ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, June 12, 2014

ካሳየን አጣሁት – አቦነሽ አድነው


 

ለጎንደሩ ጀግና ለጠፋው መቅደላ፣
አብሮ አልቅሱለት ቋራና ኦሜድላ፣
ፍቅሩም ሳይወስነው በትግሬ በወሎ፣
እራሱን የጣለው ጦቢያን አድን ብሎ።
ምንጊዜም ይወራል ዝናው፣
በታሪክ አይሞትም ጀግናው፣
ይጠራል ስሙ በዚህች ምድር፣
ላገሩ ስለዋለው ብድር።

በሰንበት ባውዳመት ተጎድቼ በባል፣
እንግዲህ ምንጠቅሞኝ ተዋበችስ ብባል፣
ከፍቅሬም ካካሌም ባንዴ እየተለየሁ፣
ቀረሁኝ በተስፋ እያልኩ ዓለማየሁ።



 እናቴ ሞሽራ ልትድረኝ ለጀግና፣
ተነስቶ ባገሩ አንድነት ያፀና፣
ሚስት ናት ገረድ ናት ሲለኝ እንዳልኖረ፣
ነፍሱን ላገር ሰጥቶ የኔ ካሳ ቀረ።
ከንግስ ከግርማዊነት ያኮራል ያለው ጀግንነት፣
ወገኔ ጥለህ ተሰደድ እያየው የሱ ጀግንነት።
ዓለማየሁ ብሎ ሀዘንን መቀበል፣
ዕጣው በኔ ሲደርስ እንግዲህ ምን ልበል፣
ጎንደርን ማሳለፍ ምንስ ጎደለብኝ፣
መቅደላ ነው እንጂ ካሳው የቀረብኝ።
 
ሙሉ ቤቴን ሳጣው አላልኩም እየዬ፣
የኑሮ መከታ ባላገር ነው ብዬ፣
ተዋቡ ለሚለኝ ለፍቅሬም ሳይሳሳ፣
ከኔ ለበለጠው ለአገር ሆኗል ካሳ።

ማተብ በጥሶ ቃል ከማጠፍ፣
ይሻላል ቆርጦ ነፍስን መቅጠፍ፣
ሆነልት እንጂ ታሪክ ርስቱ፣
አላጓጓውም ቤተመንግስቱ።
ይሄ ነው ቆራጥ ይሄ ነው ጀግና፣
በታላቅ ስራው ፍቅሩን የሚያፀና።


ስሙ አባታጠቅ የሱ ፈረስ፣
ያውቃል ካሰበው ፈጥኖ መድረስ፣
ቼ እያለ ገስጋሽ ብርቱ ጋላቢ፣
ሜዳነው ሲሉት የሚገኝ ግቢ።
ዘውዱ ነበርኩኝ በሚስትነቴ፣
ንጉሴን አጥታ ጠፋች እናቴ፣
በጎዶሎ ቀን በዕድለ አንካሳ፣
አልኖርም አለች ነፍሴ ያለካሳ።



 


ማተብ በጥሶ ቃል ከማጠፍ፣
ይሻላል ቆርጦ ነፍስን መቅጠፍ፣
ሆነልት እንጂ ታሪክ ርስቱ፣
አላጓጓውም ቤተመንግስቱ።
ይሄ ነው ቆራጥ ይሄ ነው ጀግና፣
በታላቅ ስራው ፍቅሩን የሚያፀና።






https://www.youtube.com/watch?v=ZVKUwPtV5ec 

Tuesday, June 3, 2014

የሙዚቃ ሊቁ ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ

የሙዚቃ ሊቁ ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ
(ከ 1930 - 1990 ዓ.ም)
በኢትዮጵያ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ እውቀት ላይ የተመሠረተ ትምህርት በመማር የላይኛው
ጥግ ላይ የደረሰ ነው። በሀገሩ ኢትዮጵያ ውስጥ የሙዚቃ ት/ቤት እንዲከፈት አስተዋፅኦ
ካደረጉ ሰዎች መካከል አንዱ ነው። በዚሁ የሙዚቃ ት/ቤት ማለትም በቅዱስ ያሬድ ሙዚቃ
ት/ቤት የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ዳይሬክተር ሆኖ አገልግሏል። ከዚህምአልፎ በዓለም
አቀፍ ደረጃ የሙዚቃን ጥበብ እና መንፈስ ሲያስተምር የኖረ ነው። ዛሬ የሕይወት ታሪኩን
በጥቂቱ የምናነሳሳለት ኢትዮጵያዊው የሙዚቃ ሊቅ ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ ነው። አሸናፊ
ከበደ የተወለደው እዚሁ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በ 1930 ዓ.ም ነበር። አሸናፊ ከበደ ገና
በህፃንነቱ ድክ ድክ ሲል ነው ከሙዚቃ ጋር የተዋወቀው። የተዋወቀበትም አጋጣሚ በእናቱ
በኩል ነው። ወላጅ እናቱ ሁሌም ትዘምራለች። መፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉትን ሀረጋት
ከመዝሙረ ዳዊት ውስጥ እያወጣች ትዘምራለች።
ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ዜማዎችን ታንጐራጉራለች። ታዲያ ይህ መዝሙር እና እንጉርጉሮ በሕፃኑ
አሸናፊ ልብ ውስጥ፣ ጭንቅላት ውስጥ እና በአጠቃላይ እዝነ ልቡናው ውስጥ እየተዋሀደው
መጣ። የሙዚቃ ረቂቅ ስሜት እና ፀጋ በእናቱ በኩል ወደ እርሱ ተሸጋግራ አሸናፊ ውስጥ
ጓዟን ጠቅልላ ገባች። የሥነ-ጽሑፍ መምህሩ እና ታዋቂ ገጣሚ የሆኑት ዶ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ በ
1980 ዎቹ አጋማሽ ላይ Ethiopian Review በተባለ መፅሔት ላይ እንደፃፉት ከሆነ
የሙዚቃ ለዛ እና ጣዕም ኮተቷን ሰብስባ ወደ አሸናፊ ከበደ ሰብዕና ውስጥ የገባችው በእናቱ
በኩል ነው። እናቱ አሸናፊ ከበደ የሚባል የሙዚቃ ሊቅ ፈጥራለች እያሉ ፅፈው እንደነበር
አንብቤያለሁ። ታዲያ ምን ያደርጋል ይህች እናት ተልዕኮዋን ፈፀመች መሰል፣አሸናፊ ከበደ
ገና የዘጠኝ ዓመት ጮርቃ ሳለ ሕይወቷ አለፈች።
ግን የዘራቻት ዘር ዘላለማዊ ፀጋ ተጐናፅፋለችና ከአሸናፊ ከበደ ጋር አብራ አደገች፤ በኋላም
በአሸናፊ በኩል ተወለደች። ከዚያም እነሆ እስከ ዛሬ ድረስ መላውን የኢትዮጵያ ሕዝብ
እንዳስደሰተች ትኖራለች። እ.ኤ.አ በ 1999 ዓ.ም ኪምበርሊን ቺንታ የተባሉ ፀሐፊ ስለ
አሸናፊ ከበደ የሕይወት ታሪክ ፅፈው ነበር። ርዕሱም The Scholarship and Art of
Ashenafi Kebede (1938-1998) የሚል ነበር። በአማርኛ “ምሁሩ እና ጥበበኛው
አሸናፊ ከበደ ከ 1930-1990 ዓ.ም” ብለን ልንተረጉመው እንችላለን። ታዲያ በዚህ ጽሁፍ
ውስጥ ፀሐፊው ከሚገልጿቸው ሃሳቦች መካከልየአሸናፊ ከበደን የእውቀት ርቀት እና ጥልቀት
ነው።
እንደ ፀሐፊው አባባል ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ ኢትዮጵያ ካሏት (ካፈራቻቸው)
የባህልናየማንነት ቅርሶች መካከል በሙዚቃው ዓለም ትልቁን ስፍራ የሚይዝ ነው። አሸናፊ
የኢትዮጵያ የባህል ቅርስ ነው። የሙዚቃ አቀናባሪ ነው። መራሔ-ሙዚቃ /Conductor/
ነው። የሙዚቃ ታሪክ ተመራማሪ ነው። የሙዚቃ መምህር ነው። የልቦለድ ድርሰት ፀሐፊ
ነው። ባለቅኔ ነው። ወደር የማይገኝለት ጥበበኛ እያለ ኪምበርሊን ቺንታ ፅፏል።
Professor Ashenafi Kebede, one of Ethiopia’s greatest
cultural treasurescomposer, conductor, ethnomusicologist,historical musicologist, music educator, novelist and poet.
እየተባለ ለፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ ተፅፏል።



አሸናፊ ከበደ አብሮት ያደገውን የሙዚቃ ፍቅር ቅርፅ ሊያሲይዘው በ 1950 ዓ.ም ወደ
ዩናይት ስቴትስ አሜሪካ ተላከ። እዚያም Eastman School of Music ከተባለ
ዩኒቨርሲቲ በሙዚቃ ጥናት በ B.A ድግሪ ተመረቀ። ከዚያም ወደ ሀገሩ ኢትዮጵያ መጥቶ
የቅዱስ ያሬድ የሙዚቃ ት/ቤት እንዲከፈት ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑት መካከል አንዱ ስለሆነ
በተጨማሪም ደግሞ ሙዚቃን እንደ ጥበብ ተምሮ የመጣ ወጣት በመሆኑ የመጀመሪያው
የት/ቤቱ ዳይሬክተር ሆኖ ተሾመ። በዚህ በቅዱስ ያሬድ የሙዚቃ ት/ቤት ለአምስት ዓመታት
ካገለገለ በኋላ እንደገና የሁለተኛ ድግሪውን ሊያጠና ወደ አሜሪካ ተጓዘ። Wesleyan
University ገብቶ በ 1960 ዓ.ም የማስትሬት ድግሪውን ተቀበለ። የሙዚቃ ሊቁ አሸናፊ
ከበደ በዚህ ብቻም አላቆመም። የሙዚቃን ጥግ ማወቅ ስላለበት የዶክትሬት ድግሪውንም
ሊያጠና አመለከተ። ከዚያም የመግቢያ ፈተና ተሰጠው። ፈተናውንም በከፍተኛ ውጤት
አልፎ የዶክትሬት ድግሪውን መማር ጀመረ። በአስገራሚ ብቃት እና ችሎታ የአራት ዓመቱን
ትምህርት በሦስት ዓመት ውስጥ አጠናቆ በ 1963 ዓ.ም የዶክትሬት ድግሪውን እንዳገኘ
የሕይወት ታሪኩ ያወሳል።
አሸናፊ ከበደ በሙዚቃው ዓለም የተማረውና የዶክትሬት ድግሪውን ያገኘው ሙዚቃን
ከባሕል፣ ከታሪክ፣ ከማንነት፣ ከቋንቋ፣ ከሰው አንፃር በሚያጠናው የትምህርት ክፍል ማለትም
ethno-musicology የትምህርት ዘርፍ ነው። በዚሁ የትምህርት ዘርፍ የዶክትሬት
ድግሪውን ያገኘው በከፍተኛ ማዕረግ ነው። የሚገርመው ማዕረጉ አይደለም። በዚህ
የትምህርት ዘርፍ በዩኒቨርሲቲው ታሪክ የመጀመሪያው ተመራቂ እንደሆነም ተፅፎለታል።
ስለዚህ አሸናፊ የባሕል፣ የታሪክ፣ የማንነት፣ የቋንቋ እና የሰው ልጅን ስነ-ልቦና በሙዚቃ
ዓለም ውስጥ የሚያጠና እና ሙዚቃንም የሚቀምር ባለሙያ ነበር። አሸናፊ ከበደ፣ የሕይወት
አጋጣሚ ጠለፈችውና አሜሪካ የምትባል ሀገር አለቅህም ብላ ያዘችው። በተፈጥሮ እና
በትምህርት የተሰጠውን ፀጋ በአሜሪካ ልዩ ልዩ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ማስተማር ቀጠለ።
በመጀመሪያ ያስተምር የነበረው Queens College ውስጥ ነበር። እዚያ የተወሰኑ
ዓመታትን ካገለገለ በኋላ የማስትሬት ድግሪ ተመራቂ ተማሪዎች ወደሚማሩበት The City
University of New York ተብሎ ወደሚጠራው ተቋም ተዘዋውሮ ማስተማሩን
ቀጠለ። ከዚያም Brandeis University በሚባለው የሙዚቃ ት/ቤት ውስጥ አስተማረ።
ከነዚህ ዩኒቨርሲቲዎች ሌላም በተለያዩ የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ተጋባዥ ፕሮፌሰር
እየሆነ ሙዚቃን ለአሜሪካ ያስተምር ነበር።
አሸናፊ ከበደ ከማስተማሩ ጐን n ለጐን በስፋት የሚታወቅበት ችሎታው የጥናትና የምርምር
ሰው መሆኑ ነው። በተለይ በአፍሪካ ባሕሎችና ታሪኮች ላይ የተለያዩ የምርምር ወረቀቶችን
አቅርቧል። ከአፍሪካም ደግሞ ኢትዮጵያ ላይ እያተኮረ የዚህችን ሀገር ጥንታዊ ስልጣኔና
ማንነት እንዲሁም ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም የዋለችውን የታሪክና የባህል ብሎም
የስልጣኔ ውለታ በጥናቱ ያካትት ነበር። ኢትዮጵያዊው የዜማ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ፣ 
ዓለም ገናከእንቅልፉ ሳይነቃ በዝማሬና በዜማ በኩል ያበረከተውን አስተዋፅኦ አሸናፊ ለዓለም
ሲያስተዋውቅ ኖሯል።
አሸናፊ ከበደ በተለያዩ አፍሪካዊ ጥናቶቹ እና ምርምሮቹ የፕሮፌሰርነት ማዕረግ በሙዚቃው
ዓለም ተቀብሏል። ወደ ፍሎሪዳ ስቴትስ ዩኒቨርሲቲም በመሄድ የጥቁሮች የባሕል ማዕከል
/Center for Black Culture/ ተብሎ በሚጠራው ተቋም ውስጥ ዋና ዳይሬክተር ሆኖ
ተሾመ። ይህ ተቋም በኋላ “የአፍሪካ አሜሪካውያን የባህል ማዕከል” በሚል መጠራት
ጀምሯል። እስከ አሁንም ድረስ መጠሪያው Center for African American Culture
እየተባለ ነው። ዳይሬክተሩ ደግሞ ኢትዮጵያዊው የሙዚቃ ሊቅ ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ
ነበር።በዚህ ታላቅ ተቋም ውስጥ ዳይሬክተር ከሆነ በኋላም፤ ጥቁሮች እና ነጮች እንደ ሰው
የሚያገናኛቸውን ባሕላዊ፣ ሙዚቃዊ እና ታሪካዊ ጉዳዮችን እያነሳሳ ያወያያል። ያቀራርባል።
የተለያዩ ታላላቅ የዓለማችንን የሙዚቃ ሊቆች እየጋበዘ ኮንሰርቶችን እና አውደጥናቶችን
ሲያዘጋጅ ኖሯል። ፕሮፌሰር አሸናፊ ደራሲም ነው። በተለይ የጥቁር ህዝቦችንየሙዚቃ
ታሪክና ባህል ብሎም ማንነትን በሚያሳየው Roots ofBlack Music በተሰኘው
መፅሐፍውስጥ አያሌ መጣጥፎችን በዋናነት የሚፅፈው ይኸው ኢትዮጵያዊው ሊቅአሸናፊ
ነበር። በ 1959 ዓ.ም ደግሞ ሀንጋሪ ውስጥ The Black Kodaly በተሰኘ ዝግጅት ላይ
ባለ ዋሽንቱ እረኛ /The Shepherd Flutist/ በሚል ርዕስ አጅግ ድንቅዬውን ሙዚቃ
አቀረበ። ይህ ባለ ዋሽንቱ እረኛ የተሰኘው ሙዚቃ በዘመኗም ሆነ እስከ አሁን ድረስ የረቂቅ
ሙዚቃዎች ሁሉ የቁጥር አንድ ቦታዋን እንደያዘች ትገኛለች። ፕሮፌሰር አሸናፊ
ሌሎችአያሌ ሙዚቃዎችንም ተጫውቷል። በኢትዮጵያ ሙዚቃ ላይ ሰፊ ምርምርና ጥናት
ያደረገው ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ፣ ዛሬም ድረስ ፅሁፎቹ በአሜሪካን ሀገር ዩኒቨርሲቲዎች
መማሪያዎች ናቸው። ለምሳሌ በኢትዮጵያ ሙዚቃ እና ባህል ላይ ተመርኩዞ ባህሉንና
እድገቱንየፃፈበት የዶክትሬት መመረቂያ ፅሁፉ በቅርቡ በአንድ ጆርናል ላይ ዳሰሳ
ተሰርቶበታል። የዶክትሬት መመረቂያ ፅሁፍ ርዕሱም The Music of Ethiopia: Its
Development and Cultural setting የሚል ነበር። ኢትዮጵያ ሐገሩን እናህዝቦቿን
በተለይም ደግሞ መላውን አፍሪካ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲያስጠራ የኖረው ፕሮፌሰር አሸናፊ
ከበደ ግንቦት አንድ ቀን 1990 ዓ.ም በ 60 ዓመቱ ፍሎሪዳ ውስጥ ከዚህ ዓለም በሞት
ተለየ። የኢትዮጵያ የሙዚቃ ሊቅ አረፈ እያሉ በርካታ ሚዲያዎች በጊዜው ዘግበውለታል።
አሸናፊ ከበደ የሦስት ሴቶችና የአንድ ወንድ ልጅ አባትም ነበር። የመጀመሪያ ልጁ ኒና አሸናፊ
ዳኛ ናት። ሰናይት አሸናፊ ደግሞ ተዋናይት ሆናለች። ሦስተኛዋ ሴት ልጁ ሳምራዊት አሸናፊ
ስትባል ወንድየው ደግሞ ያሬድ አሸናፊ ይባላል። በአጠቃላይ ሲታይ የፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ
የጥናትና የምርምር ፅሁፎች በአብዛኛው አሜሪካ ውስጥ ስለሚገኙ የያሬድ የሙዚቃ ት/ቤት
ሰብስቧቸው ለትውልድ መማሪያ እንዲሆኑ ማድረግ አለበት እላለሁ። በተረፈ እንዲህ አይነት
የሙዚቃ ሊቅ በኢትዮጵያ ውስጥ እንዲፈጠር ሁሉንም ነገር ያመቻቹለትንም ግርማዊ
ቀዳማዊ ኃይለስላሴም ምስጋና ይገባቸዋል።
***********************************************************
ምንጭ :--ሰንደቅ 9 ኛ ዓመት ቁጥር 447 ረቡዕ መጋቢት 24 2006 ዓ.ም.