ከደራሲያን ዓምባ

Wednesday, July 16, 2014

የግጥም ጥግ

አገር ያለፍቅር -ፍቅርም ያለአገር

(የገጣሚና ጋዜጠኛ ነብዩ መኮነን ግጥም)
*************************************
መቼም ጮኸው ካልዘመሩት ; ነጻነት ቃሉ አይሰማ
ባንዲራው የሰማይ ችካል ; የፀሐይ እግር ኅብር -አርማ
ከቶም አገር ያለፍቅር ; ፍቅርም ያለውድ ሀገር
ነብስ የለሽ ስጋ ነውና ; እርሻ ያለ -ፍሬ መከር
ጀግና በልቡ እንደሚዳኝ ; በመንፈሱ ጽናት ካስማ
አገር ያለ ፍቅር ጠበል ; ፍቅር ያለ አገር ሙቅ ማማ
ከቶ አንዱም ያለ አንዱ አይለማ !
የልብ ወኔ ንዝረትኮ ; የአበው በገና ነው ምቱ
ወትሮም የሸንጎ ተውኔቱ ; ጥበብ ፋኖ ነው ቅኝቱ !
ማተብ እንደክራር ሲከር ; ቃኝው አርበኛ ነው ጎምቱ !
ያ ነው የነፃነት ዕፁ ; የሀገር ፍቅር ዕውነቱ ::
ለዚህ ነው ጥበብ መቆሟ ; ለሰው ልጂ ለሚሟገቱ !
ዱሮም ከሰቆቃ አንጀት ነው ; ኃያል ዜማ
________________________ የሚወለድ
በአርበኝነት ጥበብ ላንቃ ; ያገር ፍቅር እሳት ሲነድ !

ከዛሬ ስልሳ ዓመት በፊት ...
አገር ተወረረችና ; በነጭ አረመኔ መዓት
ሞትና ስደት አጠጠ ; አንዱ ዘመን ጣር በዛበት ::
መቼም ሰው ጠላቱን አይመርጥ ; የባላንጣም ቦቃ
___________________________ __የለው
በተለይ ባገር የመጣ ; የአገር ክንድ ነው 'ሚቀምሰው ::
የሀቅ ዐይኗ ተደንቁሎ ; የሰላም ብሌን ተጓጉጦ
የአውሮፖ ግፍ እንደጎሽ ግት ; አመፃው እንደጉድ
________________________________ፈጦ
አበሻ ሰቆቃው መጥቆ ;መከራ ሌት ከቀን ባርቆ
ሳቅ እንደዘላለም ርቆ
ጣሊያን ባመጣው ፍዳ አሣር ;በበላዔ -ሰብ ትናጋ
ጦቢያ ባንድ ልብ ደምቶ ; ከጠላት ግንባር ሊላጋ
ከፋሺስት ጥርስ ሊወጣ ; ከግፉ መንጋ መንጋጋ
አንድም ቅኔ ; አንድም ወኔ : ነፃነት ፋና ፍለጋ
አንድም ምሬት ; አንድም እሬት ; በህይወት
________________________ተውኔት አለንጋ
አንድም ፊድል ; አንድም ገድል : የግፍ ምዕራፍ
____________________________እስኪዘጋ
ጥበብን ማተብ አረጋት ; የአርበኛ ልቡን ሲያተጋ

መቼም መከራ ዳር አያውቅ
አንዱ ጠላት ከዚያ ዘልቆ ; አንዱ ጠላት ከዚህ ፈልቆ
ፋሺስትና ባንዳ ፈልቶ ; የወራሪ ግፉ ልቆ
ዕምነት እንደቅሌት አዋይ ; እንደ እራፊ ተበጫጭቆ
ስንቱ በደል እንደባህር ;ስንቱ ዕንባ ከኅዋ መጥቆ ...
አንድነት እንደሩቅ ዋይታ ; በሚስጥር ጎራ ለጎራ ;
በሙሾው ዋልታ ለዋልታ
በመቀነት በዝናር ድግ ; በዱር ትንፋሽ -በሹክሹክታ
ነበር ; እስኪነጋ ጀንበር ::
ፋኖ የልቡን አታሞ ; በአጥንቱ ቋር እየመታ
ነብሱን ከቸነከረበት ; የነፃነት ጎለጎታ
በደሙ ስርየት ሊያመጣ ; በእልሁ ድሆ አፍታ ካፍታ
ሰንደቅ አላማ እንደግማድ ;ተሸክሞ ነው የረታ ::
ጠላት ባንድ ፊት ሲባረር ;ባንዳ ባንድ ፊት ሲወገር
አገር በኪን አፍ ሲመሰክር
ፍቅር በጥበብ ሲዘከር
ኪነት እንደኩራት እርሾ
ቴያትር እንደጎበዝ ማሾ
መራር ያገር ፍቅር ዜማ
ከመድረኩ ዱር ሲያሰማ
ሽቅብ ሲል እስከነፃነት
ቁልቁል ሲል እስከአማን መሬት
ቃሉን በቃናው ልጎ ; ዳንሱን ሶምሶማ አድርጎ
ጦር ውስጥ በደሙ ሠርጎ
ትውልድን ለዛሬ አበቃ ; ስንቱ በጥበቡ ኮርቶ
አይሰው ተሰውቶ ; እስከ ንጋት ጎሁ ሞቶ !
ያ ነው ያገር ፍቅር ማለት ; የጥቁርም አህጉር ፀጋ
ማንም የማይሽረው ምትሀት ; ደም ያጠራው ታሪክ ዋጋ
መከራ አሳር ሲቀበል ; አርበኛ ገድሉን ሲሰራ
ጣልያንን "" ጣል -ያን !"" እያለ ;ጥልያንን ""ጥል -ያኔ !""
_____________________________________እያለ
አንዱ ጎራው ጥበብ ነበር ; የአገር የሽመናው ስራ
እየታየው የንጋት ጎህ ; በደም የተቀባው ሸራ
ያው ታሪኩን ቀልሞበታል ; የውሎ ገድሉን ደመራ ::
ፈርሶ የመገንባቱ ....ወድቆ የመነሳቱ
ይኸው ነው የታሪኩ ጽንስ ;የሀገር ፍቅር እትብቱ !!
እናም አገር ያለፍቅር ; ፍቅርም ያለውድ አገር
ደሞም ያለጥበብ አጋር
ለአፍታም ለዝንተ -ዓለምም
አንዱ ያላንዱ አይኖርም ::
አገር ቢሉ ፍቅር ነው
ፍቅርም ቢሉ አገር ነው
አገር -ፍቅርም ይኼው ነው !

****************************
ሐምሌ 1993 ዓ .ም
(ለሀገር ፍቅር ዳግም ልደት )

ከስውር ስፌት ገጽ 50-52.