ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, January 16, 2025

በዓለ ጥምቀት በሀገረ ኢትዮጵያ

 


በዓለ ጥምቀት በሀገረ ኢትዮጵያ ፤ የወፍ በረር ቅኝት

ደመቀ ከበደ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በከፍተኛ ድምቀት በአደባባይ ከምታከብራቸው በዓላት ውስጥ በየዓመቱ ጥር 11 ቀን የሚከበረው የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት አንዱና ዋናው ነው፡፡ ይህ ታላቅ በዓል በመላዋ ኢትዮጵያ በገጠርም ሆነ በከተማ ከሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ከዋዜማው ጀምሮ ታቦታቱ በምስጋና ታጅበው ወደ ባሕረ ጥምቀት ወርደው በማደርና በመመለስ ከበዓላት ሁሉ በተለየ ድምቀት ይከበራል፡፡

ጥምቀት ቤተ ክርስቲያኒቱ ለምዕመናን ከምትፈጽማቸው ምሥጢራት አንዱና ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን ልጅነት በማግኘት የሚከብሩበት፣ ለሁሉም አማኞች የሚዳረስና የማይደገም ሲሆን መሥራቹም ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ በመሆኑ የቤተ ክርስቲያን የዕለት ከዕለት ክንውንና ዋና አገልግሎት ሆኖ መቀጠሉን ቅዱሳት መጻሕፍትን ጠቅሰው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስረዳሉ፡፡

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ጥምቀትን ውኃ ውስጥ ገብቶ መነከር፣ መዘፈቅ፣ መጠመቅ ማለት ነው ሲሉ ይተረጉሙታል፡፡

የጥምቀት በዓል ኢየሱስ ክርስቶስ በመጥምቁ ዮሐንስ እጅ በማየ ዮርዳኖስ መጠመቁን ለመዘከር የሚከበር በዓል ነዉ፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተገለጸው ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው በባህረ ዮርዳኖስ ነው፤ ይህም ተምሳሌትነት ስላለው ነው ይላል መላኩ በጥናት መፅሐፉ፡፡ "የሰው ሁሉ መገኛው አንድ አዳም እንደሆነ፥ ባህረ ዮርዳኖስም ከላይ ነቁ/መገኛው አንድ ነው፡፡ ነገር ግን ዝቅ ብሎ በደሴት ይከፈላል፤ ሕዝበ እስራኤልና አሕዛብም በግዝረትና በቁልፈት ተለያይተዋል፡፡ ባህሩ ወደታች ወረድ ብሎ እንደገና በወደብ ይገናኛል፤ ይህም ሕዝብና አሕዛብም በክርስቶስ ጥምቀት አንድ የመሆናቸው ተምሳሌት ነው፡፡"
ኢየሱስ ክርስቶስ ከመጠመቁ አንድ ቀን አስቀድሞ በዋዜማው ከገሊላ መንደር መጥምቁ ዮሐንስ እያጠመቀ በወደነበረት ወደማዕከላዊው የዮርዳኖስ ባሕር ክፍል ወርዷል፡፡ ሊቃውንቱ ኢየሱስ ወደ ዮሐንስ መሄዱ በተዋሐደው ሥጋ ትኅትናን ገንዘብ በማድረግ ለሰው ልጅ አርአያና ምሳሌ ለመሆን ነው ይላሉ፤ እንደ ጌትነቱ ዮሐንስን ‘መጥተህ አጥምቀኝ’ ቢለው ኖሮ፥ የየዘመኑ ጌቶች ካህናቱን ‘መጥታችሁ አጥምቁን’ ባሉ ነበርና 'ሄዳችሁ ተጠመቁ' ለማለት ለአብነት ነው፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ በውኃ መጠመቁም፥ ውኃ በዙፋን ካለ ንጉስ በአደባባይ እስካለ ጽንስ ለሁሉም በቀላሉ የሚገኝ ስለሆነ ነው፤ ጥምቀትም መሠራቱ ለሁሉ ነውና፡፡ ውኃ ያነፃል፥ ጥምቀትም ያነፃል፣ ውኃ የወሰደው ፍለጋ የለውም(አይገኝም)፥ በጥምቀት የተሰረየ ኃጢአትም በፍዳ አይመረመርም፣ ሸክላ ሠሪ ቢነቃባት ከስክሳ አፍርሳ መልሳ በውኃ አርሳ ትሰራዋለች፥ ጥምቀትም ተሃድሶ ነፍስ ያስገኛልና ለዚህ ነው ይላሉ ሊቃውንቱ።

በመሆኑም በዓለ ጥምቀት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ለተጠመቁ ክርስቲያኖች ሁሉ በጥምቀት በሚገኝ ዳግም ልደት የእግዚአብሔር ልጆች መሆናቸው የተረጋገጠበት ስለሆነ የዳግማዊ ልደታቸው ክብረ በዓል አድርገው በደመቀና በላቀ ሁኔታ ያከብሩታል፡፡

እግዚአብሔር ለእስራኤል ልጆች አወርሳችኋለሁ ብሎ ተስፋ ወደ ሰጣቸው ምድረ ርስት ሲጓዙ፥ በፊታቸው ያለውን የዮርዳኖስ ወንዝ በደህና ይሻገሩ ዘንድ ታቦተ ጽዮንን አስቀድመው ወንዙን እንዲያቋርጡ ትእዛዝ ሰጥቷቸው ነበር፡፡ ካህናቱ ታቦቱን ይዘው ወደ ወንዙ ሲገቡ ውኃው ለሁለት ተከፍሎ በራሱ ኃይል ተከትሮ ቆሞላቸው ሕዝቡ በቀይ ባህር እንደሆነው በደረቁ መሬት ተሻግረዋል፡፡

 የጥምቀት በዓል አከባበር ሥርዓት መነሻም ይሄው ነው፡፡ በሀገራችን ኢትዮጵያም በበዓለ ጥምቀቱ በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ያሉ ታቦታት በጣዕመ ዝማሬና በሆታ ታጅበው በባህረ ዮርዳኖስ አምሳል ወደሚዘጋጁት አብህርተ ምጥማቃት በተለምዶ ባህረ ጥምቀት ወርደው በማደርና በማግስቱ በመመለስ የሚከብሩበት በዓል ነው፡፡


የልጅነት ጥምቀት በኢትዮጵያውያን የተጀመረው በንግሥቷ ህንደኬ ጃንደረባ በ34 ዓ.ም እንደሆነ በታላቁ መጽሐፍ ቅዱስ የተመዘገበ ታሪክ ነው፡፡ የንግሥቲቱ ጃንደረባ ኢየሩሳሌምን ተሳልሞ ሲመለስ መጽሐፍ ሲያነብ ያገኘው ሐዋርያው ፊሊጶስ ስለ እግዚአብሔር ልጅነት አስተምሮት በጋዛ አጥምቆታል፡፡

 እስከ 326 ዓ.ም ድረስ ሕዝቡ በዚሁ መንገድ ሲጠመቅ የቆየ ሲሆን በ326 ዓ.ም አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን/ፍሬምናጦስ/ ከእስክንድርያው ፓትርያርክ ቅዱስ አትናትዮስ ጵጵስና ተቀብለው በመምጣት ሕዝበ ክርስቲያኑን ማጥመቅ እንደጀመሩ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ይተርካሉ፡፡

በመላኩ የጥናት መፅሐፍ እንደተገለፀው የበዓለ ጥምቀት አከባበር በኢትዮጵያ የተጀመረው የክርስትና እምነት እንደተሰበከ መሆኑ ይታመናል፤ ታቦትን ወደ ጥምቀተ ባህር ማውረድ የተጀመረው ግን በ328 ዓ.ም በጣና ቂርቆስ እንደሆነ ይነገራል፡፡

አቡነ ፍሬምናጦስ ጣና ሐይቅ ላይ ሕዝቡን ሲያጠምቁ ውጭ ላይ ሆነው የቀደሱበት የድንጋይ መንበር፣ ሴቶችና ወንዶች የቆሙበት ምልክት ወደ ደንባዛ ቁስቋም መሄጃ መንገድ ላይ እንደሚገኝ የአራቱ ጉባኤያት ሊቅ የሆኑት ሊቀ ሊቃውንት እዝራ ሐዲስ ያስረዳሉ፡፡ እስከ 6ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ ግን የጥምቀት በዓል አሁን በምናከብርበት ሁኔታ የሚከበር አልነበረም።

በዓለ ጥምቀትን በሜዳና በውኃ አካላት ዳር ማክበር የተጀመረው በዓፄ ገብረ መስቀል ዘመነ መንግስት(ከ530-544 ዓ.ም) እንደሆነ ይነገራል። ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ(ከ505-572 ዓ.ም) የደረሳቸው ዜማዎች መስፋፋት አስተዋጽኦ የነበረው ሲሆን ታቦታቱ በየዓመቱ ጥር 11 ቀን ጠዋት ወደ ወንዝ ወርደው ማታ ወደ መንበረ ክብራቸው እንዲመለሱ ይደረግ ነበር።

ጻድቁና ጠቢቡ ንጉሥ ላሊበላም(ከ1140–1180 ዓ.ም) በዘመኑ ሁሉም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለየብቻቸው በሚቀርባቸው ቦታ በተናጠል ሲፈጽሙት የነበረውን አከባበር አስቀርቶ በአንድ አካባቢ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት በአንድነት ተሰባስበው በአንድ ጥምቀተ ባሕር እንዲያከብሩ ትእዛዝ አስተላልፏል።

 ይህም ተግባራዊ በመሆኑ የበዓሉ አከባበር ሥነ ሥርዓት ቅንጅትና ድምቀት እንዲኖረው ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል። በዘመኑ በምድረ ኢትዮጵያ በብሕትውናና በስብከተ ወንጌል ተግተው ያገለገሉት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስም በትግራይና በጎጃም መርጡለማርያም አካባቢ እየተዘዋወሩ ባሕረ ጥምቀቱን ይባርኩ ነበር፡፡

ዐፄ ይኩኖ አምላክም(ከ1260-1275 ዓ.ም) በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አሳሳቢነት የተጀመረው የበዓል አከባበር ሥነ-ሥርዓት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና ታቦታቱም በሕዝብ ጥበቃና አጀብ ተደርጎላቸው በየጥምቀተ ባሕሩ እንዲያድሩ በዐዋጅ ወስነዋል።

የበዓሉ አከባበር ከጊዜ ወደ ጊዜ አድማሱን እያሰፋና ብሔራዊነትን እየያዘ መጣ። በመንፈሳዊነታቸውና በደራሲነታቸው የሚታወቁትና ብዙ መጻሕፍትን ጽፈው፣ ሥርዓትን ሠርተው ለቤተ ክርስቲያን ያበረከቱት ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ(ከ1426-1460 ዓ.ም) ታቦታቱ ወደ ወንዝ ወርደው ዕለቱን እንዳይመለሱ፣ በጥምቀት ዋዜማ ጥር 10 ቀን ከሰዓት በኋላ ወደ ባህረ ጥምቀቱ ወርደው እንዲያድሩና ሀገሩን በኪደተ እግር ይባርኩም ዘንድ በሄዱበት መንገድ እንዳይመለሱ በዐዋጅ ወሰኑ።

ይህንኑ ፈለግ የተከተሉት ዐፄ ናዖድም (ከ1486-1500 ዓ.ም) ማንኛውም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ ታቦተ ሕጉ ወደ ባህረ ጥምቀቱ በሚወርድበትና ከባህረ ጥምቀቱ ወደ ቤተ መቅደሱ በሚመለስበት ጊዜ አጅቦ አውርዶ፥ አጅቦ መመለስ እንዳለበት በዐዋጅ አስነግረው ነበር።

ሕዝቡም ታቦታተ ሕጉን በሆታና በእልልታ ከቤተ መቅደስ አጅቦ በማውጣት በባሕረ ጥምቀት ከትሞ አብሮ ማደርና ሊቃውንቱም እንዲሁ ለበዓሉ የሚስማማውን ቃለ እግዚአብሔር እያደረሱ ያድሩ ጀመር። በየጊዜው የነበሩ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እና በየዘመኑ የነገሡ ነገሥታትም አሁን ላለው ድምቀት የየራሳቸውን አሻራ ትተው አልፈዋል፡፡

ከቀደምት አበው የተላለፈውን እምነትና ሥርዓት ሳትለቅ የምትጓዘው ጥንታዊትና ሐዋርያዊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህን የጥምቀት በዓል አከባበር ትውፊት ጠብቃ በመያዝና በማዳበር በየዓመቱ ጥር 11 ቀን እያደር እየጎላና እየደመቀ በሚመጣ የአከባበር ሥርዓት በበዓሉ ዕለት የተፈጸመውን ድርጊት በኅሊና በማሰብ ብቻ ሳይወሰን የበዓሉን ጥንተ ታሪክ በሚከስት ይዘትና ሁኔታ የረቀቀውን አጉልቶ በሚያሳይ ክንውንም ጭምር ማክበሯን ቀጥላለች።

 ይህም የዓለምን ሕዝብ ዓይንና ጆሮ ወደ ሀገራችን እየሳበ የመጪው ዘመን የቱሪዝም መዳረሻነትን እየጋበዘ መጥቷል፡፡   

በጥምቀት ዋዜማ - ከተራ በመላዋ ኢትዮጵያ በከተማና በገጠር ባሉ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ታቦታት ከመንበራቸው ተነሥተው ወደ ተዘጋጀው ባሕረ ጥምቀት በመውረድ በድንኳን ውስጥ ያድራሉ፡፡ በሚያድሩበት ባህረ ጥምቀት በሚዘጋጀው ድንኳን ውስጥ ማኅሌቱ ከደረሰ በኋላ በማለዳው ሥርዓተ ቅዳሴ ተከናውኖ ባሕረ ጥምቀቱ ይባረክና ሕዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ በመጠመቅ የበዓሉን በረከት ይሳተፋል፡፡

 በዓሉ ታቦታቱ ወደ የአብያተ ክርስቲያናቱ ተመልሰው በመንበራቸው ላይ እስኪያርፉ ድረስም ከሁለት ቀን በላይ በየባሕረ ጥምቀቱና በየመንገዱ ሁሉ በድምቀት የሚከበር ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን አበው በብሉይ ዘመን ኪዳነ ኦሪቱን በዚያው ሥርዓት ሲያከብሩ የቆዩ በመሆኑ፥ በዘመነ ሐዲስም በጥምቀት ሥርዓት ተክተው የአዲስ ኪዳኑን ታቦት በተንቆጠቆጠ መጎናጸፊያ ተሸክመው በዝግታ እየተራመዱ፣ ካህናቱ የተዋበ ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ መስቀልና ጽንሐ ማዕጠንተ ወርቅ ይዘው፤ መብራት፣ ዣንጥላና ድባብ በያዙ ልዑካን ተከበው፤ በማኅሌታውያኑ ደብተራዎች ሀሌታ፣ በወጣት መዘምራን ምስጋና፣ በወንዶች ሆታና በሴቶች እልልታ ታጅበው ያከብሩታል፡፡

በመላኩ ጌታቸው ሀተታ መሰረት ሊቀ ነብያት ሙሴ የኪዳኑን ጽላት ከእግዚአብሔር ሲቀበል በሲና ተራራ ደመና ጋርዶት ነበርና ዛሬም ለታቦተ ሕጉ በደመናው ተምሳሌት ድባብ(ትልቅ ጃንጥላ) ይዘረጋል፡፡ ሕዝበ እስራኤልም ከግብጽ ወጥተው በበረሃው ወደ ምድረ ርስት ሲጓዙ የጸሐዩ ሐሩር እንዳይጎዳቸው ደመና ይጋረድላቸው ስለነበር በዚህ አብነት ሊቀውንተ ቤተ ክርስቲያን አባቶችም ክብር ስለሚገባቸው ድባብ ይዘረጋላቸዋል፡፡

ጥምቀትን የሚያጅበው ዘፈንና ጭፈራም ንጉስ ዳዊት ታቦተ ጽዮን ተረስታና ተጥላ ከነበረችበት አምጥቶ በኢየሩሳሌም ባዘጋጀላት ማረፊያ ድንኳን ሲያስገባት ልብሱን እስከመጣል ያደረሰውን ደስታውን የሚያስታውስ ነው፡፡

በጥምቀት ዘፈኑና ጨዋታውም ቢሆን ምስጋና ነው፤ በጌታ መገለጥ ለተገኘው ድኅነት ደስታን ለመግለጥ ነው፡፡ በውዳሴው የሚነሳሱትም ቤተ ክርስቲያን፣ ቅዱሳን፣ ሀገርና ጀግኖች ናቸው፡፡

የጥምቀት በዓል በመላው ኢትዮጵያና በውጭ ሀገራት ባሉ በሁሉም አህጉረ ስብከቶች እጅግ በደመቀ ሁኔታ የሚከበርና አከባበሩም አንድ ዓይነት ሃይማኖታዊና ትውፊታዊ ይዘት ያለው ቢሆንም እንደየአካባቢው ነባራዊ ሁኔታ ግን ታሪካዊና ባህላዊ መነሻ ኖሮት በተለየ የአከባበር ገጽታ በተለየ ቀለምና መልክ የሚከበርባቸው ባህረ ጥምቀቶች አሉ፡፡ 

ከእነዚህ ባህረ ጥምቀቶች በተለየ የሚጠቀሱት በጎንደር የዐፄ ፋሲል መዋኛ፣ የአዲስ አበባው ጃንሜዳ/የጃንሆይ ሜዳ፣ በሰሜን ሸዋ ደብረ ብርሃን የዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ፍርድ መስጫ አደባባይና አርባ አራት ታቦታት የሚያድሩበት የምንጃሩ ሸንኮራ ወንዝ ኢራንቡቲ፣ የቅዱስ ላሊበላ እንዲሁም በአክሱም የንግሥተ ሳባ መዋኛ የነበረው ‘ማይ ሹም’  ዋና ዋናዎቹ የነበሩ ሲሆን የባህር ዳሩ የጣና ዳርቻ፣ የዝዋይ ደሴቶች፣ የጋምቤላው የባሮ ወንዝ ዳርቻ እና ሌሎቹም ጥምቀተ ባሕሮች ቀጣይ መስሕቦችና መዳረሻዎች መደመሆኑ እየተሰናዘሩ መምጣታቸው ጥምቀት ከነበረው በላቀ ሀገራዊ ድምቀት እየተከበረ ለመምጣቱ ማሳያዎች ናቸው።

ለማሳያነትም፡-

የጥምቀት በዓል በጎንደር

በጎንደር ታቦታትን ወደ ባሕር ማውረድ የተጀመረው በቀዳሚ አድባራት ቀሃ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን እንደሆነ ይነገራል፡፡ ቀሃ ኢየሱስ ዐፄ ፋሲለደስ ጎንደርን ከመመስረታቸው በፊት በባላባቶች በቀሃ ወንዝ ዳርቻ እንደተተከለ ይነገራል፡፡ በዚሁ የቀሃ ወንዝ ዳርቻም ድንኳን እየተተከለ የጥምቀት በዓል ይከበር ነበር፡፡

በኋላም ዐፄ ፋሲል ጎንደርን መስርተው መንግሥታቸውን ካደላደሉ በኋላ 7 አብያተ ክርስቲያናትን ተክለው በቀሃ ወንዝ ዳርቻ ማክበሩን የቀጠሉበት ሲሆን ታሪኩን ለመጠበቅም በቦታው የጥምቀቱን ግንብና ታቦት ማደሪያ አስገንብተው አጽንተውታል፤ ወደ መጠመቂያው የሚገባውም ውኃ ከዚሁ ከቀሃ ወንዝ የተሳበ ነው፡፡

የጎንደር ጥምቀት ከዐፄ ፋሲለደስ ዘመን ጀምሮ በደማቁ የሚከበር በዓል ለመሆን የበቃው ዐፄ ፋሲል በበዓሉ ላይ የሚገኙትን ሊቃውንትና ምዕመናን በቤተ መንግሥታቸው ከፍተኛ ግብር ጥለው ይጋብዙ ነበርና ሕዝቡ ከሩቅና ከቅርብ እየመጣ ማክበር በመልመዱ ሲሆን በ7ቱ ምዕራፋት የሚቀርበው ቃለ እግዚአብሔር ድምቀትም ሌላው ምክንያት ነው፡፡

ሊቃውንቱ በነዚህ ምዕራፋት አገልግሎት ለመሳተፍ ከሩቅና ከቅርብ ይሰባሰባሉ፡፡ በርካታ የመንፈሳዊ ትምህርት ማስመስከሪያ ትምህርት ቤቶች በጎንደር መኖራቸውና በእነዚህም ብዙ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ መሆኑም ለበዓሉ ድምቀት የራሱ የሆነ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲኖረው አድርጓል፡፡

በተለምዶ “አርባ አራቱ ታቦት” የጎንደር መገለጫ ቢሆንም በጥምቀት በዓል ወደ ፋሲለደስ መጠመቂያ ግንብ የሚወርዱት መንበረ መንግሥት መድኃኔዓለም፣ አጣጣሚ ሚካኤል፣ እልፍኝ ጊዮርጊስና አባጃሌ ተክለ ሃይማኖት፣ ቀሃ ኢየሱስ፣ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ፣ ፊት ሚካኤልና ቅዱስ ፋሲለደስ ብቻ ናቸው፡፡

ይህም የሆነው የቦታ ጥበት እንዳይኖር በማሰብ ዐፄ ፋሲለደስና ሊቃውንቱ ተመካክረው በዓለ ጥምቀቱን ተምሳሌታዊ በሆነ መልኩ እንዲገልጽ በማድረግ ቀሃ ኢየሱስና መንበረ መንግስት መድኃኔዓለም ተጠማቂውን ኢየሱስ ክርስቶስን በማስመልከት፣ እልፍኝ ጊዮርጊስ ከሰማዕታት ወገን፣ አጣጣሚ ሚካኤልና ፊት ሚካኤል ከመላዕክት ወገን፣ አባጃሌ ተክለ ሃይማኖትና ቅዱስ ፋሲለደስ ከጻድቃን ቅዱሳን ወገን እንዲሁም አጥማቂው ደብረ ጽጌ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ በምዕመናን ታጅበው ወደ ባህረ ጥምቀቱ ይወርዳሉ፡፡

 አባጃሌ ተክለ ሃይማኖትና አጣጣሚ ሚካኤል ከዐፄ ፋሲል በኋላ በነገሡ ነገሥታት የተተከሉ ሲሆን በዘመኑ ሊቃውንት ወደ ሥርዓቱ እንደተካተቱ ይነገራል፡፡

 የጥምቀት በዓል በጃንሜዳ

በአዲስ አበባ በዓለ ጥምቀት በጃን ሜዳ መከበር የጀመረው በ1887 ዓ.ም ነው፤ “ጃን ሜዳ” ጃንሆይ ሜዳ ወይም ጃኖ ከሚለው ቃል ጋር ተናቦ የሚነገር ነው፡፡ የቀድሞ ነገሥታት ለመሾምም ሆነ ለመሻር፣ ዳኝነት ለማየት፣ ለሊቃውንቱ ማዕረግ ለመስጠት እንዲሁም አዋጅ ሲያስነግሩ በቤተ መንግሥቱ አቅራቢያ የሚገኝ ሰፊ ሜዳን ይጠቀማሉ፡፡

ይህ ሜዳ ለመንግሥታዊ አገልግሎት በመዋሉ ምክንያት ጃንሆይ ሜዳ በመባል ይጠራል፡፡ ነገሥታቱ በሜዳው ማዕከላዊ ቦታ ጃኖ(ቀይ) ድንኳን አስተክለው በመቀመጥ መኳንንቱ ከበው የተፈለገውን ሥርዓት ያከናውናሉ፡፡ በዚህም ከጃኖው ድንኳን ጋር በተያያዘም ጃን ሜዳ ይባላል፡፡

በዳግማዊ ምኒልክ ጊዜ ጃንሜዳ ከመንግሥታዊ ሥራ ይልቅ አድመኛና መሀል ሰፋሪ እየተሰበሰበ የሚዶልትበትና ነገር የሚሠራበት መሆኑ ያስቆጫቸው እቴጌ ጣይቱ ቦታው የክፉ ምክር መምከሪያ ሆኖ ከሚቀር ታቦት ማደሪያ ቢሆን ብለው ለዐፄ ምኒልክ ሃሳብ በማቅረባቸው የጥምቀት ማክበሪያ እንዲሆን በአዋጅ አጽንተውታል፡፡

ባህረ ጥምቀቱ ደግሞ በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን በ1936 ዓ.ም ተሰርቷል፡፡

 የጥምቀት በዓል በምንጃር ሸንኮራ

በሰሜን ሸዋ ምንጃር የሸንኮራ ወንዝ ዳርቻ ኢራንቡቲ 44 ታቦታት በአንድነት የሚያድሩበት ልዩ ጥምቀተ ባህር ነው፡፡ ይህ ቦታ መስቀሉን ከግብጾች የተቀበሉት ደገኛው ንጉሥ ዐፄ ዳዊት ያሠሩት ታሪካዊው በሳ ሚካኤል፣ ጥንታዊውን የባልጪ አማኑኤልና ታዋቂውን ሸንኮራ ዮሐንስን ጨምሮ የሌሎች ዕድሜ ጠገብ አድባራትን ታቦታት በአንድነት የሚያስተናግድና ዘመናትን ካስቆጠሩ ቀደምት ጥምቀተ ባሕሮች አንዱ ሲሆን ከዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ አባት ዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት መጨረሻ ጀምሮ ዘንድሮ 623ኛ ዓመቱን የጥምቀት በዓል የሚያከብር ጥንታዊ ጥምቀተ ባህር ነው፡፡

 የአካባቢው ሕዝብም ታቦታቱን በሆታና በእልልታ አጅቦ ከማክበር ጋር ያለፈ ያገደመውን በመጋበዝና በማስተናገድ ድንቅ ክርስቲያናዊና ትውፊታዊ ባህሉን የሚያሳይበት የአደባባይ በዓሉ ነው፡፡

ቀደምት አበው ይህን የሸንኮራ ወንዝ ዳርቻ ለባህረ ጥምቀትነት የመረጡበትን ምክንያት ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ማምራቱን በማሰብ ተፈጥሮአዊ ወንዝ ፍለጋ እንደሆነ የአካባቢው የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ይናገራሉ፡፡

 የሸንኮራ ወንዝ ዳርቻው ጥምቀተ ባህር፥ ወንዙ እንደ ዮርዳኖስ ከላይ ነቁ አንድ ሆኖ መሀል ላይ ለሁለት ተከፍሎ ዝቅ ብሎ የሚገናኝ፣ ውኃውም ከምዕራብ ወደ ምሥራቅ የሚፈስ መሆኑና ከመነሻው ጀምሮ የ44ቱም ታቦታት ጸበል መኖሩ ለጥምቀቱ ያለውን ተምሳሌትነት ከፍ ያደርገዋል ይላሉ፡፡

 ቦታው በዐፄ ልብነ ድንግል ዘመነ መንግሥት በሀገራችን ኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል በደመቀ ሁኔታ ከሚከበርባቸው ቦታዎች አንዱና ዋነኛው እንደነበረም ያወሳሉ፡፡ 

 የጥምቀት በዓል በላሊበላ

ቅዱስ ላሊበላ ከውቅር አብያተ ክርስቲያናቱ ጋር ባህረ ጥምቀቱንም አብሮ አንጾ ዮርዳኖስ ብሎ ሰይሞት እስካሁንም በዚህ ስም ይጠራል፡፡ የአካባቢው አባቶች እንደሚገልጹት በቀደመው ጊዜ ጥምቀተ ባሕሩ መንታ ውኃዎች ማለትም ‘ዮር’ እና ‘ዳኖስ’ የሚባሉ ወንዞች በሚገናኙበት ዮርዳኖስ በሚባል ቦታ ነበር የሚከበረው፤ ከጊዜ በኋላ ግን ቦታው በመራቁ በዕድሜ የገፉ ሰዎችም ለመሄድ እየተቸገሩ ስለመጡ ቀረብ ካለ ሜዳ ላይ ውኃ እየተከተረ ሥርዓተ ጥምቀቱ ይከናወናል፡፡

ወደ ቁራቁርና ሽንብርማ በሚወስደው መስቀለኛ መንገድ ገጠርጌ ላይ ታቦታቱ ከየመጡበት ተገናኝተው ወደ ጥምቀተ ባሕሩ ይገባሉ፡፡ ታቦታቱ ወደ ማደሪያቸው ከገቡ በኋላ የአስራ አንዱም አብያተ ክርስቲያናት ቄሰ ገበዞች ድንኳን ጥለው ባዘጋጁት ድግስ የመጣውን ሁሉ ያስተናግዳሉ፡፡

የበዓሉ ዕለት እንደሌላው አካባቢ ስብሐተ እግዚአብሔር በሰባት ምዕራፋት እየደረሰ ታቦታቱ በከፍተኛ አጀብና ድምቀት ወደመንበረ ክብራቸው ይገባሉ፡፡

 የጥምቀት በዓል በአክሱም

በአክሱም ማይ ሹም/የሹም ውኃ እየተባለ የሚጠራው ግድብ ከንግሥተ ሳባ ጊዜ ጀምሮ ለመጠጥ ውኃ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ሲሆን አክሱማውያኑም የጥምቀቱን ሥርዓት በዚሁ የውኃ ግድብ በመሰባሰብ ማክበር እንደጀመሩ ይነገራል፡፡

የጥምቀት በዓል በዝዋይ ሐይቅ ደሴት

ዓመታዊው የጥምቀት በዓል ከተከበረባቸው ቦታዎች መካከል በዝዋይ ሐይቅ ውስጥ የሚገኙት ገዳማት ይጠቀሳሉ፡፡ ከአዲስ አበባ 161 ኪሎ ሜትር ርቀት በምትገኘው ዝዋይ (ባቱ) ከተማ ዳርቻ፣ ባለው ሐይቅ የሚገኙት አቡነ ተክለሃይማኖት፣ ቅዱስ ሚካኤል፣ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም፣ አርባዕቱ እንስሳትና ፀዴቻ አቡነ አብርሃም ገዳማት ጥር 10 እና 11፣ 2009 ዓ.ም. በዓሉን አክብረዋል፡፡ ከአምስቱ ገዳማት አቡነ ተክለሃይማኖትና ደብረ ጽዮን ከደሴታቸው በመውጣት ሦስት ኪሎ ሜትር የሚሆነውን የሐይቁን ክፍል አቋርጠው ምድር ላይ በማክበር ብቸኛ ያደርጋቸዋል፡፡ የተቀሩት ሦስቱ ደግሞ ከሐይቁ ዳር በጣም የራቁ በመሆናቸው ከቤተ መቅደሳቸው በመውጣት በግቢያቸው የሐይቁ ጠርዝ ላይ ድንኳን በመጣል እዚያው ያከብራሉ፡፡



መልካም በዓል ለሚያከብሩ ሁሉ!
++++++++++++++++++

 [ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]



Tuesday, December 17, 2024

“ሕጽናዊነት”_አዳም ረታ

 የአዳም ረታ “ሕጽናዊነት” ምንድን ነው?_ዮሐንስ ገለታ

አዳም ረታ ልቦለድና ግጥም በአማርኛ የሚጽፍ ኢትዮጵያዊ ደራሲ ነው። የአዳም የአጻጻፍ ስልት ከሌሎች የሚለይባቼው የራሱ ስልት አለው።  ስሙ ህጽናዊነት(Inter-connectivity) ይባላል

ለሕትመት የበቁ የአዳም ረታ ስራዎች

  1. አባ ደፋር እና ሌሎች ታሪኮች _ 1977 ዓ.ም (“ድብድብ”፣ “ዕብዱ ሺበሺ”፣ “ሲሮኮ” እና “ሲፊንክስ”)
  2. ማሕሌት _ 1981 ዓ.ም
  3. ጭጋግና ጠል እና ሌሎች _ 1990 ዓ.ም (ዘላን)
  4. ግራጫ ቃጭሎች _ 1997 ዓ.ም
  5. አለንጋና ምስር _ 2001 ዓ.
  6. እቴሜቴ ሎሚሽታ _ 2001 ዓ.ም
  7. ከሰማይ የወረደ ፍርፍር _ 2002 ዓ.ም
  8. ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ _ 2003 ዓ.ም
  9. ሕማማትና በገና _ 2004 ዓ.ም
  10. መረቅ _ 2007 ዓ.ም
  11. የስንብት ቀለማት _2008 ዓ.ም
  12. አፍ _2010 ዓ.ም


መግቢያ

ከጥቂት ጊዜያት በፊት ፌስቡክላይ በሚገኝ የአዳም ረታ አድናቂዎች ቡድን ውስጥ አንድ ሰነድ አገኘሁ፡፡ ይሄ ከሀያ ገፆች በላይ ያለው የእንግሊዝኛ ጽሑፍ አዳም በተለያየ ጊዜ በአንባቢዎቹ ለተጠየቃቸው ጥያቄዎች ማብራሪያ የሰጠበት መድበል ነው፡፡ ፋይሉን አንብቤ እንደጨረስኩ ይሄንን ጽሑፍ ማግኘት ላልቻሉ ሰዎች ባጋራ ማንንም እንደማይጎዳ ስላመንኩበት ነው ይሄንን ጥሑፍ ማዘጋጀቴ፡፡ ዋናው ዓላማዬ ግን ሕጽናዊነት ምንድን ነው የሚለውን ትልቅ ጥያቄ በአጭሩ ለመመለስ ያደረግሁት ደፋር ሙከራ ነው፡፡
በዚህ የተነሳ የአዳምን ጽሑፍ በረጃጅሙ ወስጃለሁ፡፡ አዳም በመጻሕፍቱ ውስጥ ካስቀመጠልን ማብራሪያዎች ላይም ቀነጫጭቤያለሁ፡፡ በአጭሩ ለጋዜጣ ፅሑፍነት እንዲስማማ ማመቻቸት ስለ ነበረብኝ አንዳንድ ቦታ ላይ ብቻ ማያያዣ የሚሆኑ አረፍተ ነገሮችን፤ አንቀፆችንና ምሳሌዎችን ከማስቀመጤ በስተቀር ቀሪው የራሱ የአዳም ቃል ነው፡፡

 አዳም እና እንጀራ

እንጀራ ለአዳም የጽሑፉን ቅርፅ የሚቀዳበት ሞዴል ብቻ አይደለም፡፡ “It is more than a model. It is a metaphor” ይላል በራሱ ቃል፡፡ “ከሞዴልነት በላይ ነው፡፡ እንጀራ ተለዋጭ ዘይቤ ነው፡፡ እንጀራ ክብ ነው፡፡ ባለ ሦስት ዲሜንሽን ነው፤ ግን ደግሞ ጠፍጣፋ፡፡ ቀዳዳዎች አሉት ግን ደግሞ ልሙጥ ነው፡፡ በጠጣር እና ጠጣር ባልሆነ ቁስ መካከል የሚገኝ ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የእንጀራው ቀዳዳዎች (ዐይኖቹ ማለቴ ነው) ራሳቸውን ችለው የቆሙ ይመስላሉ፤ ሆኖም ውስጥ ውስጡን ውስብስብና ረቂቅ በሆኑ ቱቦዎች የተያያዙ ናቸው፡፡ በተቃርኖዎች የተሞላ መዋቅር ኖሮትም እንኳ እነኚሁ ተቃርኖዎቹ ‘ቀጥ ብሎ እንዲቆም’ የሚያስችሉት አላባውያኑ ሆነው ይሠራሉ” (It has a contrasting structure signified by opposites and yet all contributing to its whole physical ‘survival’).
ሕይወት ራሷ ከተቃርኖዎች ውህድ የተገመደች ነች፡፡ በዚህም እንጀራ ከሕይወት/ህልውና ጋር የተቆራኘ መሆኑን ለመጠቆም አዳም የምሳሌያዊ ንግግሮቻችንን እንደ ማስረጃ ያነሳል፡፡
እንጀራውን ጋገረ፤ እንጀራ ፈላጊ፤ የእንጀራ ገመዱ ተበጠሰ፤ እንጀራ በሬው፤ እንጀራውን ያበስላል ወዘተ፡፡ ህላዌ ቅጥ አልባና የተሰደረ ሁለቱንም ነው፤ ወይም የተሰደረ ቅጥ አልባነት፡፡ (Ordered chaos እንደማለት) አንዱ ከአንዱ የተያያዘ… እንጀራ ይህንን የህላዌን ተቃርኗዊ ግንኙነቶች የሚገልፅ ምሳሌ ነው፡፡ እኔም ይሄንን ዘይቤ ወደ አጻጻፍ ስልትነት ብለጥጠው ብዙም ከዕውነታው አልራራቅም፡፡ “Existence is both chaotic and ordered; or ordered chaos. Interconnected……Injera is used as a metaphor for describing or illustrating existence. And it is not far from the truth if I stretch this metaphor into a writing technique” ይላል አዳም፡፡

እንጀራዊ/ እንጆሪያዊ ቅርፅ

ከሕጽናዊነት በፊት እንጀራዊ/እንጆሪያዊ ቅርፅ ነበር፡፡ ሆኖም የቃላት መለዋወጥ እንጂ ጠለቅ ያለ የትርጉም ልዩነት አይታይም፡፡ ምናልባት እንጀራዊ ቅርፅ የሕጽናዊነት እርሾ ወይም ሕጽናዊነት የእንጀራዊ/እንጆሪያዊ ቅርፅ እጅግ የተጠና፤ የላቀና ምልዑ በኩልዔ የሆነ ‘ቨርሽኑ’ ነው፡፡ በ”ግራጫ ቃጭሎች” መግቢያ ላይ እንጆሪያዊ ቅርፅ እንዲህ ተብራርቷል፡ “የዚህን መጽሐፍ የአጻጻፍ ቅርፁን የተዋስኩት ከእንጀራ ቅርፅ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ያሉት ምዕራፎች ከእንጆሪው ጠቃጠቆ/ንዑስ ፍሬዎች ጋር ወይም ከእንጀራው ዐይኖች ጋር እንዲማሰሉ ሆኖ ነው የቀረበው (አንድ ዐይን ወይም ጠቃጠቆ አንድ ምዕራፍ) … ታዲያ በአሰያየም ውሰት ከእንጆሪ ወደ እንጀራ ከመጣን ለምን ከእንጀራ ወደ እንጆሪ አንሄድም? ከዚያ ወደዚህ የወሰደን መንገድ አይመልሰንም ማን አለ? ወደ መነሻው ሄድኩና ለዚህ ልብ ወለድ ቅርፅ እንጆሪ የተሰኘ ስያሜ ሰጠሁት ወይም መረጥኩ”፡፡
የእንጆሪ ቅርፅ ለሕጽናዊነት እንደ ጥንስስ ቢሆንም  ስሙን ይዞ መቆየት አይችልም (“የእንጀራ ቅርፅ” ካልተባለ በስተቀር)፡፡
አዳም በቅርቡ “መረቅ” የተሰኘው መጽሐፉ በሃገር ፍቅር ቴያትር ቤት ሲመረቅ፣ ከታዳሚያኑ መካከል በአንደኛው በቀረበለት አስተያየት መሠረት፤ እንጆሪ የሚለውን ቃል ምንም ዓይነት የቲዮሪ መፋለስ ስለማያስከትል ማውጣት እንደሚቻል ተናግሯል፡፡ (ይህ አስተያየት ሰጪ እንዳለው የእንጀራ ዓይኖች (ሰው ሠራሽ በመሆናቸው) አንዱ ከሌላው ያለው ርቀት ዘፈቃዳዊ ነው፤ የእንጆሪው ጠቃጠቆዎች ግን (ተፈጥሯዊ በመሆኑ) በስሌት ሊቀመጥ የሚችል ቅጥ አላቸው)፡፡

ከእንጀራ/እንጆሪያዊነት ወደ ሕጽናዊነት

አዳም ከእንጀራ/እንጆሪያዊ ቅርጽ ወደ ሕጽናዊነት ለመሸጋገር ወደ ትናንት ርቆ ይጓዛል፤ በንባቡና በማሰላሰሉ፡፡ “የድሮ ሰዎች እንደኛ ርቱእ (literal) አይደሉም፡፡ ከፊደል ገበታቸው እስከሚበሉት ነገር ብታይ የሆነ ዓይነት ለመፈታት የሚጠብቅ ሚስጥር አለ፡፡ እንዲህ ዓይነት ግንዛቤ ላይ ለመድረስ በሆነ ዓይነት ስነ-ውበታዊ ልምድ (aesthetic experience በሚባለው) ውስጥ አለፍኩኝ፤ ከዚያ ጊዜ በኋላ የዚያን ጠፍጣፋ ዳቦ ትርጓሜ ሳሰላስል ቆይቻለሁ”፡፡
የእንጀራን ዘፍጥረት ፀሐይ ትመለክበት ከነበረው ዘመን እንደሚነሳ ይናገራል አዳም፡፡ “እንጀራ የሚገርም ቅርፅ አለው፡፡ ዘፍጥረቱም ፀሐይ ትመለክበት ከነበረው ዘመን ይነሳል፡፡ በዚያን ዘመን ፀሐይ በክብ ምልክት ትወከል ነበር፡፡ የኛ ፊደል ፀሐዩ ‘ፀ’ የፀሐይ ወኪል ነው፡፡ ዐይኑ ‘ዐ’ም  የተባለው ፀሐይ በሰማዩ ላይ ያለች ‘ዐይን’ በመሆኗ ነበር፡፡ የእንጀራን ጉድጓዶች ‘ዐይን’ ማለታችን ገጠመኝ አይመስለኝም”፡፡
“ክብ ከጥንት ጀምሮ የሕብረት፣ የአንድነትና የዘላለማዊነት ምሳሌ ነው፡፡ መካከሉ ላይ አንድ ነጥብ ያለው ሰርከምፓንክ የሚባል ክብ ደግሞ አለ፡፡ ፀሐይን እና የፀሐይ አምላክ (ግብፅ ውስጥ “ራ” የሚባለውን) ይወክላል፡፡ (“እንጀራ” ውስጥ ያለችው “ራ” ከዚህ ጋር ግንኙነት ቢኖራትስ?) ክቡ እና ነጥቧ የወንዴና ሴቴ ኃይሎች መንፈሳዊ ውሕደት ትዕምርት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ አለም አቀፋዊ ትርጓሜ ነው” (This is a universal/cosmic sensibility)፡፡   
ታዲያስ እንጀራ ስላለፈው ዘመን እንዲዘክር በዕቅድ የተወጠነ፣ የወደፊቱንስ የሚያመላክት ጽሑፍ/ሐውልት ነው ለማለት አንችልምን? (አዳም ረታ)፡፡
ስለ እንጀራ አመጣጥ ሚቶሎጂ ደግሞ እንዲህ ያትታል…
“በአንድ አምላክ መመለክ ከመጀመሩ በፊት የኖሩ ማኅበረሰቦች ለእያንዳንዱ ፍጡር እና ባሕርይ የሚያብራሩት ትረካዎች ነበሯቸው፡፡ ኃላፊነትን ሁሉ ጠቅልለው ለአንድ አምላክ ከመስጠታቸው በፊት በነበረው በዚያን ዘመን የፍጡራን እና የፍጡራኑ ግብር በጠቅላላው በሚቶችና በአፈታሪኮች የማብራራት ልማድ ነበራቸው፡፡ ከ”አዲስ ነገር” ጋዜጣ ጋር ባደረግሁት ቃለ ምልልስ የጤፍን አመጣጥ የሚያብራራ አፈታሪክ ነገር እንደማይጠፋ ተናግሬያለሁ፡፡ (ያኔ ማግኘት አልቻልኩም ነበር እንጂ)፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት በለስ ቀንቶኝ ጤፍ እንዴት የኢትዮጵያዊያን ዋና ምግብ ሊሆን እንደቻለ የሚያብራራ አንድ ታሪክ አነበብኩ፡፡ አሁን የታሪኩን ዕውነተኛነት ጥያቄ ውስጥ አላስገባም፡፡ ሁሌም ቢሆን ሚቶችን ስናነብ የምናደርገው ስለ ዕውነተኛነታቸው መጨነቅ ሳይሆን ሚስጥራቸውን ፈልፍሎ ለማውጣት መጣር ነው፡፡ የተለያዩ ሕዝቦች ከላይ ሲታዩ እርባና ቢስ የሚመስሉ ጥያቄዎችን የሚመልሱባቸው ተረኮች እንዳሏቸው ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ ለምንድን ነው ቀበሮ ጭራ የበዛው ጅራት ያላት? ውሻ እንዴት ለማዳ ተደረገ?  ጨረቃ ለምን በየወሩ ትመጣለች? ሰው የተፈጠረው እንዴት ነው?
የጤፉ ጉዳይ ለየት የሚያደርገው የተወሰነ አመክንዮአዊ ድባብ አለው፡፡ የሆነ ሊታመን የሚችል ነገር፡፡
እንግዲህ ይሄ ታሪክ የተከሰተው ከክርስቶስ በፊት 1500 አካባቢ ነው፡፡ ክስተቱም በእውኑ ዓለም ከነበረ ሰው ጋር ተያያዥ ነው፡፡ ይሄውም ሰው ኢስዬል፣ አጋቦስ (የንግሥና ሥም) የሚባል ኢትዮጵያዊ ንጉስ ነው፡፡ (‘አፄ’ የሚለውን የማዕረግ ሥም ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀመ ንጉስ)፡፡ ሌላኛው ስሙ ሰንደቅ አላማ ይባላል (ብዙ ስሞች አሉት)፡፡ ሰንደቅ አላማ ዘንዶ ንጉስ ነበር፡፡ (ይህቺ የዘንዶ አፈታሪክ ዓለም አቀፋዊ ናት)፡፡ ከሕይወት ታሪኩ እንደምንረዳው፤ ይህ ሰው ንጉሥ ብቻ ሳይሆን ‘ሳይንቲስትም’ ነበር፡፡ ዘመሚትን፣ በቅሎን፣ የሜዳ አህያን የመሳሰሉ እንስሳትን ተያያዥነት ያላቸውን ዝርያዎች በማዳቀል እሱ እንደፈጠራቸው ይነገራል፡፡ ሰንደቅ አላማ በተፈጥሮ ላይ ይመሰጥ ስለነበር፣ የራሱ የሆነ የአትክልት ቦታ እና የእንስሳት ማቆያ ነበረው፡፡ ረዥም ዕድሜ ለመኖር የሚያስችል ቴክኖሎጂን ለመፈልሰፍ ታድሎም ነበር፡፡ በዚህም ከ425 ዓመታት በላይ መኖር ችሏል፡፡ የሚበላውና የሚጠጣው ሁሉ ከሰው የተለየ እንደነበር ይነገራል፡፡ የሚጠጣው ውሃ ከአለቶች መካከል ከሚፈልቅ ምንጭ ይቀዳል፤ ‘የሕይወት ውሃ’ ነበር የሚባለው፡፡ እያደር ወጣት የሚያደርግ ኃይል ያለው ድንጋይ ላይም ይተኛ ነበር፡፡
ሰንደቅ ዓላማ 425 ዓመታትን ከኖረ በኋላ ግን ሕይወት ሰለቸችውና መሞት ፈለገ፡፡ አንዲት ወጣት ልዣገረድ እንድትገድለውም አደረገ፡፡ አፄውን የገደለችው ይህች ወጣት ኋላ ላይ ንግሥት ማክዳ/ሳባ ሆነች፡፡ የቀደመ ስሟ ኢተያ/እትዬ/እቴጌ ነበር… ሳባ እንግዲህ ‘እቴጌ’ ተብሎ ለመጠራት የመጀመሪያዋ ንግሥት ነች፡፡
የሰንደቅ ዓላማ ታሪክ አላለቀም፡፡ እሱ ከሞተ በኋላ ሳባ ንግሥት ሆነች፡፡ በዘመነ መንግሥቷም ረሃብ በመላ አገሪቷ ተስፋፋ፡፡ የተራቡ ወገኖቿን መመገብ ያቃታት ሳባ፣ የሰንደቅ ዓላማ መቃብር ዘንድ ሄዳ አነባች፤ ፀሎት አደረሰችም፡፡
በሕልሟም እግዚአብሔር ቀርቦ በንጉሱ መቃብር ላይ ከሚበቅለው ሣር በሚገኘው ፍሬ ሕዝቧን እንድትመግብ ነገራት፡፡ እንደተነገረችው አደረገች፡፡ ያ የሣር ፍሬ ጤፍ ነበር፡፡ ‘ጤፍ’ ማለት ትርጉሙ ‘ጣፋጭ’ እና ‘የተትረፈረፈ ምርት’ ማለት ነው፡፡ ጤፍ ዝናዋ ገናን የሆነ ፍሬ ነበረች፤ ስለ እሷ በመስማት ብቻ ንጉስ ዳዊት የምወድስ ግጥም ጽፏል፡፡
ሰንደቅ ዓላማ ባዮሎጂስት የነበረ መሆኑ የጤፍ ግኝት የአጋጣሚ ነገር አይመስልም… ምናልባትም ንጉሱ ራሱ ይሆን ይሆናል መጀመሪያም ጤፍን ያገኘው፤ የማክዳ ተረት ነጋሪዎች ይሆናሉ የፀሎቷን፣ ሕዝብ የመመገቧንና የእግዜርን ነገር ያከሉበት፡፡ እንደው ነገሩ እንዲህ እንኳ ባይሆን፣ ጤፍ እንዲህ ባለ ንጉስ መቃብር ላይ መብቀሏ በራሱ እየሞተ ካለ የንጉሱ ገላ ረዥም ዕድሜ የመኖር ምስጢርን እየወረሰች ይመስልባታል”፡፡
እንዲህ እንዲህ እያለች የተጀመረችው ጤፍ እንግዲህ ረዥም ዕድሜ መቆየት ብቻ ሳይሆን እንጀራ  በመሆን ዘላለማዊ ሆናለች፡፡ አዳምም እንጀራ ምግብ ብቻ ሳይሆን፤ እንጀራ የአጻጻፍ ስልቴን የቀዳሁበት ሞዴል ብቻ ሳይሆን፤ እንጀራ ዘይቤ ብቻ ሳይሆን እናት ዘይቤም (root metaphor) ነው ይላል፡፡
“እናት ዘይቤ ማለት…” ይላል አዳም “እናት ዘይቤ ማለት በአንድ ቋንቋ ወይም ባሕል ውስጥ በጥልቅ በመስረጉ ዘይቤ መሆኑ ከነጭራሹ ልብ እንኳ የማይባል ነው፡፡ ሌሎች ሰዎች ደግሞ ከውስጡ ሌሎች ዘይቤዎች የሚወጡበት አንድ ዘይቤ ነው ሲሉ ይተረጉሙታል”፡፡ መቸስ እንጀራ ከዕለት ዕለት ተግተን የምናላምጠው ቋሚ ምግባችን እንደመሆኑ እንደ አዳም ቀንቶን “በሆነ ዓይነት ስነ-ውበታዊ ልምድ” ውስጥ ካላለፍን በቀር አንድም ጊዜ እንኳን አይደለም ሚስጥራዊ ዘይቤነቱ አመጣጡ እንኳን አስጨንቆን አያውቅም፡፡ ለዚህም ነው እንጀራ እናት ዘይቤ (root metaphor) ነው የሚለው አዳም፡፡
አዳም ይቀጥላል… “የማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ታሪካዊ ዝርዝር ጉዳዮቻችንን በዚህ የእንጀራ ዘይቤ ማብራራት እንችላለን ብዬ አምናለሁ፡፡ ይሄን የምናደርግበት አንዱ መስክ ልቦለድ በመጻፍ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት እየሠራሁበት ያለውን ይሄ ዓይነቱን አጻጻፍ ደግሞ ‘ሕጽናዊነት’ እለዋለሁ”፡፡

“ሕጽናዊነት”፡ የቃሉ አፈጣጠር/አመጣጥ

ሕጽናዊነት እና ዘይቤ ምን አገናኘው ብሎ የሚጠይቅ ይኖር ይሆናል፡፡ ‘ሕጽን’ የግዕዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም በሁለት ፊደሎች መካከል ያለው ክፍተት ማለት ነው፡፡ ጽሑፍ ሊነበብ የሚችለው ይሄ ባዶ ቦታ በየፊደላቱ መካከል በመኖሩ ምክንያት ነው፡፡ በፊደል ገበታ ውስጥ ያሉት ክፍት ቦታዎች ደግሞ ማሕጸን ይሰኛሉ፡፡
ሁለቱም ቃላት የተወሰነ የትርጉም መመሳሰል አላቸው፡፡ እነኚህ ባዶ ቦታዎች ከእንጀራ ዐይን ጋር በይዘት መመሳሰል እንዳለባቸው ነው የሚገባኝ፡፡ የሕጽናዊነት ዓላማ ይሄንን ባዶ ቦታ መሙላት ነው፡፡ የሚነበበው ነገር መሙያው ነው፤ አዲሱ ጽሑፍ ማለት ነው፡፡ ከ”አዲስ ነገር” ጋዜጣ ጋር ባደረግሁት ቃለ ምልልስ ይሄንን ነገር ‘ኢንተርቴክስቹዋሊቲ’ ብዬ አስቀምጬው ነበር፡፡ ይሄን ያደረግኩት ግን በወቅቱ ሕጽናዊነትን የሚያክል ተስማሚ ቃል ባለማግኘቴ ነበር፡፡
ገሃዱን ዓለም በማንፀባረቅ ረገድ አንድ ወጥ የሆነ ትረካ ሕጽናዊ ከሆነው ይሻላል ወይስ አይሻልም የሚለው ጥያቄም ነበር፡፡ ከ”እቴሜቴ ሎሚ ሽታ” [እ.ሎ.ሽ.] በፊት የጻፍኳቸውን ታሪኮች አሁን ላይ ሆኜ ሳያቸው የተሟሉ አይደሉም፡፡ ሕጽናዊነት በዚህ ረገድ የቀድሞ እኔነቴን በራሴ የለካሁበት/የሄስኩበት ስልት ነው፡፡ (“Hisinawinet” in this case becomes a critique of my earlier self)
ሕጽናዊነት የአንዱ ከሌላው መያያዝ ነው… ራሳቸውን እንደ ደሴት የሚቆጥሩ ሰዎች አሉ፡፡ ከላይ ሲታይ የተለዩ ይመስሉ ይሆናል፤ በጥልቅ ላጠናቸው ግን ሰዎች እርስ በራስ የተጠላለፉ/የተቆራኙ/የተዛመዱ ናቸው… በዘር፣ በቋንቋ፣ እልፍ የባሕል እሴቶችን በመጋራትም”፡፡ ሰዎች ከሰዎች ጋር ያላቸውን መረባዊ ግንኙነት ማሳየት የሕጽናዊነት አንዱ ግብ መሆኑ በአዲሱ መጽሐፍ “መረቅ” ውስጥ እንዲህ ተቀምጧል፡ “በሕጽናዊነት አመለካከት በሰው ልጆች መሃል ያለው የግንኙነት መስመር ቀጥተኛ ብቻ ሳይሆን በአብዛኛው በግልጽም ይሁን በሕቡዕ መረባዊ መሆኑን ማንሳት ነው” (ገጽ 599)፡፡
አዳም ቀጥሏል… “የሕዳግ ማስታወሻ የሚያገለግለው እነኚህን መረባዊ ግንኙነቶች ጠቅልሎ በአንድ ማዕቀፍ ውስጥ ለማካተት ነው፡፡ በእ.ሎ.ሽ. ከበደ ሚካኤልን ሳጣቅስ የእሳቸውን ፖለቲካዊ አቋም እደግፋለሁ ማለት አይደለም ወይም ደግሞ ባሕልን እንደሳቸው ሁሉ በወግ አጥባቂ ዐይን እቃኛለሁ ማለት አይደለም፤ ወይም ደግሞ የእሳቸውን ያክል መልከ መልካም ነኝ ማለት አይደለም፤ ወይም ደግሞ ሎሚ ሽታን ወይም የፍቅረስላሴን ልጅ ታደሠን ያውቁታል ማለት አይደለም ወዘተ…  የባሕል መረቡ በቀስታ ተስፋፍቶ እዚያች ደረጃ ድረስ እንዴት እንደሚደርስ ለማሳየት ብቻ ነው፡፡ (showing how cultural network can percolate and present itself to that minute depth)
ታዲያ ከሌላ ደራሲ ሥራ የተወሰደን አጭር ተረክ በአንድ ወጥ በሆነ ልቦለድ ውስጥ መጠቀም አዲሱን ታሪክ የፊተኛው ጥገኛ፤ በራሱ መቆም የማይችል፤ ክፍተት ያለበት አያደርገውም? ብሎ ለሚጠይቅ ቅን አንባቢ፣ አዳም ይሄንን ይመልሳል… “እቴሜቴ ውስጥ ያካተትኩትን ያን የከበደ ሚካኤልን ተረት [በማር ጠብታ ውስጥ ስለሰጠሙ ሕዝቦች የሚተርከውን] ቆርጬ ባወጣው እንኳ ልቦለዴ ያለምንም የይዘትም ሆነ የሴራ እንከን ፍሰቱን ይቀጥላል”፡፡

አንዳንድ የሕጽናዊነት መገለጫዎች

ከሕጽናዊነት መገለጫዎች አንዱ ኢንተርቴክስቹዋሊቲ ነው፡፡ ኢንተርቴክስቹዋሊቲ ማለት በቀላሉ በአንድ ትረካ ውስጥ ሌላ ገጠመኝ፣ ሌላ ልቦለድ፣ የታሪክ አጋጣሚ ወዘተ ሲጠቀስ ማለት ነው፡፡ የዚሁ ትርጓሜ ተመሳሳይ የሆነው ኢንትራቴክስቹዋሊቲም መነሳት ይኖርበታል፡፡ የሁለቱ ልዩነት በአጭሩ ሲቀመጥ፤ የመጀመሪያው አንድ ደራሲ  የሌላን ደራሲ/ገጣሚ ሥራ (የዕውንም ይሁን ምናባዊ)፤ ከዕውነታው ዓለም የተቀዳ ገጠመኝ፤ የጋዜጣ ጽሑፍ ወዘተ ሲጠቀም ሲሆን ሁለተኛው ድሞ አንድ ደራሲ የራሱን ቀደምት ሥራዎች ሲያጣቅስ ማለት ነው፡፡
“ብዙ የተማረ ዜጋ/ብዙ ያነበበ ዜጋ ባላቸው አገሮች ዋቤ ሳይጠቅሱ (የዕውነት ያለን) ጽሑፍ ማጣቀስ የተለመደ ነው፡፡ ምክንያቱም ያ ጽሑፍ የሌላ ሰው እንደሆነ ይሄኛው ደራሲ ግን እንደ ወሽመጥ እየተጠቀመው ወይ ደሞ እየተረበው እንደሆነ አንባቢው ያውቃል፡፡
በእኛ አገር ግን አለመግባባትን ለማስወገድ በሕዳግ ማስታወሻ መጠቆም ያስፈልጋል፡፡ አለመግባባቱም ሁለት ዓይነት መልክ ሊኖረው ይችላል፡
አንደኛው አንዳንድ አንባቢ (በቅን ልቦናም ይሁን በተንኮል) ያ የተወሰደው ጽሑፍ የተሰረቀ ነው ብሎ ሊያስብ ስለሚችል ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ አንባቢው የተጣቀሰው ጽሑፍ ዓላማ ላይገባው ስለሚችል ነው፡፡ አንባቢው ይሄን መረዳት ካልቻለ ደግሞ አንዱ የኢንተርቴክስቹዋሊቲ ግብ ልቦለድን ወደ ዕውነታዊ ክዋኔ ማምጣት (bring fiction as experience) ተኮላሸ ማለት ነው”፡፡
ከላይ የተጠቀሰውን በምሳሌ እንመልከት፡፡ ደራሲው በእ.ሎ.ሽ. “በማር ጠብታ ውስጥ ስለሰጠሙ ሕዝቦች አንብቤያለሁ” ሲል በሕዳግ ማስታወሻ የከበደ ሚካኤል ታሪክ እንደሆነ ገልፆዋል፡፡ በ”መረቅ”ም “ግቡ እናንተ ተስፋ ያልቆረጣችሁ” (ገጽ 73) ሲል ከዳንቴ “ዲቫይን ኮሜዲ” እንደወሰደው ጠቅሷል፡፡ በሌላ መልኩ ማንም ያነበበው፤ አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ታሪክ ነው ብሎ በማሰብ፤ ማንም “ባለ ቅን ልቦና” ወይ “ሴረኛ” የተሠረቀ (plagiarized)  ነው እንደማይለው በማመን፤ እንዲሁም ልቦለድን ወደ ዕውነታዊ ክዋኔ ለማምጣት (to bring fiction as experience) የፊታውራሪ መሸሻን፤ የሰብለን፣ የበዛብህን እንዲሁም የእንቆጳን ታሪክ (አንዳንድ ለውጦች ተደርገውባቸው) እንዲሁ በ”መረቅ” ውስጥ ተጠቅሟቸዋል፡፡
አዳም ከቲዮሪ ባሻገር በሥራዎቹ ኢንተርቴክስቹዋሊቲን ብቻ ሳይሆን ኢንትራቴክስቹዋሊቲንም ይጠቀማል፡፡ በየመጽሐፎቹ ውስጥ እዚህም እዚያም የሚገኙት የግጥምና የዘፈን ስንኞች፤ ቦታቸውን እንዳገኙ ሁሉ ስክት የሚሉት የግዕዝ ሀረጋት፤ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች፤ ምናባዊ ማጣቀሻ መጻሕፍቱ እና የጋዜጣና የመጽሔት ቃለ ምልልሶች ወዘተ የኢንተርቴክስቹዋሊቲ አብነቶች ናቸው፡፡ በሌላ መልኩ በአዳም ልዩ ልዩ መጻሕፍት መካከል እንዲሁም በአንድ የአዳም መጽሐፍ ውስጥ በሚገኙ ልዩ ልዩ ትረካዎች መካከል ያሉ እንደ ዘሀ የቀጠኑ የግንኙነት መስመሮች የኢንትራቴክስቹዋሊቲ ማሳያዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ በ”ሕማማት እና በገና” ውስጥ ያለው ትንሽ ልጅ (የብርሃኑ ጓደኛ) “አለሙ” የተሰኘ የቤት ስም አለው፡፡ “ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገድ” (ይ.መ.ያ.መ.) ላይ ያለው ዋና ገፀ ባሕሪ “አለሙ” ይሰኛል፡፡


ሁለቱም የሸማኔ ልጆች መሆናቸው የአጋጣሚ ነገር ይመስላችኋል? በ”መረቅ” ውስጥ በጨረፍታ ዳሰስ የተደረገችው ሊሊና የዚታዎ ሾፌር የሆኑት ጓደኛዋ ዘርአብሩክ በኩሳንኩስ ውስጥ አንድ የታሪክ አንጓ ተሰጥቷቸው አልተተረኩምን? የ”ይወስዳል መንገድ ያመጣል መንገዱ” ሸገኔ “መረቅ” ውስጥ ተጠቅሶ የለምን? እ.ሎ.ሽ. “ጉርሻ ተሻጋሪ ነው” በምትል ቀጭን መስመር ከ”መረቅ” አልተዛመደም? በይ.መ.ያ.መ. በእያንዳንዱ ትረካ ላይ ብቅ የሚለው ያ ጃን አሞራ በታሪኮቹ መካከል ትስስር አልፈጠረም? በእ.ሎ.ሽ. ውስጥ የሚገኙ ታሪኮችስ አንዳቸው ከሌላቸው በገጸ ባህርያቱ የትውውቅ  እና የዝምድና መረብ የተጠላለፉ አይደሉ? “ከሰማይ የወረደ ፍርፍር” ውስጥ “ለብሮት” የሚለው ታሪክ ገጸ ባሕሪ ትርንጎ፤ በ”ሕማማት እና በገና” “የሳር ልጆች” ውስጥ ተመልሳ አልመጣችም? ብዙ ብዙ፡፡ ይሄ እንግዲህ በእኔ አቅም ሊታይ የቻለ ትስስር ነው፤ ጊዜውን ሰጥቶ በጥልቀትና በጥንቃቄ ለሚያጠናው ሰው ከዚህም በላይ ግንኙነቶችን መጥቀስ እንደሚቻል እርግጠኛ ነኝ፡፡



Thursday, November 28, 2024

'ነገም ሌላ ቀን ነው' _ነብይ መኮንን

 

                                                       Margaret Mitchell _Gone with the Wind 

ነብይ መኮንንን በብዙ ነገሮች እናስታውሰዋለን። ከ20 አመታት በላይ የተወዳጁ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነበር። ለጋዜጠኝነት ስልጠና ወደ ሰሜን አሜሪካ አቅንቶ ለጥቂት ወራት በከረመበት ወቅት በዚያ የሚኖሩ የኢትዮጵያውያንን ኑሮ ተነቦ በማይጠገብ ለዛ በመጀመሪያ በዚያው በአዲስ አድማስ ጋዜጣ አምድ፣ በኋላ ደግሞ ተሰብስቦ በአንድ መጽሐፍ የእኛ ሰው በአሜሪካ በሚል ርእስ አቅርቧል። በሁለት የስውር ስፌት ግጥም መድብሎችና በሌሎችም ጥልቅ መልእክት ያላቸው ውብ ግጥሞቹን አስነብቦናል። አበበ ባልቻ፣ ፈቃዱ ተክለማርያም፣ ፍቅርተ ጌታሁን እንዲሁም ራሱ አነስተኛ ሚና ይዞ የተወነበትን እጅግ ተወዳጅ የቴሌቪዥን ድራማ "ባለጉዳይ"ን ጽፏል። ከመአዛ ብሩ ጋር በሸገር ጨዋታ ለ14 ሳምንታት የዘለቀ ተሰምቶ የማይሰለች ውብ ጨዋታ ተጫውተዋል።

እኔ ግን ነብይ መኮንን ሲባል መጀመሪያ ትዝ የሚለኝ የማርጋሬት ሚሸል Gone With the Wind 'ነገም ሌላ ቀን ነው' ነው—በብዙ ምክንያቶች። በመጀመሪያ ነብይ መኮንን የሚለውን ስም ለመጀመሪያ ግዜ የሰማሁት/ያነበብኩት ከዚህ መጽሐፍ ትርጉም ሽፋን ነው። First impressions are powerful ይባል የለ። መጽሀፉ የተተረጎመበት አጋጣሚ በራሱ epic/ድንቅ የሚባል ነው። በእርግጥ ነብይ እራሱ እንደነገረን መጽሀፉን ለመተርጎም የተነሳሳው በኢህአፓነት ማእከላዊ ለ10 አመት ታስሮ በነበረበት ወቅት ነበር። በግዜው ለማእከላዊ እስረኞች መጽሐፍ አይገባም፣ አይፈቀድም። ወረቀትና ብእር ጨምሮ። እስረኞቹ የፖለቲካ ስለሆኑ ፖለቲካዊ አመለካከታቸውን እንዲያዳብሩ ወይም እንዲያስተላልፉ አይፈለግም። የታሰረው አካላቸው ብቻ አልነበረም። አእምሮና መንፈሳቸው ጭምር እንጂ።
ታዲያ ነብይ ይህንን ድንቅ መጽሀፍ እንዴት ለመተርጎም በቃ? ነገሩ አጋጣሚ ይመስላል ግን አጋጣሚ አልነበረም። በግዜው በእስርቤቱ ውስጥ ነብይ ሊያገኝ የቻለው መጽሐፍ የማርጋሬት ሚሸል Gone With the Wind ብቻ ነበር። ይህም የሆነው አንድ ሌላ እስረኛ ወደ እስር ቤት ሲወሰድ በአጋጣሚ በኪሱ ይህንን መጽሀፍ ይዞ ነበር። ነገር ግን በዚህ አለም አጋጣሚ ብሎ ነገር የለም። "There are no accidents" ይላሉ ብልሁ ኤሊ ማስተር ኡግዌይ። ይህ መጽሐፍ ማእከላዊ እስር ቤት በዚያ ወቅት በነብይ መዳፎች ስር የወደቀው በፍጹም በአጋጣሚ አይደለም። አጋጣሚ ይመስላል ግን አይደለም።
በመጀመሪያ መጽሐፉ ስለ አሜሪካ የእርስበእርስ ጦርነት ነው። ኢትዮጵያም በዚያ ወቅት ከአሜሪካው የእርስበርስ ጦርነት መቶ ምናምን አመት በኋላ በአሰቃቂ የእርስበእርስ ጦርነት እየማቀቀች ነበር። የማይመስል አጋጣሚ አንድ። ሁለተኛ መጽሐፉ በአሜሪካ የእርስበእርስ ጦርነት አሳብቦ ለሁሉም የሰው ልጆች ትርጉም ስለሚሰጠው ስለ አይበገሬው የሰው ልጆች ጠንካራ መንፈስ ነው። በተለይ ማእከላዊ ለ10 አመታት ታስሮ ለሚማቅቅ ሰው የበለጠ ትርጉም ይሰጣል። የመጽሐፉ አብይ ጉዳይ የአንድ ሃገር ጦርነት ቢሆንም የትም፣ መቼም ላለ ሰው ጥልቅ መልእክት አለው። ደግሞም የላቀ የአማርኛና የእንግሊዝኛ እውቀት ያለው ሰው በዚያ እስር ቤት መገኘቱ መጽሐፉ በዚህ ሁኔታ መተርጎሙ ከአጋጣሚ እጅግ ያርቀዋል።
እኛ ሰዎች ነን። እውቀታችን በግዜ፣ በቦታ፣ በሁኔታ የተወሰነ ነው። ከምናውቀው የማናውቀው ይበልጣል። እናም በዚህ ውስንነታችን የተነሳ የመጽሐፉ በነቢይ መተርጎም ተራ አጋጣሚ ይመስለናል። አይደለም። ከዚህ በተጨማሪ ሌሎች አስደናቂ ነገሮችም አሉ በመጽሐፉ አተረጓጎም ዙሪያ። ለትርጉም ስራ የሚያስፈልጉት ወረቀትና እስክሪፕቶ ወደ እስር ቤቱ እንዲገቡ አይፈቀድም። ነብይ የነበረው ብቸኛ አማራጭ የሲጋራ ፓኬት ውስጥ የሚገኘውን የአልሙኒየም ወረቀት መጠቀም ነበረበት። ነብይ ይህንን መጽሐፍ ተርጉሞ ለመጨረስ 3000 የሲጋራ የአልሙኒየም ወረቀት ፈጅቷል። ይህ ብቻ አይደለም። መጽሀፉ የሚተረጎመው በድብቅ ነው። ከእስር ቤቱ ተበታትኖ የሚወጣውም በድብቅ ነው። ወረቀቱን ተከፋፍለው ይዘው የሚወጡት የመፈቻ ግዜያቸው የደረሰ እስረኞች ነበሩ። ታዲያ እስረኞቹ ተፈትተው አንዱ ወለጋ፣ አንዱ ጅማ፣ አንዱ ባሌ ይሆናል የሚሄዱት። ታዲያ ለነብይ ፈተና ከሆነበት ጉዳይ አንዱ የእስር ግዜውን ጨርሶ ሲወጣ የተበታተነውን ወረቀት ለማሰባሰብ ወደ ብዙ የኢትዮጵያ ክፍሎች መጓዝ ነበረበት። ወረቀቱን በስርአቱ አስቀምጠው የጠበቁት እንደነበሩ ሁሉ በእንዝህላልነት የጠፋባቸውም ነበሩ። ብዙ መከራ ያየ መጽሐፍ ነው—ለመተርጎም፣ ለመሰብሰብ፣ ለመታተም።
ብቻ ያ ሁሉ መከራ ታልፎ መጽሀፉ በ1982 ታተመ። በነገራችን ላይ መጽሐፉ ሁለት ቅጽ ነው ያለው። ሙሉ መጽሀፉ ከ1000 ገጽ በላይ ነው ያለው። ያኔ የታተመው ግን ግማሹ ወይም አንዱ ቅጽ ብቻ ነበር። ምክንያቱም ከሺ በላይ ገጾች ያሉትን መጽሐፍ ማሳተም ከህትመት ወጪ አንጻር አዋጭ ስላልነበር ነው። እኔም ለመጀመሪያ ግዜ ያነበብኩት ይህንኑ አንዱን ቅጽ ብቻ ነበር። በእርግጥ የመጽሐፉ የመጀመሪያው ቅጽ ከሁለተኛው ይልቅ ስነጽሁፋዊ ለዛው ይልቃል። የመጀመሪያው ቅጽ ስለ እርስበእርስ ጦርነቱ ሲሆን፣ ሁለተኛው ቅጽ ከእርስበእርስ ጦርነቱ በኋላ ደቡባውያን ስለሚያሳልፉት ፍዳና ሃገራቸውን መልሰው ለመገንባት ስለሚያደርጉት ጥረት ነው። የህትመት ዋጋ አሁን የበለጠ ንሯል። ነገር ግን ነብይ ሙሉውን መጽሐፍ ስለተረጎመው ወራሾቹ ሁለተኛውን ቅጽም ለብቻው ቢያሳትሙት ጥሩ ነው።
ነብይ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሳለ የአንድ ዝነኛ የአሜሪካ ጋዜጣ — The Guardian ይመስለኛል — ጋዜጠኛ የነብይን ታሪክ ሰምታ ተደነቀች። ተደንቃ ብቻ አልቀረችም ነብይን ለማናገር አዲሳባ ድረስ መጣች። በእርግጥ አስደማሚ ታሪክ ነው። በመጀመሪያ Gone With the Wind አሜሪካኖች ትልቅ ቦታ የሚሰጡት የስነጽሁፍ ስራ ነው። ሃገራቸውን ለሁለት ሊከፍል የነበረ ወሳኝ የታሪክ አጋጣሚ ነው። አሜሪካውያን ምንግዜም ምርጥ ፕሬዚዳንታችን ነው የሚሉት አብርሃም ሊንከን የዚህ የታሪክ አጋጣሚ አብይ ምክንያትና ውጤት ነው። ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል ደግሞ ታሪኩን በተባ ብእሯ ዘለአለማዊ አድርጋዋለች። አሜሪካንን አፍርሶ እንደ አዲስ አስበልጦ የሰራ ጦርነት ነው። ይቺ ደራሲ ጋዜጠኛ ነበረች። ባጋጠማት የጀርባ ህመም ከቤት ዋለች። ግን ስራ አልፈታችም። አስር አመት ፈጅታ ይህንን ውብ ልብወለድ አብስላ ጻፈች። እዚህ እኛ ሃገር ደግሞ ነብይ መኮንን የተባለ ጀግና ተርጓሚ እንደሷ 10 አመታት ፈጅቶ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ተረጎመው። ይቺ የዘ ጋርዲያን ጋዜጠኛ አዲስአበባ ድረስ መጥታ ነብይን አናግራ ቆንጆ መጣጥፍ ጽፋላታለች።
¤¤¤
ሬት በትለር እስካርሌት ኦሃራን አፈቀረ። እስካርሌት አሽሌ ዊክስን ፈቀደች። አሽሌ ሜላኒ ሃሚልተንን አገባ። የአራት ሰዎች የፍቅር ህይወት ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ ሆነ።
ግዜው 1860 ነው። ሬት በትለር 35 አመት ሞልቶታል። የእርስ በእርስ ጦርነቱ ሊጀምር ነው። ሁለቱም ወገኖች የጦርነት ድቤ እየደለቁ ነው። ደቡባውያኑ ሰፋፊ የጥጥ እርሻ ያላቸው ሃብታሞች ናቸው። እርሻው የሚለማው በባሮች ጉልበት ነው። ሰሜናውያኑ በበኩላቸው ባርነትን አጥፍተው ህገወጥ አድርገውታል። በምትኩ ትላልቅ ኢንደስትሪዎችን ተክለዋል።
አብርሃም ሊንከን ለፕሬዚዳንት ሲወዳደር ከተመረጠ ባርነትን ከመላው አሜሪካ እንደሚያጠፋ ቃል ገባ። ምርጫውን ሲያሸንፍ የገባውን ቃልኪዳን ለመጠበቅ ስራውን ጀመረ። አንድ ሃገር በሁለት የተለያየ ስርአት መተዳደር እንደሌለባቸው አወጀ። ይኼኔ ሁለቱም ወገኖች ተቆጡ።
ደቡባውያኑ ያላቸው አንድ ነገር ሰፋፊ እርሻ ነው። ባርነት ከተወገደ እርሻቸውን ማን ያለማላቸዋል? በባሮች ትከሻ ቀለል ያለ ኑሮ የሚኖሩ ህዝቦች ነበሩ። የባርነት ስርአትን ማፍረስ ያንን የተንደላቀቀ ህይወት መሰናበት ነው።
ሬት በትለር ግን እንደ ሌሎቹ ደቡባዊውን አይደለም። የኮንፌዴሬሲው ባንዲራ ሲውለበለብ ሰውነቱን አይወረውም። ብሔራዊ መዝሙር ሲዘመር አይነሽጠውም። እንዲያውም ሬት እንዲህ ይላል፦
"ሃገር ስትበለጽግ አብሮ ሃብታም መሆን ይቻላል። በተቃራኒው አለም ወደ ውድቀት ስትንደረደር የበለጠ እጥፍ ሃብታም መሆን ይቻላል።"
በዚህ ፍልስፍና እየተመራ ሬት በሙሉ ሃይሉ ወደ ኮንትሮባንድ ንግድ ውስጥ ይገባል። ጦርነቱ ከተጀመረ በኋላ የማይሸጠው ቁሳቁስ አልነበረም—ከሽቶ እስከ መሀረብ፣ ከመጠጥ እስከ ልብስ። ሬት በትለር መላው ሃገር ወደ አመድነት ቢቀየር ግድ የሚሰጠው ሰው አይደለም። ለሱ ዋጋ ያላቸው ነገሮች የንግድ ስራውና ትርፉ ብቻ ናቸው።
ጦርነቱ ሲገባደድ ሬት ሚሊየነር ሆኗል። ይህ ሃብት በብዙሃን ደም የተገኘ ነው። ሬት በተደጋጋሚ የሚጠቀማት አንድ ሃረግ አለች፦
"እንደ እውነቱ ከሆነ ውዴ ምንም ግድ አይሰጠኝም።"
አዎ ሬት ግድ አይሰጠውም። ሃገሪቷ በእሳት ብትነድ ግድ አይሰጠውም፤ ሚሊየኖች ቢሞቱ ግድ አይሰጠውም፤ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ ቀውስ ቢሰፍን ግድ አይሰጠውም። ለሬት ግድ የሚሰጠው አንድ ነገር ብቻ ነው—ገንዘብ፣ እጅግ ብዙ ገንዘብ። ገንዘብ የሚያስገኝለት ከሆነ ለመስዋዕትነት የማያቀርበው ነገር የለም። አለማችን ወደ ሲኦል የምትንደረደረው በነዚህ አይነት ሰዎች ምክንያት ነው።
¤¤¤
ነገም ሌላ ቀን ነው ውስጥ በጣም የምወዳት ገጸባህሪይ ሜላኒ ሃሚልተን ነች። ልቧ ትልቅ ነው— ያለ ምንም ተቀጥላ ምክንያት ሁሉንም እኩል ትወዳለች። አምስት ደቂቃ አብሯት ያሳለፈ ሁሉ ይወዳታል። ነፍሷ ምትሃታዊ ባህሪ አለው። ሰዎች ለራሳቸው እንኳን የማይታያቸውን ጥሩነት በማየት ዘወትር ታስደንቀኛለች።
ሰዎች ላይ አትፈርድም። ሁሉንም እንዳሉ ትቀበላቸዋለች ጨካኝና መጥፎ እንኳን ቢሆኑ። ልቧ ግዙፍ ስለሆነ ለሁሉም የሚበቃ ቦታ አላት።
ደቃቃ ብትሆንም ደፋር ናት—ፍርሃት የሚባል ነገር አልፈጠረባትም። ትልቅ ነፍሷ ትንሹ ሰውነቷን ሸፍኖታል። በአስፈሪ ሁኔታ ውስጥ ሆና እንኳን አትፈራም። እንደዚያ አምርራ የምትጠላት ስካርሌት እንኳን በሃቀኛነቷ ታከብራታለች። በአረብኛ እንዲህ የሚል አባባል አለ፦
"ለልበ ንጹህ፣ ሁሉም ንጹህ ነው"
.
እኔ ደግሞ በልብወለድም ይሁን በእውነታ ከሜላኒ የበለጠ ንጹህ አልገጠመኝም።
¤¤¤
እስካርሌት ከአሽሌይ ድብን ያለ ፍቅር ይዟታል። ከሱ ጋር ለመሆን የማትፈነቅለው ድንጋይ፣ የማታደርገው ነገር የለም። እሱ ግን እስካርሌትን ትቶ የምትመስለውን፣ የሚመስላትን ሜላኒን አገባ። ይኼኔ እስካርሌት አረረች ፤ ቆሽቷ ደበነ።
እስካርሌት ለሶስት ግዜ ያህል አግብታለች—ግን አንዱም ለፍቅር አልነበረም። ሌላ ድብቅ አላማ ነበራት—ቁሳዊም ሆነ ሌላ።
በመጨረሻ ሜላኒ በወሊድ ሞተች። አሁን ህይወቷን ሙሉ ስታሳድደው የኖረችው አሽሌይ ነጻ ሆነ። ነገር ግን ለሱ የነበራት ስሜት ሁሉ ተኖ ማለቁ ገረማት።
አሁን የሚወዳትን ሬት መውደድ ጀመረች። ነገር ግን ረፍዶ ነበር። እሷ ለአሽሌይ የነበራት ስሜት እንደሞተ ሁሉ፤ ሬት ለሷ የነበረው ስሜት ሞቷል። የምትወደውን አሽሌይን ስታሳድድ የሚወዳትን ሬትን አጣች። እስካርሌት ግራ የሚያጋባ የህይወት እንቆቅልሽ ሲገጥማት ዘወትር እንደዚህ ትላለች፦
"ይሄን ዛሬ አላስበውም። ነገም ሌላ ቀን ነው!"
¤¤¤
ስለ ጀራልድ እና ኤለን
ጉጉት የሚጭሩ ገፀ-ባህሪያት ናቸው፤ እና ልጃቸው ስካርሌት ከየት እንደመጣች እንድናይ ይረዱናል። ስካርሌት እንደ አባቷ ጨካኝ እና ግትርእና እንደ እናቷ የዋህ ነች። ለእስካርሌት በዚህ ዓለም ውስጥ ሁለት ሴቶች አሉ - እናቷ እና የተቀሩት ሴቶች። እናቷን እንደ አምላክ ትመለከታለች። በኤለን እና በእግዚአብሔር እናት— በማርያም— መካከል ያለውን ልዩነት አታውቅም።
ጄራልድ አጭር ቁመት አለው። ነገር ግን በአለም ላይ የሚፈልገውን ሁሉ ከማግኘት የሚያግደው ምንም ነገር የለም። ቆንጆዋን ኤለን እንኳን ቢሆን። የአይሪሽ አእምሮው አረቄን እንዴት እንደሚይዝ እና ቁማር መጫወትን ያውቃል። የመጀመሪያውን ባሪያውን እና ትልቁን ታራ በቁማር አሸንፏል። ከኤለን ፍላጎት ውጪ ሰክሮ በፈረስ ላይ የወጣበትን እና አጥሩን ለመዝለል የሚሞክርበትን ትዕይንት ሁልጊዜ አስታውሳለሁ። ስካርሌት በረንዳ ላይ ተቀምጣ ጄራልድ እየዘለለ ሲመለከት ለኤለን መልሳ አላቃጠረችበትም። የሁለቱ ምስጢር ነው።
ኤለን የአጎቷን ልጅ እና ወላጆቿ የከለከሉትን እውነተኛ ፍቅሯን ፊሊፕን ማግባት ፈለገች። ፊሊፕ ግን በቡና ቤት ጸብ ተጋድሎ ሞተ። ወላጆቿን ለማበሳጨት፣ ጄራልድ ኦሃራን አገባች፣ በኋላ ግን ተጸጸተች። ደራሲው ኤለን ለጄራርድ ምንም አይነት ፍቅር እንደሌለው ይነግሩናል. ልቧ ባዶ ቀፎ ነበር።
ከብዙ አመታት በኋላ ትልቋ ሴት ልጇ ስካርሌት የእናቷን ተመሳሳይ ስህተት ለመስራት ተነሳች። ስካርሌት አታውቀውም ነበር፣ ኤለን ግን አወቀች። እና ይህን እውነት ለመናገር ምንም አይነት ጨዋ መንገድ የለም። ኤለን እራሷን ብቻ አስቀምጣ ጋብቻውን ለመረዳት በማይቻል ሁኔታ ተቃወመች።
ኤለን እውነተኛ ፍቅሯን የተናገረችው፣ ስሙን የጠራችው በሞቷ አልጋ ላይ ብቻ ነው። የመጨረሻ እስትንፋሷን ከመውሰዷ በፊት የፊሊፕን ስም ጮኸች። ይህ የፊሊፕ ሰው ማን ነው፣ እና እሱ ለእስካርሌት እናት ምንድነው?! ከማሚ በስተቀር ማንም አያውቅም።
በሌላ በኩል ጄራልድ ኤለንን በእውነት ይወዳት ነበር። እሷ ለስላሳ እና ቆንጆ ነች። ሁሉም ያከብሯታል። ለዚህም ነው መሞቷ ሙሉ በሙሉ አለሙን ያጨለመው። አእምሮው ከኤለን ሞት ወዲህ ልክ አልነበረም። ደራሲው ማርጋሬት ሚቼል ግራ የተጋባውን የአዕምሮ ሁኔታውን በሚያምር ሁኔታ ገልጻዋለች።
¤¤¤
እነሆ በወንድማማቾሽ መካከል መራር ጦርነት ተደረገ። የደቡብ ኮንፌዴሬሲው ተደመሰሰ። የያንኪ ወታደሮች በደቡባዊ አሜሪካ ውስጥ ሴቶችን እየደፈሩ፣ ንብረት እየዘረፉ፣ ቤት እያቃጠሉ ብዙ ጉዳት አደረሱ። ደቡባውያን የተሰበረ ቅስማቸውን እያስታመሙ፣ ዳግም ከተሞቻቸውን መገንባት ጀመሩ። ባሮች ነፃ ወጡ። ዘረኛውን ኬኬኬ የሚቀላቀሉ ወጣቶች በዙ። ከጦርነቱ በኋላ ሌላ "ሰላማዊ" ጦርነት ተጀመረ።
የመፅሀፉ ርእስ "Gone the Wind" ነው። ለአማርኛ ትርጉሙ የተመረጠው ርእስ "ነገም ሌላ ቀን ነው" ነበር። ይህ መጽሐፍ የጦርነትን አውዳሚነት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው። በተለይ የእርስ በእርስ ጦርነት መዘዙ ብዙ ነው። ዳፋው ለትውልድ ይተርፋል። ቁስሉ ቶሎ አይጠግም።
ለኛ የእርስ በእርስ ጦርነት አዲሳችን አይደለም። ለዘመናት አቆርቁዞናል። ዛሬ ግን አይናችንን መግለጥ አለብን። ብልጥ ከሰው ይማራል ሞኝ ደግሞ ከራሱ። ከዚህ አለፍ ሲል ግን፣ ከራሱ የቀደመ ታሪክ የማይማር ግን ከሞኝነትም አልፎ ደደብ ነው።
¤¤¤
Gone With the Wind"/ "ነገም ሌላ ቀን ነው" የተሰኘውን ታላቅ መፅሀፍ በትንሹ አምስት ግዜ አንብቤዋለሁ― በእድሜዬ አስራዎቹ፣ ሀያዎቹ፣ ሰላሳዎቹ ውስጥ ሆኜ። ታድያ መፅሀፉን ደጋግሜ ሳነሳው ሁሌም አዲስ ነገር አገኝበታለሁ። በእርግጥ መፅሀፉ የድሮው ነው፤ ቃላቶቹ አልተለወጡም፤ ገፆቹ አልተለጠጡም። ታዲያ እንዴት ይህ አሮጌ መፅሀፍ በእኔ ውስጥ አዲስ ሐሳብና ስሜት ፈጠረ ብዬ ስጠይቅ መልሱ ብሩህ ሆኖ ታየኝ። ምንም እንኳን መፅሀፉ ባይለወጥም፣ እኔ አንባቢው ተለውጬያለሁና ነው። እኔ ስለወጥ አሮጌውን መፅሀፍ የማይበት መነፅር አዲስ ነው፤ ፍፁም ከተለየ አቅጣጫ /perspective ነው ታሪኩን ገፀ ባህሪያትን የማየው።
¤¤¤
በማያልቅ የእርስበርስ ጦርነት ውስጥ ለምንኖረው እኛ ይሄ መጽሐፍ ትልቅ መልእክት አለው። ከታሪክ የምንማረው ከታሪክ አለመማራችንን ነው ይባላል። እንኳን ከአሜሪካ የእርስ በእርስ ጦርነት፣ ከራሳችንም ታሪክ አልተማርንም። በናፍቆት የሚጠበቅ የኦሎምፒክ ውድድር ይመሰል በየ10 አመቱ ጦርነት እንገጥማለን።
¤¤¤
Gone with the Wind
ይህን ልብወለድ በብዙ ምክንያቶች እወደዋለሁ። አሜሪካንን ለመረዳት ይሄንን የCivil War Era የእርስበርስ ጦርነት ዘመን ልብወለድ ማንበብ ተገቢ ነው። በሌላ አነጋገር ገን ዊዝ ዘ ዊንድ ጠቃሚ የታሪክ ሰነድ ነው። የሬት በትለርና የእስካርሌት ኦሃራ የፍቅር ታሪክ መንፈስን ሰቅዞ የመያዝ አቅም አለው። በአጠቃላይ ግሩም የስነጽሁፍ ስራ ነው።
ብዙውን ግዜ ታላቅ የስነጽሁፍ ስራ የሆነ መጽሐፍ ወደ ፊልም ሲላመድ ይኮስሳል፤ ግዙፍ ግርማ ሞገሱን ያጣል። Gone With the Wind መጽሐፉ በ1936 ተጽፎ ወደ ፊልም የተላመደው ቶሎ ከሶስት አመት ብቻ በኋላ በ1939 ነበር። በእርግጥ በብዙ ምክንያቶች ፊልሙን ለማየት ጓጉቼ ነበር—ሆሊውድ የክላሲካል ኢራው ማስተርፒስ ከሚላቸው ፊልሞች አንዱ ነው። ጋሽ ስብሐት ራሱ ፊልሙን አለመጠን ሲያዳንቅ "ፊልሙን ከተመለከትኩ በኋላ በጣም ስለረካሁ መጽሐፉን ለማንበብም አላሰኘኝ" እኔ ግን ጥርጣሬዎች ነበሩኝ። ከ1000 በላይ ገጾችና እጅግ ብዙ ዝርዝር ታሪክ ያለውን መጽሀፍ በሶስት ሰአት ፊልም ሳያጎድሉ ማሳየት ይቻላል?! በመጨረሻ የገባኝ አንድ ትልቅ እውነት አለ። መጽሐፍ እና ፊልም እጅግ የተለያዩ ሚዲየሞች ወይም ቅርጾች ናቸው። እርስበእርስ አይወዳደሩም። መመዘን ያለባቸውም እንደ አውዳቸው ነው። ለመዝናናት፣ ግዜ ለመቆጠብ ፊልም ጥሩ አማራጭ ነው። ለቁምነገር ከሆነ ግን መጽሀፉን ማንበብ ይመረጣል። በዚህ መመዘኛ ሁሌም መጽሀፍን እመርጣለሁ። ግን ፊልሙም ጥሩ መዝናኛ ነው።
በነገራችን ላይ መጽሀፉን ከማንበብና ፊልሙን ከመመልከት ባሻገር፣ ይህ መጽሀፍ በአሁን ወቅት በሬዲዮ ፋና እየተተረከ ነው። የመጽሀፍት ትረካ ለምትወዱ ጥሩ አማራጭ ነው። ዩትዩብ ላይም ስላለ አውርዳችሁ ልትመሰጡበት ትችላላችሁ። ተራኪው ዳንኤል ሙሉነህ ነው። መጽሀፉ በአንድ አረፍተ ነገር ሲጠቃለል፦
"Yesterday has Gone With The Wind. Tomorrow is another day"
"ትላንት ከንፋሱ ጋር አልፏል። ነገም ሌላ ቀን ነው"



Sunday, July 7, 2024

ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን ወንድም

ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን ወንድም (1946 - 2016)

ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ ከአባቱ ከአቶ መኮንን ወንድም እና  ከእናቱ ከወይዘሮ በለጤ በድሉ፣ በነሐሴ ወር 1946 ዓ.ም፣ በቀድሞዋ ናዝሬት፣  በአሁኑ አዳማ ከተማ ተወለደ፡፡

 ወደ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከመግባቱ አስቀድሞ፣ መምህር ተከስተ ጋር የቄስ ትምህርቱን የተከታተለ ሲሆን፤ እዚያም ሳለ ዳዊትን በቃሉ በመሸምደድ የማስታወስ ችሎታውን አዳበረ፡፡  
 የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እዚያው ናዝሬት በአጼ ገላውዲዮስ ት/ቤት  የተከታተለው ነቢይ መኮንን፤ በትምህርት አቀባበሉም ከጎበዞቹ ተርታ የሚሰለፍ ነበር፡፡ ለዚህ ደግሞ ለትምህርት ጥልቅ ፍቅር የነበራቸው  የገንዘብ ሚኒስቴር ባልደረባ የነበሩት አባቱ፤ ጉልህ ሚና ነበራቸው፡፡  ልጃቸው ሁልጊዜም  በትምህርቱ ብርቱ ሆኖ  ምክራቸውን  ይለግሱት  ነበር፡፡ ነቢይም፣ ከክፍሉ አንደኛ በመውጣት አባቱን ከማስደሰት ቸል ብሎ አያውቅም፡፡  ነቢይ አባቱን አቶ መኮንን ወንድምን በሞት ያጣው  የ7ኛ ክፍል ተማሪ ሳለ ነበር፡፡
ነቢይ መኮንን፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን  እንዳጠናቀቀ፣ ስድስት ኪሎ በሚገኘው ልኡል በእደ ማርያም ተማሪ ቤት ከገቡ ጎበዝ ተማሪዎች አንዱ ነበር፡፡  በመቀጠልም በ1966 ዓ.ም፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሳይንስ ፋኩልቲን የተቀላቀለው ነቢይ፤ ኬሚስትሪን በዋናነት (ሜጀር)፣ ሂሳብን ደግሞ  ማይነር በማድረግ አጥንቷል፡፡
  


እንደ ዘመነኞቹ  በወቅቱ  የተማሪዎች  ንቅናቄ ውስጥ ተሳትፎ የነበረው ነቢይ መኮንን፤ ከደርግ ወጥመድ አላመለጠም፡፡ በኢህአፓ አባልነቱ ታስሮ ለ10 ዓመታት መከራውን በልቷል፡፡ ነገር ግን ደርግንም ሆነ አገሪቱን ወይም ሌላ ወገን ሲያማርር፣ ሲወቅስ ወይም ሲረግም ተሰምቶ አይታወቅም፡፡  እንደ ብዙዎቹ ፖለቲከኞች፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ ታግዬለታለሁ፣ ሞቼለታለሁ ወዘተ እያለም መመጻደቅ አያውቅበትም፡፡  በሚመጻደቁትም ይስቃል፡፡ እሱና ዘመነኞቹ በአብዮቱ ወቅት ያሳለፉትን በጎም ሆነ ክፉ፣ ያሁኑ ትውልድ እንዲማርበት ከመጻፍና ከመናገር ግን  ቦዝኖ አያውቅም፡፡ ጽንፈኝነትና አክራሪነት እንደማያዋጣ ሲመክር ኖሯል፤ በጽሁፎቹ፡፡    
 ነቢይ፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ኬሚስትሪ ያጠና  ቢሆንም፣ በገጣሚነት፣ በደራሲነት፣ በተርጓሚነትና በጋዜጠኝነት  በርካታ ሥራዎችን ለአንባቢያን  ያበረከተ ታላቅ የኪነ ጥበብ ባለሙያ ነበር።



በ1992 ዓ.ም ህትመት የጀመረችውን አዲስ አድማስ ጋዜጣን ከመሰረቱት አንዱ የነበረው አንጋፋው የጥበብ ባለሙያ  ነቢይ መኮንን፤ ለሁለት አስርት ዓመታት ጋዜጣዋን በዋና አዘጋጅነት በመምራት፣ ከሥራ ባልደረቦቹ ጋር ስኬታማ አድርጓታል፡፡ የአዲስ አድማስ ዋና አዘጋጅ የነበረው ነቢይ፣ በጋዜጣው ላይ በየሳምንቱ በተረትና ምሳሌ እያዋዛ በሚጽፋቸው ርዕሰ አንቀጾች ታዋቂነትን ያተረፈ ሲሆን፤ ለጋዜጣዋም ተነባቢነትን አቀዳጅቷታል፡፡  
ሁለገቡ ከያኒ ነቢይ መኮንን፣ ከአሰርት ዓመታት በፊት “ባለጉዳይ” የተሰኘ ተወዳጅ የቴሌቪዥን ድራማ ለዕይታ ከማብቃቱም በላይ በትወናም ተሳትፎበታል፡፡ የእዚህ ተከታታይ ድራማ ጭብጥ ከመሬት ጋር የተያያዘ የሙስና ጉዳይ ሲሆን፣ ታዋቂዎቹ ተዋናዮች  አበበ ባልቻ፣ ፈቃዱ ተክለማሪያምና ፍቅርተ ጌታሁንን ጨምሮ ሌሎችም ተሳትፈውበት ነበር፡፡
ነቢይ፣ “ናትናኤል ጠቢቡ” እና “ጁሊየስ ቄሳር” የተሰኙ ተውኔቶችንም ተርጉሞ ለመድረክ አቅርቧል። ”ባለካባ እና ባለዳባ” በተሰኘ ተውኔት ላይ ደግሞ በትወና ተሳትፏል።
“ከሁሉም በላይ ገጣሚ ነኝ” የሚለው ነቢይ መኮንን፤ “ጥቁር፣ ነጭ፣ ግራጫ ግጥሞች” እና “ስውር ስፌት- (ሁለት ቅጾች)” የግጥም መድበሎችን ለንባብ  አብቅቷል፡፡  

ነቢይ፤ “የኛ ሰው በአሜሪካ” - የተሰኘ የጉዞ ማስታወሻው፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ ሲወጣ ቆይቶ፣ በመጨረሻ  በመጽሐፍ ተዘጋጅቶ ለህትመት የበቃ ሌላኛው ሥራው ነው። ለንባብ የበቃው ሌላው  የነቢይ መጽሐፍ ደግሞ “የመጨረሻው ንግግር” የተሰኘ ሲሆን፤ “ዘ ላስት ሌክቸር” ከሚለው መጽሐፍ የተተረጎመ  ነው።
ነቢይ፤ ዳን ብራውን የጻፈውንና በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ መነጋገሪያ ሆኖ የነበረውን "The Davinci Code" የተሰኘ መጽሐፍ ወደ አማርኛ ተርጉሞ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ አስነብቧል፡፡  
ከነቢይ ጥበባዊ ሥራዎች  ሌላው  የሚጠቀሰው  "ማለባበስ ይቅር" ነው፡፡ ኤች አይቪ-ኤይድስ  የሀገር አደጋ በሆነበት ዘመን፣ ነቢይ መኮንን "ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩትን ማግለል በሽታውን ያባብሳል፤ ስለዚህ ፍቅር እንስጣቸው፤ አናግልላቸው"  የሚል መልእክት ያዘለ  ግጥም ገጥሞ  ታዋቂ ወጣት ዘፋኞች አቀንቅነውታል፡፡  "ማለባበስ ይቅር" የተሰኘው የሙዚቃ ሥራ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በተደጋጋሚ ይታይ እንደነበር ይታወቃል፡፡
ከ32 ዓመት በፊት ሜጋ ኪነጥበባት ማእከልን ከመሰረቱት አንዱ የነበረው ነቢይ መኮንን፤ በጊዜው በሜጋ ኪነጥበባት ማእከል አሳታሚነት ትወጣ የነበረችውን  ‹‹ፈርጥ›› የኪነ-ጥበብ መጽሄትንም በዋና አዘጋጅነት በመምራት ይታወቃል፡፡
ነቢይ፣ ከጋዜጠኝነቱና ከጥበብ ሥራው ጋር በተገናኘ የተለያዩ የዓለም አገራትን የመጎብኘት ዕድል የገጠመው ሲሆን፤ ከጎበኛቸው ሀገራት  መካከልም ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ አሜሪካ፣ ኢራን፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ዛምቢያ፣  ኬንያና   ሱዳን ይገኙበታል፡፡
ነቢይ ለሀገሩ ኪነጥበብ ማደግ ከወጣትነቱ ጀምሮ ብዘ የለፋ ታላቅ የሀገር ባለውለታ እንደመሆኑ መጠን፣ ይህንኑ ግምት ውስጥ በማስገባት፣ የቅርብ ወዳጆቹ ግንቦት 30 ቀን 2011 ዓ.ም፣ በአዲስ አበባ ቴአትርና ባህል አዳራሽ፣ ነቢይ በሀገሩ ይከበራል የሚል  የምስጋና መሰናዶ አዘጋጅተውለት ነበር፡፡  
.ከሁሉ ወዳጅና  ተግባቢ የነበረው ነቢይ መኮንን፣ ባለትዳርና  የሦስት ሴት  ልጆች አባት ነበር፡፡ አንጋፋው ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ ባደረበት ህመም በህክምና ሲረዳ ቆይቶ፣ ረቡዕ ሰኔ 26 ቀን  2016 ዓ.ም  በተወለደ በ69 አመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ ለቤተሰቦቹ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹና ለአድናቂዎቹ  መጽናናትን እንመኛለን፡፡

********************************
ስለ ነቢይ መኮንን የማውቀውን ልንገራችሁ!

ኢዮብ ካሳ -

ለራስ የተጻፈ ወቀሳ

እንጠራራ እንጂ
እንፋለግ እንጂ
ከያለንበቱ
ሰው የለም አንበል፣ አለ በየቤቱ
ምን ቢበዛ ጫናው፣ አንገት ቢያቀረቅር
ምን አፉ ቢታፈን፣ዝም ቢልም አገር
ምን መሄጃ እስኪያጣ፣ መንገዱ ቢታጠር
ጎበዝ እንደ ጭስ ነው፤ መተንፈሻ አያጣም
ቀን መርጦ ሰው መርጦ መነሳቱ አይቀርም፡፡
(ነቢይ መኮንን፤ አዲስ አድማስ ግንቦት 9፣1995 ዓ.ም)

**

በዚህች አጭር ማስታወሻ በቅርበት ስለማውቀው ገጣሚ፣ ተርጓሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን በጥቂቱ አወጋችኋለሁ - በወፍ በረር እንደሚሉት፡፡ ነቢይ የትያትርና ድራማ ጸሃፊም ነው፡፡ ከዓመታት በፊት ባለጉዳይ የተሰኘ ተወዳጅ የቴሌቪዥን ድራማ ለዕይታ አብቅቷል፤ አንጋፋው አርቲስት አበበ ባልቻ፣ ራሱ ነቢይ መኮንንና ሌሎችም አርቲስቶች የተወኑበት፡፡ ጭብጡ ዛሬም ድረስ ተባብሶ የቀጠለው ከመሬት ጋር የተያያዘ የሙስና ጉዳይ ነው፡፡ የሚገርመው ደግሞ ድራማው ከ10 ዓመታት በኋላ በድጋሚ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርቦ፣ እንደ አዲስ በከፍተኛ አድናቆት መታየቱ ነው፡፡ ናትናኤል ጠቢቡ የተሰኘ ተውኔትም ተርጉሞ ለመድረክ አቅርቧል፡፡ ጁሊየስ ቄሳር ሌላው ተርጉሞ ለዕይታ ያበቃው ተውኔት ነው፡፡

ነቢይን ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቅሁት የዛሬ 20 ዓመት ገደማ ነው - በተወዳጇ ሳምንታዊ ጋዜጣ አዲስ አድማስ በኩል፡፡ ዕድሜ ለአዲስ አድማስ፤ ይኸው እስከ ዛሬ ድረስ በሥራ ባልደረባነትና በቅርብ ወዳጅነት አብረን ዘልቀናል፡፡ የጋዜጣዋ መሥራችና ባለቤት የነበረውን (ነፍሱን ይማረውና) አሰፋ ጎሳዬንና ነቢይን እኩል ነው የማውቃቸው፡፡ አለቃዬ ቢሆኑም አንድም ቀን እንዲያ ተሰምቶኝ አያውቅም፡፡ ወይም እንዲሰማኝ አላደረጉም፡፡ የጓደኝነትና የታላቅ ወንድምነት እንጂ የአለቃና ሎሌነት ስሜት ኖሮን አያውቅም፡፡

ሥራ ስጀምር በዕድሜና በህይወት ተመክሮ ከነቢይ በእጅጉ ባንስም፣ አጠገቡ ሆኜ አንድ ቢሮ እየሰራን፣ ሁሉንም ነገር እንድማር ዕድል ሰጥቶኛል፡፡ ይሄ እምብዛም በአበሻ ዘንድ የማይገኝ ደግነቱና ቅንነቱ ሁሌም ይደንቀኛል፡፡ ይታያችሁ --- ያኔም ቢሆን ነቢይ የታወቀ የሥነጽሁፍ ባለሙያ ነው፡፡ ዝነኛ ገጣሚ ነው፡፡ ዝነኛ ተርጓሚ ነው፡፡ ዝነኛ ጸሃፌ ተውኔት ነው፡፡ ዝነኛ የጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነው፡፡ ነገር ግን በችሎታውም ሆነ በታዋቂነቱ አይታበይም፤ አይኮፈስም፡፡

በደርግ ዘመን በኢህአፓ አባልነቱ ታስሮ ለ10 ዓመታት መከራውን በልቷል፡፡ ነገር ግን ደርግንም ሆነ አገሪቱን ወይም ሌላ ወገን ሲያማርር፣ ሲወቅስ ወይም ሲረግም ሰምቼው አላውቅም፡፡ እንደ ብዙዎቹ ፖለቲከኞች፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ ታግዬለታለሁ፣ ሞቼለታለሁ ወዘተ እያለ አይመጻድቅም፡፡ በሚመጻደቁትም ይስቃል፡፡ እሱና ዘመነኞቹ በአብዮቱ ወቅት ያሳለፉትን በጎም ሆነ ክፉ ያሁኑ ትውልድ እንዲማርበት ከመጻፍና ከመናገር ቦዝኖ አያውቅም፡፡ ጽንፈኝነትና አክራሪነት እንደማያዋጣ ሲመክር ኖሯል፤ በጽሁፎቹ፡፡ ቁምነገርን በቀልድ እያዋዛ ማቅረብ ይወዳል - በጽሁፉም በንግግሩም፡፡ መድረክ ላይ ከወጣ ታዳሚን በሳቅ ያፈርሳል - አፍ ያስከፍታል፡፡ አንደበቱም ብዕሩም የተባ ነው፡፡

ነቢይ ባህልና ጥበብ አገርን እንደሚለውጥ ጽኑ እምነት አለው፡፡ በዚህ እምነቱ ነው አዲስ አድማስ በተለይ ጥበብና ባህል ላይ አተኩራ እንድትሰራ ያደረገው፡፡ የየሳምንቱን ርዕሰ አንቀጽ በተረትና ምሳሌ መጻፍ የጀመረው ያለምክንያት አይደለም፡፡ ሃሳብ አዕምሮን ከአዕምሮ የሚያገናኝ ድልድይ ነው ብሎ ያምናል፡፡ ለዚህም ነው የተለያዩ ሃሳቦችና አስተያየቶች በአዲስ አድማስ ላይ ያገደብ በነጻነት ሲስተናገዱ የኖሩት፡፡ እሱም እንደ ጋዜጣው መሥራችና ባለቤት አሰፋ ጎሳዬ ሁሉ ሃሳብን አይፈራም፡፡ ለህዝብና ለአገር የሚጠቅም አንዳች ሃሳብ ያላቸው ወገኖች ሁሉ፣ እንዲጽፉ ሲያበረታታና ሲደግፍ ነው የኖረው፡፡

ወጣት ገጣምያንና ጸሃፍት በአዲስ አድማስ ላይ ሥራዎቻቸውን የሚያቀርቡበት ሰፊ መድረክ ፈጥሮላቸዋል፡፡ በዚህም ብዙዎቹ ዛሬ መጽሐፍት ያሳተሙ ታዋቂ ደራስያንና ገጣምያን ለመሆን በቅተዋል፡፡ በአጭሩ ተተኪ ጸሃፍት፣ ደራሲያን፣ ገጣሚያን፣ ወዘተ-- ፈጥሯል - በዋና አዘጋጅነት በሚሰራባት አዲስ አድማስ በኩል፡፡

እኔም የዚያ ውጤት ነኝ፡፡ በአዲስ አድማስ ላይ ከ30 የማያንሱ አጭር ልብወለዶችን ተርጉሜ አቅርቤአለሁ፡፡ ወደ አምስት ገደማ መጻህፍት አሳትሜአለሁ፡፡ ጋዜጣዋን ከ15 ዓመታት በላይ በምክትል ዋና አዘጋጅነት መርቼአለሁ፡፡ ዛሬ ለደረስኩበት ደረጃ የነቢይ መኮንን በጎ ተጽዕኖ የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ገና ከፍተኛ ሪፖርተር ሳለሁ፣ የተለያዩ ጽሁፎችን በጋራ እየተረጎምን በስማችን ጋዜጣው ላይ እንዲወጣ ያደርግ ነበር - በእኔ ጥያቄ ወይም ግፊት ሳይሆን በሱ ደግነትና ቅንነት፡፡ ፕሮፌሰሩ እና የዩክሬን ትራክተሮች የተሰኙ መጻህፍትን ለሁለት እየተረጎምን በተከታታይ አስነብበናል፡፡ የኔ ስም ከታዋቂው ገጣሚና የሥነጽሁፍ ሰው ነቢይ መኮንን ስም ጎን አብሮ ሲወጣ የሚፈጥርብኝን አዎንታዊ ስሜትና ብርታት አስቡት፡፡ በዚህ ሂደትም በነቢይ አስገራሚ የሥነጽሁፍ ብቃትና መክሊት እየተደመምኩ ብዙ ተምሬአለሁ፡፡ ነቢይ እኔን ገጣሚ ባያደርገኝም፣ከግጥም ጋር በፍቅር እንድወድቅ ማድረግ ችሏል፡፡ ደግነቱና ቅንነቱ ተጋብቶኝ ይሁን አይሁን ግን በእርግጠኝነት መናገር ያዳግተኛል፡፡

በነገራችን ላይ ዛሬ ስለ ነቢይ መኮንን እንዳወጋ ያነሳሳኝ፣ በነገው ዕለት ሦስት መጻሕፍት የሚያስመርቅ መሆኑ የፈጠረብኝ የደስታ ስሜት ነው፡፡ እናም ይህች አጭር ማስታወሻ ገጣሚውንና ሁለገብ የሥነጽሁፍ ሰው የሆነውን - ነቢይ መኮንን -እንኳን ደስ ያለህ- ለማለት ያህል፣ የከተብኳት ተደርጋ ትቆጠርልኝ፡፡ እንደሱ ገጣሚ ብሆን ኖሮ፣ ይሄን ሁሉ ሃሳብ በአጭር ግጥም ጽፌው እገላገል ነበር፡፡ እኔ ግን የግጥም አፍቃሪና አድናቂ እንጂ ገጣሚ አይደለሁም፡፡ ምናልባት ወደፊት --- ማን ያውቃል?

በነገው ዕለት በፍሬንድሺፕ ሆቴል ከሚመረቁት የነቢይ ሦስት መጻህፍት አንዱ፣ በ1970ዎቹ መጨረሻ ለህትመት የበቃውና በደርግ ዘመን በእስር ቤት ሳለ የተረጎመው ነገም ሌላ ቀን ነው የተሰኘው ዳጎስ ያለ መጽሐፍ ነው፡፡ ነቢይ መኮንን Gone With The Wind የተሰኘውን የአሜሪካ ክላሲክ መጽሐፍ የተረጎመበትና ያሳተመበት ሂደት፣ በራሱ አስደናቂ መጽሐፍ ይወጣዋል፡፡ ጎበዝ የፊልም ባለሙያ ይፈልጋል እንጂ አስገራሚ ፊልምም የሚወጣው ነው፡፡

በደርግ ዘመን እንደ እኩዮቹ ሁሉ፣ በጸረ-አብዮተኝነት ተጠርጥሮ ወህኒ የተወረወረው ነቢይ መኮንን፤ ከዛሬ ነገ ይሙት ይትረፍ እርግጠኛ ባልሆነበት ሁኔታ፣ Gone With The Wind የተሰኘውን ዳጎስ ያለ መጽሐፍ በሲጋራ ወረቀት ላይ እየተረጎመ፣ በድብቅ በማስወጣት ነው፣ በመጨረሻ ሲፈታ ያሳተመው፡፡

በነገራችን ላይ ይህን አስገራሚ ታሪክ ሰምታ የተደመመች አንዲት አሜሪካዊት ጋዜጠኛ፣ በ1990ዎቹ አጋማሽ ላይ ባህር ተሻግራ አዲስ አበባ በመምጣት፣ ከነቢይ ጋር ሰፊ ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ እኔ ደግሞ ወደ ሃገሯ ልትመለስ አንዲት ቀን ሲቀራት የማግኘት ዕድል አግኝቼ፣ ኢንተርቪው በማድረግ፣ ለአዲስ አድማስ አንባቢያን ታሪኩን አጋርቼዋለሁ፡፡

ነገም ሌላ ቀን ነው የተሰኘው መጽሐፍ የመጀመሪያ ዕትም በሳንሱር ምክንያት መግቢያውና አንዳንድ ሃሳቦቹ ተቆራርጠው መውጣታቸውን የሚያስታውሰው ነቢይ መኮንን፤ አሁን - ያልታተመው መግቢያ- ታክሎበት በአዲስ መልክ መታተሙን ተናግሯል፡፡
በነገው ዕለት የሚመረቀው ሌላው መጽሐፍ፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ለዓመት ያህል በተከታታይ ሲወጣ የነበረውና ከፍተኛ ተነባቢነትን የተቀዳጀው የኛ ሰው በአሜሪካ - የተሰኘ የጉዞ ማስታወሻ ነው፡፡ በአሜሪካ በሚኖሩ ዳያስፖራ ኢትዮጵያውያን ህይወት ላይ ያጠነጥናል፡፡ ሦስተኛው መጽሐፍ የመጨረሻው ንግግር የተሰኘ ሲሆን The Last Lecture ከሚለው መጽሐፍ የተተረጎመ ነው፡፡

እኒህ የነቢይ ሥራዎች ታትመው ለምርቃት መብቃታቸው በእጅጉ አስደስቶኛል፡፡ ከዚህ በላይ ግን የህይወት ታሪኩን ጽፎ እንደጨረሰና በአጭር ጊዜ ውስጥ ለህትመት እንደሚበቃ መስማቴ አስፈንድቆኛል፡፡ ነፍሴ በደስታ ጮቤ ረግጣለች፡፡ የመጽሐፍቶቹን ምረቃ በተመለከተ ባለፈው ሐሙስ በብሔራዊ ቤተመዘክርና ቤተመጻህፍት ኤጀንሲ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የተገኙት የኤጀንሲው ሃላፊ፣ ነቢይ መኮንን ራሱ ቤተመጻህፍት መሆኑን ጠቅሰው፤ የዚህን ሁለገብ የሥነጽሁፍ ሰው የህይወት ታሪክ መጽሐፍ ለህትመት ለማብቃት መጠነኛ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል - በተቋማቸው ስም፡፡ ይሄም ዜና ተስፋ ሰጪና አበረታች ነው፡፡ ለነቢይ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ደራሲያንና ሥነጽሁፍም ጭምር፡፡

በዚህ አጋጣሚ የነቢይ ሥራዎች ተሰባስበውና ተደራጅተው በመጽሐፍ መልክ ለትውልድ ይተላለፉ ዘንድ ከጎኑ ሆነው በትጋት እየሰሩ ያሉትን ወገኖች ሁሉ ማመስገን ተገቢ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡

በድጋሚ ለነቢይ መኮንን -እንኳን ደስ ያለህ- ለማለት እወዳለሁ፡፡
ረዥም ዕድሜ፣ የተትረፈረፈ ፍቅርና የተሟላ ጤና ተመኘሁልህ!



https://www.facebook.com/photo.php?fbid=8507341872617042&id=245686495449329&set=a.316574961693815