ከደራሲያን ዓምባ

Monday, November 28, 2022

22ኛው የዓለም ዋንጫ በኳታር_2022

22ኛው የዓለም ዋንጫ ኳታር 


በባህረሰላጤዎች የተከከበች
ኳታር ልዩ መልክዓምድር ያላት አገር ናት።  በምዕራብ እስያ የምትገኝ ሲሆን በሰሜን ምስራቅ የኳታር ባህረሰላጤ፤ በደቡብ በኩል የሳውዲ አረቢያ ባህረሰላጤ፤ የተቀረው ግዛቷ በፋርስና በባህሬን ባህረሰላጤዎች  ተከብቧል። የዓለማችንን ረጅሙን የባህር ጠረፍ  በ534 ኪሜትር አስመዝግባለች፡፡ በ338 ጫማ ከፍታዋ ከዓለማችን ረባዳማ ስፍራዎች በሁለተኛ ደረጃ የምትጠቀስ ሲሆን አንደኛውን ደረጃ በ6 ጫማ ከፍታ የያዘችው ማልድቪስ ናት፡፡  ካ ሆር አልአዳይድ  Khor Al Adaid የተባለው ክልል ባህርና በረሐ ከሚገናኝባቸው የዓለማችን አስደናቂ ስፍራዎች አንዱ ሲሆን በዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ሆኖ እንዲመዘገብ ጥረት እየተደረገ ነው፡፡



የውጭ አገራት ዜጎች የበዙበት
የኳታር አጠቃላይ የህዝብ ብዛት ከ2.6 ሚሊዮን በላይ እንደሆነ የሚገመት ሲሆን የውጭ አገራት ዜጎች አብላጫውን ቁጥር ይይዛሉ። ከህዝቧ 12%  እስከ  315,000 ኳታራዊያን ሲሆኑ 88 በመቶው ከ2.3 ሚሊዮን በላይ ከተለያዩ አገራት የገቡ ስደተኞች ናቸው። በኳታር ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የውጭ ዜጎች ህንዳውያን ሲሆኑ እስከ 700ሺ ይደርሳሉ። 40% ከአረብ፤  36% ከደቡብ ኤስያ፤ 18% ከህንድ፤ 18% ከፓኪስታን፤ 10% ከኢራን እንዲሁም 14% ከተለያዩ የዓለም አገራት የመጡ ዜጎች ይገኙበታል፡፡


የቱሪዝም መስህብነቷ

ኳታር በቱሪዝም መስክ ፈጣን እድገት ካሳዩ አገራት አንዷ ነች። በየዓመቱ ከ2.3 ሚሊዮን በላይ አለም አቀፍ ቱሪስቶች ይጎበኟታል፡፡  በቅርቡ ባደረገችው የቪዛ ማሻሻያ የ88 ሀገራት ዜጎች ከቪዛ ነፃ እንዲገቡ አድርጋለች፡፡ ይህም በመካከለኛው ምስራቅ ካሉ የአረብ አገራት ተወዳጅ የቱሪስት መናሐርያ ያደረጋት ሆኗል። ከዓለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ የእግር ኳስ አፍቃሪዎችና ቱሪስቶች እንደሚጎበኟትም ይጠበቃል፡፡ ከኳታር የቱሪዝም መስህቦች መካከል የአርኪዮሎጂ ስፍራዎች፤ የባህር ዳርቻዎች፤ ወደቦች፤ ሙዚዬሞች፤ ብሄራዊ ፓርኮችና የገበያ ማዕከሎች ይጠቀሳሉ።


የአልታኒ ቤተሰብ

ከ1868 እኤአ ጀምሮ ኳታርን የሚያስተዳድረው መንግስት በአልታኒ ቤተሰብ የሚመራ ነው፡፡ የቤተሰቡ ልዩ አስተዳደር ስልጣን ላይ የወጣው ከኳታር እና ባህሬን ጦርነት በኋላ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የአገሪቱ ኢምር ወይም መሪ ታሚም ቢን ሃማድ አልታኒ የሚባሉ ሲሆኑ ከ203 እኤአ ጀምሮ በስልጣን ላይ ናቸው፡፡ የቤተሰቡ የሃብት መጠን ከ335 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ ይገመታል፡፡ የአልታኒ ቤተሰብ በዓለም በስነጥበብ ስራዎች ላይ ኢንቨስት በማድረግና በመግዛት ግንባር ቀደም ናት፡፡
የዓለም ስነጥበብ ዋና ሰብሳቢ
በኳታር የመንግስት አስተዳደር ላይ የሚገኙት የአልታኒ ቤተሰብ በእስልምናና ዘመናዊ ስነጥበብ ፍቅራቸውና አሰባሳቢነታቸው ይታወቃሉ፡፡ ከ14 ዓመታት በፊት በአረቡ ዓለም ምርጡን የእስልምና ጥበብ ሙዚየም The Museum of Islamic Art  መስርተዋል፡፡  በኳታር ሙዚየሞች ባለስልጣን ስር የሚተዳደሩ ሌሎች በርካታ ሙዚየሞች በዶሃ ከተማ ውስጥ የተገነቡ ሲሆን Arab Museum of Modern Art ይጠቀሳል፡፡ በመላው ዓለም ከ65 በላይ አገራትን የወከሉ ከ300 በላይ አርቲስቶችን የሚያስተናግደው ኳታር ኢንተርናሽናል አርት ፌስቲቫልም QIAF  አገሪቱ ለስነጥበብ የሰጠችውን ትኩረት ያመለክታል፡፡


ሙሉ ከተማ የሆነው ሃማድ

ሃማድ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በ2021 እኤአ ላይ ስካይትራክስ በሰጠው የዓለም አየር ማረፊያዎች አዋርድ ላይ የዓለም ምርጥ ተብሏል። ተመሳሳይ ሽልማትን ለ6 ጊዜያት በመውሰድም ከፍተኛውን ስኬት አስመዝግቧል፡፡ የአየር ማረፊያው የአውሮፕላን መንደርደርያ እስከ 4850 ሜትር ርዝማኔ በማስመዝገብ በምዕራብ ኤስያ ቀዳሚው ሲሆን በዓለም በ6ኛ ደረጃ የሚጠቀስ ነው፡፡ በሰባቱም አህጉራት የበረራ መስመሮችን በመዘርጋትም የሚታወቀው አየር ማረፊያው፤  በዓመት እስከ 50 ሚሊዮን ተጓዦችን ያስተናግዳል፡፡ ተመሳሳይ አቅም ያላቸው የአየር ማረፊያዎች የቶኪዮው ሃኔዳ፤ የሲንጋፑር ቻንጊ፤ ተዱባዩ ዲአየኤ እና የለንደኑ ሂትሮው ናቸው፡፡ የሃማድ ዓለም አቀፍ ማረፊያ 29 ስኩዌር ኪሎሜትር በመሸፈን  በግዝፈቱ ከዓለም በ9ኛ ደረጃ ይቀመጣል፡፡ ቅጥር ጊቢው ከ100 በላይ ህንፃዎች ፤ ከ100 በላይ ሱቆችና ሬስቶራንቶችን ይዟል፡፡


ኳታር ኤር ዌይስ


ኳታር ኤርዌይስ በዓለም ዙርያ ከ45 ሺ በላይ ሰራተኞችን ቀጥሮ የሚያስተዳድር ነው። ከዓለማችን ትልልቅ አየር መንገዶች አንዱ ሲሆን ከዶሃ በመነሳት  ከ150 በላይ ዓለምአቀፍ መዳረሻዎች አሉት፡፡


የአየር ማቀዠቀዣ ያላቸው ስታድዬሞች
22ኛው የዓለም ዋንጫው የሚካሄዱትን 64 ጨዋታዎች የሚያስተናግዱ 8 ስታድዬሞች ልዩ አየር የማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂ  ተገጥሞላቸዋል። በጨዋታ ሜዳ ላይ የሚያስፈለገውን የሙቀት መጠን ለማመጣጠን ተግባራዊ በሆነው ቴክኖሎጂ በየስታድዬሙ ያለውን የሙቀት መጠን  እስከ 26 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ እንዲሆን ማድረግ ተችሏል፡፡ የአየር ማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂው ዘላቂ እና ኃይል ቆጣቢ በሆነ መንገድ ከመስራቱም በላይ በየስታዲየሙ የሚገኘውን ተመልካች በመመርኮዝ የሙቀት መጠኑን መቆጣጠር የሚቻልበት ነው፡፡



የኤሌክትሪክ አውቶብሶች
22ኛው የዓለም ዋንጫ ላይ ተግባራዊ ከሚሆኑ አስደናቂ ቴክኖሎጂች መካከል በኤሌክትሪክ የሚሰሩ አውቶብሶች ይገኙበታል። ደጋፊዎችን ወደ ስታዲየሞችና ወደ የተለያዩ የዶሃ ከተማ ስፍራዎች የሚያመላልሱ ናቸው፡፡  በዓለም ዋንጫ ታሪክ የኤሌክትሪክ አውቶቡሶች ለትራንስፖርት አገልግሎት ሲውሉ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን በከፍተኛ የቴክኖሎጂ የመረጃ መሳሪያዎች የሚታገዙ የትራንስፖርት አገልግሎት ናቸው።


ከጨዋታ ውጭን የምትቆጣጠረው ኳስ
አል ሪሃላ Al Rihla ለ22ኛው የዓለም ዋንጫ በአዲዳስ የተሰራች ኳስ ናት፡፡ የዓለም ዋንጫዋ ኳስ  እውነተኛ መረጃን ለVAR ባለሙያዎች የምታስተላልፍ፤ ፊፋ ለመጀመርያ ጊዜ ተግባራዊ ከሚያደርገውና በከፊል አውቶሜትድ ከሆነ የኦፍሳይድ መቆጣጠርያ ቴክኖሎጂ ጋር በመናበብ የምትሰራም ነች፡፡ በሜዳው ዙርያ የሚገጠሙ  12 ካሜራዎችን ከኳሷ እንቅስቃሴ ጋር በማዋሃድ  የሚሰራ ቴክኖሎጂ ተለጥፎባታል፡፡ከጨዋታ ውጭ የሆኑ ኳሶችን ለመቆጣጠር ፊፋ ተግባራዊ የሚሆነው አዲስ ቴክኖሎጂ ዳኞች ትክክለኛ ውሳኔዎችን እንዲሰጡ ያግዛቸዋል፡፡



ረጅሙ የብስክሌት ጎዳና

ኳታር የዓለማችንን ረጅሙን የብስክሌት ጎዳናም ገንብታለች፡፡ በዶሃ የሚገኘው የኦሎምፒክ ደረጃ ያለው የብስክሌት ጎዳና በ33 ኪሜ ርዝማኔው በጊነስ ሪከርድ ሬከርድ የተመዘገበ ነው፡፡ ከጎዳናው 25.3 ኪሜትር በአስፋልት ኮንክሪት መነጠፉም ክብረወሰን ላይ ሰፍሯል፡፡


ከዓለም ሃብታም አገሮች ተርታ
ኳታር በድፍድፍ ነዳጅ ና ተፈጥሮ ጋዝ በተገነባው ኢኮኖሚዋ ከዓለማችን ሃብታም አገራት ተርታ ትሰለፋለች፡፡    ነዳጅ የኢኮኖሚ ዋልታዋ ሲሆን በጥልቀት ከተቆፈሩ ጉድጓዶች አንዱ 12290 ሜትር ተለክቷል፡፡ ኳታር ከሉክሰምበርግ፣ ስዊዘርላንድና ሲንጋፖር በመቀጠል አራተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ የዓለም ሃብታም አገር ናት፡፡  አንድ የኳታር ዜጋ የነፍስ ወከፍ ገቢ እስከ 100ሺ ዶላር ይደርሳል፡፡


አረቢያን አጋዘን
አረቢያን አጋዘን የኳታር ብሄራዊ እንስሳ ሆኖ ይታወቃል፡፡ ይሄው አጋዘን  መሰል እንስሳ የኳታር ኤርዌይስ ሎጎ ሆኖ ያገለግላል፡፡ በ1972 እኤአ ላይ ከዱር የጠፋው እንስሳ ከ10 ዓመት በኋላ እንደገና ወደ ዱር እንዲመለስ በማድረግ በማድረግ የኳታር መንግስት ከምድር ገጽ እንዳይጠፋ ተረባርቧል፡፡



በዓለም ዋንጫ ታሪክ ከፍተኛው የገንዘብ ሽልማት
በዓለም ዋንጫው ታሪክ ከፍተኛ የሽልማት ገንዘብ የተመደበ ሲሆን አጠቃላይ መጠኑ 440 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ ከ4 ዓመታት በፊት ራሽያ ካስተናገደችው 19ኛው የዓለም ዋንጫ በ40 ሚሊየን ዶላር ጭማሪ አሳይቷል፡፡ የዓለም ዋንጫው አሸናፊ 46 ሚሊዮን ዶላር የሚያገኝ ያገኛል፡፡ በ21ኛው ራሽያ ላይ 38 ሚሊዮን ዶላር፤ በ20ኛው ብራዚል ላይ 35 ፤ በ19ኛው ደቡብ አፍሪካ ላይ 30፤ በ18ኛው ጀርመን ላይ 20  እንዲሁም በ17ኛው በጃፓንና ደቡብ ኮርያ ላይ 8 ሚሊዮን ዶላር ለዋንጫው አሸናፊዎች ተሸልሞ ነበር፡፡



ሌሎች ተሳታፊዎች የሚሸለሙት
በ22ኛው የዓለም ዋንጫ ለሁለተኛ ደረጃ 30 ሚሊዮን ዶላር፤ ለሶስተኛ ደረጃ 27 ሚሊዮን ዶላር፤ ለአራተኛ ደረጃ 25 ሚሊዮን ዶላር፤ ከአምስት እስከ 8ኛ ደረጃ ለሚያገኙት 17 ሚሊዮን ዶላር፤ ከ9 እስከ 16ኛ ደረጃ ለሚያገኙት 13 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ከ17 እስከ 32ኛ ደረጃ ለሚኖራቸው 9 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ የሚከፈል ይሆናል፡፡


የጭልፊት አደንና በረራ ስፖርት
በኳታር ጭልፊት ማልመድ፤ ልዩ የአደንና የበራራ ውድድር ማካሄድ የእግር ኳስን ያህል  አድናቂዎች እያፈራ ነው፡፡  የአየር ሙቀቱ ለጭልፊቶቹ ተስማሚ በሚሆንበት ጊዜ  ለአሸናፊዎች ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማቶች እየተዘጋጀ ልዩ ስፖርታዊ ውድድሮች ይካሄዳሉ። ጭልፊቶች ከኳታራዊያን የእለት ኑሮ  ፈጽሞ የራቁ አይደሉም፡፡ በዶሃ ከተማ ያሉ የጭልፊት መሸጫ ሱቆች የቅንጦት መኪና ከሚሸጥባቸው ማዕከሎች ደረጃቸው ይስተካከላል፡፡ ዋጋቸው ከ2000 ፓውንድ ጀምሮ እስከ 200ሺ ፓውንድ ይደርሳል፡፡



የግምሎች ሽቅድምድም

በኳታር ተወዳጅ ከሆኑ ስፖርቶች የግምሎች ሽቅድምድም ዋንኛው ነው፡፡ ስፖርቱ በዶሃ ከተማ ውስጥ አልሻሃንያ የሚባል ዘመናዊ የመወዳደርያ ትራክ ተሰርቶለት የኳታር ባህል መለያ ሆኗል፡፡  የስፖርት አይነቱ የቱሪስት መስህብ ሆኖ ቆይቷል። ከዶሃ መሃል ከተማ የአንድ ሰአት የመኪና መንገድ ርቆ የሚገኘው አልሻሃኒያ በግመሎች የሚካሄዱ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ውድድሮችን ያስተናግዳል፡፡ በአንድ አመት ውስጥ ከ6000 በላይ ግመሎች በዚህ ውድድር ይሳተፋሉ፡፡ ተወዳዳሪ ግመሎች በሰዓት እስከ 40 ማይል ይሮጣሉ፡፡


ቡርጃ ዶሃ
በዶሃ ከተማ ከሚገኙ አስደናቂ  ህንፃዎች ቡርጃ ዶሃ ታወር አንዱ ሲሆን በፈረንሳዊው አርክቴክት ጂን ኖቭል የተሰራው ባለ 48 ፎቅ ህንፃ ነው፡፡


 ማቻቡስ
ማቻቡስ የኳታር ተወዳጅ ብሄራዊ ምግብ ነው፡፡ ከሩዝ፤ ስጋ፤ ሽንኩርት፤ ቲማቲም እና ከጀተለያዩ ቅመማ ቅመሞች ጋር ተዋህዶ ይሰራል፡፡


ስፖርት አዘጋጅነት በኳታር
በ22ኛው የዓለም ዋንጫ መስተንግዶ ኳታር ከዓለማችን ታላላቅ የስፖርት መድረኮች የመጀመርያውን ማዘጋጀቷ ነው፡፡  በ2006 እኤአ ላይ ያዘጋጀችውን የኤስያ ኦሎምፒክ በ2030 እኤአ ላይም እንድታስተናግድ ተመርጣለች፡፡


አዳዲስ ታሪኮች የበዙበት የዓለም ዋንጫ
22ኛው ዓለም ዋንጫ  በታሪክ ትንሿ አገር የምታዘጋጀው፤ በፈረንጆች አዲስ አመት ዋዜማ ለመጀመርያ ጊዜ የሚካሄድ፤ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ እግር ኳስ አፍቃሪዎችና ቱሪስቶች የሚሳተፉበት፤ በድምሩ እስከ  5 ቢሊዮን ተመልካች እንደሚያገኝም የተገመተ ፤ እስከ 7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ሊያስገኝ እንደሚችል የተጠበቀ ነው፡፡



የምንግዜም ውዱ የዓለም ዋንጫ

በ220 ቢሊዮን ዶላር ወጭው የምንግዜም ውዱ ዓለም ዋንጫ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ከብራዚልና ከራስያ ዓለም ዋንጫዎች በ10 እጥፍ፤ ከደቡብ አፍሪካ ዋንጫ በ64 እጥፍ የሚልቅ በጀት ወጥቶበታል፡፡



*********

ግሩም ሠይፉ_ አዲስ አድማስ ጋዜጣ 

https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=30194:%E1%8B%93%E1%88%88%E1%88%9D-%E1%89%A0%E1%8C%89%E1%8C%89%E1%89%B5-%E1%8B%A8%E1%88%9A%E1%8C%A0%E1%89%A5%E1%89%80%E1%8B%8D-%E1%8B%A8%E1%8B%93%E1%88%88%E1%88%9D-%E1%8B%8B%E1%8A%95%E1%8C%AB-%E1%8A%90%E1%8C%88-%E1%89%A0%E1%8A%B3%E1%89%B3%E1%88%AD-%E1%8B%AD%E1%8C%80%E1%88%98%E1%88%AB%E1%88%8D&Itemid=101

https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=30164:%E1%8B%A8%E1%88%B0%E1%8B%93%E1%88%8A-%E1%89%B0%E1%88%B0%E1%88%9B-%E1%88%A5%E1%8A%90%E1%8C%A5%E1%89%A0%E1%89%A3%E1%8B%8A-%E1%8B%B2%E1%8D%95%E1%88%8E%E1%88%9B%E1%88%B2-%E1%89%A0%E1%8A%B3%E1%89%B3%E1%88%AD&Itemid=276


ዶሃ:- የባሕረ ሰላጤዋ ዕንቁ
(ከመኩሪያ መካሻ)

***************
የባብ ኤል ባህር ዳርቻ ነው። መሻሽቷል። ሂልተን ዶሃ ስምንተኛው ፎቅ ላይ ነው ያለሁት። ቁጥር 81ዐ። ከዚያ ፎቅ ላይ የዶሃ ከተማን ዙሪያ ገባ መመልከት ይቻላል። በቀን ብርሃን ዶሃን በወፍ በረር ከመቃኘት ይልቅ አመሻሹን መመልከት የልብ ሃሴትን ይሰጣል። ዶሃ የካጣር ዋና ከተማ ናት።


በመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢተ ኢሳይያስ የተጠቀሰውን ምዕራፍ 21ን መለስ ብዬ አነበብኩ። ‹‹ዐውሎ ነፋስ ከደቡብ እንደሚመጣ፣ እንዲሁ ከሚያስፈራ አገር ከምድረ በዳ ይወጣል›› ይላል። አዎን! Qatar ካጣር፣ (አንዳንዶች ኳታር ይሏታል) ምድረ በዳ ናት። ዳሩ ግን የምታስፈራ ምድረ በዳ አይደለችም። እንዲያውም ‹‹ማርና ወተት የሚፈልቅባት›› ቢባል ያንሳታል እንጂ አይበዛባትም። ይህች ትንሽዬ የባህረ-ሰላጤ ሀገር በዕንቁና በጥቁር ወርቅ ሀብቷ መትረፍረፍ ሰማይ ጥግ ደርሳለች።
የዛሬዋ ካጣር (Qatar) ከመመሥረቷ በፊት ጥንታዊቷ ካጣር የዕንቁ ንግድ የሚካሄድባት ነበረች። ከቻይና፣ ከአውሮፓ፣ ከአፍሪካውያን ጋር ስትነግድ ኖራለች። በ2ዐኛው ክፍለ ዘመን በእንግሊዝ የበላይ ጠባቂነት ሥር ስትተዳደር ቆይታለች። በ1971 (እ.ኤ.አ.) ነው ነፃነቷን የተጐናፀፈችው። ነፃነቷን ከማግኘቷ በፊት እንግሊዞች ባወጡት የነዳጅ ሀብት ትንሽየዋ ሀገር ፈረጠመች። ነፃነቷን ከመጐናፀፏ አንድ ዓመት በፊት ደግሞ የተፈጥሮ ጋዝ አገኘች። ከዚህ በኋላማ ማን ይድረስባት። ሀብት፣ በሀብት ሆነች። ተድላና ደስታ በእያንዳንዱ ካጣሪ ቤት ውስጥ ገባ። በነገራችን ላይ የዜጋው አማካይ የገቢ መጠን ከ9,5ዐዐ ዶላር በላይ ሁኗል። እስቲ ይህን ገቢ ከኢትዮጵያውያን ገቢ ጋር አስሉት፣ ከ14 እጥፍ በላይ ነው። ይህ የሀገሪቱ ሀብት ለ3ዐዐሺ ዜጐቿ ይከፋፈላል። በካጣር አስገራሚው ነገር የውጭ ሀገር ዜጋ ከሀገሬው ዜጋ በአሥር እጥፍ መብለጡ ነው። በየስፍራው የፓኪስታንን፣ የህንድን፣ የሲሪላንካን፣ የኔፖልን፣ የፊሊፒንስን፣ የዩክሬይን ወዘተ. ዜጐች የሀገሪቱን ህይወት ወደፊት ይመራሉ። ለአንድ ካጣሪ አሥር የውጭ ዜጋ ይደርሰዋል እንደማለት ነው።
ሳውዲን ከሳውዲ ቤተሰብ (House of Saud) የወጡት እንደሚመሯት ሁሉ ካጣርን የአል-ታኒ ቤተሰቦች (House of Thani) ይመሯታል። የዶሃን የዘንድሮውን ዓለማቀፍ ፎረም (Doha Forum) በንግግር የከፈቱት ዘንካታው ሼህ አልታኒ (ታማም ቢን ሃማድ አልታኒ) ነበሩ። ዛሬ በዓለማችን ታዋቂውን የአልጀዚራ የቴሌቪዥን ጣቢያ 15ዐ ሚሊዮን ዶላራቸውን ሆጭ አድርገው ያቋቋሙት እኚሁ ሰው ናቸው። በካጣር ከሌላው የዐረብ ዓለም የተሻለ ዘመናዊነትና የሴቶች መብት ይከበራል። በዶሃ ጐዳናዎች ረጃጅም ሌክሰስና ጂኤምሲ (GMC) መኪናዎችን ሴቶቹ በነፃነት ያሽከረክራሉ። የእኛ ሴቶች የሚያዘወትሯት ቪትዝ ትኖር ይሆን? ብዬ ነበር፤ አንድም ለዓይን የለችም። የካጣር ሴቶች ተነግሮ የማያልቅ ውበት አላቸው። ከጥቁሩ ሂጃብ ውስጥ ለተመለከታቸው የዕንቁ ፈርጦች ናቸው። ከነዚሁ ሴቶች አንደኛዋና ወደ ዶሃ የጠሩኝ ወይዘሮ ሎልዋህ ራሽድ አልካጠር ነበሩ። አዲስ አበባ ሲመጡ የካጣር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሆነው ሲሆን፣ አሁን ዶሃ ፎረም ላይ ሳገኛቸው በስልጣናቸው ጨምረው ጠበቁኝ። በሚፍለቀለቅ ፈገግታቸው ተቀበሉኝ። ‹‹ሹመት ያዳብር!›› አልኳቸው። ‹‹በናንተ መጀን የኢትዮጵያ ምልኪ (Omen) መልካም ነበር፣ ይኸው ለዚህ በቃሁ›› አሉኝ። በሉ፣ ይበርቱ!›› ብያቸው ተለያየን።
ከፊት ለፊት በሻይ ጠረጴዛ ዙሪያ ወ/ሮ ሙፈሪያት፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ከባለቤታቸው ጋር፣ አምባሳደሯ ወ/ሮ ሳሚያ ያወራሉ። ጠጋ ብዬ ተወወቅሁ። አለፍ ስል ወርቅነህ ገበየሁን ተመለከትኩ። ለሠላምታ እጄን ስሰነዝር በቁመታቸው ልክ የሞቀ ሠላምታ ሰጡኝ። ከዐቢይ መንግሥት ወዲህ የባለስልጣኖቻችንን የባህርይ ለውጥ ተመለከትኩ። ከመጀነን ይልቅ ሠላምተኛ ሆነዋል። ከእኔ ትይዩ የፍልስጤሟ የፖለቲካ ሰውና ቃል አቀባይ ሃናን አሽራዊ ተከበው ያወራሉ። እሳቸውንማ መተዋወቅ አለብኝ ብዬ ተጠጋሁ። ተዋወቅኳቸው። ‹‹ኢትዮጵያዊ ነኝ፣ ኦሪያና ፋላቺ የፃፈችውን የአቡ አማርን (የያሲር አረፋት የሽምቅ ስም) ቃለምልልስ ወደ ሃገሬ ቋንቋ ተርጉሜ አስነብቤያለሁ›› አልኳቸው። ፊታቸው ደስታን ረጨ። ፎቶ ራስ-ገጭ (ሰልፊ) ተነስተን ተለያየን። ሃናን ደስ አላቸው፤ እኔም ውስጤ ደስታን አዝሎ ተሰናበትኳቸው።
አለፍ እንዳልኩ በግራንድ ሸራተን መስተናገጃ ስፍራ ቡና ማፍያና ማቅረቢያ ስኒዎች የደረደረ ሰው ተመለከትኩ። ዕጣንም አጠገቡ እያጨሰ ሀድራው ሞቅ ብሏል። የቡና ሱሴ ውል አለብኝ። የሊሙ ኢናሪያን ቡና ሲለቅምና ሲጠጣ ላደገ ለእኔ ዓይነቱ ሰው ቡና ሁሉም ነገር ነው። የግራንድ ሸራተኑ ቡና ከእኛ ሀገሩ ቡና ጋር አይመሳሰልም። ልዩ አቀራረብና መልክ አለው። እንደኛው ዓይነት የፈረስ ጭራ የመሰለ ቡና አለመሆኑ ደንቆኛል። ጠጋ ብዬ ቡና ቀጂውን ሰዒድ አቡበከርን ‹‹ይቻላል?›› አልኩት። ግማሽ ፍንጃል ለቅምሻ የሚሆን ቀዳልኝ። ስመለከተው ጠጅ ሊያስቀምሰኝ የቀዳልኝ እንጂ ቡና አይመስልም። ለመጀመሪያ ጊዜ ብጫ ቡና ልጠጣ ነው። ፉት ስላት አለቀች። ፍንጃሉን መለስኩለት። ደገመኝና ቴምር ሰጠኝ፤ የሚገርም ቴምር፣ የሚገመጥ ቴምር ነበር።
የካጣር ቡና አይቆላም። ጥሬው ተጨምቆ ነው የሚፈላው። ለዚህም ነው መልኩ ብጫ የሚመስለው። ፍፁም አርኪ ቡና ነበር። ወዲያው ሱሴን አበረደልኝ። ‹‹ሹክረን›› ብዬ ሰዒድን ተሰናበትኩና ወደ ማረፊያዬ ተመለስኩ። የኤሌክትሮኒክ ቁልፉን ለበሩ አሸተትኩት። ተበረገደ። ለዓይን ያዝ ማድረግ ጀምሯል። የቁጥር 81ዐን መስኮት ከፍቼ ቀዝቃዛውን አየር ማግ፣ ማግ አደረኩ። የተለየ ጠረን አወደኝ። የቱስካኖ ሲጋራም፣ የሺሻም ሺታ መሰለኝ። ለማንኛውም ወደ ባህሩ ዳርቻ ልውጣ ብዬ ወደዚያው አመራሁ። የባብ ኤል ባህር ሰርጥ ዳርቻ አሸብርቋል። ከቡና ቤቱ የሚፈሰው ሙዚቃ ይንቆረቆራል። የሪታ ኦራ ‹‹Let you Love me›› ሙዚቃ ነው። የዌስት ቤይ የባህር ወጀብ ፋልማውን ተጠግቶ ይገማሸራል። ከባህሩ ወጀብ ጋር የቀዘቀዘ አየር እየማጉ ጊዜያቸውን ያሳልፋሉ። ነጫጭ ጀለቢያቸውን የለበሱ አሚሮች፣ ሼኮች፣ የዶሃ እመቤቶች ተቀምጠው የሺሻቸውን ኵርቢት ይምጋሉ። ስለ ቢዝነስ ያወራሉ። ስለፍቅርም ሊሆን ይችላል የሚያወሩት። አንዱ ሼህ ከኋላዬ ከሎንደን የቢዝነስ አጋሩ ጋር በሞባይሉ ያወራል። ጆሮዬን ጣልኩበት። በዶሃ 2ዐ22 በሚዘጋጀው የዓለም ዋንጫ ውድድር ስለሚያስገባው ዕቃ ነበር ድርድሩ። ‹‹ሦስት ቢሊዮን ነው?›› አለው። ጆሮዬን አላመንኩም። ሦስት ቢሊዮን! ‹‹ከሎንደን ወገን ከ2.6 እስከ 3 ቢሊዮን ዶላር ቢሆን ነው›› ይለዋል። ‹‹ችግር የለም ቶሎ እንዲገባ ይሁን!››። ‹‹Let you love me›› ሙዚቃን በዓይን የማዬት ያህል በኦራ ድምጽ ሲንቆረቆር ወደ ሌላ ትዝታ ይዞ ይነጉዳል። ሺሻ ይጨሳል፣ ድርድር ይካሄዳል። የዶሃ ወይዛዝርት ለሁለት፣ ለሦስት፣ ሆነው በሺሻ ማጨሺያ ክፍሎች ሺሻውን ይምጉታል። የዶሃ ምሽት እንዲህ እየተንተከተከች ከሺሻው ጭስ ጋር የዶሃ ወይዛዝርትና አሚሮች ሃሳባቸውን አራግፈው ከዶሃ ሂልተን ወደየቤታቸው ይለያያሉ።
ከባህሩ ፋልማ ላይ ተቀምጨ ስቆዝም ባህሩ ላይ ቱሪስቶች ምሽቱን ተጠግተው በፈጣን ጀልባ ይንሸራሸራሉ። እኔን ባደረገኝ ያሰኛል። መልካም ያበሻ ቅናት። በመሃሉ ጨረቃዋ ሰማዩን ቀዳ ከባህሩ ስትወለድ ታየችኝ። እኔ ከልምዴ ጨረቃን ሰማይ ሲያዋልድ ነው የማውቀው። በገልፍ ሀገሮች ግን ባህር ቀዳ የምትወጣ ነበር የምትመስለው። ከዚያም ባህሩ ላይ ባውዛዋን ረጨች። ለካስ ዐረቦች ከጨረቃ ጋር ያላቸው ቁርኝት ከምንም ተነስቶ እንዳልሆነ ገባኝ። ድምቀቷ ጤፍ የሚያስለቅም ነበር። ‹‹Let you love me›› ቀጥሏል።
ፋታ ሳገኝ ‹‹መቀመጥ-መቆመጥ›› በሚለው መርህ መሠረት ወጣ ማለት ፈለግሁ። የሆቴሉን አስተናጋጅ ግብፃዊ መሀመድን ‹‹ዬት ሄጄ ታሪካዊ ነገር ብቃኝ ትመክረኛለህ?›› ስል ጠየኩት። ‹‹ወደ ሱቅ ዋቂፍ ሂድ!›› ሲል መከረኝ። መቼም ዶሃና የዶሃ ፎቆች የሚጠገቡ አይደሉም። ሁሉም ፎቆች ትናንት አልቀው ርክክብ የተደረጉ የሚመስሉ ጥርትና ልቅም ያሉ ናቸው። የፎቆች ዝናብ በዶሃ የዘነበ ይመስላል። ዲዛይናቸው ምርጥ የተባሉና አስደማሚ ናቸው። የዶሃ ዘንባባዎች እንደ ክብር ዘብ በሰልፍ ቆመው ይዘናፈላሉ። ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ፈጥረዋል። አንዱን አይተው ሳይጨርሱ ሌላኛው ፎቅ ይማርካል። የከተሜነት አዋሲስ (illusion) ሰቅዞ ባለ በሌለ ሀይሉ ይይዛችኋል። ምናለ የእኛ አርክቴክቶች ለአንዲት ቀን ዕድል አግኝተው ቢያዩዋት ያሰኛል። የአል-ታኒ ቤተሰቦች ገንዘባቸውን በሀገራቸው ግንባታ ላይ ማዋላቸውን መመስከር ይቻላል። ከቤጂንግ፣ ወይም ከኒውዮርክ ፎቆች በላይ የጐብኚን ዓይን መማረክ የሚችሉ ናቸው። ፎቆች ላይ የሚለጣጠፉ ማስታወቂያዎች ዓይን አይረብሹም። ምናለ የእኛዎቹ የከተማ አስተዳዳሪዎች ዶሃን በጐበኙ ያሰኛል። የኢቢሲው አብዱል ጀሊል በህንፃዎቹ ከመማረኩ የተነሳ ቀንም ማታም ህንፃዎቹን ፎቶ ያነሳል። ‹‹ምን ዓይነት ተአምር ነው?›› እያለ መልስ የሌለው ጥያቄ ይጠይቃል።
እስቲ የዶሃን ታላቅ ሱቅ ልጐብኝ ብዬ ወደ ሱቅ ዋቂፍ (Waqif) አመራሁ። ሱቅ ዋቂፍ ከዶሃ ዘመናዊነት መንጥቆ ወደ ቀድሞ የዶሃ ጥንታዊነት የሚወስድ ቋሚ ገበያ ነው። ይህ የደራ ገበያ አልባሳት፣ ቅመማ-ቅመሞች፣ ዕጣኖች፣ ሽቱዎች፣ የዐረብ ጣፋጮች፣ የስጦታ ዕቃዎችና ስዕሎች ይገኙበታል። ከካጣር ዘመናዊነት ዓለም አውጥቶ የካጣር ጥንታዊነትን ለመጎብኘት ትክከለኛው ሥፍራ ሱቅ ዋቂፍ ለመሆኑ ጥርጥር የለውም። ባለእጆችና ባህላዊ ልብስ ሰፊዎች ይታዩበታል። የሶሪያ፣ የሊባኖስ መመገቢያ ሥፍራዎችና የሺሻ ማጨሻዎች ዓይንና ልብን ሰቅዘው ይይዛሉ። ዋጋቸው ግን ለአበሻ ኪስ የሚሆኑ አይደሉም። በዓይን ጠግቦ መውጣት የሚቻልበት ሥፍራ ሱቅ ዋቂፍ ብቻ ይመስለኛል።
ከጣርን ከገልፍ ሀገሮች ሁሉ እጅግ ተፈላጊ ያደረጋት ስትራቴጂካዊ አቀማመጧ ነው። የአሜሪካና የእንግሊዝ የአየርና የህዋ ኦፕሬሽን ማዕከል የሚገኘው እዚያ ነው፤ በአል ኡዴድ የአየር ምድብ። ይህ የኃያላን ሀገራት የዕዝና ቁጥጥር ማዕከል ከኢራን እስከ አፋጋኒስታን ዘልቆ 17 ሀገራትን ይቆጣጠራል። ስለዚህ ካጣር ዋና ስትራቴጂካዊ ማዕከልና ለአሜሪካኖቹ እጅግ አስፈላጊ ሀገር ናት። በዚህ ልዩ ቦታዋ ዓለማቀፋዊ ኮንፈረንሶችን ታዘጋጃለች። የዘንድሮው የዶሃ ፎረም እንኳ 4ዐዐዐ ሰዎችን ከ1ዐዐ ሀገራት አስተናግዷል። በዚህ ሸብ-ረብ ውስጥ ዋነኛውን ሚና የሚወጣው አልጀዚራ ሲሆን፣ የአልጀዚራ ጋዜጠኞች በአስተባባሪነት፣ በመድረክ መሪነት፣ በጠያቂነት፣ ሪኮርድ በማድረግ ይሳተፋሉ። የእኛን የኢትዮጵያውያንን ጉዞ ያደራጀልን ወዳጄ፣ ዕውቁ ጋዜጠኛና የአልጀዚራ የኢትዮጵያ የቢሮ ሃላፊ መሀመድ ጠሃ ተወከል በዚህ አጋጣሚ ሊመሰገን ይገባል። ሀገር ቤት ገብቼ ኢ-ሜሌን ስከፍት ሙሉ ዶክመንቱ ደረሰኝ። ደስም አለኝ።
የዶሃ ፎረም ስብሰባ እንደተጠናቀቀ ጉብኝቴን የቀጠልኩት በአልጀዚራ ጣቢያና የሚዲያ ማሠልጠኛ ተቋም ጉብኝት ነበር። አልጀዚራ ሚዲያ ከሥራውና ካለበት ህንፃ ጋር ሲወዳደር ‹‹አልጀዚራ እዚህ ሆኖ ነው እንዴ ዓለምን የሚያነጋግር ሥራ የሚሠራው?›› ያሰኛል። የተቋሙ አባል የሆነውና አስጐብኚያችን ሙንታሲር ሙራይ እንደነገረኝ ‹‹ለሚዲያ ጥንካሬ ዋናው ህንፃና ዕቃ ሳይሆን የያዘው ሙያተኛ ነው ወሳኙ›› ሲል ነበር የሰው ኃይልን ወሳኝነት የገለፀልኝ።
*****
የመጨረሻው የዶሃ አዳሬ ዶሃን ብቻ ሳይሆን ሀገሬን እንዳስብ አደረገኝ። አንዲት የባህረ-ሰላጤ ትንሽ ሀገር 3 ሚሊዮን ለሚበልጡ የውጭ ሀገር ዜጐች የሥራ ዕድል ፈጥራ ስታሰራ ስመለከት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ዬት ነን? እላለሁ። ቅናት አይሉት የውድድር አባዜ ብቻ በእዝነ-ልቡናዬ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ተመላለሱብኝ። ዛሬ የሚታየው የኢትዮጵያውያን እርስ በርስ መናከስ፣ መበላላትና የሰው ልጅ ሊፈጽመው ይችላል ተብሎ የማይታሰብ የአውሬነት ባህርይ ከየት መጣ? ስል ጠየቅኩ። ይህች የባህረ-ሰላጤ ዕንቁ ከተማና የእኛ ከተሞች ህይወት በንጽጽር በዓይኔ እየተደቀኑ በማይጐረብጠው፣ እጅግ ምቾት - በምቾት በሆነው 81ዐ ክፍል ውስጥ ዕንቅልፍ በዓይኔ ሳይዞር ነቃሁ። ለካስ ምቾትም እንቅልፍ ይነሳል?
ወለል ብሎ የዶሃ ሰማይ በርቷል። በመስኮት ስመለከት የባብ ኤል ባህር ዳርቻ ህይወት እያንሰራራ ነው። የባህረ-ሰላጤው ባህር ፋልማውን እየገጨ ይፎክራል። የዶሃ-ህይወት መንተክተኳን ቀጥላለች። በስሱ የተለቀቀ የEasy Listening ሙዚቃ ጆሮ ሰርስሮ ይገባል። የልብ ሀሴትን ይሰጣል። ‹‹Lake of Peace›› ሙዚቃ ነበር የሚንቆረቆረው።
አሁን ሰዓቱ ደረሰ። በፍቅር የጣለችኝን ዶሃ ለቅቄ መብረሬ ነው። ከኢትዮጵያ ከመጣነው የቡድን አባላት ጋር የሃማድ አለማቀፍ አይሮፕላን ማረፊያን መንገድ ተያያዝነው። የዶሃን ልዩ ከተማነት፣ የህዝቡን ሥርዓትና እንግዳ አክባሪነት እያደነቅን ሃማድ አለማቀፍ አይሮፕላን ማረፊያ ደረስን። በአይሮፕላን ጣቢያው ልክ እንደ ግራንድ ሸራተኑ የካጣር ቡና (ቃዋ ነው እነሱም የሚሉት) ተፈልቶ ጠበቀን። አንድ ፍንጃል ቃዋዬን አወራርጄና ቴምር ቀምሸበት ዶሃን ተለየሁ። ዶሃ የባህረ-ሰላጤዋ ዕንቁ ከተማ ሁሌም ከአእምሮዬ የምትጠፋ አትሆንም። የሪታ ኦራ ‹‹Let you love me›› አሁንም በውስጤ ይሞዝቃል።



https://www.facebook.com/photo/?fbid=5979201378771420&set=a.100394486652168

https://www.youtube.com/watch?v=TiTg-op7yc0

2፡የዓለም ዋንጫ 2022፡

የዓለም ዋንጫ 2022

የዓለም ዋንጫ 2022

የዓለም ዋንጫ 2022

የዓለም ዋንጫ 2022

Thursday, November 24, 2022

የጃፓን መንገድ

 የጃፓን መንገድ _ እንደ ማንቂያ ደወል


በፍቅር እወዳቸዋለሁ! እጅግ አከብራቸዋለሁ! ፍፁም የተለዩ ህዝቦች ናቸው! ሰለጠኑ ከሚባሉት ምዕራባውያኖቹ ጋር ሲነፃፀሩ በትንሹ 20 ዓመታትን ጥለዋቸው ሄደዋል!
"...ህዝቦቿ ደማቸውን አፍስሰው፣ አጥንታቸውን ከስክሰው የዛሬዋን ሃገራቸውን ገነቡ!" ቢባልላቸው አያንስባቸውም!
ፀዴ ናቸው፣ ስልጡን ናቸው፣ ሰው አክባሪ ናቸው፣ ሃገራቸውን አብዝተው ይወዳሉ ሳይሆን ያፈቅራሉ። ስልጣኔ ማማው ቢታይ ጃፓን ላይ ነው። የህዝብ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም! 126 ሚልዮን ገደማ ናቸው።
ቤትህ አልበላሽ ያለህ "Sony" ቴሌቪዥን የነሱ ነው፣ ያሳደገህ ብረቱ "Hitachi" ፍሪጅ የነሱ እጅ ያረፈበት ነው፣ ሃገራችንን ብቻ ሳይሆን ዓለማችንን ያጥለቀለቀው "Toyota" መኪና የነሱ ጥበብ ውጤት ነው፣ "Nikon" እና "Canon" ካሜራዎች የነሱ አሻራዎች ናቸው፣ እንደዛ በፍቅር የምትወደው "Toshiba" ላፕቶፕህ የነሱ ነው፣ "Mazda", "Lexus", "Mitsubishi", "Honda", "Nissan", "Isuzu", "Suzuki" ምናምን የምትላቸው መኪናዎች የተፈበረኩት በነሱ ነው። እጃቸው የነካው ምርት ሁሉ ብሩክ እና ብረት ነው።
ከሁሉም በላይ የሚደንቀኝ የጃፓናዊያን የስራ ባህል ነው። የእረፍት ትርጉሙ አይገባቸውም! የዓለማችን ረጅም ሰዓታቸውን በስራ ላይ የሚያሳልፉ ዜጎች ጃፓናዊያን ናቸው። በስራ ብዛት የሰው ልጅ የሚሞተው ጃፓን ውስጥ ብቻ ነው! ሞቱን "Karoshi" ብለው ይጠሩታል። በዓመት ካላቸው የ 20 ቀን እረፍት ውስጥ 10 የሚሆነውን እንኳን በአግባቡ አይወስዱም። 63% የሚሆኑ ጃፓናዊያን በእረፍት ሰዓታቸው በሚከፈላቸው ገንዘብ ደስተኛ አይደሉም። ጌታዬ! መንግስት "....የአመት እረፍታችሁን እባካችሁ ውሰዱ! በስራ ብዛት እና ጭንቀት እየሞታችሁ ነው! እስቲ ትንሽ ዘና በሉ!..."ብሎ ሲለምን የምትሰማው የጃፓን መንግስትን ብቻ ነው።
ከለሊቱ 9 ሰዓት ላይ የጃፓን መንገዶችን ብትመለከት ሽክ ብሎ ሱፉን ለብሶ እና "briefcase" ይዞ ወደ ስራ የሚሄድ ብዙ ሰው ታያለህ። አብዛኛው ጃፓናዊ "ለምን ትሰራለህ?" ተብሎ ሲጠየቅ "ሃገሬን ስለምወድ እና ብቁ ዜጋ ሆኜ መገኘት ስላለብኝ!" ብሎ ይመልስልሃል። ያለ እረፍት ከመስራታቸው ብዛት የጃፓን መስሪያ ቤቶች ውስጥ ጠረጴዛቸውን ተደግፈው የሚያንቀላፉ ሰዎችን ማየት የተለመደ ነው። የታታሪነት፣ የብርቱነት እና ሃገር ወዳድነት መገለጫ ነው። ከአጠቃላይ ህዝብ ቁጥሩ ውስጥ 3% የሚሆነው ብቻ ስራ አጥ ሲሆን ሰዎች ስራ ፈትተው በመቀመጣቸው ምክንያት በጭንቀት እራሳቸውን የሚያጠፉባት ሃገር ናት።
ተማሪዎቿ!
ከዓለማችን ብቁ ተማሪዎች ተርታ ይሰለፋሉ። 100% የሚሆነው የሃገሪቷ ወጣቷ በሚገባ ፊደል የቆጠረ እና ቀጥቅጦ የተማረ ነው። ህፃናት ሃገራቸውን እንዲወዱ፣ ቤተሰባቸውን እና ማህበረሰባቸውን እንዲያከብሩ ተድርገው ያድጋሉ! የጃፓን ትምህርት ቤቶች ውስጥ የፅዳት ሰራተኛ አይቀጠርም! "ለምን?" ካልከኝ ከትምህርት በኃላ ሁሉም መምህራን እና ተማሪዎች ለ 15 ደቂቃ ልብሳቸውን ቀይረው ትምህርት ቤቱ ውስጥ የሚገኙ ሁሉንም ክፍሎች(መፀዳጃ ቤትን ጨምሮ) እኩል ያፀዳሉ! የጃፓን ተማሪዎች በሂሳብ፣ ፊዚክስ እና ቋንቋ መጎበዝ ግዴታቸው ነው። ተማሪዎች የፍቅር ግንኙነት መመስረት አይችሉም! እሱ ብቻ ሳይሆን ትምህርት ቤት ውስጥ መሳሳምም ሆነ መተቃቀፍ አይቻልም፣ ያስቀጣል፣ አለፍ ካለም ያስባርራል!
# 1 ገራሚ ነገር አንድ!
የዓለማችን ትልቁ አማካይ የመኖርያ እድሜ ያለው ጃፓን ነው። አንድ ጃፓናዊ በአማካይ 83 ዓመት ይኖራል። ውፍረት እንደ ሃጥያት የሚቆጠርባት ጃፓን ውስጥ የተዝረጠረጠው ህዝብ ከ 4% አይበልጥም። ጌታዬ! ይህ አሃዝ አሜሪካ ውስጥ 40% ነው! የመኖራችን ሚስጥር ስፖርት፣ አሳ እና ቅጠላ ቅጠል ነው ይላሉ! ብታምነኝም ባታምነኝም ጃፓን ውስጥ 50 ሺህ እድሜያቸው ከ 100 በላይ የሆኑ ሰዎች ይኖራሉ!
# 2 ገራሚ ነገር ሁለት!
የጃፓን ዋና ከተማ የሆነችው "ቶክዮ" ውስጥ ብቻ 38 ሚልዮን ህዝብ ይኖራል! አባዬ! አዲስ አበባ ከ 10 ሚልዮን በታች ሆና ነው እንግዲህ ልንፈነዳ የደረስነው!😀
ይህንን 38 ሚልዮን ህዝብ በብዛት ከቤት ወስዶ ወደ ቤት የሚመልሰው ባቡር ነው። ባቡር ስልህ ታድያ መሃል ላይ መብራት ጠፍቶበት የሚቆመውን አይደለም! የዓለማችን ቁጥር አንድ ቀጠሮ አክባሪ ባቡሮች ያሉት እዛ ነው። አረፈዱ ከተባለ 6 ሰከንድ ነው! አንዴ አንድ ባቡር 18 ሰከንድ አርፍዶ ጉድ ተብሏል! ስራ በሃገሪቷ ባቡሮች መዘግየት ምክንያት ብታረፍድ እራሱ ባቡር ጣብያው "...እገሌ የሚባለው ስራተኛችሁ ያረፈደው በእርሱ ድክመት ሳይሆን በእኛ እንዝላልነት ነውና ይቅርታ!..." የሚል ደብዳቤ ሰጥቶህ ትሄዳለህ! በሰዓት ከ 320 ኪሎ ሜትር በላይ የሚበሩ "bullet train" የሚባሉ ባቡሮች ያሉት እዛ ነው! ጃፓኖች ጋር ባቡር ውስጥ ድምፅን ከፍ አድርጎ ማውራት ሳይቀር እንደ ነውር ይቆጠራል!
# 3 ገራሚ ነገር ሶስት!
የምትስተናገድበት ሆቴል ወይም ሬስቶራንት ውስጥ "Tip" ለአስተናጋጅ መስጠት ነውር ነው። ለአንድ አስተናጋጅ "Tip" አስቀምጠህለት ብትሄድ እየሮጠ ተከትሎህ ይመልስልሃል! ለምን?
"...አንተን ማስተናገድ እና መንከባከብ ግዴታችን ነው፣ ስራችን ነው! ለዚህ ስራችን ደግሞ ደሞዝ ይከፈለናል! ስለዚህ ተጨማሪ ብር በ "Tip" መልክ መስጠት አይጠበቅብህም!..." ይሉሃል! እጅግ ሰው አክባሪ እና ትሁት ከመሆናቸው የተነሳ ማንኛውንም እቃ፣ ምግብ ወይም መጠጥ በሁለት እጃቸው እንጂ በአንድ እጃቸው በፍፁም አይቀበሉህም! እሱንም ከወገባቸው ጎንበስ ብለው ነው። የሚገርመው ቤት ውስጥ ውጪ የዋልክበትን ጫማ አድርጎ መግባት ነውር ነው። አይደለም ቤትህ አንዳንድ ምግብ ቤቶች ሳይቀር ተስተናጋጆች ጫማቸውን አድርገው እንዲገቡ አይፈቀድም! በር ላይ ሸበጥ/ሲሊፐር ስለሚቀመጥልህ ቀይረህ መግባት ግድ ነው።
# 4 ገራሚ ነገር አራት!
የዓለማችን ሶስተኛው ግዙፍ ኢኮኖሚ የጃፓን ሲሆን ከአጠቃላይ ኤክስፖርት ከሚያደርጉት ምርት 23% የሚሆነው መኪና ነው። 38% የሚሆነው ደግሞ ኤሌክትሮኒክስ ምርት ነው። 98% የሚሆነው ህዝብ በብሄር፣ በቋንቋ እና በባህል ተመሳሳይ(Homogeneous) ነው። ጃፓናዊያን እጅግ ስርዓት ያላቸው፣ ሰው አክባሪዎች እና በህግጋት የተመሉ ስለሆኑ ከሌላ ሃገራት ለስራም ሆነ ለጉብኝት የሚመጡ ሰዎች ጃፓን ውስጥ መኖር ይቸገራሉ!


# 5 ገራሚ ነገር አምስት!
ለሃገር ቅድሚያ መስጠት፣ ለሃገር ክብር መሞት(መሰዋት) እና ለሰዎች ቅድሚያ መስጠት ጃፓን ውስጥ እንደ ባህል ይቆጠራል። የ "Titanic" መርከብ በሰመጠችበት ወቅት እንደምንም ብሎ የተረፈ አንድ ጃፓናዊ ወደ ሃገሩ ሲመለስ "እራስ ወዳድ ነህ! እንዴት መርከቧ ስትሰጥም ከሞቱት ሰዎች ጋር አብረህ አትሞትም!?" ተብሎ እንደተንቋሸሸ ይነገራል!
አስደማሚ ታሪክ!
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት (እ.ኤ.አ 1939-1945) ጃፓን በአሜሪካ ከፍተኛ ሽንፈት እየገጠማት ትመጣለች! የጃፓን የጦር ጀቶች በቀላሉ በአሜሪካ እየተመቱ መውደቅ ይጀምራሉ! ወታደሮቿም ማለቅ ጀመሩ! ጦርነቱን መሸነፋቸውም እውን እየሆነ ይመጣ ጀመር!
በወቅቱ የጃፓኑ ንጉስ ጋር ወታደሮች እና የጦር አውሮፕላን አብራሪዎች እየተሸነፉ መምጣታቸው አሸማቋቸዋል! እንደ አምላክ የሚታየው የሃገሪቱ ንጉስም "...ተሸንፋችሁ ከምትመጡ ለሃገራችሁ እና ለዙፋኔ ክብር ስትሉ አጥፍታችኃቸው ጥፉ!..." ብሎ አዘዛቸው!
ጌታዬ!
የጦር አውሮፕላን አብራሪዎቹ ሳያቅማሙ ተስማሙ! እራሳቸውንም "kamikaze pilots" ብለው ሰየሙ። ለሃገራቸው እና ለንጉሱ ክብር ሲሉ የሚያበሩት የጦር አውሮፕላን ውስጥ ቦንብ እና ጋዝ(ነዳጅ) ጭነው ቀጥታ የአሜሪካ የጦር መርከቦች ያሉባቸው ቦታዎች ጋር በከፍተኛ ፍጥነት በመብረር እራሳቸው መከስከስ ጀመሩ! አባዬ! ይሄንን ያደረገው አንድ ጃፓናዊ ፓይለት አይደለም! በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ጃፓናዊ ፓይለቶች ናቸው። በዚህ ሂደት 34 ግዙፍ የአሜሪካ የጦር መርከቦች እንዲሰምጡ እና ከፍተኛ ውድመት እንዲደርስባቸው አደረጉ! በአንድ ተልኮ ብቻ ከ 5000 በላይ የአሜሪካ ባህር ሃይሎች እንዲሞቱ ማድረግ ችለዋል።
እንደምትሞት እያወክ የጦር አውሮፕላንህ ውስጥ ቦንብ እና ጋዝ ጭነህ የጠላት መርከብ ላይ ወስደኸው መከስከስ ምን ያህል ድፍረት እንደሚጠይቅ አስበው እንግዲህ!
አሰቃቂ መገባደጃ!
በጃፓን ጥቃት ደርሶብኛል በማለት አሜሪካ ለመጀመርያ ግዜ በሰው ልጅ ላይ "ሄሮሺማ" እና "ናጋሳኪ" የሚባሉ ሁለት ከተሞች ላይ "አቶሚክ ቦንቦችን" ጣለች! በአንዴ ከ 150 ሺህ እስከ 200 ሺህ የሚጠጉ ንፁሃን ጃፓናዊያኖችን በሁለት ቦንብ ስልቅጥ አድርጋ በላች። ጃፓንም በመጨረሻ "ተሸንፌያለው፣ ጦርነቱ ይብቃ!" ብላ እጅ ሰጠች! ሁለተኛው የዓለም ጦርነትም ያኔ አበቃ። የሩቅ ምስራቋ ጃፓን "አቶሚክ ቦንብ" የተጣለባት የመጀመርያዋም የመጨረሻማው ሃገር ሆና አለፈች።
ግን... ግን
.
.
.
.
ፍፁም ይቅር ይባባላሉ ተብለው የማይታሰቡት ሁለቱ ሃገራት ከአመታት በኃላ ወዳጅ ሆኑ፣ ታሪክ አለፈ፣ አሜሪካ ይህንን ታሪክ ይቅር የማይለውን ወንጀል ለማንጣጣት በሚመስል መልኩ ፅኑ የጃፓን ወዳጅ ሆነች፣ መሰረተ ልማቶቿን እና ከተሞቿን ገነባች! ሁለቱ ሃገራት በውትድርና፣ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት እና ቴክኖሎጂ እጅግ የተሳሳሩ ሃገራት ሆኑ!

Wendye Engida የፌስቡክ ገፅ የተወሰደ

ርዕስ ፦ የጃፓን መንገድ
ቋሚ ጥቅም እንጂ ቋሚ ጠላት የለም
ጸሓፊ ፦ በአሰፋ ማመጫ አርጋው
የታተመበት ዘመን:- የመጀመሪያ እትም 2014 ዓ.ም
የገጽ ብዛት ፦366
ዋጋ፦389 ብር
የታተመበት ቦታ፦Falcon Printing Enterprise
ከ25ዐ ዓመታት በላይ እንደ አለት በደደረ መዳፍ ያስተዳደረው የቶኩጋዋ ሥርወ መንግሥት ሲገረሰስ በመቃብሩም ላይ ሜጂ (የብርሃን ዘመን) ሲሉ የሰየሙት መንግስት በጃፓን ተመሠረተ፡፡ አዲሶቹ “የለውጥ ሃይሎች” ጃፓንን ለመለወጥ የወሰዱት የመጀመሪያ እርምጃ፣ በርዕዮተ ዓለም መነታረክ ሳይኾን በዕድገት ከቀደሙት ምዕራባውያን አገሮች መማርን ነበር፡፡
ዲፕሎማቱ አሰፋ ማመጫ አርጋው፤ በጃፓን የኢኮኖሚና የዲፕሎማሲ ጉዞ የቀሰመውን ዕውቀት በ366 ገፆች አሰናድቶ አቅርቦልናል፡፡
ጃፓን ላለፈችበት መከራ ሁሉ መንስኤው መረን ለቆ የነበረው ብሔርተኝነት ይመስለኛል። መዳኛው ደግሞ ሽንፈትን ተቀብሎ አንገትን ከመድፋት ይልቅ በአዲስ አቅጣጫ በአዲስ መንገድ እና መንፈስ፣ እንደ አገር አንድ ልብ፣ አንድ ሃሣብ ይዞ መነሣት መቻላቸው ነው፡፡
ከሁለት ምዕት ዓመት በላይ አገሪቱን ዘግቶ ያቆያት ሥርወ መንግሥት እንደወደቀ፤ አብዮተኞቹ ቀጣይ ሥራቸው አገራቸውን እንደምን አበልጽገው ከሃያላን ተርታ ማሰለፍ እንጂ በርዕዮተ ዓለም ጎራ ለይቶ መፋጀት አልነበረም፡፡ እኒያ የጃፓንን የብርሃን ዘመን ሻማ የለኮሱ ቀደምት እንደምን በአንድ ልብ ተነስተው አገሪቱን ሃያል እንዳደረጓት አሰፋ መረዳቱን እንካችሁ ብሎናል፡፡
አገር ከርዕዮት ዓለም በላይ ናት፡፡
አገር ከብሔር በላይ ናት።
አገር በዘፈን እና ዳንኪራ፣ ዘመን ባነገሰው የብሔር ብሔረሰብ ድለቃና ገድሎ በመሞት ብቻ አትበየንም፡፡ አገር በሁሉ ስምም ርዕይ የጋራ ምሰሶና ካስማ፣ ሁሉን አቅፋ የምታኖር የትናንት አደራ፣ የነገ ስም የዛሬ ማረፊያ ናት፡፡ እንጂ ለ”ከእኔ በላይ ለአሣር” በሚል የምትሰዋ በግ፣ አይደለችም፡፡
ጃፓን እንዲህ ነው ያደገችው፡፡ ለዘመናት ዘግቶና ጠርንፎ የያዘ የሾገኑ አገዛዝ ተገረሰሰ ብለው የተነሱ ወጣት አብዮተኞች፤ ለሌላ ትግል መነሻ እርሾ አልኾኑም፤ የተነሱበትን ዓላማ ከተነሱለት ሕዝብ ጋር ተገበሩት እንጂ፡፡
የሰውን ልጅ የሕይወት ፍኖት አቅጣጫ የሚቀይረው አንድ አሳቢ ነው፡፡ ሃሣቡ ግን መሬት የረገጠ፣ የሰው ልብ የሚገዛ፣ ገቢራዊ የሚሆን፣ ውጤቱ የሚገለጥ ነው፡፡ የማኀበረሰቡ ሕይወት እና አስተሳሰብ ላይ በልካም ተጽዕኖ የሚያሣድር አንድ ሰው አገር ያነቃል፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የምናየው ፋኩዛዋ ዩኪቺ እንደዚያው ነው፡፡
ፀሐፊው የጃፓንን ማኀበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዞ ቀለል አድርጎ በሚነበብ መልኩ አቅርቦልናል ፡፡ ስለ ጃፓን የእርስ በርስ ጦርነት፣ በቅኝ ገዢነት ያደረገችው ጦርነት ብሎም ስላስከፈላት ዋጋ፣ በሁለቱ የዓለም ጦርነቶች ስለደረሰባት ውድቀት ፣ በሽንፈት ከመሰበር እንደምን መንቃት እንደሚቻል፤ ስለ ይቅርታ፣ እንደ አገር በአንድ ርዕይ እንደምን መነሣት እንደሚቻል፣ የሥራ ባሕልን በማኀበረሰብ ውስጥ ስለ ማስረፅ እጅግ በአስደማሚ ሁኔታ አስነብቦናል፡፡
በአለማችን ብቸኛዋ በአቶሚክ ቦምብ የጋየች አገር ከዚያ ውድመት እንዴት እንዳንሰራራችና ከተረጂነት ወጥታ ወደ ቁጥር አንድ እርዳታ ሰጪነት እንደተቀየረች ያስነብበናል ፡፡

Meseret Alemayehu Dagnew የፌስቡክ ገፅ የተወሰደ


የጃፓን መንገድ - እንደ ማንቂያ ደወል
#Ethiopia | ፈር መያዣ
ለመቶ ዓመታት ያኽል በመሣፍንት እና በጦር አበጋዞች ስትታመስ ለነበረችው ጃፓን ቶኩጋዋ ኤያሱ የተባለ የጦር መሪ ተነሣላት፡፡ በየመንደሩ እና በየጎጡ ነፍጥ አንስተው ሲታጋተጉ የነበሩ ጦረኞችን ድል ነስቶ የራሱን ወታደራዊ መንግሥት መሠረተ፡፡
የቀደመውን የንጉሥ ሥርዓት ለይስሙላም ቢኾን ወደ መንበሩ መለሰው፡፡ ይኽ ከ25ዐ ዓመታት በለይ የዘለቀው ወታደራዊ የመንግሥት ሥርዓት ሾገን በመባል ይታወቃል፡፡
ይኽ ወታደራዊ ሥርዓት የጃፓንን በር ጠርቅሞ ከሌላው ዓለም ጋር ያላትን ግንኙነት በማቋረጥ ነጠላት፡፡
የአገሩን ሕዝብ በመደብ ለይቶ፣ በሥራም ኾነ በማኀበራዊ ግንኙነት እንዳይተሳሰር ከፋፈለው፡፡ የእያንዳንዱ ጃፓናዊ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ እንኳ በሕግ ተደነገገ፡፡ ጃፓን ውስጥ የነበሩ አውርጳውያንን ከአገሩ አስወጣ፡፡
የአገሩም ሰው ከጃፓን ውጭ ወደየትም ውልፍት እንዳይል አዘዘ፡፡ ቀደምት መጻተኞች የሰበኩትን ክርሰትና አገደ፣ አብያተ ክርቲያን እሣት በላቸው፡፡
የወቅቱን ሁኔታ በአጭር ለመግለጽ ፀሃፊው ከባለቅኔ ከበደ ሚካአልን “ጃፓን እንደምን ሰለጠነች?” ይጠቅሳል፡፡
“. . . ከእንግዲህ በኋላ ፀሐይ በመሬት ላይ አብርታ እስከምትኖርበት ጊዜ ማንም ሰው ቢኾን ጃፓን አገር ለመግባት አይድፈር . . . ይኽን ዐዋጅ ጥሶ ሲገባ የተገኘ የውጭ አገር ሰው ሁሉ በሞት ይቀጣል፡፡” (ገጽ፤26)
የሰው ልብ በቅጥር አይያዝም
የሰው ልብ፣ የሰው ምኞት ግን አይቀጠርም፡፡ በሥፍራ ተለይቶ አገር ድንበር ተበጅቶለት ይቀመጥ እንጂ ሰው ልቡ እግረኛ ነው፡፡ የትም መቸም፡፡ ዘራሰብ ሉላዊ ነው፡፡ ዘመነኞች ስደት በሚል ይበይኑት እንጂ ዕጣ ፈንታ እንዲህም እንዲያም ብሎ ያገናኘዋል፡፡
ሰይፉ መታፈሪያ ፍሬው “ጉልበተኛ የፈጠራት ዓለም” የሚለው ግጥማቸው እንደህ የሚል ሃሣብ አለው፡-
እስኪ ከዚህች ወዲህ፤ ከዚያ ወዲያ ብሎ፤
ዛቻ ከፖለቲካ ቀላቅሎ፤
ከለላት እንጂ
አሰመራት
ዓለማችን
መች ድንበር ነበራት
ከመሣፍንትና የጦር አበጋዞች ነፍጥ አስጥሎ፣ የአገሪቱን መግቢያ መውጪያ የከረቸመው የሾገኑ አስተዳደር ከምዕራቡ ዓለም የዕድገት ወሬ የጃፓናውያንን ልብ በቅጥርም ኾነ በነፍጥ መከለል አልቻለም፡፡
በተለይ የባህር ዳርቻ ግዛት አስተዳዳሪዎች የወሬው ነፋስ እና እነርሱ ያሉበት ኹኔታ ከተራ መንፈሳዊ ቅናት አልፈ፡፡ የአገራቸው መፃዒ ዕድል ያሣስባቸው ጀመር፡፡
በአናቱ ጥቁር ጢሱን እያትጎለጎለ “ጥቁሩ መርከብ” (The Black Ship) ደረሰ፡፡
ይኽን ተከትሎ ከሁለት መቶ ሃምሣ ዓመታት በላይ ተዘግቶ የነበረው በር ተከፈተ፡፡ የመርከቡ ጢስ ለቶኩጋዋ ሥርወ መንግሥት መፍረክረክ ለለውጥ ፈላጊ ወጣተቶች ግን የማንቂያ ማጠንት ኾነላቸው፡፡ ዓመጽ ማቀጣጠሉን ገፉበት፡፡
የተፍረከረከውን ነባር ሥርዓት ለማስቀጠል የቆረጡ “ታማኞች” በለውጡ እሣት አቀጣጣዮች ላይ ብረት አነሱ፡፡ ብረት ያነሱ በብረት ይጠፉ ዘንድ ተጽፏልና የሾገኑ ሥርዓትና ጭፍሮቹ ማብቂያ ኾነ፡፡
ጃፓንን ከ25ዐ ዓመታት በላይ እንደ ብረት በጠነከረ መዳፍ ያስተዳደረው የቶኩጋዋ ሥርወ መንግሥት ተገረሰሰ፡፡
በመቃብሩም ላይ ሜጂ (የብርሃን ዘመን) ሲሉ የሰየሙት መንግስት ተመሠረተ፡፡ የጃፓን አዲስ ጉዞ ተጀመረ፡፡
አዲሶቹ “የለውጥ ሃይሎች” ጃፓንን ለመለወጥ የወሰዱት የመጀመሪያ ርምጃ በርዕዮተ ዓለም መነታረክ ሰይኾን በዕድገት ከቀደሙት ምዕራባውያን አገሮች መማርን ነበር፡፡



መብሰልሰል
ከጃፓን መንግሥት በተገኘ የባሕል፤ የቋንቋና የዲፕሎማሲ ስልጠና ለስምንት ወራት ያህል ጃፓን የቆየው ዲፕሎማቱ አሰፋ ማመጫ አርጋው በጃፓን የኢኮኖሚና የዲፕሎማሲ ጉዞ ያደረበትን ምሳጤ በ366 ገፆች ቀንብቦ አቅርቦልናል፤- በ “የጃፓን መንገድ”፡፡
የዓለምን ኢኮኖሚ ከሚመሩት አገሮች አንዷ የኾነችውን የዚህችን ትንሽ አገር ውድቀትና አነሣስ ድርሳናት አገላብጦ፣ የዜና አውታሮችን ዘገባ ፈተሾ ቅልል ባለ ቋንቋ አጠገባችን ኾኖ እንደሚተርክ ሰው እስኪሰማን ድረስ ወጉን ይቀዳልናል፡፡
እውነት እውነት እላችኋላሁ በየምዕራፎቹ እንደ መስታዎት የእኛን የእስካሁን የአብዮትም የነውጥም ጉዞ የሚያስታውሰ ተረኮች በርካታ ናቸው፡፡ የፀሐፊው ዋና ቁብ ይኽው ይመስለኛል፡- ቁጭትን መፍጠር፡፡
ጃፓን ላለፈችበት መከራ ሁሉ መንስኤው ልጓም ያልተበጀለት ብሔርተኝነት ይመስለኛል፡፡ መዳኛዋ ደግሞ ሽንፈትን ተቀብሎ ከመሰበር ይልቅ በአዲስ አቅጣጫ በአዲስ መንገድ እንደ አገር አንድ ልብ አንድ ሃሣብ ይዞ መነሣቷ ነው፡፡
ከሁለት ምዕት ዓመት በላይ አገሪቱን ዘግቶ ያቆያት ሥርወ መንግሥት እንደተቀየረ፤ አብየተኞቹ ቀጣይ ሥራቸው አገራቸውን እንደምን አበልጽገው ከሃያላን ተርታ ማሰለፍ እንጂ በርዕየተ ዓለም ጎራ ለይቶ መታጋተግ አይደለም፡፡
እኒያ የጃፓንን የብርሃን ዘመን ማሾ የለኮሱ ቀደምት እንደምን በአንድ ልብ ተነስተው አገሪቱን ሃያል እንዳደረጓት አሰፋ ከሰው አውግቶ፣ ከማዕምራን ጠይቆ እና ዳርሣናት ፈትሾ ነው መብሰልሰሉን የሚያካፍለን፡፡
. . . ለኔ ብለህ ስማ
የአሰፋ ትረካ ስማትን የሚበረብር ነው፡፡
መጽሐፉ ከገጽ ገጽ በተገለፀ እና በተነበበ ቁጥር ወረቀትነቱ ተዘንግተ የእኛን የእስከዛረ ጉዞ እና አሁናችንን እንድንጠይቅ፣ የት ጋር እንደጎደልን ውስጣችንን እንድንበረብር የጎተጉታል፡፡ ለምን በመፈክርና ቃላት በማሽሞንሞን ላይ ተቸነክረን ቀረን? የጃፓን መንገድ እንዲህ ውስጥን ይሞግታል፡፡



“. . . የቀድሞው መንግሥት በአመጽ ተወግዶ የሚጂ ንጉሣዊ መንግሥት ወደ ሥልጣን ሲመጣ ጃፓን ድሃ እና ኋላቀር አገር ነበረች፡፡
[. . .]
እናም አገሪቱን ከኋላቀርነት ፈጥና ለማውጣት ለለወጡ መበዎቹ ከለሎች የሠለጠኑ አገራት ልምደ መቅሰም ወሳኝ ጉዳይ ኾነ፡፡
[. . .]
ለዚሁ ዓላማ ሥልጣን የጨበጡት ወጣተቹ የለውጥ መሪዎች በታሪክ “ኢዋኩራ ሚሽን” በመባል የሚታወቀውን የልዑካን ቡድን አዘጋጁ” (ገጽ 46-47)
በወቅቱ እንደተነገረን የኢትየጽያ አብዩት በግብታዊነት ከፈነዳ በኋላ እና ከግማሽ ምዕት ዓመት መንበራቸው ንጉሡን ከገረሰሰ በኋላ ምን ተፈጠረ? ከአንድ ጥራዝ የሶሺያሊዝምን ፍልስፍና ያነበቡ ወጣት ተማሪዎች ጎራ ለይተው መተጋተግ ጀመሩ፡፡ ስልጣኑን የጨበጠው ወታደር በበኩሉ ተማሪ አርፈ ትምህርቱን ይማር፡፡
በዚህ ግርግር ይህች አገር እንደ እንቁላለ ከእጃችን ወድቃ እምቦጭ ማለት የለባትም አለና ጠብመንጃውን አቀባበለ፡፡ ያነ የተጀመረ መናቀር አንድ ደርዝ ሳይበጅለት የትውልድ ዕድማ እየበላ ይገኛል፡፡
አገር ከርዕየተዓለም በላይ ናት፡፡ አገር ልብ በሚያሞቅ ዘፈን፣ ነፋስ በሚነሰንሰው የሰንደቅ ዓላማ ዳንስ፣ ገድሎ በመሞት ብቻ አትበየንም፡፡
አገር በሁሉ ስምም ራዕይ የጋራ ምሰሶና ካስማ፣ ሁሉን አቅፋ የምታኖር የትናንት አደራ፣ የነገ ስም የዛሬ ማረፊያ ናት፡፡ እንጂ ለ”ከእኔ በላይ ለአሣር” የምትሰዋ በግ፣ ጭዳ የምትኾን ዶሮ አይደለችም፡፡
ጃፓን እንዲህ ነው ያደገችው፡፡ ለዘመናት ዘግቶ እና ጠርንፎ የያዘ የሾገኑ አገዛዝ ተገረሰሰ ብለው የተነሱ ወጣት አብየተኞች ለሌላ ትግል መነሻ እርሾ አልኾኑም፤ የተነሱበትን ዓላማ ከተነሱለት ሕዝብ ጋር ተገበሩት እንጂ፡፡
ሰው ጥሩ አንድ ሰው
የሰውን ልጅ የሕይወት ትልም በአንድም በሌላ መልኩ የሚቀይረው የአንድ አሳቢ (አፈንጋጭ) ሃሣብ ነው፡፡ ሃሣቡ ግን መረት የረገጠ፣ የሰው ልብ የሚገዛ፣ መረት የሚወርደ፣ ውጤቱ የሚገለጥ ነው፡፡
የማኀበረሰቡን ሕይወት እና አስተሳሰብ በበጎ ተጽዕኖ የሚያሣድር አንድ ሰው አገር ያነቃል፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የምናየው ፋኩዛዋ ዩኪቺ እንደዚያው ነው፡፡
መደምደሚያ
ፀሐፊው የጃፓንን ማኀበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዞ ቀለል አድርጎ በሚነበብ መልኩ አብርቧል፡፡
ጃፓን ከእርስ በርስ ጦርነት፣ በቅኝ ገዢነት ያደረገችው ጦርነት ስላስከፈላት ዋጋ፣ በሁለቱ የዓለም ጦርነቶች ስለደረሰባት የሰው እና የቁስ ውድመት፣ በሽንፈት ከመሰበር እንደምን መንቃት እንደሚቻል፣ ስለ ይቅርታ፣ እንደ አገር በአንድ ርዕይ እንደምን መነሣት እንደሚቻል፣ የሥራ ባሕልን በማኀበረሰብ ውስጥ ስለማስረፅ እጅግ በአስደማሚ ሁኔታ አስነብቦናል፡፡
ብቸኛዋ በአቶሚክ ቦምብ የተመታች አገር ከዚያ ውድመት እንዴት እንዳንሰራራችና ከተረጂነት ወደ ቁጥር አንድ የልማት ትብበርና ርዳታ ሰጪነት እንደተቀየረች ያሣያል፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ ከንባብ አንፃር አንጽንኦት ለመስጠት በማሰብ አንዳንድ ምዕራፎች መግቢያ ላይ ቀድሞ የተነገረ ታሪክ ይደገማል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ “ወረድ ብለን እንደምናየው”፣ “በሌላ ቦታ በሰፊው እንደምናየው” የሚሉ አገላለፆች አንባቢውን ከንባቡ ፍሰት የሚያናጥቡ በመኾኑ በቀጣይ ሕትመት ቢስተካከሉ ተመራጭ ይመስለኛል፡፡
በቀረው ፀሐፊው የካበተ ልምድ እንዳለው ዲፕሎማት የጃፓንን ጉዞ በንስር ዓይን መርምረው ይኽን ሥራ ማበርከታቸው የሚያስመሰግናቸው ነው፡፡



ክቡር ዶ/ር ደራሲ ከበደ ሚካኤል ‹‹ጃፓን እንደምን ሠለጠነች?›› ብለው ጀምረው ከዚያም የተለያዩ ሀገሮችን እንዴት እንደሠለጠኑ መጻፍ ጀመሩ፡፡ ሦስተኛው መጽሐፍ ላይ ሲደርሱ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አስጠሯቸው፡፡

‹‹ከበደ ምን እየሠራህ ነው?›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ ከበደ ሚካኤልም:-
‹‹እንትን እንዴት ሠለጠነች? የሚል አራተኛ መጽሐፍ ልጽፍ ነው፡፡›› በማለት መለሱ፡፡

‹‹እንዳትጽፍ፤ አቁም እንዳትጽፍ›› አሉ ንጉሡ፡፡

‹‹ለምን?›› ጠየቁ ከበደ ሚካኤል፡፡

ንጉሡም:-
‹‹ሥነ ምግባር የሌለው ሕዝብ ቢሠለጥን ጥቅም የለውም፡፡ የገነባውን ያፈርሰዋል፤ የሰራውን ይንደዋል፡፡ ስለዚህ መጀመሪያ ስለ ሥነ ምግባር ጻፍ፡፡ የጀመርከውን ከዚያ በኋላ ትጽፈዋለህ›› አሏቸው፡፡

ክቡር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል ደስ ሳይላቸውም ቢሆን ወደ ቢሮአቸው ሄዱ፡፡ ከዚያ በኋላ ‹‹ታሪክና ምሳሌ›› የሚባሉትን እጅግ በጣም የምንወዳቸውን እንዲሁም የተማርንባቸውን የሞራል ማስተማሪያ መጻሕፍትን ጻፉ።

ከ  Tadele tibebu - ታደለ ጥበቡ  የፌስቡክ ገፅ የተወሰደ











Wednesday, November 16, 2022

አውራ አምባዎች - የሰላም ሠፈርተኞች

 አውራ አምባዎች - የሰላም ሠፈርተኞች_አዲስ ዘመን ቅዳሜ ሰኔ 25 ቀን 2014 ዓ.ም 

(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)


አንዲህም ይኖራል! 
“ላለፉት 50 ዓመታት ያህል አውራ አምባ ፍጹም ሰላማዊ ሆኖ የኖረ ማሕበረሰብ ነው። አንድም ጊዜ ተከሶም ሆነ ከሶ አያውቅም። ከግጭቶች ነፃ ምድር ነው። ይህ ሰላማዊ ማሕበረሰብ ለዓለምና ለሰው ልጆች ሁሉ የሚያስተምረው የሰላም ሕይወት ምሥጢር አለው። ዓለም በሰላም እጦት እንዲህ ስትናወጥ አውራ አምባ ማሕበረሰብ እንዴት 50 ዓመታት ሙሉ ፍጹም ሰላማዊ ሆኖ ኖረ? - [ይህ እውነታ] እንደ መስታወት ሆኖ ራሳችንን የት እንዳለን እንድንጠይቅ ይሞግተናል” (ዝክረ አውራ አምባ - ዙምራ፤ ሰኔ 2014 ገጽ 14። ) በሰላም እጦት ርሃብተኛ ለሆነው ለእኛ ለዛሬዎቹ የሀገሪቱ ወርተረኛ ትውልዶች፤ በእኛው ቀዬ በአውራ አምባ ማሕበረሰብ መካከል እየተመረተ ያለው ይህን መሰሉ “ለዓለምና ለሰው ልጆች ሁሉ የሚተርፍ” የተባለለት የሰላም አዝመራ ስለምን ብርቅና ሩቅ ሆኖብን ባይተዋር በመሆን የተለያዩ ግጭቶችና ጦርነቶች እያስተናገድን ለመኖር ምርጫችን ማድረጉን ማሰቡ በራሱ ግራ ያጋባል። ለሃምሳ ዓመታት ያህል እድሜያችንን አባክነን ዛሬ እንደ አዲስ ይህን ጥያቄ ጠይቀን መልስ መፈለጋችን እፍረት ቢሆንብንም “በሆድ ይፍጀው” ለሆሳስ ከማለፍ ይልቅ የአውራ አምባዎችን ድንቅ ሰላማዊ አኗኗር እየጠቃቀስን ደፈር ብለን ራሳችንን ብንወቅስ ይበጅ ይመስለናል።

 በሰላም እጦት ወጀብ እየተላጋች ያለችው ሀገር ይህንን የልጆቿን መልካም እሴት ተቀብላ ለማስፋፋት እውነት ስለምን ዐይኗ ተጨፈነ? የዘንባባ ዝንጣፊ በአፏ ይዛ በዚያ ማሕበረሰብ ውስጥ ሃምሳ ዓመት ሙሉ በዓየሩ ላይ ስትቀዝፍ የነበረችውን የሰላም ተምሳሌት ርግብ “ነይ ርግብ አሞራ!” እያልን ከማሕበረሰቡም ከፍ ብላ በራ ወደ ሌሎች ክልሎችም የምሥራች እንዳታበስር በእርግጡ ዐይነ ጥላውን ያሳረፈብን አዚም ምን ይሆን? ቢቸግረውና መልሱ ግራ ቢያጋባው ሳይሆን አይቀርም፣ አንጋፋው ነፍሰ ሄር ድምጻዊ “ጥያቄ አቅርቤያለሁ መልሱን ብትሰጡኝ…” በማለት ያንጎራጎረው። “ግዛዋ ሳለ ከደጅሽ፤ ለምን ሞተ ልጅሽ” አለች ይባላል ግራ የተጋባች አንዲት ስም የለሽ እናት ባለሀገር። አውራ አምባዎች ያስታወሱን የጥበብ ምሳሌ፤ ከአሁን ቀደም ጠቀስ አድርጌ ያለፍኩትን አንድ ጥበብ ነክ ታሪክ ለማዋዣነት እንዲረዳ ደግሜ ላስታውስ። በአንድ ሀገር ውስጥ ታላላቅ የዓለም ሠዓሊያንን ያሳተፈ የሥዕል ውድድር ተደርጎ ነበር ይባላል። ሁሉም ሠዓሊያን በሥዕላቸው እንዲወክሉ የተወሰነው “የሰላምን” ማሳያ ነበር። ውድድሩ ብዙ ፍልሚያ ተደርጎበት ለመጨረሻው የደረጃ ፍጻሜ የደረሱት ሦስቱ ተወዳዳሪ ሠዓሊያን ብቻ የጥበብ ሥራቸውን እንዲያስገመግሙ የተለያዩ የየግላቸው ስቱዲዮ ተሰጣቸው ይባላል። የመጀመሪያው ሠዓሊ ሰላምን የወከለው የተንዠረገገና አጓጊ ፍሬ በተሸከመ አንድ ትልቅ ዛፍ አማካይነት ነበር። ሦስቱ ዓለም አቀፍ ዳኞች ይህንን የፈጠራ ውጤት ለማየት የስቱዲዮውን በር ከፈት አድርገው ሲገቡ ከየት መጣች የማትባል ወፍ እየበረረች ሄዳ አብራቸው ዘው ብላ በመግባት ፍሬው የጎመራው ያ ዠርጋዳ ዛፍ እውነተኛ መስሏት በላዩ ላይ ለማረፍ ሥዕሉ ሸራ ላይ ታንቧችር ጀመር። ዳኞቹ በእጅጉ ተገርመው “እንኳን ሰብዓዊ ፍጡርን ቀርቶ ተፈጥሮን ሳይቀር ያማለለ የጥበብ ስራ” የሚል አስተያየት በማስታወሻቸው ላይ በማስፈር ወደ ሁለተኛው ሠዓሊ ስቱዲዮ አመሩ። ሁለተኛው ሠዓሊ ሰላምን የወከለው እጅግ በሚማርክና በተዋበ መጋረጃ ነበር። ዳኞቹ ልክ ወደ ስቱዲዮው እንደገቡ መጋረጃው ከፊት ለፊት ባለው ሸራ ላይ ዧ ብሎ ተዘርግቶ ሲያስተውሉ እውነተኛ መጋረጃ መስሏቸው ለመግለጥ እጃቸውን ዘረጉ። ሥዕል መሆኑን ሲያውቁ ግን በራሳቸው ድርጊት እንዳፈሩ አቀርቅረው በየግል ማስታወሻቸው ላይ እንዲህ ሲሉ ሃሳባቸውን አሰፈሩ። “የመጀመሪያው ሠዓሊ ተፈጥሮን እንኳን የማሞኝት ከፍተኛ ክህሎት ያዳበረ የምር ጠቢብ ሲሆን ይህ ሁለተኛው ሠዓሊ ደግሞ እኛን ዳኞቹን ሳይቀር የማቄል ከፍተኛ ተሰጥዖ ያለው ታላቅ ባለሙያ ነው። ” በሁለቱ የጥበብ ሥራዎች እጅግ የተመሰጡት ዳኞች ወደ ሦስተኛው ሠዓሊ ስቱዲዮ ያመሩት እየተገረሙ ነበር። በዚህ በሦስተኛው ስቱዲዮ ውስጥ ሰላምን ወክሎ የቀረበው የሥዕል ስራ እጅግም የተወሳሰበና የሚያማልል አልነበረም። አንድ የተንጣለለ ታላቅ ውቂያኖስ ከዳር ዳር ተዘርግቷል። ውቂያኖሱ በከባድ አውሎ ነፋስ እንደሚላጋ በግሩም ሁኔታ በቀለማት ጥበብ ተከሽኗል። በውቂያኖሱ መሃል ለመሃል አንድ ቋጥኝ ከፍ ብሎ ተገሽሯል። በዚያ ቋጥኝ ላይ እንዲት ወፍ አንገቷን ወደ ላይ ቀና አድርጋ ትዘምራለች። ከሥዕሉ በላይ “ሰላም” የሚል ቃል ተጽፏል። የሥዕሉ አጠቃላይ ይዘት ይኼው ነበር። ዳኞቹ ሥራቸውን አጠናቀው ውጤት ለመስጠት ተሰበሰቡ። “ለሰላም ውክልና” የቀረበውን የመጀመሪያውን ሥዕል በተመለከተ ሦስቱም ዳኞች የተስማሙበት አስተያየት እንዲህ የሚል ነበር። “እርግጥ ነው የሠዓሊው የተንዠረገገ ዛፍ እንኳንስ እኛን ወፏን እንኳን እውነተኛ ዛፍ እስኪመስል ድረስ አሞኝቷል። ድንቅ ስራ ነው። ቢሆንም ሰላምን ለመወከል አቅም የለውም። ” ወደ ሁለተኛው የጥበብ ስራ ተሸጋገሩ፤ “የሁለተኛው ሠዓሊ የመጋረጃ ሥዕልም በጥበብነቱ እጅግ ሊደነቅ ይገባል። ቢሆንም ግን ሰላም የሚገኘው በውብ መጋረጃ ውስጥ ታልፎ በሚገኝ ደስታ ብቻ ከሆነ ስህተት ነው። ስለዚህም ሰላምን በሚገባ አይገልጥም። ” ሦስተኛው የሥዕል ስራ ለውሳኔ አሰጣጥ አላዳገታቸውም። በአውሎ ነፋስ ወጀብ በሚላጋው ውቂያኖስ መሃል በሚገኘው ቋጥኝ ላይ ያረፈችው ወፍ አንገቷን ቀና አድርጋ ተረጋግታ ትዘምራለች እንጂ በሚደነፋውና “ዱታ ነኝ” ብሎ በሚፎክረው ማዕበል ተረትታ ከዝማሬዋ አልተገታችም። እውነተኛ ሰላም የሚመዘነው በወጀብና በአውሎ ነፋስ መካከል አለመናወጥ ነው። ስለዚህ ሦስተኛው ሥዕል ማሸነፍ ሲያንሰው ነው። ” ዳኞቹ ውሳኔያቸውን አሳውቀው ለሠዓሊው ተጨበጨበለት፤ አድናቆትና ሽልማትም ተዥጎደጎደለት። 

ክብር ዶ/ር ዙምራ ኑሩ
                                                                የክብር ዶ/ር ዙምራ ኑሩ

 የአውራ አምባ ማሕበረሰብ በሦስተኛው አሸናፊ ሥዕል ቢመሰል ያንስበት ካልሆነ በስተቀር ይበዛበታል ተብሎ አያከራክርም። የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ ዙሪያ ገባዋ በውስጥና በውጭ ጠላቶቿ አማካይነት በሰላም እጦት ወጀብና አውሎ ነፋስ እየተላጋች ባለችበት ወቅት “መድኃኒቱ በደጃፏ እያለ” ይህ የአውራ አምባ ማሕበረሰብ ሃምሳ ዓመት ሙሉ ወጀብ በበዛበት ሀገር በሰላም እየኖርኩ ነው ብሎ እኛን ባለሀገሮችን ብቻም ሳይሆን የዓለምን ማሕበረሰብ ጭምር ማስደመሙ ከማስገረም የሚዘል አድናቆት ሊቸረው ይገባል። ለመሆኑ ይህንን ማሕበረሰብ የሰላም ተምሳሌት ያሰኙት ምሥጢሮች ምንድን ናቸው? የአጀማመሩን ዳራ ጠቃቅሰን ከብዙ እሴቶቹ መካከል ጥቂቶን እሴቶቹን ብቻ ለማመላከት እንሞክራለን። የአውራ አምባ ማሕበረሰብ የተመሠረተው በ1964 ዓ.ም ሲሆን መገኛውም ከባሕር ዳር ከተማ በሰሜን ምሥራቅ አቅጣጫ 67 ኪ.ሜ በሚርቀው በደቡብ ጎንደር አስተዳደር በፎገራ ወረዳ በወጅ አውራ አምባ ቀበሌ ውስጥ ነው። መስራቹ ደግሞ የክብር ዶ/ር ዙምራ የኑስ ናቸው። ማሕበረሰቡ “አንቱታ ያራርቃል” የሚል እምነት ስላለው “አንተ/አንቺ” መባባልን ስለሚያዘወትር ይህ ጸፊም ዕድሜው ወደ ሰማኒያው እየተንደረደረ ያለውን መሥራቹን ዙምራን አንተ እያለ የሚገልጸው ባህላዊ አክብሮቱ ሳይጓደል ነው። 
የአውራ አምባ ማሕበረሰብ ከተመሰረተ ሃምሳ ዓመታት ቢያስቆጥርም የጉዞው ውጣ ውረድ ግን በመከራና በፈተና የታጀበ እንደነበር ሰኔ 21 ቀን 2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት አዳራሽ ውስጥ ክብርት ከንቲባዋን ጨምሮ በርካታ የመንግሥት ሹመኞች በተገኙበት ፕሮግራም ላይ በቀረበው ዶኪዩመንተሪ ፊልምና በተመረቀው መጽሐፍ ውስጥ በዝርዝር ተተርኳል። ባለ ራእዩ ዙምራና የማሕበረሰቡ አባላት በቆራጥነት ተቋቁመው ያሳለፏቸው እንግልት፣ ስደትና መገለል ዓይነታቸውም ሆነ አበዛዛቸው ለቁጥር ያታክታል። ተርበዋል፣ ተጠምተዋል፣ በግፈኞች ተሳደዋል። ከትውልድ አካባቢያቸው ብቻም ሳይሆን ተሰደው ከሚያርፉባቸው አካባቢዎችም ጭምር ማረፊያ በሚያሳጡ አሳዳጆች ግፍ ተፈጽሞባቸዋል። ስለምን? ሰላምን ስለሚሰብኩ፣ በሰው ልጅ እኩልነት ስለሚያምኑ፣ የጾታ ልዩነትን ስለማይቀበሉ፣ ከሃይማኖቶች ቀኖና ይልቅ በአንድ ፈጣሪ ብቻ በማመናቸው ወዘተ. ዋና ዋናዎቹ ምክንያቶች ነበሩ። ለሰላማዊ አኗኗራቸው እንደ ሕይወት ፍልስፍና የሚከተሏቸው እሴቶች የሚከተሉት ናቸው። እነዚህ እሴቶች የአብዛኛዎቹን የሀገራችን ማሕበረሰቦች ነባርና ቅቡል ልምምዶች ስለሚገዳደሩ አውራ አምባዎች እንደ ተለየ የማሕበረሰብ ክፍል እንዲታዩ፣ እንዲገፈተሩና እንዲገለሉ ምክንያት ሆነዋል። 
አንባቢው የራሱን ፍርድ እንዲሰጥ ዋና ዋናዎቹ ብቻ እንደሚከተለው ይታወሳሉ፡ ሀ. ሰው ሁሉ እኩል ነው። ማንኛውም ሰው አዳምና ሔዋን (አደምና ሐዋ) ከተባሉ ሁለት የዘር ምንጮች የተገኘ ነው። ስለዚህ ከአንድ አባትና እናት የተገኘ ሰብአዊ ፍጡር ሁሉ በምንም መስፈርት ሊበላለጥና ከእከሌ እንቶኔ ይሻላል ተብሎ በምንም መስፈርት እየተመዘነ ሊፈረጅ አይገባውም። ለምን ቢሉ ሴት በሴትነቷ እናት ናት፤ ወንድ በወንድነቱ አባት ነው። እናት በሌለችበት አባት የለም፤ አባት በሌለበትም እናት የለችም። ስለዚህም፡- ለ. የጾታ ልዩነት ተፈጥሯዊ እንጂ አብሮ በመኖር ሕይወት ውስጥ መለያያና መከፋፈያ ሊሆን አይገባም። የጾታ ልዩነት እየተደረገም ለወንድና ለሴት በሚል የተግባር ክፍፍል ሊደረግ አይገባም። ወንዱም ሆነ ሴቷ እኩል የማጀቱንም ሆነ የውጭውን ስራ እየተጋገዙ መስራት ይገባል። ሊጥ አቡክቶ፣ አብሲት ጥሎ እንጀራ መጋገርም ሆነ እንዝርት እያሾሩ ፈትል መፍተል ለሴቶች ብቻ የተሰጠ ሳይሆን ወንዶችም ሊሰሩት ይገባል። እርሻም ቢሆን በሬ ጠምዶ ማረስ ለወንዶች ብቻ የተሰጠ ሳይሆን ሴቶችም ሊተገብሩት ይገባል። ሐ. ለራስ የሚደረገውን ለሌሎች ማድረግ፣ በራስ ላይ እንዲደረግ የማይፈለገውንም በሌላው ላይ አለመፈጸም። መ. አረጋውያን የትውልድ መሰረት፣ ጌጥና ውበት ስለሆኑ ተገቢው አክብሮትና እንክብካቤ ሊደረግላቸው ይገባል። አቅመ ደካሞችም መደገፍና መጦር ይገባቸዋል። ሕጻናትም የነገው ትውልድ እርሾዎች ስለሆኑ በተገቢ እንክብካቤ፣ ትምህርትና ሥነ ምግባር ተኮትኩተው ሊያድጉ ይገባል። በቤተሰብና በማሕበረሰቡ አዋቂዎች ውይይት ወቅትም ልጆች ናችሁ ተብለው ሳይናቁ ተገቢው ወንበርም ሆነ የመወያየትና የማወያየት እድል ሊነፈጋቸው አይገባም። ሠ. የማሕበሩ አባላት ጥረው ግረው የሚያፈሩት ሀብት ሁሉም እኩል የሚከፋፈሉት እንጂ የተበላለጠ ድርሻ ሊኖር አይገባም። ረ. የእነዚህ ሁሉ መልካም እሴቶች ማሰሪያው ሰላም ነው። የሰላም ጉዳይ በማሕብረተሰቡ ውስጥ ለድርድር የሚቀርብ አይደለም። ጠብና ጭቅጭቅ፣ ንትርክና አተካራ በእነርሱ ዘንድ አይታወቅም ለምን ቢሉ ሁሉም ሰው በማሕበረሰቡ ውስጥ እኩል ነው፣ ሃሳቡ ይደመጣል፣ ውጤቱ ይመዘናል፣ ቅሬታው ሳይውል ሳያድር ይፈታል፤ ስለዚህም አምባጓሮ ጥዩፍ ነው። ምንጭም ስርም አይኖረውም። 
 በአጠቃላይ አውራ አምባዎች የሚገለጹት ከኢትዮጵያ ምድር የተገኙ የሀገር ውበትና የዓለም ሀብት እንደሆኑ ነው። መርህና እሴታቸው በመላው ሀገሪቱ ውስጥ ቢስፋፋና ቢሰርጽ የዛሬው መከራችን በአጭሩ በተቀጨ፣ እምባችንም በታበሰና የዓለም ሕዝብ “ወደ ሰላም ምድር” እንፍለስ ብሎ አዋጅ ባስለፈፈ ነበር። ይህ ጸሐፊ ይህንን ምስክርነት የሚሰጠው በቀዬአቸው ተገኝቶ ጎብኝቷቸው፣ የተመለከተውንም በመጽሐፍና በጋዜጦች አስተዋውቆ፣ የሃምሳኛ ዓመት ክብረ በዓላቸውን ሲያከብሩም ምስክርነቱን አጠንክሮ የሰጠ ስለሆነ መልእክቱ እውነተኛ፣ ራእያቸውም ለሀገራችን ሥር የሰደዱ ወቅታዊ ችግሮች መፍትሔ ሊሆን ስለሚችል እሴቶቻቸው የጋራና የሕዝብ መርህ እንዲሆኑ እውቅና ሊያገኙ ስለሚገባ የሚመለከታቸው መንግሥታዊ ተቋማት ፈጥነው ምላሽ ይስጡ። በመጨረሻም ሃሳቡን የምናጠቃልለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ስለዚህ የሰላም ተምሳሌት ማሕበረሰብ ከቀናት በፊት በሰጡት ምስክርነት ይሆናል፤ “የአውራ አምባ ማሕበረሰብ እምነት፣ ብሔርና የፖለቲካ አመለካከት አንድ ሆነን ከመኖር እንደማያግዱን ሕያው ምስክር ነው። የጾታ እኩልነት፣ የሕጻናትና የአካል ጉዳተኞች ማሕበራዊ ፍትሕ በተግባር ተፈትኖ ያየንበትም ነው። ” ረጂም እድሜ ለባለራእዩ ለክብር ዶ/ር ዙምራ ኑሩ፣ የተባረከ ቀሪ ዘመን ለአውራ እምባ ማሕበረሰብ አባላት ይድረስልን። 
ሰላም ይሁን!