ እንድትወጣ አስችሏታል፡፡
ለአፍሪካ፣ ለአፍሪካ አሜሪካውያንና በጃማይካና በካረቢያ ላሉ የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ትግል መለኮስ ይኸው የአድዋው ድል ትልቅ አስተዋጽኦ ነበረው፡፡ የእነ ማርከስ ጋርቬይና የትግል አጋሮቹ የጥቁር ሕዝቦች የነፃነትና የመብት ጥያቄ ውሉ የሚመዘዘው ከኢትዮጵያዊነት የነጻነት መንፈስ፣ የአባቶቻችን የአይበገሬነትና ቆራጥ የተጋድሎ ታሪክ ውስጥ ነው፡፡ የአፍሪካውያኑ የፓን አፍሪካ አቀንቃኞችና የፀረ ቅኝ ግዛት ታጋዮች የእነ ንኩርማ፣ የእነ ጆሞ ኬንያታ የአፍሪካዊነት ስሜትና ቆራጥ መንፈስ መፍለቂያ ምንጩም ይኸው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ከተሸከሙት ክቡር የነጻነት ተጋድሎ አኩሪ ታሪክና ቅርስ የሚመዘዝ ነው፡፡
ከአፄ ምኒልክ የዓድዋው ድል በኋላ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከኃያላኑ አገሮች እኩል የተሠለፈችው ብቸኛው የጥቁር ሕዝብ አገር ኢትዮጵያ ይህ ገናና የነጻነት ተጋድሎ ታሪኳ ከአፍሪካ እስከ አሜሪካ፣ ከአውሮፓ እስከ ኤዥያ፣ ከመካከለኛው ምስራቅ እስከ ቻይና፣ ሩሲያ፣ ጃማይካና ካረቢያን ምድር ድረስ ዘልቆ ተሰምቶ ነበር፡፡ ይህ የኢትጵያዊነት የነጻነት መንፈስ ውሉ ሳይቋረጥ በአፍሪካውያንና በጥቁር ሕዝቦች ደም ውስጥ በሚገባ ተዋህዶ፣ በተባበረ ክንድ የጸናችና አንድ የሆነች አፍሪካ በዓለም መድረክ ከፍ ብላ እንድትታይ ደግሞ ትልቁን ሚና በመጫወት ረገድ አፄ ኃ/ሥላሴ የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡
ይህን ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ኢትዮጵያና አፄ ኃ/ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦና ተደናቂ ሥራ በተመለከተ በወቅቱ በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ የተገኙት የናይጄሪያው ጠቅላይ ሚኒስቴር የሆኑት፣ ክቡር ሰር አል ሃጂ አቡበከር ታፌዋ ባሌዋ እንደሚከተለው ነበር ያሉት፡- መላው የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎችና የመንግሥታት ባለ ሥልጣኖች በአዲስ አበባ ላይ ሊገኙ ለመቻላቸው በግርማዊነትዎ ጥረት ስለሆነ በተለይ ለግርማዊነትዎ እጅግ ከፍ ያለ ክብር የሚያሰጥ ነው፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ አንድነት እንዲገኝ የምናደርገው ጥረት ወደፊት የኢትዮጵያን መናገሻ ከተማ የአዲስ አበባ ስም ደጋግሞ የሚያወሳ ስለሆነ የአዲሲቱ አፍሪካ ታሪክ የግርማዊነትዎን ስም በተቀዳሚው ገጹ ላይ አሳምሮ የሚያኖረው ለመሆኑ ጥርጥር የለበትም፡፡ አፄ ኃ/ሥላሴ በ1930ዎቹም ኢትዮጵያ የሊግ ኦፍ ኔሽን አባል እንድትሆን በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ኢትዮጵያንም ብቸኛዋ አፍሪካዊትና የጥቁር አገር ሊግ ኦፍ ኔሽን አባል በማድረግ ጥረታቸውን በሚገባ አሳክተዋል፡፡
በኋላም በተባበሩት መንግሥታት ምሥረታ ስብሰባ ወቅትም ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ፍራንክሊን ዴላኖ ሩዜቬልት፣ ከብሪታንያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዊንስተን ቸርችልና ከቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ስታሊን ጋር በያልታ ጥቁር ባሕር ልዩ ስብሳባ ላይ ተሣትፈዋል፡፡ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጋራ ስምምነት መሠረትም በኮሪያ ልሣነ ምድር የኢትዮጵያን የሰላም አስከባሪ ኃይል በማሰማራት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡ በዚህም አፄ ኃ/ሥላሴ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በዓለም አቀፍ መድረክ እንዲታወቁ ትልቁን ሚና ተጫውተው አልፈዋል፡፡
ፍቅር፣ ወንድማማችነት፣ ሰላም፣ አንድነትና ኅብረት ለአፍሪካና ለአፍሪካውያንን ወሳኝና ተቀዳሚ ነገር መሆኑ የተረዱት አፄ ኃ/ሥላሴ አፍሪካውያን አባቶችን፣ ፖለቲከኞችንና መሪዎችን በማስተባበር የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲቋቋም የላቀ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
በወቅቱ ድርጅቱ ሲቋቋም የነበሩ ሰዎች እንደመሠከሩት አፄ ኃ/ሥላሴ እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ የአፍሪካ መሪዎችን ጉባኤ ስብሰባ በመምራት፣ ይህ የአፍሪካውያን የወንድማማችነት፣ የአንድነትና የፍቅር ሰነድ ሳይፈረም ማንኛችንም ብንሆን ከዚህ ስብሰባ አዳራሽ ውስጥ በጭራሽ አንወጣም በማለት የተኮራረፉና የተለያዩ ፖለቲካዊ ቁርሾ ውስጥ የገቡትን የአፍሪካ አገራት መሪዎችን በማግባባትና በማሸማገል ንጉሡ ኅብረቱ እውን እንዲሆን ታላቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡
የትላንትናው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ኅብረት በሁለት እግሩ እንዲቆም በማስቻል የኢትዮጵያ የሺህ ዘመናት ታሪክ፣ ሥልጣኔና ቅርስ፣ የቀደሙ አባቶቻችን ጽኑና አይበገሬ የሆነው የኢትዮጵያዊነት ብሔራዊ ኩራትና መንፈስ እንዲሁም ጥቁር ሕዝቦችን ሁሉ ያኮራውና አንገቱን ቀና አድርጎ እንዲራመድ ያስቻለው የኢትዮጵያውያኑ የነፃነት ተጋድሎ፣ በባርነትና በቅኝ ግዛት ስር ይማቅቁ ለነበሩ ለአፍሪካ አገሮች ነፃነትና አንድነት እውን መሆን ትልቁን መሠረት ጥሏል፡፡
ይህን የኢትዮጵያንና የኢትጵያውያንን ታላቅ ታሪክ፣ ሥልጣኔ፣ ብሔራዊ ኩራትና የአባቶቻችንን አኩሪ የነፃነት ገድል ለዘመናዊው ዓለም በማስተዋወቅና ረገድ የኢትዮጵያ መሪ የነበሩት ኃ/ሥላሴ በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ ክቡር ስምና ዝናና የፈተረላቸውን በርካታ አኩሪ ስራዎችን ሠርተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ዛሬ የ50ኛ ዓመቱን የወርቅ ኢዮቤልዩ ልደቱን ለማክበር ዋዜማ ላይ ያለውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/ኅብረት እንዲቋቋም ከሐሳብ ወይም ከጽንሱ አንስቶ እስከ ተግባራዊነቱ ድረስ የላቀ ተሣትፎ ነበራቸው ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ፡፡
ንጉሡ ቀዳማቂ አፄ ኃ/ሥላሴ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ ጉባኤ ስብሰባ ላይ ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው እንዲህ ነበር ያሉት፡- በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል፡፡ ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው፡፡ ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው … ፡፡ የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮ ቱሬም በአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያና ንጉሡ አፄ ኃ/ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦና ሥራ በተመለከተ ሲናገሩ እንዲህ ነበር ያሉት፡-
… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው፡፡ ይህ በንጉሠ በአፄ ኃ/ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖችም ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል … ፡፡ ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ከአገራችን ኢትዮጵያና ከአፄ ኃ/ሥላሴ ጋር አብሮ ስማቸው የሚነሡ ኢትዮጵያውያን ምሁራንና ድርጅቱንም በጸሐፊነት ያገለገሉ ባለ ታሪክ የሆኑ ሰዎች አሉ፡፡ እነርሱም የውጭ ጉዳይ ሚኒስተሩ አቶ ከተማ ይፍሩና የድርጅቱ የመጀመሪያ ዋና ጸሐፊ ሆነው የተመረጡት አቶ ክፍሌ ወዳጆ ናቸው፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ አቶ ከተማ ይፍሩ በመላው አፍሪካ አገራት በመዞርና መሪዎቹን ወደ ጉባኤው እንዲመጡ በመጋበዝና በማግባባት ታላቅ የሆነ ሚና ተጫውተዋል፡፡ አንዳንድ ጸሐፊዎችና ታሪክ አዋቂዎች እንደሚሉትም አቶ ከተማ ይፍሩ ከመሪዎቹ ማረጋገጫ እስከሚያገኙ ድረስ ወደ አገራቸው መሄድ እንደማይችሉ በመግለጽ አፍሪካውያን መሪዎች በስብሰባው ላይ እንዲገኙ በማድረግ ትልቅ ጥረት ማድረጋቸውን ብዙዎች ይመሰክሩላቸዋል፡፡
የዛሬውን መጣጥፌን ከማጠናቀቄ በፊት በቀጣይ ጽሑፌ ስለ ፓን አፍሪካ አመሠራረትና፣ በፓን አፍሪካ እንቅስቃሴ ውስጥ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውን ድርሻ ምን እንደነበር ከታሪክ ማሕደር በማጣቀስ ለመጻፍ እሞክራለሁ፡፡ በጽሑፌም ቀንደኛ ፓን አፍሪካኒስት ስለነበረው የጋናው ዶ/ር ንኩርማ በጥቂቱ ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡ የዛሬውን አጭር መጣጥፌን ኢትዮጵያ፣ ጀግና ልጆቿና ንጉሠ ነገሥቷ የነበሩት አፄ ኃ/ሥላሴ ለአፍሪካ አንድነት ድርጅትና መመሥረትና በኋላም ለኅብረቱ እውን መሆን ያበረከቱትን ትልቅ አስተዋጽኦ ያዘከርኩበትን አጭር የታሪክ ማስታወሻ፣ አፄ ኃ/ሥላሴ በአዲስ አበባ ላይ በተደረገው የግንቦት 15ቀን 1955 ዓ.ም. የአፍሪካ መሪዎች መክፈቻ ጉባኤ ላይ ባሰሙት ታሪካዊ ንግግራቸው ጽሑፌን ልቋጭ፡፡
ዛሬ የገጠመን ዕድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ መቼም ያልተገኘ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ በፊታችን የተደቀኑት ችግሮች ያንኑ ያህል ከፍ ያሉና ከባድ ናቸው፡፡ ታሪክና ጊዜ የጣሉብን ከፍተኛ ኃላፊነት ሁላችንም ረጋ ብለን እንድናስብና እንድናመዛዝን ያስገድደናል፡፡ የተነሳንበትን ከፍተኛ ተግባር በመልካም አከናውነን ብንገኝ ስማችንና ተግባራችን በታሪክ መልካም ስም ይኖረዋል፡፡ ተግባራችንን ሳንፈጽም ብንቀር ግን ይታዘንብናል፡፡ ስለዚህ እምነታቸውን የጣሉብንን ሕዝቦቻችን በሚመጡት ጊዜያቶች ውስጥ ከእኛ የሚጠብቁትን ሁሉ ለመፈጸም እንዲያበቃን ሁሉን የሚችለውን ፈጣሪያችን ጥበብንና አስተዋይነትን እንዲሰጠን እናምነዋለን፣ እንለምንዋለን፡፡
ክብር ለአፍሪካ አንድነት ለደከሙ አፍሪካውያን አባቶቻችንና ጀግኖቻችን ሁሉ! ሰላም! ሻሎም!

 

 

***********************************

የዛሬው አፍሪካ ሕብረት የትላንቱ የአፍሪካ አንድነት ምስረታ

 
የትናንቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ የዛሬው የአፍሪካ ህብረት የተመሰረተው ከ57 አመታት በፊት በዚህ ሳምንት ግንቦት 16 ቀን 1955 ዓ.ም ነበር::
ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ በጉባኤው ላይ ለተገኙት የአፍሪካ መሪዎች ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግራቸው እንዲህ አሉ፡-
"በዚህ በዛሬው ቀን በዚህች በዋና ከተማችን በአዲስ አበባ የዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ተካፋይ ለመሆን የመጣችሁትን የነፃ አፍሪካ አገር መሪዎች፣ ወንድሞቻችን በራሳችንና በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ስንቀበል በጣም ደስ ይለናል:: ይህ ዛሬ እኛ የአፍሪካ ነፃ መንግሥታት መሪዎች የምናደርገው ጉባኤ በዓለም ላይ እስካሁን ድረስ ተወዳዳሪ የለውም:: የዚህን ታላቅ ጉባኤ መደረግና የመላው አፍሪካ አገሮች መሪዎች ተካፋይ በመሆን ለዚህች ክፍለ ዓለማችን በውስጧም ለሚገኙት ሕዝቦቻችን ላለን ጥልቅ አሳቢነት ዓይነተኛ ምስክር ነው:: ባጭሩ ይህ ቀን ለአፍሪካና ለአፍሪካውያን በመላ ታሪካዊና ታላቅ ቀን ነው … ::"
ዕለታዊው የአዲስ ዘመን የወርሀ ግንቦት 15 ቀን 1955 ዓ.ም ዕትሙ በፊት ለፊት ገጽ ላይ፣ ‹‹ሠላሳ የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ጉባኤ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፈተ:: ግርማዊ ጃንሆይም የጉባኤው የክብር ሊቀመንበር እንዲሆኑ ተመረጡ::›› በሚል ዐቢይ ርዕስ ስር እንዲህ ይላል፡-
"ቁጥራቸው ከ250 ሚሊየን በላይ በሆኑ አፍሪካውያን እጅግ በጋለ ስሜት ይጠበቅ የነበረውና መላው ዓላም ህዝብ ሁኔታውን በቅርብ ይከታተለው የነበረው የ30ዎቹ የአፍሪካ ነጻ መንግስታት መሪዎች ጉባዔ ግንቦት 14 ቀን ትናንት ከእኩለ ቀን በኋላ በአፍሪካ አዳራሽ ተከፍቷል:: … ጉባኤውን የከፈቱት ግርማዊ ንጉሠ ነገስት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጉባኤው ስራውን ከመጀመሩ በፊት የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት እንዲደረግ አሳስበው ጸሎት ተደረገ:: ቀጥሎም የሊቀ መንበር ምርጫ እንዲደረግ አሳስበው የጊኒው ፕሬዚደንት ሴኩቱሬ የመጀመሪያውን ምርጫ እንዲያደርጉ ጠየቁ:: ክቡር ፕሬዚደንት ሴኩቱሬ ቀደም ብሎ ተደርጎ የነበረው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጉባዔ ጠቅላላ ውሳኔ ያልሰጠ መሆኑን በመግለጽ ከተናገሩ በኋላ፣ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት የጉባዔው ፕሬዚደንት የላይቤሪያው ፕሬዚደንት ተብማን፤ የተባበረው የአረብ አንድነት ሪፐብሊክ ፕሬዚደንት ናስርና የጋናው ፕሬዚደንት ንኩሩማህ፤ የአይቮሪኮስቱ ፕሬዚደንት ቧኜ፤ የናይጄሪያው ታፌዋ ባሌዋ የሴኔጋሉ ሊዎፖልድ ሴንጎር፤ የኮንጎ ብራዛቪሉ ኦቦ ፋልቤር ዩሉና የታንጋኒካው ጁሊየስ ኔሬሬ የጉባኤው ተከታታይ ፕሬዚደንቶች እንዲሆኑ ሐሳብ አቀረቡ::
ይህ ሐሳብ በጉባኤው አባሎች በሙሉ በመደገፉ በፕሬዚደንት ሴኮቱሬ የቀረበው ምርጫ ጸደቀ:: ከዚህ በኋላ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ለዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ሥራ ታላቅ መመሪያ የሚሰጥ ንግግር አደረጉ::"
አፄ ኃይለ ሥላሴ በወቅቱ ባደረጉት ታሪካዊ ንግግራቸው እንዲህ ብለው ነበር::
"ዛሬ የገጠመን ዕድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ መቼም ያልተገኘ ትልቅ ዕድል ነው:: በፊታችን የተደቀኑት ችግሮች ያንኑ ያህል ከፍ ያሉና ከባድ ናቸው:: ታሪክና ጊዜ የጣሉብን ከፍተኛ ኃላፊነት ሁላችንም ረጋ ብለን እንድናስብና እንድናመዛዝን ያስገድደናል:: የተነሳንበትን ከፍተኛ ተግባር በመልካም አከናውነን ብንገኝ ስማችንና ተግባራችን በታሪክ መልካም ስም ይኖረዋል:: ተግባራችንን ሳንፈጽም ብንቀር ግን ይታዘንብናል:: ስለዚህ እምነታቸውን የጣሉብንን ሕዝቦቻችን በሚመጡት ጊዜያቶች ውስጥ ከእኛ የሚጠብቁትን ሁሉ ለመፈጸም እንዲያበቃን ሁሉን የሚችለውን ፈጣሪያችን ጥበብንና አስተዋይነትን እንዲሰጠን እናምነዋለን፣ እንለምንዋለን::"
ግንቦት 17 ቀን ማታ ከምሽቱ ሁለት ሰኣት ጀምሮ በታላቁ ቤተመንግስት ስለአፍሪካ መሪዎች እንግድነት ክብር ታላቅ የእራት ግብዣ አድርገው ነበር::
ሰኞ ግንቦት 19 ቀን 1955 ዓ.ም የወጣው የአዲስ ዘመን ጋዜጣ "ካዛብላንካና ሞኖሮቪያ ተሰርዞ አንድ ቻርተር ተፈረመ" በሚል ርዕስ ባወጣው ዜና ‹‹የካዛብላንካና የሞኖሮቪያ የሌሎችንም ብሎኮችና ቻርተሮች ሠርዞ የአፍሪካ አንድነትን የሚመሠርተው ‹የአፍሪካና የማላጋሲ አገሮች ድርጅት ቻርተር› ግንቦት 17 ቀን ለግንቦት 18 ቀን አጥቢያ 1955 ዓ.ም ከሌሊቱ 7 ሰዓት ከ45 ደቂቃ ላይ በአፍሪካ አዳራሽ ውስጥ ተፈርሟል::"
ተደናቂ ሥራ በወቅቱ በአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ የተገኙት የናይጄሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር ታፌዋ ባሌዋ ለአፍሪካ አንድነት እውን መሆን ኢትዮጵያና አፄ ኃይለ ሥላሴ ያደረጉትን ታላቅ አስተዋጽኦ ሲገልጹ ተከታዩን ብለው ነበር::
"መላው የአፍሪካ መንግሥታት መሪዎችና የመንግሥታት ባለ ሥልጣኖች በአዲስ አበባ ላይ ሊገኙ ለመቻላቸው በግርማዊነትዎ ጥረት ስለሆነ በተለይ ለግርማዊነትዎ እጅግ ከፍ ያለ ክብር የሚያሰጥ ነው:: በዚህ ጉባኤ ላይ አንድነት እንዲገኝ የምናደርገው ጥረት ወደፊት የኢትዮጵያን መናገሻ ከተማ የአዲስ አበባ ስም ደጋግሞ የሚያወሳ ስለሆነ የአዲሲቱ አፍሪካ ታሪክ የግርማዊነትዎን ስም በተቀዳሚው ገጹ ላይ አሳምሮ የሚያኖረው ለመሆኑ ጥርጥር የለበትም::"
የጊኒ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሴኮቱሬም በአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ለአፍሪካ አንድነት ምስረታ ኢትዮጵያ ያደረገችውን ታላቅ አስተዋጽዎ እንዲህ ገልጸውታል፡-
"… ኢትዮጵያዊ ታላቅ ሕዝብ ነው:: ስለ አፍሪካ ነፃነት በጀግንነት የተዋጋ፣ ነፃነትም ቋሚ እንዲሆን፣ ሕዝቦቻችን ያለ ምንም የውጭ መንግሥታት ተቆጣጣሪነትና ጣልቃ ገብነት በተገቢ ሥልጣናቸው እየተመሩ የገዛ ራሳቸውን ዕድል እንዲመሩ ያላቸው ሥልጣን እንዲጠበቅላቸው የደከመ አፍሪካዊ ሕዝብ ነው:: ይህ በንጉሡ በአፄ ኃይለ ሥላሴ አስተባባሪነትና መሪነት፣ የአፍሪካውያኖች ጉባኤ የተደረገው በኢትዮጵያ መናገሻ ከተማ ስለሆነ፣ አዲስ አበባና ኢትዮጵያ አሁንም የበለጠ ከአፍሪካ ታሪክ ጋር የተሳሰሩ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል:: ከዛሬ ጀምሮ ወደፊት በአንድ አኅጉር ሕዝቦች ፈቃድ ተነሳስቶ በሚመራው የዕድገት ፍላጎትና ሥራ ሁሉ ሳይቋረጥ ስማቸው ተያይዞ የሚኖር ይሆናል …::"
በፍቅር ለይኩን የተባሉ የታሪክ ባለሙያ የአፍሪካ ኅብረት የ50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓልን አስመልክተው ባሰናዱት ጽሑፍ ድርጅቱን በመመስረት ረገድ አፄ ኃይለ ሥላሴ የነበራቸውን ሚና እንደገለጹት ፣ "‹ኢንሳክሎፒዲያ ብሪታኒካ› ስለ አፄ ኃ/ሥላሴ ባቀረበው አጠር ያለ ጽሑፍ ‹Haile Selassie played a very important role in the establishment of the Organization of African Unity in 1963›› ብሏል:: …
ፍቅር፣ ወንድማማችነት፣ ሰላም፣ አንድነትና ኅብረት ለአፍሪካና ለአፍሪካውያንን ወሳኝና ተቀዳሚ ነገር መሆኑ የተረዱት አፄ ኃይለ ሥላሴ አፍሪካውያን አባቶችን፣ ፖለቲከኞችንና መሪዎችን በማስተባበር የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲቋቋም የላቀ አስተዋጽኦ አድርገዋል::
በወቅቱ ድርጅቱ ሲቋቋም የነበሩ ሰዎች እንደመሠከሩት አፄ ኃይለ ሥላሴ እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ የአፍሪካ መሪዎችን ጉባኤ ስብሰባ በመምራት፣ ይህ የአፍሪካውያን የወንድማማችነት፣ የአንድነትና የፍቅር ሰነድ ሳይፈረም ማንኛችንም ብንሆን ከዚህ ስብሰባ አዳራሽ ውስጥ በጭራሽ አንወጣም በማለት የተኮራረፉና የተለያዩ ፖለቲካዊ ቁርሾ ውስጥ የገቡትን የአፍሪካ አገራት መሪዎችን በማግባባትና በማሸማገል ኅብረቱ እውን እንዲሆን ታላቅ ሚና ተጫውተዋል::

***********************************

ታሪክ በዛሬው ዕለት
ግንቦት 17 ቀን ከተፈፀሙ የታሪክ ክስተቶች መካከል
•1955 ዓ/ም - የ22 ነጻ የአፍሪቃ አገራት መሪዎች አዲስ አበባ ላይ ተሰብስበው የአፍሪቃ አንድነት ድርጅትን መሠረቱ።
•1963 ዓ/ም - በአዲስ አበባ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሰላማዊ ሰልፍ፤ በከተማው ወጥቶ-እብሶች እና ንብረት ላይ ጉዳት አደረሱ። በዚህም ምክንያት አሥር ሁለተኛ ደረጃ ትምሕርት ቤቶች ተዘጉ።
•1977 ዓ/ም - በባንግላዴሽ ታላቅ አውሎ ነፋስ ተነስቶ ያስከተለው የዝናብ ጎርፍ ፲ ሺ የሚጠጉ ሰዎችን ገደለ።
•1989 ዓ/ም - በሲዬራ ሌዎን፣ በሻምበል ጆኒ ፖል ኮሮማ የተመራ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ፕሬዚደንት አህመድ ቴጃን ካባህን ከሥልጣን አወረደ።
.......................................................
#የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ምስረታ - 57ኛ ዓመት
የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (የአሁኑ "የአፍሪካ ኅብረት - AU") የተመሰረተው ከዛሬ 57 ዓመታት በፊት (ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም) ነበር፡፡
እ.አ.አ በ1884/85 ከተካሄደው የበርሊን ጉባዔ (Berlin Conference) በኋላ ኃያላኑ የአውሮፓ አገራት የአፍሪካ አገራትን በመቀራመት የቅኝ ግዛት አደረጓቸው፡፡ አውሮፓውያኑ አገራትም በቀጥተኛ አስተዳደር እንዲሁም በከፋፍሎ መግዛት መርሆች በመታገዝ አፍሪካውያኑን ለባርነት ዳረጓቸው፡፡ የአፍሪካን የተፈጥሮ ሀብት ለኢንዱስትሪዎቻቸው ግብዓት ወደ አገራቸው አጋዙት፡፡
የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም አውሮፓዊው ወራሪ የኢጣሊያ ጦር በታላቁ ንጉሰ ነገሥት ዳግማዊ አጤ ምኒልክ በተመራው የኢትዮጵያ ጦር ሲሸነፍ በቅኝ ግዛት ቀንበር ስር ያሉ አፍሪካውያን ስለነፃነት በርትተው ማለም ጀመሩ፡፡ ታላቁ የዓድዋ ድል የማንቂያ ደወል ሆነላቸው፡፡ ከዚህ ጊዜ በኋላ አፍሪካውያን በአንድም ይን በሌላ መንገድ ለነፃነታቸው መዋጋት ጀመሩ፡፡ ጋና የጀመረችው የነፃነት ችቦ በሌሎቹም አገራት አበራ፡፡
የአኅጉሩ መሪዎች በዓለም መድረክ ላይ ለበለጠ ተሰሚነትና የትብብርን ግንባር ማሳየት እንደነበረባቸው በመገንዘብና ገና ነጻ ላልወጡትም ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ሉዐላዊነት መታገል ስለነበረባቸው ዓላማቸውን ግብ ለማድረስ የሚያስችል ኅብረት/ማኅበር ለመመስረት አሰቡ፡፡ ማኅበሩን በመመስረት ሂደት ላይም ኢትዮጵያና ከቅኝ ግዛት ነፃ የወጡት አገራት በሁለት የተለያዩ ጎራዎች ተከፈሉ፡፡
አንደኛው ቡድን ራሱን ‹‹የዘመናዊ ተራማጅ›› ብሎ የሚጠራው ‹‹የካዛብላንካ ቡድን›› ሲሆን የቡድኑ አባላት በፖለቲካና በኢኮኖሚ የተዋሃደች የአፍሪካ ፌደሬሽንን የመመስረት ዓላማና የግራ ዘመም ፖለቲካ አቀንቃኝ በሆኑ መሪዎች የተዋቀረ ነበር፡፡ በዚህ ጎራ የተሰለፉት አገራት ጋና፣ አልጄሪያ️፣ ጊኒ🇬🇳️፣ ሞሮኮ🇲🇦️፣ ግብጽ🇪🇬️፣ ማሊ🇲🇱️ እና ሊቢያ 🇱🇾️ሲሆኑ የቡድኑ መሪም የወቅቱ የጋናው ፕሬዝደንት ክዋሜ ንክሩማህ ነበሩ፡፡
ሁለተኛው ቡድን ደግሞ ‹‹የሞንሮቪያ ቡድን›› ሲሆን የአፍሪካ አገራት ያለፖለቲካዊ ውህደት በኢኮኖሚያዊና በሕዝብ ለሕዝብ ትስስሮች ተባብረው መዝለቅ እንዳለባቸው ያምናል፡፡ በዚህ ጎራ የነበሩት አገራት ሴኔጋል🇸🇳️፣ ናይጄሪያ🇳🇬️፣ ላይቤሪያ🇱🇷️ እና ኢትዮጵያ 💚💛🧡 ነበሩ።
በመጨረሻም በወቅቱ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ታላቅ ጥረትና በንጉሰ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ ሁለቱም ወገኖች አዲስ አበባ ላይ እንዲገናኙ በተደረገው ጥሪ መሠረት ግንቦት 14 ቀን 1955 ዓ.ም የ32 ነጻ አገራት ተወካዮች አዲስ አበባ ላይ ለስብሰባ ተቀመጡ፡፡ ከሦስት ቀናት ውይይት በኋላም፣ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም አገራቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን የስምምነት ውል (OAU Charter) ሲፈርሙ የድርጅቱ ምስረታ እውን ሆነ።
በወቅቱም የአገራቱ መሪዎች ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ንጉሰ ነገሥት ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ፣ ጸሐፌትዕዛዝ ክቡር አቶ አክሊሉ ሀብተወልድና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ያበረከቱት አስተዋፅኦ ላቅ ያለ ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ በርካታ ወገኖች ለቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ‹‹የአፍሪካ አባት›› የሚል ስም ሰጥተዋቸዋል፡፡
ጃንሆይ - የአፍሪካ አባት! 
 
ምንጭ:- ልዑል ዓምደጽዮን ሠርፀድንግል እና ልዩ ልዩ


**********************************

የአፍሪካ ኅብረት (አንድነት ድርጅት) ምሥረታ የዓይን እማኝ የነበሩት ፊታውራሪ ምን ይላሉ?

መንግሥቱ አበበ__Saturday, 01 June 2013 

 *************************************

እንግዶች በመሳፍንትና በመኳንንት ቤቶች አርፈዋል ሁፌት ቧኜ አውሮፕላን ስለማይወዱ በመርከብና በባቡር ነበር የመጡት

የኋላ ማርሽ አስገብተን ወደ ዛሬ 51 ዓመት እንጓዝ፡፡ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት ከቅኝ አገዛዝ ነፃ የወጡበት ጊዜ ነበር፡፡ ነፃ ያልወጡም አገራት ነበሩ፡፡ አፍሪካ ተባብራ ችግሮቿን እንድትፈታ፣ ነፃነቷንም እንድታስከብርና ነፃ ያልወጡ አገራትን እንድትደግፍ፣ በአንድነት የምንትቀሳቀስበት ኅብረት ያስፈልጋታል በማለት የፓን አፍሪካኒዝም የሚቀነቀንበት ወቅት ነበር፡፡ ከብዙ ጥረት በኋላ ሐሳቡ ተቀባይነት አገኘና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲመሠረት ነፃ የአፍሪካ መንግሥታት ተስማሙ፡፡

ነገር ግን ማን አስተባባሮ ድርጅቱ ይመሥረት? ቻርተሩንስ ማን ያዘጋጀው? የድርጅቱ መቀመጫስ የት ይሁን? … የሚሉት ምላሽ የሚሹ ጥያቄዎች ነበሩ።

በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያ እኔ ኃላፊነቱን እወጣለሁ አለች፡፡ ይኼኔ ከየአካባቢው ተቃውሞ ተነሳ፡፡ “ኢትዮጵያ መሰብሰቢያ አዳራሽ፣ ሆቴል፤ መንገድ፤ ንፅህና፣ … የላትም፡፡ ካይሮ፣ ሌጐስ፣ ናይሮቢ፣ … እያሉ እንዴት አዲስ አበባ መቀመጫ ትሆናለች? በማለት የተቃወሙ ፖለቲከኞች ብዙ ናቸው፡፡ ነገር ግን ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ በነበራቸው ብልህ ፖለቲካዊ ብስለት፣ ከፍተኛ ጥረትና የማሳመን ችሎታ፣ አዲስ አበባ ከ51 ዓመት በፊት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የአፍሪካን አንድነት ድርጅት ምሥረታ ጉባኤ እንድታዘጋጅ ተወሰነ፡፡ ከውሳኔው በኋላ ጃንሆይ የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸውን ሰብስበው፣ ጉዳዩን ካስረዱ በኋላ “ጊዜ የለንም፤ ያሉን 12 ወራት ብቻ ናቸው። የአውሮፕላን ማረፊያ ሜዳ፣ መሪዎች ሲመጡ የሚያርፉበትና የሚሰበሰቡበት አዳራሽ የለም። ጎበዝ! እንዴት ይህን ኃላፊነት እንወጣ? በማለት ጠየቁ፡፡ ለዝግጅት የተሰጠው ጊዜ በጣም አጭር ነው፡፡

ለምን ስብሰባው ለሌላ ጊዜ አይተላለፍም? በማለት ሐሳብ ያቀረቡ ሚኒስትሮች ነበሩ፡፡ ልዑል ራስ መንገሻ ስዩም (በወቅቱ ደጃዝማች) “ዕድሉ ሊያመልጠን አይገባም፡፡ ገንዘቡ ከተፈቀደልኝ በተባለው ጊዜ ውስጥ (እንዲያውም ከዚያ ቀደም ብዬ በዘጠኝና በአስር ወር) ሥራውን አጠናቅቄ አስረክባለሁ” በማለት ቃል ገቡ፡፡ ንጉሡም፣ ልዑል ራስ መንገሻ የተግባር ሰው መሆናቸውን ስለሚያውቁ “መንገሻ አደርገዋለሁ ካለ ያደርገዋል” በማለት በሐሳባቸው ተስማሙ፡፡ “ሥራው ወዲያውኑ ተጀምሮ ሌት ተቀን እየተሠራ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ፣ የአፍሪካ አዳራሽና የግዮን ሆቴል ተሠርተው ስላለቁ፣ ጉድ ተባለ፡፡ ልዑል ራስ መንገሻም “ልጄ ተባረክ” በመባል በንጉሡ ተመሰገኑ ያሉት በወቅቱ የፓርላማ አባል የነበሩት ፊታውራሪ አበበ ሥዩም ደስታ ናቸው፡፡

ፊታውራሪ አበበ ሥዩም የዛሬ 50 ዓመት የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሠረት በፓርላማ ሕግ መምሪያ ም/ቤት የተንቤን ሕዝብ እንደራሴና የበጀት ኮሚቴ ሊቀመንበር ነበሩ፡፡ ስለ አፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ፣ ስለ እንግዶቹ አቀባበልና ዝግጅት፣ … የሚናገሩት አላቸው። ዛሬ ፊታውራሪ አበበ የ83 ዓመት አዛውንት ናቸው። በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ በዝርዝር ሲናገሩ የማስታወስ ችሎታቸው ይደንቃል፡፡ ከ50 ዓመት በፊት የነበረውን ነገር ከዓመትና ከሁለት ዓመት በፊት እንደተፈፀመ ታሪክ ነው የሚያንበለብሉት፡፡ የሕይወት ታሪካቸውንም ጽፈው “ዝክረ ሕይወት” በሚል ርዕስ አሳትመዋል፡፡

ፊታውራሪ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተመሠረተው እንዴት እንደነበር ያጫውቱናል፤ እንከታተላቸው፡፡ በዚያን ጊዜ አፄ ኃይለ ሥላሴ አፍሪካን አንድ የማድረግ ሕልም ነበራቸውና ሕልማቸው ተሳካ። በንጉሡ ዙሪያ የተሰባሰቡት ሚኒስትሮች በሳል ዲፕሎማቶች ነበሩ፡፡ ካቢኔው የሚመራው በጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀ/ወልድ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ክቡር ከተማ ይፍሩ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር፣ ክቡር ዶ/ር ተስፋዬ ገ/እግዚ የማስታወቂያ ሚ/ር፣ ክቡር ዶ/ር ምናሴ ኃይሌ፤ ክቡር አቶ ሰይፉ ማኅተመ ሥላሴ፣ እንዲሁም አፈ-ንጉሥ ተሾመ … የሚባሉ ሚኒስትሮች ወደ ተለያዩ የአፍሪካ አገሮች እየሄዱ ሲያስተባብሩና ሲያግባቡ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ብዙ ተደማጭነት የነበራቸው የግብፁ መሪ ጋማል አብዱልናስር ነበሩ፡፡ እሳቸውን ለማግባባት ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡ ይኼው የማግባባት ጥረት ተሳክቶ ስብሰባው በአዲስ አበባ እንዲካሄድ ሲወሰን እንግዶቹ መጥተው የሚሰበሰቡበት አዳራሽ፣ የሚያርፉበት ሆቴል፣ የለም፡፡ የተሰጠን ጊዜ ደግሞ አንድ ዓመት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ካላዘጋጀን ዕድሉ ለሌላ ይተላለፋልና ምን ይደረግ? ተባለ።

የሲዳሞ ጠቅላይ ገዥ የነበሩት ክቡር ደጃዝማች መንገሻ ሥዩም የሥራና መገናኛ ሚኒስትር ሆነው ስለተሾሙ፣ “ገንዘብ ከተሰጠኝ በአንድ ዓመት ውስጥ አይደለም፤ በዘጠኝ ወር ግፋ ቢል በአስር ወር ጨርሼ አስረክባለሁ” በማለት ለጃንሆይ ቃል ገቡ፡፡ “መንገሻ አያደርግም አይባልም፤ ይሠራል” ተባለ፡፡ የገንዘብ ሚ/ር የነበሩት እነ ክቡር አቶ ይልማ ዴሬሳና አንዳንድ ሚኒስትሮች “ይኼ እንዴት ይሆናል?” በማለት ጥያቄ አንስተው ነበር፡፡ ሥራው ተጀምሮ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፍያና የአፍሪካ አዳራሽ የተሠራው ያኔ ነው፡፡ 24 ሰዓት ሌት ተቀን በሦስት ፈረቃ ሲሠራ 11 ሰዎች ሞተውበታል፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ጽ/ቤት የድሮው ረዥሙ ሕንፃ ለአባዲና ፖሊስ ኮሌጅ የተሰጠ ሕንፃ ነበር፡፡ ጽ/ቤቱ የት ይሁን ተብሎ ሲፈለግ የድሮው ዓለም በቃኝ (ወህኒ ቤት) የነበረበት አጠገብ ያለው ሕንፃ ተመረጠ፡፡ ሌሎች ዙሪያውን ያሉት ከዚያ በኋላ የተሠሩ ናቸው፡፡


 

በዚያን ጊዜ የነበሩት ግዮን፣ ኢትዮጵያ፣ ራስ፣ ጣይቱ፣ ሒልተንና ገነት ሆቴሎች ብቻ ነበሩ፡፡ መሪዎቹ ሲመጡ የት ይረፉ ሲባል፣ በግዮን ሆቴል 32 መሪዎች የሚይዝ ቅጥያ ሁለት ፎቅ የተሠራው ያኔ ነው፡፡ ስብሰባው የተካሄደው አሁን ብሔራዊ ቤተመንግስት (ያኔ ኢዮቤልዩ ቤተ-መንግሥት) ተብሎ በሚጠራው ነበር፡፡ አዲስ አበባ አሸብርቃለች፡፡ በተለይ ከፒያሳ ማዘጋጃ ቤት እስከ ለገሃር ባቡር ጣቢያ ያለው ቸርችል ጐዳና፣ ከመስቀል አደባባይ እስከ ስድስት ኪሎ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ (ያኔ ገነተ - ልዑል ቤተመንግሥት) ድረስ በኢትዮጵያና በተለያዩ አገራት ባንዲራና መብራት አጊጦ ነበር፡፡ ዝግጅቱ ከተጠናቀቀ በኋላ መሪዎቹ የሚመጡበት ቀን ተቆረጠና ግንቦት 1955 ዓ.ም እንዲሆን ተወሰነ፡፡ የዝግጅቱ ዋና ተዋናይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ነበሩ።

በወቅቱ ኃይለኛ ዝናብ ስለነበር ጃንሆይ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ እየተገኙ ሁሉንም መሪዎች የተቀበሉት በዣንጥላ ነው - ዝናብ እየዘነበባቸው፡፡ ቀይ ምንጣፍ ተነጥፎና ፖሊስ ባንድ ማርሽ እያሰማ፣ ለእያንዳንዱ መሪ 21 ጊዜ መድፍ እየተተኮሰ ነበር የተቀበሏቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ትዝ የሚለኝ፣ የኮትዲቫር (ያኔ አይቮሪኮስት) መሪ የነበሩት ሁፌት ቧኜ በፍፁም በአውሮፕላን መጓዝ አይወዱም፡፡ ስለዚህ በመርከብ እስከ ጅቡቲ መጥተው ከዚያ ደግሞ በልዩ ባቡር ግንቦት 16 ቀን አዲስ አበባ ሲገቡ ደማቅ አቀባበል ተደርጐላቸዋል፡፡ በተወካይ የተሳተፉ አገሮች ቢኖሩም ኢትዮጵያን ጨምሮ 32 አገራት በመሪዎቻቸው አማካኝነት በስብሰባው ላይ ተሳትፈዋል፡፡ መሪዎቹና የልዑካን ቡድኑ አባላት አዲስ አበባ መግባት የጀመሩት ከግንቦት 13 ቀን ጀምሮ ሲሆን ተጠቃለው የገቡት ግንቦት 15 ቀን ነበር፡፡ ግንቦት 16 ቀን ምሽት ጃንሆይ በታላቁ ቤተመንግሥት በአፄ ምኒልክ አዳራሽ ለመሪዎቹ ክብር፤ ለልዑካን ቡድን አባላት፣ ለዲፕሎማቶች፣ ለጋዜጠኞች፣ በሀገር ውስጥ ላሉ መሳፍንት፣ ጳጳሳት፣ ሚኒስትሮች፣ መኮንኖች፣ ለታዋቂ ነጋዴዎችና ግለሰቦች በአጠቃላይ ከሦስት ሺም አምስት መቶ በላይ ለሚሆኑ እንግዶች ታላቅ የራት ግብዣ አደረጉ፡፡

ተጋባዦቹ ወደ አዳራሹ ከመግባታቸው በፊት በቤተመንግሥቱ ፊት ለፊት ባለው ሜዳ ላይ የተለያዩ ቀለማት ያላቸው ሪችት ተተኩሷል። አዳራሹ በአገር ባህል ቁሳቁሶች፣ የኢትዮጵያን ጥንታዊ ሥልጣኔ በሚያሳዩና በታዋቂ አርቲስቶች በተሣሉ ሥዕሎችና በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓለማ አሸብርቋል፡፡ የክብር ዘበኛ፣ የጦር ሠራዊትና የፖሊስ ሠራዊት የሙዚቃ ቦንቦችም ልዩ ልዩ ጥዑመ ዜማዎችን በማቅረብ እንግዶቹን ሲያስደስቱ አምሽተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካዊቷ ማሪያ ማኬባ “የጥንቱ ትዝ አለኝ” የሚለውን የዶ/ር ጥላሁን ገሠሠን ዜማ ስታንቆረቁር ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ ወደ አዳራሹ የተገባው ሁለት ለሁለት እጅ ተያይዞ ነበር፡፡ በመጀመሪያ የገቡት የኢትዮጵያ ንጉሥ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና የግብፁ ፕሬዚዳንት ጋማል አብዱልናስር ነበሩ፡፡ ጃንሆይ አጭር እንደ መሆናቸው መጠን፣ እጅ ለእጅ ተያይዘው ሲገቡ ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ በጣም ረዥም ከሚባሉት ጋማል አብድልናስር ሌሎችም በፊደል ተራቸው መሠረት ሁሉም መሪዎች እንዲገቡ ተደረገ፡፡

እራት ከተበላና ከተጠጣ በኋላ ክቡር ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ ከፈረንሳዊት ሚስታቸው ጋር ወደ መድረክ በመውጣት ዳንስ አስጀምረዋል። በማግሥቱ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም 32ቱ መሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካን አንድነት ድርጅት ቻርተር በፊርማቸው አፀደቁ፡፡ ቻርተሩ ለም/ቤቱ ቀርቦ በሙሉ ድምፅ አፀደቅነው። ቻርተሩ ለፓርላማ የቀረበው፣ ዓለም አቀፍ ውሎችንና ስምምነቶችን ም/ቤቱ ማወቅ ስላለበትና በቻርተሩ አንቀጽ 23 መሠረት አባል አገሮች ለድርጅቱ በየዓመቱ የሚከፍሉትን መዋጮ በበጀት ተይዞ መፅጸቅ ስላለበት ነው፡፡ ክቡር ፊታውራሪ አበበ ሥዩም ግን ጥቂት ቅሬታ አላቸው፡፡

“ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እንግሊዝኛ ፈረንሳይኛ ተናጋሪ በመጋል የተከፋፈሉትን የአፍሪካ መንግሥታት አስተባብረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ቻርተር እንዲፈረም ያደረጉ ታላቅ መሪ ነበሩ፡፡ አሁን በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ ፊትለፊት የጋናው መሪ የክዋሜ ንኩሩማ ሐውልት ብቻ እንዲቆም በመደረጉ ቅሬታ አለኝ፡፡ ወደፊትም ቢሆን ለጃንሆይና ለመሥራች መሪዎች መታሰሲያ ሐውልት ይቆምላቸዋል የሚል እምነት አለኝ” ብለዋል፡፡ ሌላው ቅሬታቸው ደግሞ የአፍሪካ አንድነት ሲመሠረት የነበሩ ጥቂት የዓይን እማኞች ስላሉ እነሱ በአፍሪካ ኅብረት ምሥረታ 50ኛ ኢዮቤልዩ በዓል ላይ እንዲገኙ ያለመጋበዛቸው አሳዝኖአቸዋል፡፡

 

Friday, December 22, 2023

እያዩ ፈንገስ

እያዩ ፈንገስ ‹‹ከፌስታሌን›› እስከ ‹‹ቧለቲካ›› 

      ደራሲ፣ ገጣሚና ጋዜጠኛ በረከት በላይነህ

      ተዋናይ ግሩም ዘነበ

 

“እያዩ ፈንገስ” የተባለው ገፀ ባህሪ “ፌስታሌን” ሆኖ የሙሉ ሰዓት ተውኔት እስኪሆን ድረስ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል በየወሩ በሚቀርበው ግጥምን በጃዝ ላይ ለሁለት ዓመት በ25 ክፍል ለተመልካች እይታ ቀርቧል።

የዚህ ገፀ ባህሪ ፈጣሪ ደራሲ፣ ገጣሚና ጋዜጠኛ በረከት በላይነህ ነው። በአንቲገን፣ ንጉስ አርማህ፣ፍቅርን የተራበና በበርካታ የመድረክ ትያትሩ የትወና ብቃቱ የሚታወቀው አርቲስት ግሩም ዘነበ ደግሞ ብቻውን መድረክ የሚቆጣጠርበት ሥራው ነው።


እያዩ ፈንገስ በኢትዩጵያ የአንድ ሰው ቴዓትር ታሪክ ውስጥ ዝነኛውና ግምባር ቀደም ገጸ ባህሪ እንደሆነ ይነገርለታል። ይኼ ገጸ ባህሪ ከዛሬ አሥር ዓመት በፊት በደራሲ በረከት በላይነህና በተዋናይ ግሩም ዘነበ አማካይነት ለተመልካቾች እንዲታይ ሆነ።

ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ በራስ ሆቴል በየወሩ የጃዝ ግጥም ምሽት ይዘጋጃል፡፡ ይህንን አጋጣሚ በመጠቀም የሥነ ጽሑፍ ሥራዎችን ለማቅረብ የሄደው በረከት፣ በዚያው መድረክ ላይ ግሩም ዘነበ የአውግቸው ተረፈን እያስመዘገብኩ ነው የሚለውን አጭር የመፅሀፉ ታሪክ ሲጫወት ያየዋል።

 ‹‹ገጸ ባህሪው አንድ ጭቃ አቡኪ ሲሆን በማኅበራዊ ሕይወታቸው የተበደሉና የሚያዝኑ ዓይነት ገጸ ባህሪ ነበሩ፣ ግሩምም በጥሩ ሁኔታ ስለሠራቸው የተመልካች አድናቆት ልዩ ነበር፤›› ሲል በረከት ያስታውሳል።

ይህንን ገጸ ባህሪ በየወሩ የማስቀጠል ፍላጎት ያደረበት በረከት፣ ግሩምን በማናገር ገጸ ባህሪው በሚቀጥልበት ሁኔታ ተነጋግረው ተስማሙ። ነገር ግን ገጸ ባህሪው በረከት መናገር የሚፈልገውን ሐሳብ ለማንፀባረቅና ለመሸከም ስለማይችል እያዩ ፈንገስ የሚለውን ገጸ ባህሪ ለመፍጠር ተገደደ።

ፈንገስ የሚለው ቃል አፍራሽ ነገርን ይወከላል ያለው የገጸ ባህሪው ደራሲ በረከት በላይነህ፣ በማኅበራዊ፣ በፖለቲካዊ፣ በኢኮኖሚያዊ እንዲሁም በመንግሥት ውስጥ ያለውን ንቅዘት የሚነካካና የሚገልጽ ዓይነት ገፀ ባህሪ ለመጻፍ መብቃቱን ይናገራል።

ገጸ ባህሪው መጀመርያ ላይ ሲጻፍ ስሙ ክንፉ የሚባል  እንዲሆን የተደረገ ቢሆንም፣ ተዋናይ ግሩም ዘነበ ስሙን እያዩ ወደሚል መጠሪያ ቀየረው።

በሚቀጥለው የራስ ሆቴል የግጥም ምሽት ፕሮግራም አንድ የአዕምሮ ሕመም ያለበት ዓይነት ሰው፣ በቁም ነገርና በቀልድ እያደረገ የሚናገር ገጸ ባህሪ ለሃያ ደቂቃ ያህል የአንድ ሰው አጭር ፕሌይ ለመጀመርያ ጊዜ መጋቢት 4 ቀን 2006 ዓ.ም. ለዕይታ ቀረበ፡፡

በሰው ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት በማግኘቱም  ለተከታታይ ሃያ ወራት በግጥም ምሽቱ ፕሮግራም ለታዳሚው ቀረበ።


በእዚ መሀል የሰውን በጎ ምለሽ የተመለከቱት ግሩምና በረከት ይኼን መልካም አጋጣሚና ተወዳጅነቱን በመጠቀም በ2011 ዓ.ም. ከሃያ ደቂቃ ፕሌይ ሰፊ ወደሆነ የሁለት ሰዓት ተኩል ርዝማኔና የራሱ ታሪክ እንዲሁም መነሻና መድረሻ ያለው (ፌስታሌን) የሚል ቴዓትር፣ በሳምንት ለአራት ቀናት በአዶትና በዓለም ሲኒማ በማሳየት ተወዳጅነትን አተረፉ። አዳራሽ ሙሉ ታዳሚ የነበረው ይኸው ፕሌይ ለአሥር ወራት ያህል ተካሂዷል፡፡

ፌስታሌን የሚለው ቴዓትር በአጭሩ ሲተነተን አንድ ፌስታሉ የጠፋበት ሰው እሱን በመፈለግ ላይ ሆኖ፣ ነገር ግን እሱን በማስታከክ የተለያዩ ማኅበራዊ፣ ፓለቲካዊ፣ መንግሥታዊ ጉዳዮችን በኮሜዲ፣ በትራጄዲና በፍልስፍና እያጣቀሰ የሚተውን ገጸ ባህሪ ነው።

‹‹በአሜሪካ የሚገኙ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች አገር ውስጥ ያገኘነውን ዝና ሰምተው ቲዓትሩን እንድንጫወትላቸው ግብዣ አቀረቡልን›› ይላል በረከት፡፡ በዚህም መሠረት ለአሥራ አንድ ወራት በሃያ ሰባት የአሜሪካ ግዛቶች ፌስታሌን የሚለውን የአንድ ሰው ቴዓትር ማቅረባቸውን ያስረዳል።

ከአሜሪካ ከተመለሱም በኋላ ጊዜ ሳያጠፉ የፌስታሌን ቀጣይ ክፍል የሆነው አጀንዳዬን የተሰኘውን ቴዓትር ለተመልካች ቢያቀርቡም፣ ብዙም ሳይቆይ የኮሮና ወረርሽኝ እንዲሁም በሰሜኑ ጦርነት ምክንያት አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመደንገጉና የሰዎች መንቀሳቀስ መብት በመገደቡ ቲዓትሩ እንዲቋረጥ ተገደደ።

ገጣሚ፣ ጋዜጠኛና ደራሲ በረከት በላይነህ
                                       ገጣሚ፣ ጋዜጠኛና ደራሲ በረከት በላይነህ

ግሩምና በረከት ይኼ ቴዓትር እንዲባክን ስላልፈለጉ ለሰው መድረስ አለበት ብለው ስላመኑ ይህንን በተለያዩ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጾች እንዲለቀቅ አደረጉት።

አጀንዳዬን የፌስታሌን ቀጣይ ክፍል ሲሆን፣ ፌስታሌን ካቆመበት የሚቀጥል ነው፡፡ በውስጡም ከፌስታሌን ጋር  ተመሳሳይ ይዘት ያለው ቴዓትር ይዟል፡፡ የታሪክ መነሻና መድረሻም አለው።

አዲሱና ሦስተኛው ቧለቲካ የተሰኘው ቴዓትር ከጥቅምት 2016 ዓ.ም. ጀምሮ በሳምንት ሁለት ጊዜ በዓለም ሲኒማ እየቀረበ ይገኛል። ቦለቲካ ከፌስታሌንና አጀንዳዬን ቀጥሎ እንደ አንድ ሰው ቴዓትር ሆኖ በበረከት በላይነህ ደራሲነት እንዲሁም በግሩም ዘነበ ተዋናይነት የቀጠለ ቢሆንም፣ የቲዓትሩ ይዘቶች የተለዩ ናቸው፡፡

 እንደ ቀድሞዎቹ ሁለት ቴዓትሮች መነሻና መድረሻ እንዲሁም አንድ ወጥ ታሪክን ተከትሎ የሚሄድ ታሪክ ባይኖረውም፣ እንደ ሁለቱ ቴዓትሮች ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ መንግሥታዊ ጉዳዮችን ይዳስሳል።

ቧለቲካ ለዘጠነኛ ጊዜ በዓለም ሲኒማ ታይቷል፡፡ የተመልካች ቁጥርም ከሌሎች ቴዓትሮች በተለየ ከፍተኛ መሆኑን ከዓለም ሲኒማ ሠራተኞች ያገኘነው መረጃ ያስረዳል።   

‹‹የእኔ አገራዊ ዕይታ የሚመነጨው ከፖለቲካ ሥርዓቱ ነው፤›› ይላል በረከት። ለዚህም እንደ ምክንያትነት ሲያነሳ፣ ‹‹አንድ አገር ውስጥ ለሚከናወነው በጎም ነገር በማኅበራዊ ቀውስ የሚታየው መጥፎ ነገር ዋናው መሠረቱ የፖለቲካ ሥርዓቱ ነፀብራቅ ነው፤›› ብሎ ያምናል፡፡ ‹‹የአንድ አገር የፖለቲካ ፍልስፍናና የሚከተለው የፖለቲካ ሥርዓት በአገር ላይ የሚታዩ ነገሮችን የሚወልድ በመሆኑ፣ ፖለቲካን በተለያየ ዓይን ብናየው ጥሩ ነው፤›› ያለው በረከት፣ በዚህም ምክንያት ድርሰት በሚጽፍበት ወቅት አብዛኛውን ጊዜ ፖለቲካ ነክ እንደሆነ ያስረዳል።

 


‹‹የፖለቲካ ይዘት ያለው ድርሰት እንደመጻፌ መጠን፣ እስካሁን  ምንም ዓይነት እስርም አካላዊ ጉዳትም አልደረሰብኝም” ያለው በረከት፣ ነገር ግን ራስ ሆቴል በሚሠሩበት ወቅት ፕሮግራሙ ላይ በሚነሱ ጉዳዮች የተናደደ አንድ የመንግሥት ካድሬ ሊያስፈራራቸው እንደሞከረ ያስታውሳል።

‹‹ማስተላለፍ የምንፈልገው እውነት ነው ወይስ ውሸት፣ ከዚያ ውጪ የምንዋሸው ነገር እስከ ሌለ ድረስ የምንፈራበት እንዲሁም የሚያሰጋን ነገር የለም››ሲል በረከት ያስረዳል።

ስለሦስቱ ቴዓትሮች ተፅዕኖ ሲያስረዳ፣ ‹‹በተለምዶ አካሄድ አንድ ቴዓትር በኪነ ጥበብ ሥራ ውስጥ ምንድነው ተፅዕኖው የሚለውን ለማየት በብዙ ነገር እንለካዋለን፡፡ በእዚህ ሰዓት የፊልምም የቴዓትርም ተመልካች ቀንሷል፡፡ ጠቅላላ ኢንዱስትሪውም ደክሟል፡፡ ሆኖም ሰው ተሠልፎ ቴዓትራችንን ያየዋል፣ በየዘርፉ ትልልቅ የሚባሉ ሰዎችም እየመጡ ያዩታል ለእኛም የገንዘብ ምንጭ በመሆን በግል ሕይወታችን ላይ ብዙ ጥሩ ነገር ይዞልን መጥቷል፤›› ይላል።

 በቀጣይም ለሦስት ወር ያክል በአውሮፓ፣ በአሜሪካ፣ አውስትራሊያና በደቡብ አሜሪካ ሄደው ቦለቲካን እንደሚያሳዩ ያስረዳል።

ተዋናይ ግሩም ዘነበ ስለሚተውነው ገጸ ባህሪ እያዩ ፈንገስ ሲናገር፣ ‹‹እኔና እያዩ የግል ታሪካችን ካልሆነ በስተቀር ለምሳሌ እሱ ሚስቱ የሞተችበት ነው፣ መምህር ነው፣ እሱ ካልሆነ በስተቀር ለሕዝብ ይድረስልኝ የሚላቸው መልዕክቶች ሙሉ በሙሉ የእኔ ሐሳብ ነው፡፡ ገጸ ባህሪው ሊናገር የሚፈልጋቸውን ነገሮች ተቃውሜ አላውቅም፤›› ይላል።

ገጸ ባህሪውን ስለሚወደው ለማጥናትና ወደራሱ ለመቀላቀል ያን ያህል እንዳላስቸገረው፣ ለአገሩ አንደበት ለመሆን ሚገርም ዘመን ላይ ያገኘው ገጸ ባህሪ በመሆኑም አክብዶ እንደሚሠራ፣ ግሩም ይናገራል።

‹‹እያዩ ፈንገስ የመጀመሪያው የአንድ ሰው ቴዓትር እንደመሆኑ መጠን ተጠቃሚ ነው ብዬ አስባለሁ፤›› በማለት ተዋናይ ግሩም ያስረዳል፡፡


 

የእያዩ ፈንገስ ገጸ ባህሪ የተዋቀረባቸው ማለትም ኮሜዲ፣ ትራጄዲና ፍልስፍና ወይም ወሳኝ ጉዳዮችን የሚያይበት ነገር በጣም ትልቅ አድርጎታል፡፡ ገጸ ባህሪውን የሚጽፈው ሰው ጎበዝ ባለተሰጥኦ በመሆኑ፣ ተወዳጅነቱን እንደያዘ አሥር ዓመታት አስጉዞታል፡፡ በመሆኑም ለባልደረባው ለደራሲ በረከት ያለውን አድናቆት ይገልጻል።

ስለቧለቲካ ቴዓትር ሐሳቡን ሲገልጽም፣ ‹‹የእኛ ፍላጎት ቶሎ ቶሎ ለሰዎች ማድረስ ነው፣ ነገር ግን የመድረክ ሥራ በመሆኑ ያንን ለማድረግ ዕድል ስለማይሰጥ የተወሰኑ ወራት ለዕይታ ይቀርባል፤›› ብሏል፡፡

 

 

የእያዩ ፈንገስ ‹‹ፌስታሌን››

የቴአትሩ አዘጋጅና ተዋናይ :- ግሩም ዘነበ 

 ደራሲው:- በረከት በላይነህ 

‹‹…በነገራችን ላይ ጋሽ ቆፍጣናው ማለት የሠፈራችን ደረጃ አንድ ታጥቦ የተቀሸረ ሙጢ ማለት ነው፡፡ ፊት ለፊት ተናጋሪ እና ሐቀኛ፡፡ ለማንም የማይመለሱ ቆፍጣና፡፡ የነገር ጠጠር ውርወራና ምክራቸው፡፡ በሰከንድ በአሽሙር ቋጥኝ ይፈረካክሱኋል፡፡ ቆፍጣናው እንዲህ ናቸው፡፡ አንድ የፈረደበት ተከራይ ጋዜጠኛ አላቸው፡፡ እንዲሁ ፍዳውን የሚያሳዩት፡፡ አንድ ቀን የሆነ ባለሥልጣኖችና ባለሀብቶች ኳስ ጨዋታ አድርገው ነበር መሰለኝ፡፡ ይኼንን ዘገባ ሠርቷል ጋዜጠኛው ተከራይ ሲመጣ ምን ቢሉት ጥሩ ነው በምን ለየሃቸው ግን?…››

ንግግሩ የተቀነጨበው ‹‹ፌስታሌን›› ከተሰኘው ዋን ማን ሾው (አንድ ተዋናይ ብቻውን የሚተውንበት ቴአትር) ነው፡፡ ቴአትሩ የታየበት መድረክ ከተጨናነቁ የመዲናችን መንደሮች አንዱ ይመስላል፡፡

የደሳሳው ጭቃ ቤት ልስን ፈራርሶ የቤቱ ማገር ይታያል፡፡ ከቤቱ አጠገብ ያሉ ሌሎች መኖሪያዎች ግርግዳዎችም እንዲሁ ያረጁ ናቸው፡፡ የጭቃ ቤቱ መጠነኛ መስኮትና በር ላይ ‹‹ታሽጓል›› የሚል ጽሑፍ ተለጥፏል፡፡ እዛው አካባቢ የሚታዩ ማስታወቂያዎች የአብዛኛውን የአዲስ አበባ መንገዶች ገጽታ ያስታውሳሉ፡፡

‹‹ሠርግዎን በዲጄ››፣ ‹‹ዋ ትሸናና፤ ከሸናህ ትሸነሸናለህ››፣ ‹‹አርቲስት መሆን ይፈልጋሉ?›› እና ‹‹እፀነፍስ የባህል መድሐኒት ቤት›› የሚሉ የኮምፒዩተር ጽሑፎች ይጠቀሳሉ፡፡

ካረጁ ቆርቆሮዎች እንደነገሩ የተሠራው መጠለያ ባደፉ ጨርቆች ተሸፋፍኗል፡፡ መጠለያው ውስጥ ጋደም ብሎ የነበረው እያዩ ፈንገስ ወደ መንገድ ዳር ይወጣል፡፡ ፊቱን በንዴት ቅጭም አድርጓል፤ በቁጭትም ይንዘፈዘፋል፡፡ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ፌስታሉን ሌቦች ሰርቀውታል፡፡ ይገኝበታል ብሎ በገመተው ሥፍራ ሁሉ ተዘዋውሮም ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በፍለጋ ላይ ሳለ ይባስ ብሎ ዘለፋ ይደርስበታል፡፡ እንዲህ ሲልም እያዩ ምሬቱን ይገልጻል፡፡

‹‹… የእትዬ ምልጃን ምክር ሰምቼ እኮነው ጉድ የሆንኩት፡፡ የሰፈሩን ቆሻሻ የሚያነሱት እነሱ ስለሆኑ ጠይቃቸው ያገኙልሃል ብለውኝ ሄጄ እኮ ነው በጠዋት ያገኙኝ፡፡ የቆሻሻ ገንዳቸውን እየገፉ ቁልቁል ሲወርዱ አየዋኋቸውና ሮጥ ሮጥ ብዬ ደረስኩባቸው፡፡ ያለ የሌለ ትህትናዬን አጠራቅሜ እባካችሁ ወንድሞቼ ትናንትና አሮጌ ልብሶች የያዘ ፌስታል ጠፍቶብኝ ነበረ፤ ምናልባት ካገኛችሁት ብዬ ነው አልኩኝ፡፡ አንደኛው እስኪ ምልክቱን ተናገር አለኝ፡፡ ሁሉም ፌስታሉ ውስጥ ያለውን ልናገር አልኩ፡፡ ታዲያስ ምልክት አይደለም እንዴ ሁሉንም ነው እንጂ መናገር አለኝ፡፡

ድምፄን ከፍ አድርጌ አራት የሽንት ጨርቆች ከነመዓዛቸው፣ አንድ እግር ጫፍ አይጥ የበላው የሕፃን ልጅ የዳንቴል ካልሲ፣ ጡጦ ክዳኑ የተሰነጠቀ፣ ሁለት የሴት ፓንቶች፣ ድርያ ከድሬዳዋ ፊልድ ስመለስ የተገዛና እንዲሁም ተረከዛቸው የሳሱ ነጠላ ጫማዎችና ቀዩ አጀንዳዬ፡፡ የእኔና የብዙ ሰዎች ሐሳብ የሰፈረበት ቀዩ አጀንዳዬ፡፡ ይኼ ሁሉ ውድ ንብረት ፌስታሌ ውስጥ ነበር አልኳቸው፡፡ ዘውድዬ ትሙት እርስ በርስ ሲተያዩ ልቤ ቀጥ ነበር ያለው፡፡ አግኝተውታል ብዬ ጠርጥሬ እኮ ነው፡፡ ከዛ በአንክሮ ካዩኝ በኋላ አንደኛው ምን ቢለኝ ጥሩ ነው? 904 ደውለህ አዘጋው፡፡ እየሳቁ ሄዱ፤››

እያዩ ፈንገስ የተባለው ገፀ ባህሪ የአዕምሮ ሕመምተኛ ነው፡፡ በገጠመው መሪር ሐዘን ሕይወቱ እንዳይሆን ሆኗል፡፡ ቴአትርሩም እያዩ የጠፋበትን ፌስታል መነሻ ያደረገ ነው፡፡

ብዙዎች የእያዩ ፈንገስን ገፀ ባህሪ የሚያውቁት በጦቢያ ግጥምን በጃዝ መርሐ ግብር ላይ ነው፡፡ በየወሩ በሚካሄደው ዝግጅት ላይ በዋነኛነት ግጥሞች የሚደመጡ ሲሆን፣ ወግ፣ መነባንብ፣ ዲስኩርና ሌሎችም ሥነ ጽሑፋዊ ሥራዎች ይስተናገዳሉ፡፡ ታዳሚዎች የየወሩን የመጀመሪያ ረቡዕ በጉጉት እንዲጠባበቁ ከሚያደርጉ አንዱ ደግሞ የእያዩ ፈንገስ ትዕይንት ነው፡፡

ለአንድ ዓመት ያህል ወደ 13 የሚደርሱ ክፍሎች ታይተዋል፡፡ የእያዩ ፈንገስ አንደኛ ዓመት የመድረክ ቆይታ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ተከብሮ ነበር፡፡ በየክፍሎቹ የተወሰኑ ደቂቃዎች ይወስድ የነበረው ትዕይንቱ አሁን የሙሉ ጊዜ ቴአትር ሆኗል፡፡ ሰኞ ሐምሌ 27፣ 2007 ዓ.ም. በአዶት ሲኒማና ቴአትር ተመርቋል፡፡

አስቂኝ በሆነ ዘዬ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ትችቶችን በመሠንዘር የሚታወቀው እያዩ፣ በ‹‹ፌስታሌን›› ላይም በርካታ ርዕሰ ጉዳዮችን ያነሳል፡፡ የኅብረተሰቡን አኗኗርና የወቅቱን ሥርዓት ያጠይቃል፡፡ መጨካከን፣ መታበይ፣ ሸፍጥና ሌሎችም ሕፀፆችን ይተቻል፡፡ የመሠረተ ልማት አለመስፋፋት፣ ኢኮኖሚያዊ ችግርና መሰል ጉዳዮችን ይዳስሳል፡፡

 

በምርቃት ሥነ ሥርዓቱ ታዳሚዎች እየሳቁ፣ በጭብጨባ ድጋፋቸውን እየገለጹም ተውኔቱን ይከታተሉ ነበር፡፡ ሲገባደድም ከመቀመጫቸው ተነስተው ለደቂቃዎች በማጨብጨብ አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡ እያዩ ፈንገስን ሆኖ የሚተውነው እንዲሁም የቴአትሩ አዘጋጅ ግሩም ዘነበ ሲሆን፣ ደራሲው በረከት በላይነህ ነው፡፡

እያዩ የሚነቅሳቸውን ችግሮች ‹‹ፈንገሱ ነው›› በማለት ይገልጻል፡፡ በተለያየ ዘርፍ አግባብ ያልሆኑ አካሄዶች ሥር መስደዳቸውንና በፍጥነት መስፋፋታቸውን ያመላክታል፡፡ ‹‹ፈንገስ›› የሚለው ቃል በማኅበረሰቡ ውስጥ የተንሰራፉ ችግሮችን እንደሚያሳይ በረከት ይናገራል፡፡ እያዩ አንድም የባዬሎጂ መምህር ስለነበር፣ በሌላ በኩል ደግሞ ፈንገስ በፍጥነት የመራባት ባህሪ ስላለው ለገፀ ባህሪው መጠሪያ እንዲሆን መመረጡን ይገልጻል፡፡

እሱ እንደሚለው፣ ገፀ ባህሪው የተጠነሰሰው ግሩም ከአውግቸው ተረፈ ‹‹ያስመዘገብኩት›› ላይ በጥቂቱ ቀንጭቦ በጦቢያ ግጥምን በጃዝ መድረክ ላይ ባቀረበበት ወቅት ነበር፡፡ ግሩም መኩሪያ የሚባል ገፀ ባህሪን ተላብሶ ነበር የሚጫወተው፡፡ ከተመልካቾች ያገኘውን በጎ ምላሽ በመመልከትም ቴአትሩ ተጀምሯል፡፡

እያዩ በነጻነት እንዲናገር ሲባል የአዕምሮ በሽተኛ ገፀ ባህሪ እንደተሰጠው በረከት ይናገራል፡፡ ‹‹ብዙ ነገሮችን መናገር የምችለው በእያዩ ነው፤›› ይላል፡፡ በአንድ ጉዳይ ዙሪያ ሐሳብ ይሰጣሉ ተብለው ከሚጠበቁ ግለሰቦች ውጪ ያልተገመቱ ሰዎች ሲናገሩ የበለጠ ተሰሚነት እንደሚኖራቸውም ያምናል፡፡

የአዕምሮ ሕመምተኛው እያዩ የተቀዳደደ ልብስ ለብሶ በደሳሳ መጠለያ ይኖራል፡፡ ፌስታሉን ፍለጋ ከቆሻሻ መጣያ ገንዳ ውስጥም ሳይቀር ይገባል፡፡ ‹‹ይህን ዓይነት ሰው ተመልካች የማይገምተውን ነገር ሲናገር ተደማጭነት ይኖረዋል፤›› ይላል በረከት፡፡

እንደ ደራሲው ገለጻ፣ የአዕምሮ ሕመምተኞች ወይም በልዩ ልዩ ምክንያት ማኅበረሰቡ የገፋቸው ሰዎች በምሬት የተሞሉና ቁጡ የሚሆኑበት አጋጣሚ ሰፊ ነው፡፡ ተውኔቱም ይህን እውነታ ተመርኩዞ ወቅታዊ የሆኑ ጉዳዮች ላይ ያተኩራል፡፡ ‹‹ቴአትሩ በዋነኛነት ማኅበራዊ ትችት አዘል ነው፤ ፖለቲካዊ ሽሙጥ (ፖለቲካል ሳታየር)ና ፍልስፍናዎችም አሉት፤›› በማለት ይዘቱን ያብራራል፡፡

እያዩ በገጠመው መሪር ሐዘንና የሕይወት ውጣ ውረድ አዕምሮውን ቢስትም ንግግሮቹ ፍልስፍናውን እንደሚያንፀባርቁ ይናገራል፡፡ የታዳሚዎችን ቀልብ ለመግዛትና መሰላቸት እንዳይኖርም አስቂኝ ሁነቶች ይካተታሉ፡፡

በደራሲው እምነት፣ በኅብረተሰቡ ዘንድ የግለሰቦች መብት በሚገባ አልተተነተነም፡፡ የየራሳቸው ስሜትና ምልከታ ያላቸው ግለሰቦች ማንነት በተናጠል መፈተሽ ሲገባው በቡድን መፈረጅ እንደሚያመዝን ይገልጻል፡፡ እያዩን ሰዎች እንደገፉት በመጥቀስ፣ ‹‹እያዩ ጨርቁን ስለጣለ አገር ጨርቁን አይጥልም፤ ሰው በሕይወቱ አሳዛኝ ነገር ይገጥመዋል፤ ዋናው ጥያቄ ሌሎች ሰዎች እንዴት ይቀበሉታል የሚለው ነው፤›› ሲል ይናገራል፡፡

ቴአትሩ መገፋፋትና ጭቆና ተቀርፎ አጠገባችን ያለውን ሰው ትኩረት እንስጠው የሚል መልዕክት ያስተላልፋል ይላል፡፡ የአንድ ማኅበረሰብ ጥንካሬና ትስስር የሚታየው ለግለሰቦች በሚሰው ቦታ መሆኑን በአጽንኦት ይናገራል፡፡

በየወሩ ይቀርብ የነበረው የእያዩ ትዕይንት በየመድረኩ የተለያዩ ጉዳዮች አንስቷል፡፡ በአንፃሩ ‹‹ፌስታሌን›› ወጥና የቴአትር ግብዓቶችን ያሟላ ነው፡፡ ባለቤቱ ዘውድዬን የመሰሉና ከእያዩ ጋር የሚታወቁ ገፀ ባህሪያት በአዲሱ ተውኔትም ይገኛሉ፡፡ ቴአትሩ የራሱ ማጀቢያ ሙዚቃ አለው፡፡ ተውኔቱ የሚያጠነጥንባቸውን ጉዳዮች የሚያጎሉት ሙዚቃዎች ከአንድ ትዕይንት ወደ ሌላው እንደመሸጋገሪያ የሚለቀቁ ሲሆኑ፣ የሚያዜሙት በዛወርቅ አስፋውና ግዛቸው ተሾመ ናቸው፡፡

ቴአትሩ የፌስታሉን ፍለጋ ተከትሎ በሚያስቁ በሚያሳዝኑም ሁነቶች የተሞላ ነው፡፡ በረከት እንደሚናገረው፣ ተመልካች ትዝብትና ስላቁን እንዲሁም አዝናኝነቱን ፈልጎ ይሄዳል፡፡ አንዳንዴ በትዕይንቱ መሳቅ ብቻ ሊያመዝን ቢችልም እያንዳንዱ ሰው የሚወስደው መልዕክት እንዳለ ያምናል፡፡



‹‹የእያዩ ሥራ ሌላ አይን የመትከል ያህል ነው፤ ታዳሚው ወደየቤቱ ሲገባ ራሱን እንዲመለከት እንፈልጋለን፤›› ይላል፡፡ የተመልካቾችን ቀልብ ለመሳብ ሲባል የሚያስቁ ሁነቶች ቢኖሩም ጠቃሚ መልዕክቶችም ተሳስረው እንደሚቀርቡ ያክላል፡፡ እያዩ እያዝናና መልዕክቱን ማስተላለፉ እንደ ገፀባህሪ እውቅና እንዲያገኝ እንዳደረገውም ያምናል፡፡

ደራሲው ከመድረክ ቆይታቸው የማይዘነጉ ከሚላቸው የእያዩ ፈንገስ መድረኮች አንደኛ ዓመት ክብረ በዓሉ ላይ የቀረበውን ይጠቅሳል፡፡ በዝግጅቱ ላይ ግሩም የ40 ደቂቃ ትዕይንት አቅርቦ ነበር፡፡ ትዕይንቱ ‹‹ፌስታሌን›› ወደሚለው የሙሉ ጊዜ ቴአትር ለመሸጋገር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ይናገራል፡፡ ሰዎች ለረዥም ደቂቃ ያለ ምንም ቴአትራዊ ግብዓት መመልከታቸው፣ ግብዓቶች ተካተውና ተራዝሞ ቢቀርብ ተመልካች እንደሚያገኝ እንዳመለከታቸው ይገልጻል፡፡

የዋን ማን ሾው አለመለመድ ቴአትሩ ተመልካች ያገኝ ይሆን የሚል ጥያቄ እንዳጫረባቸው ይናገራል፡፡ በአንድ ተዋናይ የሰውን ስሜት መንካትና ቀልብ ገዝቶ ለረዥም ጊዜ መመልከት እንዲቻል ለማድረግ ፈታኝ እንደነበረም ይገልጻል፡፡

እሱ እንደሚለው፣ አንዳንዶች እያዩን የሚረዱበት መንገድም ሌላው ችግር ነው፡፡ ‹‹እያዩን የፖለቲካ መሣሪያ አድርገው የሚወስዱ አሉ፡፡ እውነታው ግን እንደዛ አይደለም፡፡ ስለ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ሲያነሳ ፖለቲካውን ይዳስሳል፡፡ ይህ ደግሞ የተቃውሞ ጽምፅ አይደለም፤›› ይላል፡፡

እያዩ በጦቢያ ግጥምን በጃዝ መድረክ ሲቀርብ ካገኛቸው ምላሾች መካከል ጥቂቱን ይጠቅሳል፡፡ እያዩ ላይ ያተኮረ ጥናት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መሠራቱን፣ ከአዲስ አበባ ውጪ ጎንደርና ሻሸመኔ በሄደበት ወቅት የተገኘውን ምላሽና በእያዩ ስም በማኅበረሰብ ድረ ገጽ የተከፈተውን ገጽ ማንሳት ይቻላል፡፡ ቴአትሩ ስኬታማ መሆኑ ሌሎች ባለሙያዎችንም ወደ ዘርፉ የሚስብ እንደሆነ ተስፋ ያደርጋል፡፡

 

ቴአትሩን ፕሮዲውስ ያደረገው አበባው መላኩ ሲሆን፣ ማጀቢያ ሙዚቃው ላይ የተሳተፉ ባለሙያዎች አበጋዝ ክብረወርቅ ሺኦታ፣ ግሩም መዝሙር፣ ጆርጋ መስፍንና አለማየሁ ደመቀ ናቸው፡፡ ተውኔቱን ከአዲስ አበባና ከኢትዮጵያ ውጪ የማሳየት እቅድ እንዳለ በረከት ይናገራል፡፡ ቴአትሩ አንድ ተዋናይ ያለው መሆኑ ከቦታ ቦታ ለመዘዋወር እንደሚያመች ያክላል፡፡

 ‹‹ፌስታሌን›› ለጥቂት ጊዜ ከታየ በኋላ ‹‹አጀንዳዬን›› የሚል ቀጣይ ክፍል ይኖራል፡፡ ቴአትሩን በቪሲዲ የማሳተም እቅድም አለ፡፡ የእያዩ ትዕይንት በጦቢያ ግጥምን በጃዝ መድረክም ይቀጥላል፡፡ በያዝነው ሳምንት ምርቃቱን ምክንያት በማድረግ አርብና ቅዳሜ በ12 ሰዓት በአዶት ሲኒማና ቴአትር ይታያል፡፡

 ምን

https://www.ethiopianreporter.com/124596/ 

https://www.ethiopianreporter.com/53041/ 

https://amharic.voanews.com/a/ethiopia-poltical-satire-festalen/3585071.html
 
 

 

Wednesday, December 13, 2023

የኢትዮጵያን የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ እንዴት ማምጣት ይቻል ይሆን?

 የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትና የኢትዮጵያ የሥነ-ጽሑፍ ሐብት

 

አፍሪቃዉያን በተለያየ ግዜያት የሥነ-ጽሑፍ ኖቤልን አሸንፈዋል። ይህ የአፍሪቃን ብዙ ዓመታት የሥነ-ጽሑፍ ታሪክን ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ እንዲገባና ሌሎች የአፍሪቃ እንቅስቃሴዎችም በዓለም ትኩረት እንዲያገኙ ይረዳል። 

የኢትዮጵያ የሥነ-ጽሑፍ ሃብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ እንዴት ማስገባት ይቻል ይሆን?

«አፍሪቃዉያን በተለያየ ግዜያት የሥነ-ጽሑፍ ኖቤልን አሸንፈዋል። ዘንድሮም አንድ አፍሪቃዊ ተሸላሚ ተገኝቶአል። ይህ የብዙ ዓመታት የሥነ-ጽሑፍ ታሪክ ያላትን አህጉር አፍሪቃን የሥነ ጽሑፍ ሃብቷ ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ እንዲገባ እና  አፍሪቃ ከስነ-ጥበቡ ዘርፍ በተጨማሪ በሌሎችም እንቅስቃሴዎችም በዓለም ያላትን ትኩረት እንዲጎላ ያደርጋል።»  

በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት አዘጋጅ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ፤  ታንዛንያዊው የ72 ዓመቱ ደራሲ፤ አብዱልረዛቅ ጉርናህ የዘንድሮዉን የዓለም የሥነ-ጽሑፍ የኖቤል ሽልማት ማሸነፋቸዉን ተከትሎ የሰጡን አስተያየት ነበር። በየዓመቱ እንደሚደረገዉ ሁሉ፤ ባለፈዉ ሳምንት ሃሙስ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ቀትር ላይ፤ በስቶክሆልም የሚገኘዉ የስዊድኑ ንጉሣዊ የሳይንስ አካዳሚ ሕንጻ ዉስጥ የሚገኘዉ ከባድ የሚመስል ትልቅ በር፤  ስዊድናዊዉ ታዋቂ ደራሲ ማትስ ማለም ከፍተዉ የሚያነቡትን ጽሑፍ ይዘዉ፤ የድምፅ ማጉያ እና መቅረጫ ወዳለበት ቆም ብለዉ፤ ተከታዩን ለዓለም አወጁ።

«የ 2021  » የሥነ-ጽሑፍ የኖቤል ሽልማት ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ አሸንፈዋል። በዛንዚባር የወተወለዱት እና በአሁኑ ወቅት ኑሮአቸዉን እንጊሊዝ ያደረጉት ደራሲ ለሽልማት የበቁት የቅኝ ግዛት በባህልና፤ በአህጉር መካከል በስደተኛዉ እጣ ፈንታ ላይ ያሳደረዉን ጉልህ ተጽዕኖ የሚጋፈጡ ሥነ-ጽሑፎችን በማበርከታቸዉ ነዉ።»

ታንዛንያዊዉ ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ ምናልባት የሆነ ሰዉ ቀልድ ቀልዶ የሚያታልላቸዉ ስለመሰላቸዉ፤ ነገሩ ቀልድ ነዉ ብለዉ አልተታለልኩም ቢጤ ለማለት ለመልስ ተዘጋጅተዉ እየተጠባበቁ ነበር። በቴሌቭዥን ላይ ቀርበዉ ከስዊድኑ የንጉሳዊ ሳይንስ አካዳሚ የአብዱልራዛቅ ጉርናህን አሸናፊነት ለዓለም ያወጁት ስዊድናዊዉ፤ ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ  ጋር ስልክ ደዉለዉ እንኳን ደስ ያሎ የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትን አሸንፈዋል ብለዉ፤ ሲልዋቸዉ ነዉ ጥቂት እንደማመን ቢጤ የዳዳቸዉ። ከዝያም በተለያዩ የዜና ምንጮች በዜና መልክ መቅረቡን ሲሰሙ፤ እዉነት ለመናገር ይህ ጉዳይ በተለያዩ ጣብያዎች በይፋ መነገሩን እስክሰማ ድረስ ማመን ተስኖች ነበር ብለዋል።

 በሞዕራብ አፍሪቃዊትዋ ቤኒን ታዋቂ የሆነዉ ደራሲ ፍሎሪን ኩዋዞቲ ዜናዉ የአፍሪቃን የኪነ-ጥበብ ዓለም የሚያነቃቃ ነዉ። «ይህ ለመላው አፍሪቃ ኪነ-ጥበባዊ ዓለም ታላቅ ዜና ነው። ሌሎች የአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፍ ባሞያዎች የእሱን ፈለግ እንደሚከተሉ ተስፋ አደርጋለሁ። ከዚህ ቀደም የናይጀርያዉ ደራሲ፤ ቮለ ሲይንካ ይህን የስነጽሑፍ ኖኔል ሽልማት ሲሸለም ሰማን ዓመት እስኪሞላዉ በጠበቁ ይቆጨናል። የታንዛንያዊዉ ደራሲ ገና የ 20 እና 30 ዓመት እድሜ ክልል ሳለ ጀምሮ በስደት ዓለም ነዉ የሚኖረዉ። ታንዛንያዊ እንደሆነም ነዉ የሚናገረዉ።  በርካታ ጽሑፍንም አቅርቦአል። ሽልማቱን እስኪያገኝ ግን ብዙ ጊዜን ወስዶአል። የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማት ከሰሃራ በታች ካሉ አፍሪቃ ሃገራት መካከል ለሦስተኛ ደራሲ ብዙ ዓመታት ሳንጠብቅ ያገኛል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።» 

የቶጎዉ ተወላጅ እና በቶጎ በፈረንሳይኛ ሥነ-ጽሑፋቸዉ የሚታወቁት ኮሲ ኢፎይ የዛንዚባሩ ተወላጅ የዘንድዎዉን ሥነ-ጽሑፍ ማሸነፋቸዉ፤ ለአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፍ እዉነተኛ ማበረታቻ ነዉ ብለዋል። «ይህ ለአፍሪቃ አንባቢዎች መልካም ዜና ነው። ምክንያቱም አፍሪቃውያን አንባቢዎች የአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፎች ለምን በኢንጊሊዘኛ አይተረጎሙም ብለው እራሳቸውን ስለሚጠይቁ ነዉ። እንዳየነዉ ብዙ ጊዜ አይተረጎምም።  ይህ ጉዳይ በእንግሊዝኛ የሌሉ ፈረንሣይ ተናጋሪ ደራሲያን ስራዎችን ይመለከታል። ግን ደግሞ ከሁሉ በላይ በአፍሪቃ ቋንቋዎች የሚጽፉ ብዙ የአፍሪቃዉያን ድርሰቶች አልተተረጎሙም። ይህንን ሽልማት አንድ አፍሪቃዊ ደራሲ ማግኘቱ ለአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፍ እውነተኛ ማበረታቻ ነዉ ብዬ አምናለሁ» 

በጎርጎረሳዉያኑ  በ1948 ዓ.ም በታንዛንያዋ ዛንዚባር የተወለዱት ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ በ1960ዎቹ ዓመታት በስደት ወደ ብሪታንያ ከሄዱ በኋላ የከፍተኛ ትምህርታቸዉን እዝያዉ በብሪታንያ አጠናቀዉ ፤ እስከአሁኑ ጊዜ ድረስ  በኬንት ዩንቨርስቲ የእንጊሊዘኛ እና የድሕረ-ቅኝ ግዛት ዘመን ታሪክ አስተማሪ ሆነዉ በማገልገል ላይ ናቸዉ። ወጣቱ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ ወደ ብሪታንያ የተሰደዱት ከዛንዚባር አመጽ እና አብዮት ብሎም ነጻነት በኋላ፤ 21 ዓመት ሲሞላቸዉ ነበር። አብዱልራዛቅ ጉርናህ ቅን ግዛትን ጠቅሰዉ ሥነ-ጽሑፍን የጀመሩት በጣም በወጣትነት እድምያቸዉ እንደሆነ ይነገራሉ።

በሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ተሸላሚዉ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ የቀድሞውን የትውልድ አገራቸዉን ታንዛንያን ደጋግመዉ የሚጠቅሱበት እና የጀርመን እና የእንግሊዝን የቅኝ ግዛት አገዛዝ የሚያወሳ፤ አሥር ልብ ወለዶችን እና በርካታ አጫጭር ታሪኮችን አሳትመዋል። ደራሲ አብዱልራዛቅ የአፍ መፍቻ ቋንቋዋቸዉ የስዋሂሊ ቋንቋ ቢሆንም ፣ ያሳተምዋቸዉ መጽሐፍቶች ሁሉ ግን በእንግሊዝኛ ናቸዉ።

በአፍሪቃ የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትን ያገኙ አፍሪቃዉያን ከዘንድሮዉ ተሸላሚ ጋር በቁጥር ስድስት ናቸዉ።  

በ 1986 ዓ.ም ናይጀርያዊዉ ደራሲ ዎሌ ሶይንካ በጎርጎረሳዉያኑ ሽልማቱን ወስዶአል።


ዎሌ ሶይንካ _Wole Soyinka

በ 1988 ዓመት፤ ግብጻዊዉ ነጂብ ማህፉዝ ተሸላሚ ነበር።

 ነጂብ ማህፉዝ_Najib Mahfuz

በ 1991 ነጭዋ ደቡብ አፍሪቃዊት ፀሐፊ በመባል የምትታወቀዉ ናዲን ጎርድሜር የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትን ተቀብላለች።

ናዲን ጎርድሜር _Nadine Gordimer

2003  ዓመት ደቡብ አፍሪቃ የተወለደዉ ነጩ አፍሪቃዊ ጆን ማክስዌል ኮቲዝ የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ተሸላሜ ነበር።

ጆን ማክስዌል ኮቲዝ_John Maxwell Coetzee

በ 2008 ደግሚሞ የሞሪታንያ እና የፈረንሳይ ዜንግነት ያለዉ ደራሴ ጂያን ማሬ ጉስታቭ ለክለዚዮ በሥነ-ጽሑፎቹ ኖቤልን አግኝቶአል።

ጂያን ማሬ ጉስታቭ ለክለዚዮ_Jean-Marie Gustave Le Clézio

2021 በዛንዚባር የተወለዱት አብዱልራዛቅ ጉርናህ ተሸላሚ ናቸዉ።

አብዱልራዛቅ ጉርናህ_Abdulrazak Gurnah  

 

በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት አዘጋጅ፤ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ፤ ሽልማቱ ዳግም ወደ አፍሪቃ መምጣቱ ትልቅ ትርጉም እንዳለዉ ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ በጣም ግዙፍ የሆነ የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ያላት ሃገር ናት። እና ይህን የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ ለማምጣት ምን አይነት ጥረት እየተደረገ መሆኑንም በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት አዘጋጅ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ዉስጥ መጽሐፍን የማንበብ ባህል እየተበረታታ እና እየተጠናከረ መሆኑን በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ- ፅሑፍ ሽልማት አዘጋጅ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ ተናግረዋል። ነገር ግን መጽሐፍን ለማሳተም የህትመት ዋጋ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ የዘርፉን እንቅስቃሴ እንዳይጎዳዉ የሚል አስተያየትም አለ። በዚህም በህትመት አኳያ መንግሥት እርዳታ እንዲያደርግ ጥያቄ ቀርቦአል።     

በስዊድናዊዉ የኬምስትሪ ልሂቅና አዲስ ነገር ፈጣሪ በአልፍሪድ ኖቤል ስም የተሰየመዉና፤ በሞተበት በጥቅምት ወር የስዊድኑ የንጉሳዊ ሳይንስ አካዳሚ ሽልማት መስጠት የጀመረዉ ከጎርጎረሳዉያኑ 1901 ዓመት ጀምሮ እንደሆነ ጽሑፎች ያሳያሉ። በብሪታንያ ነዋሪ የሆኑት የሥነ-ጽሑፍ  ኖቤል አሸናፊ ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ በያዝነዉ የጎርጎረሳዉያን ዓመት 2021 ዓመት መጨረሻ ላይ ከንጉሳዊዉ የሳይንስ አካዳሚ፤ 10 ሚሊዮን የስዊድን ክሮን ወይም ወደ አንድ ሚሊዮን ዶላር ይቀበላሉ።

ከዛንዚባር የመጡት አብዱልራዛቅ ጉርናህ የዘንድሮዉን የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት ማግኘታቸዉን የሰሙት በካሜሩን ታዋቂዉ ደራሲ ኤጉኔ አቦዴ ለሽልማቱ አፍሪቃዉያን ልንደሰት ልንኮራ ይገባል ብለዋል። “ለዚህ ድንቅ ሽልማት እና ክብር በመብቃታቸዉ አብዱልረዛቅ ጉርናንን እንኳን ደስ አሎት እላለሁ! አፍሪቃ ስትሸለም ማየት ሁሌም ትልቅ ክብር ነው። በአፍሪቃ ከሰሜን እስከ ደቡብ ፣ ከምስራቅ እስከ ምዕራብ ያለን ሁሉ ዜጎች ሁሉ በሽልማቱ ደስተኞች መሆን አለብን!” 

የኢትዮጵያን የሥነ-ጽሑፍ ኃብት በዓለሙ መድረክ እንዲነበብ ምን እናድርግ? 

 

የኢትዮጵያን የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ እንዴት ማምጣት ይቻል ይሆን? – DW – 4 ጥቅምት 2014

የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትና የኢትዮጵያ የሥነ-ጽሑፍ ሐብት (ethiopanorama.com)



  • * Wole Soyinka (Nigeria, 1986): ...
  • * Naguib Mahfouz (Egypt, 1988): ...
  • * Nadine Gordimer (South Africa, 1991): ...
  • * John Coetzee (South Africa, 2003) ...
  • *  Abdulrazak Gurnah (Tanzania 2021)

Thursday, November 16, 2023

የምስኪኖቹን መንደር በስካቫተር ያፈረሰው ሚሊየነር

የምስኪኖቹን መንደር በስካቫተር ያፈረሰው ሚሊየነር

Chinese Millionaire Bulldozes This Village’s Run Down Huts And Builds Free Houses For Residents

በደቡባዊ ቻይና ግዛት የምትገኘው የደሳሳዋ ዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎች ፡ ሸቀጣሸቀጥ ጭነው ከሚመጡ አሮጌ ከባድ መኪኖች ውጭ አንድም መኪና ወደመንደራቸው ዘልቆ አይተው አያውቁም ። ዛሬ ግን እጅግ ዘመናዊ ፡ መርሰዲስ መኪና መጥታ ቆማለች ።

እናም ነዋሪዎች ፡ በመኪናዋ እዚህ መገኘት በመገረም ዙሪያውን ከበው በማየት ላይ እያሉ ፡ አንድ በጠባቂዎች የታጀበ እድሜው በሀምሳዎቹ የሚገመት ሰው ከመኪናው ወጣ ። ማንም ደፍሮ ሰላም ሊለው ወይም ሊያናግረው የመጣ ሰው ግን አልነበረም ። እናም ሰውየው መንደሩን ለደቂቃዎች ከተመለከተ በኋላ ተመልሶ ወደመኪናው ገብቶ ሄደ ።


ይህ በሆነ በማግስቱ ወደዛች ደሳሳ መንደር ሌላ መኪና መጣ ። ከመጡት ሰወች ውስጥ የትናንቱ ሰውዬ አልነበረም ። በቁጥር በዛ የሚሉ መሀንዲሶች ነበሩ የመጡት ። በዚህ ጊዜ ነዋሪዎቹ ነገሩ ገባቸው ፡ የትናንቱ ሰው ባለሀብት መሆኑን በሁኔታው አውቀዋል ፡ እናም ይህን መንደር ሊያፈርስ መሀንዲሶች ልኳል ።


እነዚህ ነዋሪዎች ፡ ይህም ኑሮ ሆኖ ፡ ደሳሳ ጎጇቸውን የሚያፈርስ ሰው ይመጣል ብለው መቼም አስበው አያውቁም ነበር ። እና ሽማግሌዎች ቀርበው መሀንዲሶቹን አናገሯቸው ። ፍርሀታቸው ልክ ነበር ፡ ትናንት የመጣው ባለሀብት እዚህ መንደር ላይ ሪል ስቴት መገንባት ፈልጓል ፡፡ ለዚህም ከመንግስት ፍቃድ እንዳገኘ ፡ ከሰባ በላይ ለሚሆኑት ለመንደሩ ነዋሪዎችም ካሳ እና መኖሪያ ቤት የሚገነቡበት ገንዘብ እንደሚሰጣቸው እስከዛ ግን በመጠለያ መቆየት እንደሚችሉ ፡ እስከነገ ድረስም እቃቸውን አውጥተው በተዘጋጀላቸው ማረፊያ እንዲያስቀምጡ ነግረዋቸው ሄዱ ።

ከቀናት በኋላም ፡ ብዛት ያላቸው ግሪደሮች እና የህንጻ ሰራተኞች ትንሿን መንደር አጥለቀለቋት ።

ያለቻቸውን አሮጌ እቃ አውጥተው ከቤታቸው አቅራቢያ በተዘጋጀላቸው መጠለያ ውስጥ የገቡት የዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎች ፡ ቆመው እያዩ ለዘመናት የኖሩባቸው ደሳሳ ጎጆዎች በስካቫተር ፈረሰ ።


ቃል የተገባላቸው ቤት መስሪያ ቦታም ሆነ ካሳ ሳይሰጣቸው ለወራት በመጠለያ እየተረዱ ቆዩ ። ከአመታት በፊት ከነሱ ብዙም በማይርቅ ቦታ የሚገኙ መንደሮች ልክ እንደነሱ በጨካኝ ባለሀብት ተፈናቅለው ፡ መሰደዳቸውን እያሰቡ ፡ እጣ ፈንታቸውን መጠባበቅ ጀመሩ ።

ይህ በሆነ በጥቂት ወራት ውስጥም የባለሀብቱ ዘመናዊ ቪላዎች ተገንብተው ተጠናቀቁና ፡ ነዋሪዎቹ በስነስርአቱ ላይ እንዲገኙ ፡ በፕሮግራሙም ላይ ለነሱም ቃል የተገባላቸው ካሳ እንደሚሰጥ ተነገራቸው ። ብዙዎች ነዋሪዎች ግብዣውን ተቃወሙ ።


ትንሿ የዦንኪንግ መንደር ዛሬ በልዩ ሁኔታ ደምቃለች ። ከሰባ በላይ ዘመናዊ መኖሪያዎችን ለመመረቅ የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል ። ያቺ የድሆች መንደር ፡ አይታ በማታውቀው ሁኔታ በዘመናዊ መኪኖችና በሀብታሞች ተጥለቅልቃለች ።

የምረቃው ፕሮግራም ተጀመረ ።

 

ያ ፡ በመጀመሪያ ቀን መርሰዲስ መኪና ይዞ ወደዚህ መንደር የመጣው ባለሀብት ፡ ንግግር ለማድረግ ወደ መድረኩ ወጣ ።
ክቡራንና ክቡራት የዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎችና ፡ ክቡራን እንግዶች ዛሬ ልዩ የሆነውን ይህን የዘመናዊ መኖሪያ ቤት ፕሮጀክት ለመመረቅ ስለተገኛችሁ አመሰግናለሁ ።

እኔ የማየው ዛሬ ሚሊየነር መሆኔን አይደለም ። የኔ ስብእና የኔ የሀብት ምንጭ ይሄ መንደር ነው ።. ... እኔ ..... ትንሽ ልጅ ሆኜ የምታውቁኝ Xiong Shuihua ነኝ ። 


በርግጥ ከዚህ መንደር ከወጣሁ ብዙ አመታት ተቆጥረዋልና ፡ አላወቃችሁኝም ። እኔ ግን ሁላችሁንም አስታውሳለሁ ።

ለኔና እጅግ ድሆች ለነበርነው ቤተሰቦቼ በየወሩ ቀለብ ይቆርጥልን የነበረው ሚስተር ዣይን ፡ ከልጆቻቸው እኩል ልብስ ይገዙልኝ የነበሩት የሚስ ታዮኒ ቤተሰቦች ፡ ሲርበን የሚያበሉን የዚህ መንደር ነዋሪዎች ሁላችሁንም አስታውሳለሁ ።

የኔ የአሁን ህይወት ላይ የመሰረት ድንጋይ ያስቀመጣችሁ እናንተ ናችሁ ። ለዚህም ነው መንደሩን ለመለወጥ በተሻለ ህይወት እንድትኖሩ ለማሰብ የተገኘሁት ።


 

እናም እነዚህ ቤቶች የተሰሩት ለናንተ ነው ። ያለምንም ክፍያ በነዚህ ቤቶች ትኖራላችሁ ። ቤቶቹ ንብረቶቻችሁ ናችሁ ። በነጻ የተሰጧችሁ አይደሉም ፡ ከአመታት በፊት ለኔና ለቤተሰቦቼ መልካም ነገር በማድረግ ኢንቨስት አድርጋችሁበታል ።

እያለ እንባ እየተናነቀው ሲናገር የመንደሩ ሰወች በሙሉ በታላቅ ድንጋጤ ውስጥ ሆነው ይሰሙት ነበር ።
ባለሀብቱ ንግግሩን ቀጥሏል ።


 

እናም ከሀምሳ ሚሊየን ዶላር በላይ ወጭ ተደርጎባቸው የተሰሩት ፡ እነዚህ ቤቶች በፈረሱት ቤቶቻችሁ ቁጥር ልክ የተሰሩ ናቸው ፡ ነገ አዳዲስ የቤት እቃ የጫኑ መኪኖች ይደርሳሉ ። መብራትና ውሀም አትከፍሉም ። መስራት ለምትችሉ የስራ እድል ይዘጋጃል ፡ ለአቅመ ደካሞችና ማብሰል ለማይችሉ ደግሞ ዘመናቸውን ሙሉ የሚፈልጉትን መርጠው የሚመገቡበት መመገቢያ አዳራሽም ተገንብቷል ። 

 

የናንተ ውለታ ከዚም በላይ ነው አላቸውና ፡ ከመድረኩ ወረደ ።

 

 


 

ከመጻሕፍት ዓለም - Book shelf 📗📚📖
© Wasihune Tesfaye

https://www.atchuup.com/xiong-shuihua-acts-of-kindness/

https://www.dailymail.co.uk/news/article-2850436/Millionaire-Chinese-businessman-bulldozes-run-huts-village-grew-builds-luxury-flats-residents-instead-free.html