ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, March 14, 2019

የአክሱም ጫፍ አቁማዳ

ገጣሚ ደበበ ሰይፉ
*****************



















ትግራይ ላከ ወሎ ጋ አበድረኝ ብሎ አንድ ቁና ጤፍ
ወሎም አፈረና የለኝም ማለቱን ባህሉን መዝለፍ ቆሌውን መንቀፍ
ላከ ወደ ሸዋ ምናልባት ቢሰጠው ለሰው እሚተርፍ፡፡
ሸዋም አፈረና የለኝም ማለቱን ወደ ሐረር ዞረ
ሐረርም መልሶ ባሌን አተኮረ
ባሌም ወደአርሲ ፤ አርሲ ሲዳሞን
ሲዳሞም ተክዞ ፤ ግን የለኝም ብልስ ማን ያምነኛል ብሎ
ወደጋሞ ላከ አቁማዳ ጠቅሎ፡፡

ጋሞን ብርድ መታው ሐዘን ገባውና
የራሱን ምንዳቤ የግል ስቅየቱን ችሎት በጥሞና
በጋቢ ደቡኖ የልቡን ጠባሳ ሲኖር እንደደህና
ዛሬ የወንድሙን የእርዳኝ አቤቱታ መስማት አልቻለና፡፡
አውጥቶና አውርዶ ላከ ወደ ከፋ እጅግ አስተዛዝኖ
ከሀፍረት ያድነኛል ፤ከረሃብ ያወጣኛል ሲል ባያሌው አምኖ፡፡
ከፋ እንደደረሰው በድንገት አቁማዳው በነብሱ ዋይታ
ሐራራው ተሰማው የሥጋው ድንፋታ
በብልሃት አዛጋ ቆይቶ ቆይቶ የተስፋ ጠል ቀዳ
ሲልክ ከኢሉባቦር አበድረኝ ብሎ እህል በአቁማዳ፡፡
ጭምቱ ኢሉባቦር ይኖር የነበረ የቤቱን ጉድ ጓዳ
በሞኝሞኝ ገላው ቆዳው ውስጥ ወሽቆ
ጠየቀ ወለጋን ሐፍረቱን ደብቆ ኩራቱን ዘቅዝቆ፡፡
ኬት አመጣ ብሎ ወደኔ ላከብኝ እያለ ወለጋ
እጅጉን ተደሞ
ሄደ ወደጎጃም ዛሬን ሁነኝ ብሎ ሲማፀነው ቁሞ፡፡
ጎጃምም ተሰምቶት ፤ሰቀቀን ሐዘን
ደረት እየመታ ፤ ቅኔ እያወረደ ፤እንባ እያፈሰሰ
ወግና ኩራቱን በየቦዳው መሐል እየነሰነሰ
ዐባይን ተሻግሮ ከጎንደር ደረሰ፡፡
ፋሲል ላይ ተነጥፎ፤ ጎንደርም ሐዘን ላይ ነበረ ተቀምጦ
ተድላ ልጁ ሙቶ ፣ ገናን ክንዱ ታጥፎ በዘመን ተድጦ
ጎጃም መጣ ሲሉት የእዝን የተመኘን ልቡን በታዘበ
የኩራት ካባውን ሊጥል ባንጓበበ
የወንድሙ መምጣት እቅጩ መንስዔ ፤መሆኑን ሲረዳ ረሀብ አበሳ
ጥንትም አልሆነኝም ከእንግዲህ ይበቃኛል ለይሉኝታ አልሳሳ
ብሎ ከኤርትራ እህል ለመበደር በርትቶ ተነሳ፡፡

የዘመዱ እጦት ነበረና እጦቱ በዝቶ ሰቀቀኑ
ኤርትራ ታመመ ደም ጎረፈ ከዓይኑ
ወደትግራይ ላከ መላ ባገኝ ብሎ ከአደራ ደብዳቤ
"እባክህ ላክልኝ አንድ አቁማዳ እህል ልሞት ነው ተርቤ፡፡"
ትግራይ አስተውሎ አቁማዳው የራሱ መሆኑን ለይቶ
ረሃብ ዕጣቸው የሁሉ ወንድሞቹ መሆኑን አካቶ
ሐዘኑ አነቀው ፣ትንፋሹ መረረው ትካዝ ሆዱ ገብቶ፡፡
"እኔና ወንድሞቼ" አለ በለዘብታ
ለራሱ እንዲያወራ የራሱን ስሞታ፣

"እኔና ወንድሞቼ ሁላችን...ሁላችን
ከባዶ አቁማዳ ነው እሚዛቅ ፍቅራችን
ይህ ነው አንድነታችን
ይህ ነው ባህላችን
ዘመን ማ
ጋቱ በያንደበታችን፡፡
ለኋላ ትውልዶች ተረት እንዳይመስል ይህ ብካይ እሮሮ
ይህ ጠፍ ሰብእና ይህ ስቁይ አእምሮ
እንዳኖረው ያሻኛል ይህንን አቁማዳ ከፍ ካለ ስፍራ መጥቆ እንደባንዲራ
ምንም ባዶ ቢሆን በውስጡ አይጠፋና የታሪክ አዝመራ"

ይህንን ተናግሮ ከአክሱም ሐውልት ዘንድ ትግራይ ተጠግቶ
አንዴ እየፀለየ አንዴ እያወዘመረ ያለመጠን ተግቶ
ጫፉ ላይ ሰቀለው ያን አቁማዳ አውጥቶ፡፡
*************************************
ደበበ ሰይፉ
1967 ዓ.ም.

                   ይህው በድምፅ:-
                                          https://www.youtube.com/watch?v=7rSJw8ipadQ