ከደራሲያን ዓምባ

Saturday, October 25, 2025

የመጀመሪያዎቹ የኢትዮጵያ ሚኒስትሮች

 


የመጀመሪያዎቹ የኢትዮጵያ ሚኒስትሮች
(ከጥቅምት 14 ቀን 1900 ዓ.ም. እስከ ጥቅምት 14 ቀን 2018 ዓ.ም. __118 ዓመት)

በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ሚኒስትሮች የተሾሙት

ጥቅምት 14 ቀን 1900 ዓ.ም ነው ።

በዳግማዊ አጤ ምኒልክ የተሾሙት የመጀመሪያዎቹ ሰባት ሚኒስትሮች የሚከተሉት ናቸው፦

1. ኣፈንጉሥ ነሲቡ መስቀሉ...የዳኝነት ሚኒስትር
2. ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ...የጦር ሚኒስትር
3. ፀሐፌ ትእዛዝ ገብረ ሥላሴ ወልደ አረጋይ...የጽሕፈት ሚኒስትር
4. በጅሮንድ ሙሉጌታ.....የገንዘብና የጓዳ ሚኒስትር
5. ሊቀ መኳስ ከተማ.......ያገር ግዛት ሚኒስትር
6. ነጋድራስ ኃይለ ጊዮርጊስ....የንግድና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር
7. ከንቲባ ወልደ ጻዲቅ ጐሹ......የርሻና የመሥሪያ ሚኒስትር



ምኒልክ እነኚህን ሚኒስትሮች እንደሾሙ በአዲስ አበባ ያሉ የውጭ አገር መንግሥታት ተወካዮች ሹመቱን እንዲያውቁት የሚከተለውን ደብዳቤ ጻፉ ።

.....የሮፓን ፡ ሥርዓት ፡ በአገራችን ፡ በኢትዮጵያ ፡ ካሰብን ፡ ብዙ ፡ ጊዜ ፡ ነው ። እናንተም ፡ የሮፓ ፡ ሥርዓት ፡ በኢትዮጵያ ፡ ቢለመድ ፡ መልካም ፡ ነው ፡ እያላችሁ ፡ ስታመለክቱኝ ፡ ነበር ። አሁንም ፡ የእግዚአብሔር ፡ ፈቃዱ ፡ ሆኖ ፡ ለመፈፀም ፡ ቢያበቃኝ ፡ ምኒስትሮች ፡ ለመሾም ፡ ዠምሬ ። አፈንጉሥ ፡ ነሲቡን ። ፊታውራሪ ፡ አብተ ፡ ጊዮርጊስን ። ጸሐፌ ፡ ትእዛዝ ፡ገብረ ፡ ሥላሴን ። በጅሮንድ ፡ ሙሉጌታን ። ሊቀመኳስ ፡ ከተማን ። ነጋድራስ ፡ ኃይለጊዮርጊስን ። ከንቲባ ፡ ወልደጻዲቅን ፡ አድርጌአለሁና ፡ ይህንን ፡ እንድታውቁት ፡ ብዬ ፡ ነው ።

ጥቅምት ፲፬ ቀን ፲፱፻ ዓመተ ምህረት አዲስ አበባ ተጻፈ


ሚኒስትሮቹ ከተሾሙ ከ15 ቀናት በኋላ ደግሞ ለሚኒስትሮቹ መመሪያ የሚሆን ደንብ አወጡ። የወጣውንም ደንብ በሚቀጥለው ደብዳቤ ሸኚነት ለእያንዳንዱ ሚኒስትር ላኩላቸው ።


የመንግሥት ሥርዓት ባገራችን በኢትዮጵያ የሮጳ ሰው ነገሥታቱም ቆንሲል ሁሉ ገቡ። እነዚህም በኢትዮጵያ መንግሥት ሥራት ያልተለመደ ነው። ሥራት የሌለው አገር ምን መንግሥት ይባላል እያሉ አገራችን መወረፉን ታውቃላችሁ። ለመውሰድም በኛ ላይ እንደተነሱም ታውቃላችሁ።
አሁንም ምንም የቀድሞው የኢትዮጵያ ሥራት ቢኖር ከጥቂት ቀን በኋላ ቀርቷልና አገራችንን እንደ አሮጳ ሥራት ለማድረግ አስቤ ይሄንን ባንደኛ ወረቀት የተፃፈውን ደንብ ጽፌላችኋለሁና በዚሁ ባስያዝኳችሁ ሥራ ሳትጣሉ ፡ ሳትመቀኛኙ በእውነት እርስ በርሳችሁ ተስማምታችሁ ጠንክራችሁ መንግሥታችንን መርዳት ነው።
እንዲህ ሁነን በሚገባ ሥራት ሕዝባችንን ጠብቀን ከያዝነው ለመንግሥታችንና ለሀገራችን ጥቅም ይሆናል። አገራችንን ሌላ አይመኘውም። እኔም እስካሁን ብደክም ብደክም ሚኒስቴር ፡ መማክርት ፡ ቆንሲል የለበት ፡ ባንድ ሰው አሳብ ብቻ እያሉ አሙን እንጂ አላመሰገኑንም።
አሁንም እንቅልፍ ሳትወዱ ፡ መጠጥ ሳታበዙ ፡ ገንዘብን ጠልታችሁ ፡ ሰውን ወዳችሁ ፡ ተግታችሁ ይሄንን ሥራ እንድትፈፅሙልኝ ተስፋ አለኝ። ለዚህ ሥራ እኔ እናንተን አምኜ ስላደረግሁ እናንተም የምታምኑትን ፡ ገንዘብ የማይወደውን ፡ ድሃ የማይበድለውን ፡ እናንተን የሚረዳችሁን ሰው እየፈለጋችሁ እያመለከታችሁኝ ከሥራው ማግባት ያስፈልጋችኋል።
ገንዘብም ቢሆን እኔ ደሞዝ እሰጣለሁ እንጂ ከድሃ ፡ እንኳን ትልቅ ገንዘብ አንድ መሀለቅም እንኳ ቢሆን ከዚያው ከተወሰነለት ከግብሩ በቀር ሌላ እንዳይነካ ማድረግ ነው። ከዚህ ከተጻፈው ደንብ አልፋችሁ ድሃ አላግባብ የተበደለ እንደሆነ እኔም እጠላችኋለሁ። እናንተም ትዋረዳላችሁ። በነፍሳችሁም በወንጌል ፡ በመስቀል አምላችኋለሁ አስገዝታችኋለሁ።


የመጀመሪያዎቹ ሰባት ሚኒስትሮች ተሹመው ሥራ ከጀመሩ በኋላ ሥራ የሚበዛበትና አስፈላጊ የሆኑ ሚኒስቴሮች እየተከፈቱ በተጨማሪ አዛዥ መታፈሪያ የግቢ ሚኒስትር ፡ ቀኛዝማች መኰንን ተወንድ በላይ የሥራ ሚኒስትር ተብለው ተሾሙ ። የፖስታና የቴሌፎን ሥራ በዚያን ጊዜ እጅግም ያልተስፋፋ ስለነበረ በግቢ ሚኒስቴር ሥር ሆኖ የበላይ አለቃ ልጅ በየነ ይመር የፖስታ ቴሌግራፍና ቴሌፎን ሹም ተብለው ተሾሙ ።

ዳግማዊ አጤ ምኒልክ የመጀመሪያዎቹን ሚኒስትሮች ከሾሙ ከአምስት ወር በኋላ ደግሞ ለጠቅላላ ተሿሚዎቹ የሚከተለውን ደብ ዳቤ ፃፉላቸው ።

እኔ እናንተን ምንስቴርም ፥ ወንበርም መሾሜ ለመንግሥታችንና ለሕዝባችን ጥቅም እንዲሆን ነው ።አሁንም በዚህ ባስያዝኳችሁ ሥራ ሳትጣሉ ፥ ሳትመቀኛኙ እንቅልፍ ሳትወዱ መጠጥ ሳታበዙ ገንዘብ ጠልታችሁ ፡ ሰውን ወዳችሁ እርስ በርሳችሁ ተስማምታችሁ ፥ ጠንክራችሁ ፡ በውነት መንግሥ ታችንን እንድትረዱ ይሁን። በዚህም በያዛችሁት ሥራ ከእውነተኛው ነገር በቀር እገሌን አንወደውም በዚህ ነገር እንጉዳው እንዳትሉ ። ገንዘብም መተያያ ብትቀበሉ ገንዘብ ሰጥቶናል ብላችሁ ሳታደሉ ፥ በእውነት ሕዝባችንን ልትጠብቁ አምኛችኋለሁና እናንተም በዚሁ ቃል ታመኑልኝ።
ሚያዝያ ፩ ቀን ፲፱፻ ዓመተ ምህረት አዲስ አበባ ከተማ ተፃፈ "


============================

ምንጭ:- ጳውሎስ ኞኞ አጤ ሚኒሊክ

sewasew.com

Thursday, August 14, 2025

የተራራው ምርኮኞች

 የተራራው ምርኮኞች_አሳፍ ሃይሉ
 Alive : The Story of the Andes

 Survivors




"ሁላችንም ጥቂት ጥቂት የተራራ ምርኮኞች ነን!"

ይሄን መፅሐፍ የኢትዮጵያ አንባብያን "የተራራው ምርኮኞች" በሚል በሀዲስ እንግዳ አይቼህ ግሩም ተደርጎ ተተርጉሞልን አንብበነዋል። ሁልጊዜ ከሃሳቤ የማይጠፋ መፅሐፍ ነው።

በዕለተ አርብ፣ በፈረንጆቹ አቆጣጠር Friday 13 October 1972 ዓመተ ምህረት፣ የፓራጓይን የራግቢ ኳስ ተጫዋቾች ቡድን የያዘ የአየር ኃይል አውሮፕላን፣ በላቲን አሜሪካ እጅግ ግዙፉ በሆነው የአንዲዝ በበረዶ የተሸፈነ ተራራ ላይ ይከሰከሳል።

ይህ መፅሐፍ፣ ከአደጋው በህይወት የተረፉት እነዚያ ተሳፋሪዎች፣ በዚያ ከዜሮ በታች በሆነ በረዷማ ተራራ ላይ ለቀናት፣ ለሣምንታት፣ ... ብሎም ከሁለት ወራት በላይ ከበረዶ፣ ከረሃብ፣ ከጥማት፣ ከአሰቃቂ ህመምና ከሞት ጋር እየታገሉ ለመቆየት የተገደዱበትን እጅግ አስከፊ የህልውና ግብግብ የተረከ መፅሐፍ ነው።

ከታሪኩ የማይረሳኝ እነዚያ የተራራ ምርኮኞች የሚፈልጋቸውና የሚያድናቸው አካል ጠፍቶ፣ እነሱን ፍለጋ ይደረግ የነበረውም የቅኝት በረራ በተስፋ መቁረጥና በአስቸጋሪ አየር ንብረት ተቋርጦ፣ በቅርቡ እንደሰማናቸው የማሌይዢያ አየር መንገድ ተሣፋሪዎች ደብዛቸው ስለመጥፋቱ የመርዶ ዜናዎችን ዓለምና ቤተሰቦቻቸው እየተቀባበሉ እያለ፣ የሚላስ የሚቀመስ በሌለበት፣ በመጨረሻ በህይወት ለመሠንበት አንድ ነገር መወሰን ነበረባቸው።

ከመካከላቸው የበረዶውን ቅዝቃዜና ስቃይ መቋቋም ያልቻሉ ጓደኞቻቸው ሞተው፣ አስከሬናቸው በበረዶው እንደቀዘቀዘ አለ። ሁላችንም በረሃብ ከምንሞት ቀድመው የሞቱትን አስከሬን እንብላና የቻልነውን ያህል እንሰንብት፣ እስከዚያ እርዳታ ይደርስልን ይሆናል የሚል ሃሳብ ያመጣሉ።

ሃሳቡ አሰቃቂ ነው። ግን ካሉበት ነቅነቅ ለማለትም የሚበላ መቅመስ አለባቸው። መኖር፣ መትረፍ አለባቸው። ብዙዎቹ በመጨረሻ እየዘገነናቸውም ቢሆን በሃሳቡ ይስማማሉ። አልበላም የሰው ሥጋ ልሙት ብሎ ከነአቋሙ በጠኔ የሞተም አለ።

ሌሎቹ ግን የቀዘቀዙ የጓደኞቻቸውን አካል ቀስ በቀስ እየቆነጠሩ በሉ። ቀድሜ ከሞትኩ ብሉኝ የሚሉም ነበሩ ከመሐላቸው። ከፊት ሆኖ እያበረታ ይመራቸው የነበረ ጓደኛቸው በመጨረሻ አቅሙም ቅስሙም ዝሎ ወደ ወዲያኛው ሲያሸልብ፣ ቀድሞ የመነሳሳት መንፈስ ያልነበረው ሰው፣ አስገራሚ ቆራጥነትን ተላብሶ የተረፉትን አደፋፍሮ ሲመራቸው ይታያል።


በዚያ የፍጡራን ዘር ዝር በማይልበት የበረዶ ተራራ፣ 72 ቀናት ዙሪያቸውን ከከበባቸው ነጭ ሞት ጋር ታላቅ የሰርቫይቫል ግብግብ ገጥመው፣ በቃላት ሊነገር የማይችል ስቃይን ተቋቁመው፣ አሳሽ ሄሊኮፕተሮች ሊያዩአቸው ወደሚችሉበት ቦታ እያነከሱም፣ እየተሳቡም በበረዶ መሐል ተጉዘው፣ በመጨረሻ 16 ሰዎች በህይወት ተገኙ።

ዜናው ሲሰማ ዓለም ተንጫጫ። ግማሹ በአድናቆት። ግማሹ በውግዘት። በሰው ልጅ የቅርብ ዘመን ታሪክ በአንዲዝ ተራራ 72 ቀን አይደለም፣ ለአስር ቀን ብቻውን ተጥሎ ሊተርፍ የሚችህ ሰው አይታሰብምና ለብዙዎች የመትረፋቸው ዜና ተዓምር ሆነ።

አስከሬናቸው በጓደኞቻቸው የተበሉትን ተጓዦች ቤተሰቦች ሆነህ አስበኸዋል? ምን ዓይነት ሰቆቃ እንደሚሆንብህ?

ተጫዋቾቹ የጓደኞቻቸውን ሥጋ በልተው እንደተረፉ መጀመሪያ ደብቀው ነበር፣ በኋላ ያገራቸውን ጋዜጠኞች ለብቻ ጠርተው፣ በቃ እውነቱን እንንገራችሁ፣ የሆነው ይህ ነበር አሉ።

ከፈለጋችሁ ፍረዱብን፣ ማንም ህሊና ያለው ሰው በኛ ቦታ ቢሆን ማድረግ የነበረበትን ውሳኔ ወስደን አድርገነዋል። ለመትረፍ ያላየነው ስቃይ የለም። በህይወት ያለን ጓደኛችንን ለመብላት ስንል አልገደልንም። ...

ያለፍንበትን ገሃነማዊ ቆይታ ተረዱን፣ ይህ የፅናት ታሪካችን ነው። ከሰቆቃ የተረፍን ንፁህ ሰዎች ነን። ይህ በማንም ላይ እንዲደርስ አንፈልግም። ተገደን ያደረግነውን አድርገናል አሉ። የሰማ ሁሉ በድንጋጤ ተያዘ። እውነቱን ተናግረው ሀዘንና ፍቅር ግን ዘነበላቸው።

ይሄ እንግሊዛዊ ጋዜጠኛና ደራሲ፣ ተራፊዎቹን፣ ቤተሰቦቻቸውን፣ የአሳሽ ግብረሃይል አባላትንና የህክምና ቡድኖችን ሁሉ ጠይቆ፣ ተዓምራዊው ዜና በተሰማ በሁለት ዓመቱ በመፅሐፍ መልክ አተመው። የራሳችንን ጨምሮ፣ 20 በላይ ቋንቋዎች ተተርጉሞ ታሪካቸው ለዓለም ተዳረሰ። ፊልሞችም ተሠርተውበታል።

የሰው ልጅ ከማይቻል መከራ ጋር ሲጋፈጥ፣ ችሎ የሚወጣ ፅኑ ፍጥረት መሆኑን የእነዚህ ኡራጓውያን እውነተኛ ታሪክ ህያው ምስክር ሆኖ፣ ተደጋግሞ ይወሳል።

ስሱ የሚመስለው ሰው፣ የቁርጡ ቀን ሲመጣ፣ መኖሩንም የማያውቀው ተፈጥሮ በውስጡ ያኖረችው የመኖር instinct ይወጣል። ያላሰበውን ቆራጥነት ይላበሳል። ተፈጥሮ ከሰው ልጅ አቅበላይ የሆነ ችግርን አልደቀነችም። ሰው ብርቱ ነው። ፅኑ መንፈስ የሰው ልጅን በመከራዎች መሐል ያኖረው ትልቁ ፀጋው ነው።

ዛሬ በመከራ የተከበብን ሰዎች፣ በተስፋ አስቆራጭ ችግር የተያዝን ሰዎች፣ እንደ አንዴዝ ተራራ፣ ከአቅማችን በላይ የመሠለን ስቃይ ዙሪያችንን ያጠረብን ምስኪኖች፣ ችግራችን እንደ ተራራ ተከምሮ ገዝፎ የታየን፣ አትተርፉም አበቃላችሁ የተባለልን፣ ከንፈር የተመጠጠልን ሰዎች... ከእነዚህ ባለታሪኮች ምን እንማር ይሆን?

በምንም ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ብንገኝ ተስፋ አለመቁረጥን። ፅናትን። ዕምነትን። የማንቋቋመው የመከራ ተራራ እንደሌለ። ሰው በመሆናችን ብቻ አይበገሬነት በውስጣችን እንዳለ።...

ዕምነት ካለን ተራራውን ከፊታችን ነቅለን ማንሳትና መሻገር እንደምንችል። ከመከራ ፊት ቀድሞ ከመሸነፍ፣ እየታገሉ መሸነፍ ታላቅ ክብር እንደሆነ።...

እና ደሞ በሰው ቶሎ አለመፍረድን...! በሰው ቦታ ብሆን እኔስ ምን አደርግ ነበር? ብሎ ቆም ብሎ ማሰብን። ...

እና ምናልባት... የፈጣሪንም ተዓምር አለመርሳትንም የሚያስተምር ይመስለኛል ይሄ የተራራው ምርኮኞች ታሪክ።

ሁላችንምኮ የዚህን ያክል extreme የወጣ ባይሆንም፣ የየራሳችን ተራራ ያለን ነን። ሁላችንም የየራሳችንን የኑሮ ዐለት በተራራው ላይ የምንገፋ የየራሳችን ሲሲፈሶች ነን። ሁላችንም ትንሽ ትንሽ የተራራው ምርኮኞች ነን።...

ይህን አለመርሳት፣ ህይወትን እንዳመጣጧ ማስተናገድ፣ ትዕግሥት፣ ፅናት፣ ተስፋ፣ ፍቅር..! የሰው ልጅ የመከራ ቀን ማለፊያዎች፣ የደስታ ቀን ጌጦች ናቸው። Nothing is impossible! Even the sky is not the limit!😊

Live and Let Live!

ሸጋ ቀን ተመኘሁ።

*****************

Assaf Hailu Facebook page

https://web.facebook.com/photo/?fbid=24143585448603261&set=a.222487634473044