ከደራሲያን ዓምባ

Friday, November 21, 2014

የባንዲራ ታሪክ_በኑረዲን ዒሣ

የግጥም ጣዕም 

የባንዲራ ታሪክ_ኑረዲን ዒሣ

 

በሃበሻ ምድር
እንዲህ እንደዛሬው ዋጋው መሣ ሳይሆን
እኩል ከእራፊ ጨርቅ
ለሃገር ክብር ሲባል
ከባንዲራ በፊት – ሰው ነበር የሚወድቅ።
መሣፍንቱ በጎጥ ሸንሽኖ ከፋፍሎ
የማሽላ ዳቦ ያረጋትን ሃገር
ገብርዬ ሲለካት – እንቅጯን ሁለት ክንድ
በሆነች ባንዲራ ገጣጥሞ በማሰር
አንድን ሕዝብ አንድ አርጎ
ማኖር እንደሚችል ከተዋበች በቀር
ሕዝቡም፣ ሹማምንቱም፣ እራሱ ቴዎድሮስም – ከቶ አያውቅም ነበር።
የዛን ቀን ለሊት ግን
እንደ ነገ ጠዋት፣ ደረስጌ ማርያም ላይ
ንግሥና ሊቀባ፣ ክፉኛ ሃሳብ ይዞት
እንቅልፍም እንደሰው ሙልጭ አርጎ ክዶት
እልፍኙ ውስጥ ሆኖ….
ስለአንዲት ሃገሩ፣ ስለአንዲት ወዳጁ
እቋፍ ላይ ስላለች
ላሳቡ ማሰሪያ አጥቶ – እግር ተወርች
እንዲህ ሲንጎራደድ
ሌላኛ ወዳጁ
የሴት ባለመላ – ተዋበች አሊ ግን ልታነቃው አለች።
«ካሣ መከታዬ»
ሃሳብ ለምን ገባህ አልልም የኔ አባት
ቅድምም አየውህ – ማዱን ስትገፋው
አልዋጥ ብሎ፣ ባፍህ ሲንከራተት የጎረስከው እራት።
አውቃለሁ ጌታዬ
የእንቅልፍህ፣ የእረፍትህ፣ ያንዠትህም ጠላት
ይቺው ሃገርህ ናት።
ደሞ ምናባቱ…እንቅልፍስ ይቅርብህ – ወዴት ታውቀውና
እጣህን የመንቃት አድርጎት ሲያበቃ…
ምኑን ታርፈዋለህ
ይኼው ጎበጥክ አይደል – ሃገር ስታቀና።
እንቅልፍስ ይቅርብህ ወዴት ታውቀውና።
ቁስሉን ነካችበት
ብሶቱ ልፋቱን – መከራውን አልፋ ሕልሙን አየችበት።
ካሣ አንገቱን ደፋ
እሷ ፊቷን ዞረች።
እንዲህ የሆነ ዕለት – ከሱና እሷ በቀር – ባዕድ የማያውቃት
ያይኑን ገደብ አልፋ – የምትፈስ እንባ አለች
ያቺ ዕንባ ጠብ አለች።
እንግዲህ አለ መይሳው
እንግዲህ…
በእኔ ልፋትና በኔ ድካም ሳይሆን
በእግዜር ይሁን ማለት
ለዚህ ማዕረግ መርጦ – ሰጥቶኛል ይኽን ሹመት
እኔ ስሰነዝር እሱ ከኔ ቀድሞ ባላንጦቼን እየጣለ
ወሰኔን እያሰፋ – የታጠቅ ጉልበት እንደቻለ
ሞገሴን እያገዘፈ….
እንደልቤ መሻት—እርከኔን እያከለ።
እግዛቤር ይመስገን
ይኼው … ለዚህ በቅቻለሁ
ተመስገን ከማለት ውጪ
ለስለት እከፍለውስ—ምን የከበረ አስገባለሁ።
ግን አለ መይሳው!
ግን ነገ ማለዳ…ቅባቱን ተቀብዬ – ዘውዱን ስደፋ
ሕዝቡ!
ይጠብቃልና…እገባለት ኪዳን – ፈቅደህ ስጠኝ ስለው ይቺን ትልቅ ሃገር
ምን ይዤ ልማልለት – ምን ጨብጬ ልቁረብለት
ምንስ ብዬ ልናገር
እስኪ መላ ካለሽ – ተዋቡ – ካንቺ እንኳን ልበደር።
በማተቤ እንዳልምል
የባለሌጣ አንገቱም የእስላሙም ናት ይቺ ሃገር
በጊዮን እንዳልምል
ኦሞ፣ ጉደር፣ አዋሽ፣ ቦርከና፣ ባሮ፣ ተከዜ፣ ጉማራ በይው ሎኒያ
ሁሉም ገንዘቧ ነው
የቱ ከየትኛው በልጦብኝ – በየትኛው ልማልላት ለኢትዮጵያ!
ሽናሻ፣ ጋምቤላ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ፣ አገው፣ ወላይታ
ትግሬ በይው አማራ፣
በምድሯ የተቀነበበ ሁሉ በስሟ ነው የሚጠራ።
እህም…አለች ተዋቡ
እህም…አሁን እስላም ስትል – ሸማኔው ትዝ አለኝ
እጀ ወርቅ የሚሉት – አህመዴ ቦጋለ
በል ቶሎ በል ካሣ – አሽከር አስጠራልኝ – ገብርዬ የታለ
ገብርዬን አስጠራው
እሱ ነው የልቤ – ሲጋልብ የሚነፍስ
ከጎህ ቅዳጅ በፊት – መልዕክቴን ይዞልኝ – ከደጁ የሚደርስ።
ካሣን ግራ ገባው፣ ግን አይጠይቃትም፣
አምስት ስድስት ጊዜም እንደዚህ አዋክባው
እሷው ነድፋ፣ እሷው አባዝታ
እሷው አድርታ፣ እሷው ፈትላ
ባመጣችው ሃሳብ፣ ባሳየችው መላ
ብትንትን ሃሳቡን ገጣጥማ ስትሰፋው – አይቷልና ባይኑ
ለምን ማለት ትቶ፣ እንዴት ማለት ትቶ
«ገብርዬ ይጠራ» አለ ወዲያውኑ።
ገብርዬ
ከታንጉት ሙቅ እቅፍ
በውድቅት ተላቆ – ከነ ጋሻ ጃግሬው ገና እንደደረሰ
«እሰይ የኔ አንበሳ» ስትለው ተዋበች
ገና እንኳን በወጉ የወጉን እጅ መንሳት ሰጥቶም አልጨረሰ።
«እሰይ የኔ አንበሳ…
እንትፍ ይቺ ምራቅ ምድር መጥጧት ሳትከር
ስትገሰግስ ሄደህ…ደገኞቹ መንደር
አህመዴ ለሚባል
እጀ ወርቅ ሸማኔ … ቃሌን ቃል ሳትጨምር፣ እንዲህ ብለህ ንገር።
ባገር ሠማይ ስትፈልቅ
የቅርቡም የሩቁም እኩል እንደሚያያት የማሪያም መቀነት፣
በዚህ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ጥለት
አንተ ስትለካት – ሁለት ክንድ የሆነች – ጥብቅ ምት ባንዲራ፣
ሁነኛ አርጎ ሰርቶ
ነገ ማሪያም ድረስ – ይዟት እንዲመጣ – አጥብቀህ … አርቀህ ንገረው አደራ።
በማለት ተዋበች…
ግብጦች ለእጅ መንሻ – ከላኩላት መሐል -
የሃር የሆነውን ጥለት ጥድፍ ብላ
ለገብርዬ ሰጥታው – እሱም ጥድፍ ብሎ
ከነጀሌዎቹ ከወጣ በኋላ
ካሣ ፈገግ አለ፣
የጥድፈቷ ሚስጥር ቋጠሮው ተፈትቶ፣ ብትንትን ሃሳቡን
ባንድ ስላዋለ
ካሣ ፈገግ አለ።
ሺህ ስምንት መቶ አርባ አምስት – ዓመተ ምህረት
የተራራው አናት – ገና ሳይላቀቅ
ካድማስ ጥቁር እግር
ባህመዴ አማርኛ – ሠማዩ ሳይቀላ ባግባቡ ሳይፈጅር
አህመዴ ቦጋለ
የንጋት ስግደቱን – አስላምቶ አብቅቶ
ልክ! ፊቱን እያበሰ
ፊታውራሪ ገብርዬ
ከነጀሌዎቹ ደጁ ላይ ደረሰ።
የፈረሶች ኮቴ – ደጁን ሲረመርም የሰማው አህመዴ
ልቡ ድንግጥ አለ፣
«እንዲህ በማለዳ – የሚደርስ ከደጄ
መርዶ ነጋሪ ነው
ደሞ ማን ተለየኝ – የትኛው ዘመዴ?
ከቶ የኔ ሐዘን ዳርም የለው እንዴ
«እንዴት አደራችሁ…ቤቶች»
ይበልጥ ተረበሸ ይኼን ድምፅ ያውቀዋል፣
ምላሽም አልሰጠ፣ በርም አልከፈተ
ድርቅ ብሎ ቁሞ – ወይ ወንድሜን አለ
ክተት ሲባል ከቶ ከመይሣው ጋራ አብሮ የዘመተ
አንድ ወንድም ነበረው… ያ ወንድሙ ሞተ?
«ቤቶች…ቤቶች
ገብርዬ ጥሪውን እንዲህ ሲደጋግም
ገፋ አድርጎ ወጥቶ የጎጆውን ግርግም
ድሮ አውቄዋአለሁ
ለደግም አልነበር አደባባይ ቆሜ
ሸማ ሳውለበልብ ያየሁት በህልሜ
ወይ ወንድሜን ወንድሜ!
«የለ እንደሱም አይደል» ገብርዬ አቋረጠው
«ተዋበች ልካን ነው»
አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ጥለቱን ሰጠው።
አስከትሎ ደግሞ
ቃሌን ቃል ሳትጨምር – ያለችውን መልዕክት
ቃሏን ቃል ሳይጨምር – ረግጦ ሲነግረው
የመናቡ ተፍሲር – ብስራት ሆኖለት
እጀ ወርቅ ደስ አለው።
አለም፦
እንዴት ያንድ እናት ሆድ፣ አንድ ላይ ያበቅላል፣ አንድ ደህና አንድ ጠፍ
ብረገም ነው እንጂ
ክተት ሲል ከትቼ – እንደዚያ ወንድሜ – ከመይሣው ጋራ ጎኑ ማልሰለፍ፣
ብዬ እቆጭ ነበር፣… ይኼው ዛሬ ግና
አላህ ያለ ለታ፣ ላገር ሥራ ሲለኝ ረብ ያለው ሥራ
ያውም የመይሳውን ያውም የኢትዮጵያን … ያውም ያገሬን ባንዲራ
ያውም በኔ ጥበብ…
ያውም በሰው እጆች … ከሰውም በኔ እጆች … በሸማ እንድሰራ
ታሪክ እድል ሰጠኝ፣ ብሞትም አይቆጨኝ ከዚህስ በኋላ!
አህመዴ ሸለለ፣
አህመዴ ፎከረ … በደስታ ሰከረ፣ በደስታ አለቀሰ
ሩጦ ቤቱ ገባ፣ ሦስቱንም ልጆቹን – ሚስቱን ቀሰቀሰ።
ነገራት ለሚስቱ፣
ከምርጥ ዘሃ መሀል – ምርጡን ዘሃ መርጣ
እንድታቀርብለት – ቶሎ ብላ አዝግታ።
አዘዘ ልጆቹን
ቱባ ተከፋፍለው – ከየአንዳንዱ ጥለት
አሥር አሥር ቀለም – እንዲያዳውሩለት።
ሦስት ሰዓትም አልፈጀ
መቀነት ሸማቃው ከኖረበት ወርዶ
ዝግ ዘሃው ተቋጥሮ
ጥለቱ ተጥሎ.. ድምድሙ ተመትቶ – ባንዲራው ሲቆረጥ
በቅሎው ከጋጥ ወጥቶ
በጌጥ ተሸልሞ አህመድ ተነሚስቱ እጋማው ላይ ወጥቶ
እሱ – ሲኮለኩል – በቅሎው ንሮ ሲሮጥ … ሲሮጥ … ሲሮጥ
ደረስጌ ማሪያም ላይ ደርሰው ሆታው ሲቀልጥ
በዚያ መሀል አልፈው አህመድ ለመይሣው ባንዲራውን ሲሰጥ
ሰዓትም አልፈጀ
መይሣው ደስ አለው
የወርዱ ምጣኔ፣ የጠርዙ ጥብቅነት፣
የጥለቱ አጣጣል፣ ጥበቡ ደነቀው፣
ቁርጥማት አይንካህ
በሆዱ መረቀው
ካሣ ዞሮ ሄደ።
አህመዴ ተጣራ
መይሳው ዞር አለ
ባንዲራው ሲሰራ
ተርፎ ስለነበር ብዙ የሃር ጥለት ካቁማዳው አውጥቶ … እጁን ዘረጋለት።
ካሣ….!!
የዚህን ደሃ ሰው – ፍፁም ታማኝነት፣ ገራገር ልቦና ባስተዋለ ጊዜ፣
የጎንደር አዝማሪ ያቀነቀናትን በልቡ እያዜማት
በልቡ ያላትን … ያቺኑ ምርቃት…
ተባረክ እጅህን አይንካው ቁርጥማት
በአፉም ደገማት።
የጎንደር አዝማሪ በእነ አህመዴ ዘመን፣
«እስላም አልኩሽ እንጂ – እጁ የሚታመን
ሸማኔማ ሞልቷል ደሞ ለመሸመን»
ይል ነበር።                        

https://www.youtube.com/watch?v=rekboLUx2wI

Wednesday, November 19, 2014

የሚጸልዩ እጆች_እና_አልብሬሽት ዱረር

(እውነተኛ ታሪክ)
*************


ከስድስት ምእት ዓመታት በፊት በጀርመን ኑረምበርግ ከተማ በአንድ ትንሽ መንደር ውስጥ አሥራ ስምንት ልጆች ያሉበት አንድ ቤተሰብ ይኖር ነበር፡፡ አሥራ ስምንት! ለዚህ ሁሉ ማቲ ምግብ ለማቅረብ በሙያው አንጥረኛ የሆነው አባ ወራ በቀን አሥራ ስምንት ሰዓት በሙያውና ከሙያው ውጪ መሥራት ነበረበት፡፡

የቤተሰቡ የኑሮ ሁኔታ የከፋ ቢሆንም ከልጆቹ ውስጥ ሁለቱ ታላላቆች ልዩ ሕልም ነበራቸው ሥነ ጥበብን ማጥናትና ዝነኛ ሠዓሊ መሆን፡፡ አባታቸው ማንኛቸውንም ኑረምበርግ ወደ ሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ ልኮ ሊያስተምራቸው የሚያስችል የገንዘብ አቅም እንደሌለው ግን ሁለቱም ያውቁ ነበር፡፡

አንድ ምሽት በተጨናነቀው አልጋቸው ላይ ሆነው በሕልማቸው ዙሪያ ለረጅም ሰዓት ተወያዩና ወደ አንድ ስምምነት ደረሱ፤ ዕጣ ሊጣጣሉም ወሰኑ፡፡ በዕጣው የተሸነፈው በአቅራቢያቸው ወደ ሚገኝ አንድ የማዕድን ማውጫ ሄዶ እንዲሠራ፣ በሚያገኘውም ገቢ ወደ ከፍተኛ ትምህርት የሚሄደውን ወንድሙን እየረዳ እንዲያስተምር፡፡ ዕጣ የወጣለት ወንድም ደግሞ በኑረምበርግ ከተማ በሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ የአራት ዓመታት ትምህርቱን እንዲማርና ትምህርቱንም ሲጨርስ፣ በሚመረቅበት የሥነ ጥበብ ሙያ ከሚሠራቸው ሥዕሎች ሽያጭ በሚያገኘው ገቢ ወይም አስፈላጊ ከሆነ እርሱም በማዕድን ቁፋሮ ሥራ ተቀጥሮ በተራው ያስተማረውን ወንድሙን ሊያስተምር ወደ ውሳኔ ደረሱ፡፡

አንድ እሑድ ጠዋት ዕጣው ተጣለ፣ ታላቁ አልብሬሽት ዱረር የተባለው ወንድም ዕጣው ወጣለት፡፡ ኑረምበርግ ከተማ ወደ ሚገኘውም የሥዕል አካዳሚ ገባ፡፡

ዕጣ ያልወጣለት ወንድም ወደ አደገኛው የማዕድን ቁፋሮ ሥራ አመራ፣ ለተከታዮቹ አራት ዓመታትም ወንድሙን በገንዘብ እየረዳ አስተማረ፡፡ አልብሬሽት የአካዳሚው የሥዕል ትምህርት ተዋጣለት፡፡ በልዩ ልዩ የሥዕል ሥራዎች የተካነ ሆነ፡፡ የሚሠራቸው የቅብ ሥዕሎች ከመምሕራኖቹ ሥራዎች ይልቅ እየላቁና እይተወደዱ መጡ፡፡ በኮሚሸን ለሚሠራቸውም ሥዕሎች ዳጐስ ያለ ገንዝብ ይከፈለው ጀመር፡፡

ወጣቱ ሠዓሊ ትምህርቱን አጠናቆ ወደ መንደሩ ሲመለስ ቤተሰቡ በድል መመለሱን ምክንያት በማድረገ ድግስ ደግሶ ጠበቀው፡፡ በሙዚቃና በሳቅ በደመቀው ግብዣ መጨረሻ ላይ ሠዓሊው አልብሬሽት ከክብር ወንበሩ ተነሳና ለተወዳጅ ወንድሙ፣ ላመታት ስለከፈለው መስዋዕትነት፣ ሕልሙንም እንዲያሳካ ስለ ረዳው ጽዋ አነሳ፡፡ በመዝጊያ ንግግሩም፣ ‹‹የተባረክህ ወንድሜ አልበርት ሆይ፣ አሁን እንግዲህ ተራው ያንተ ነው፣ ወደ ኑረምበርግ ትሄዳለህ አንተም ሕልምህን ታሳካለህ፣ እኔም በተራዬ እንከባክብሃለሁ›› አለ፡፡

በገበታው የታደሙት ሁሉ አንገታቸውን ከገበታው አንድ ጥግ ላይ ወደ ተቀመጠው የማዕድን ሠራተኛ አልበርት አዞሩ፡፡ በገረጣው ፊቱ ላይ እንባው እየተንከባለለ በጉንጮቹ ላይ እይፈሰሰ ነው፣ ራሱንም ከግራ ወደ ቀኝ እያወዛወዘ፣ ሳግም እየተናነቀው ደጋግሞ፣ ‹‹አይሆንም….. አይሆንም ወንድሜ ሆይ፣….. አይሆንም!›› አለ፡፡

በመጨረሻ ብድግ ብሎ እንባውን ከጉንጮቹ ላይ በማበስ፣ አሻግሮም በገበታው ላይ የታደሙትን የሚወዳቸውን ፊቶች በፍቅር እየተመለከ፣ ሁለት እጆቹን አጣምሮ ወደ ቀኝ አገጩ በማስጠጋት ለስለስ ባለ ድምጽ ‹‹የለም ወንድሜ ሆይ፣ ወደ ኑረምበርግ ልሄድ አልችም፣ ለእኔ ዘግይቷል፣ የአራት ዓመታት የማዕድን ቁፋሮ ሥራ እጆቼን ምን እንዳደረጋቸው ተመልከትማ በጣቶቼ ላይ ያሉ አጥንቶች ሁሉ በቀን ቢያንስ አንድ ጊዜ ይጐዱ ነበር፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በከባድ የቁርጥማት በሸታ እየተሰቃየሁ ነው፣ በእርሳስና በብሩሽ በሸራ ላይ ሥዕሎችን መቀባት ይቅርና፣ አላስተዋልከኝም እንጂ፣ ጽዋችንን እናንሳ ስትል ጽዋውን ለመያዝ እንኳ የቀኝ እጄ አልቻለም፡፡ አሁን ለእኔ ዘግይቷል›› አለ፡፡

ይህ ታሪክ ከተፈጸመ ከ450 ዓመት በላይ አልፈዋል፡፡ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ የአልብሬሽት ዱረር እጹብ ድንቅ ሥራዎች፣ የራስ ምስሎች፣ የእርሳሰና የውኃ ቀለም ቅቦች፣ የቻርኮል ሥራዎች፣ የእንጨት ቅርጻ ቅርጾችና፣ የመዳብ ውቅሮች በመላው ዓለም ባሉ ሙዚየሞች ተሰቅለው ይገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ ብዙ ሰዎች ከሌሎች ሥራዋቹ ይልቅ ‹‹እጆቹ›› የሚለው ሥራውን ቅጅ በየቤቶቻቸውና ቢሮዎቻቸው ግድግዳዎች ላይ አንጠልጥለውታል፡፡

አንድ ቀን ወንድሙ ለከፈለለት መስዋዕትነት አክብሮት ለመስጠት፣ አልብሬሽት ዱረር በከፍተኛ ጥንቃቄ የወንድሙን የተጎዱ እጆች፣ መዳፎቹ ተጋጥመው፣ ቀጫጭን ጣቶቹ ወደ ሰማይ ተዘርግተው የሚታዩበትን ሥዕል ሳለ፡፡ ይህን ድንቅና ኃያል ሥራውንም ‹‹እጆቹ›› የሚል ስያሜ ሰጠው፡፡ ብዙም ሳይቆይ በዓለም ዙሪያ ሥዕሉን የተመለከቱ ሁሉ፣ ለዚህ ታላቅ እጹብ ድንቅ ሥራ ልባቸውን ከፈቱለት፡፡ ይህን ከፍቅር የተነሳ የተሳለ ሥዕልም ‹‹የሚጸልዩ እጆች›› ብለው ሰየሙት፡፡



አልብሬሽት ዱረር (Albrecht Dürer) ማን ነው?
 
Albrecht Dürer (German: 21 May 1471 – 6 April 1528)


ንደ አውሮፓው አቆጣጠር ግንቦት ፳፩ ቀን ፲፬፻፸፬ ኑረምበርግ ጀርመን ተወልዶ በ፶፮ ዓመቱ (ሚያዚያ ፮ ቀን ፲፭፻፳፰) እዛው ኑረምበርግ ከተማ የሞተው አልብሬሽት ዱረር (ከዚህ በኋላ ዱረር ብለን እንጠራዋለን) (German: [ˈalbʁɛçt ˈdyːʁɐ]) የተሳካለት የወርቅ ኣንጥረኛና ከሃንጋሪ ወደ ኑረምበርግ የፈለሰው አባቱና እናቱ ሦስተኛ ልጅ (ሁለተኛው ወንድ) ሲሆን፤ ወላጆቹ ከ፲፬ እስከ ፲፰ ልጆች እንደነበራቸው ይገመታል።
      ዱረር ለጥቂት ዓመታት ትምህርቱን ከተከታተለ በኋላ የወርቅ አንጥረኝነትና የስዕል ሙያ መሰረቶችን ከአባቱ ተማረ። ምንም እንኳን አባቱ በአንጥረኝነቱ እንዲቀጥልበት ቢፈልግም፤ በጣም ላቅ ያለ የስዕል ችሎታ በማሳየቱ ምክኒያት ገና በ፲፬ ዓመቱ በኑረምበርግ ታዋቂ አርቲስትና የኪነ ጥበብ ማዕከል (የአርት ወርክ ሾ) ባለቤት ለነበረው ሚካኤል ዎልጌሙት (Michael Wolgemut) ረዳት ሆነ።
 
 ‹‹የሚፀልዩ እጆች›› /Betende Hände/ በእንግሊዘኛ Praying hands (በጀርመንኛም Studie zu den Händen eines Apostels in German, ወይም "Study of the Hands of an Apostle": የሐዋሪያው እጅ ጥናት) በመባል የሚታወቀው በብዕርና ቀለም በጀርመናዊው የኪነ ጥበብ ሰው አልብሽሬት ዱረር በ፲፭፻፰ የተሰራ ሲሆን፤ ይህ ሥራ ቪየና/ኦስትሪያ (Vienna, Austria) በሚገኘው አልበርቲና (Albertina) ሙዚየም ይገኛል።በብዕርና (እራሱ በሰራው) ሰማያዊ ወረቀት ላይ ዱረር ነጩ ሄይተኒንግ በመባል የሚታወቀውን ቴክኒክ ለዚህ ስራው ተጠቅሟል። ሥዕሉ እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ የሚፀልዩ ሁለት የወንድ እጆች ሲሆን፤ የቀኙ እጅ ሙሉ ክፍል ካለመታየቱ ባሻገር፣ የፀላዩን እጅ የሸፈነው ልብስ (ክሳድ) ጫፍ በጥቂቱ ወደላይ ተቀልብሶ ይታያል። ይህ ሥዕል በ፲፯፳፱ በእሳት የነደደው ባለ ሶስት ክፍሉ የሄለን መስዋዕት ማቅረቢያ (the Heller altar,) በመባል ይታወቅ ለነበረው የዱረር ሥራ መካከለኛው ክፍል ላይ ለተሳለው ሐዋሪያ እጅ (an apostles' hand) እንዲሆን ታስቦ የተነደፈ ነው። ይህ የእጅ ንድፍ ሊደረግ በታሰበበት ሥዕል በመካከለኛው ክፍል በቀኝ በኩል በተመሳሳይ ግን በትንሽ መጠን ተስሎ ይገኛል። በወረቀቱ የሐዋሪያው ራስ ንድፍ የተሰራበት ቢሆንም፤ ሁለቱ የተቀመጡት ተለያይተው ነው። ዱረር ለዚህ (የሄለን መስዋዕት ማቅረቢያ) ስራው በጠቅላላ ፲፰ ንድፎችን ሰርቷል። ቪየና ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሕዝብ ዕይታ በ፲፰፻፸፩ ቀረበ። ሥራው ምናልባት የሰሪው እጅ እንደሆነ ይገመታል።
 
*******************************************************************************

ምንጭ፥ http://www.ethiopianreporter.com/issues/Reporter-Issue-1419.pdf __ኃይል   ከበደ «ምስካይ» (2004)
         :- http://enaseb.blogspot.com/2013/12/blog-post_2986.html 
         :-  የ ኛ ጉ ዳ ይ - Yegna Guday Blog