ከደራሲያን ዓምባ

Tuesday, May 18, 2021

ይህ የኢትዮጵያ ሬዲዮ ነው

 

“የሕዝቡን ዐይን በሬዲዮ እንክፈት” 

በሚል በፈር ቀዳጅነት የተተከለው የኢትዮጵያ ሬዲዮ፤ 

የ85ኛ ዓመት ሻማውን 
(መስከረም 2 ቀን 2013 ዓ.ም.) ለኮሰ።


 

በአሁኑ ወቅት ንፋስ ስልክ በሚል የምናውቀው አካባቢ ስሙን ያገኘው ሬዲዮ ለሚለው ቃል ሀገራዊ መጠሪያ ሲወጣለት በነፋስ የሚሄድ “ያለ ሽቦ ቃል የሚያሳልፍ መኪና” ተብሎ ከመሰየሙ ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሬዲዮ ታሪክ ከቴሌ ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የቴክኒክ ሰራተኞቹ ቅጥር በቴሌ ስር ነበር፡፡ በቀደምቱ ጊዜ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ለሚሰራ ጋዜጠኛ ትልቁ እድሉ ከአንጋፋዎቹና ነባሮቹ ጋር መካከለኛዎቹና አዲሶቹ ተጣምረው ስለሚሰሩ ደቀ መዝሙሮቹ ከመምህሮቹ የካበተ እውቀትና የተፈተነ ልምድ የሚቀስሙበት ሰፊ እድል ነበር፡፡ ጀማሪዎች ወደ ህዝብ ከመቅረባቸው በፊት በሙያ ተገርተው ተቃንተው እውቀትን ከክህሎተ በማዳበር የሙያ ስነ ምግባርን ከማህበራዊ ህይወት አዋዶ ለመማር የሚያግዝ ታላቅ ኮሌጅ ነው ብሎ ደፍሮ መናገር ይቻላል፡፡

ግርማዊ ቀዳማዊ ሀ/ስላሴ የማእዘን ድንጋይ በ1923 ሲያስቀምጡ “ያለሽቦ ቃል የሚያሳልፍ መኪና” ብለው ነበር ሬዲዮን የጠሩት፡፡ የኢትዮጵያ ሬዲዮ የኢጣሊያ አንሶልዶ ኩባንያ በንፋስ ስልክ አካባቢ በሰራው ሬዲዮ ጣቢያ ስራውን መስከረም 2 / 1928 ጀምሮ ዛሬ ላይ 85ኛ አመቱን ሲያከብር የመጀመሪያዎቹ የሬዲዮ አንባቢዎች ከወንዶች ከበደ ሚካኤል ከሴቶቸ ደግሞ ወ/ሮ ሮማነወርቅ ካሳሁን ይጠቀሳሉ፡፡

ዲዮው ያኔ ከአ/አ ርቆ አለመሰማቱ ብቻ ሳይሆን ፉጨትና ይጮህም ስለነበር ጥራት ይጎድለዋል፡፡ ግርማዊነታቸው በነገሱና ሬዲዮውም በጀመረ አጭር ጊዜ ውስጥ ኢጣሊያዎች ጣቢያውን አስቀርተው የራሳቸውን ጣቢያ አቡነ ጴጥሮስ አደባባይ ላይ መስርተው ዘመናዊ ትምህርት ያላቸውን ኢትዮጵያውያን አሳደው መግደልና የተረፉትንም ለራሳቸው ቢሮ ግልጋሎት እየነጠቁ ከተወሰዱት መካከል ብላታ ወ/ጊዮርጊስ ወ/ዮሀንስና ከበደ ሚካኤል ይጠቀሳሉ፡፡ ጣቢያውንም አፍሪካ ኦሪዬንታሌ ኢታልያና በማለት የኢጣሊያ ምስራቃዊ አፍሪካ ሬዲዮ በማለት በኢትዮጵያ _ በኤርትራና በሶማሊያ ሀገርን የሚያዳክም ፐሮፖጋንዳ ይሰራጭበት ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ሬዲዮም በ1933 ቀድሞ ወደነበረበት ንፋስ ስልክ አልተመለሰም፡፡

በይዘት ደረጃ ደግሞ ከ1950ዎቹ ወዲህ በእንግሊዝኛ ውጭ ተምረው የመጡት እነ ጋሽ ሉልሰገድ ኩምሳ ‘ ወ/ሮ እሌኒ መኩሪያ እና ሳሙኤል ፈረንጅ አይዘነጉም፡፡ ያኔ በሞጋችና በይዘት ጥልቅ ቅንብሮቻቸው ስመጥር ከነበሩት መካከል አሳምነው ገ/ወልድ ‘ በመምህሬ አብራራው መጠሪያ የሚታወቀው መንግስቱ መኮንን ‘የስፖርቱ ሰለሞን ተሰማ ‘ በአጠቃላይ ትንተን አሀዱ ሳቡሬና አቶ ነጋሽ ገ/ማርያም በሳይንስ ሻምበል አፈወርቅ ዮሀንስ ‘ ጳውሎስ ኞኞ ‘ በአሉ ግርማ እንዲሁም በጥበባት ደግሞ ዮሀንስ አድማሱ ‘ አብዬ መንግስቱ ለማ ‘ ሰአሊና ገጣሚ ገ/ክርስቶስ ደስታ ‘ ሰለሞን ደሬሳና ተስፋዬ ገሰሰ “የኪነ ጥበባት ጉዞ” የሚል ፕሮግራምን ያዘጋጁ ነበር፡፡

ያኔ በሬዲዮ ጅማሮው ወቅት የማስታወቂያ ሚኒስትር የነበሩት ድጃዝማች ግርማቸው ተ/ሀዋርያት በ1954 የአለም አቀፍ አገልግሎቱ ጅማሮ ሁነት ላይ፡_ “ከእንግዲህ ወዲህ ኢትዮጵያ ወዳጅ በሆኑት አፍሪቃ ‘መካከለኛው ምስራቅና አውሮፓ የምትሰማ ይሆናል፡፡ ከአለም ህዝቦች ጋር ለመቀራረብም እንደሚረዳ የታመነ ነው ብለው ነበር፡፡

እኔ ከ1980ቹ አጋማሽ ወዲያ ከዩኒቨርስቲ ወጥቼ ከጥቂት ወራት መምህርነት ቀጥሎ ዜና ፋይልን ስቀላቀል ከአንጋፋዎቹ ጋሽ ጥላሁን በላይና ከጋሽ ዳሪዎስ ሞዲ አለቆቻችን አንስቶ ‘ የፈረቃ መሪዎች ከነበሩት እጅግ ነባሮቹ ዳንኤል ወ/ሚካኤል ‘ በቃሉ ደገፋው ‘ ንግስት ሰልፉ ‘ ዋጋዬ በቀለና ነጋሽ መሀመድ ነበሩ፡፡ በመቀጠል አሁንም ከነባሮቹ መካከል አማረ መላኩ ‘ ተካልኝ ይርሳው ‘እ/ህይወት ደምሴ ‘ ደበበ ዱፌራ ‘ ገነት አስማረ ‘ ተስፋዬ መክብብ ‘ አለምነህ ዋሴ ‘ ደስታ ሎሬንሶ ‘ብርትኩዋን ሀ/ወይን ‘ ተፈሪ አንለይ ‘ ተፈሪ ለገሰ ‘ ሺበሺ ጠጋዬና ቴዎድሮስ ነዋይ ሲወሱ በተከታይነትም እሸቱ ገለቱ ‘እሸቱ አበራ ‘እሸቱ አለሙ ‘ ስለሺ ሽብሩ ‘ ደግነህ ገ/ስላሴ ‘ ዘመድኩን ተክሌ ‘ ብሩከ ነጋሽ ‘ ታደሰ ዝናዬ’ አማኑኤል አብዲሳ ‘አዲስ አለማየሁ ‘ የኔነህ ከበደ ‘ አብዱልሰመድ መሀመድ ‘ቢኒያም ከበደ ‘ ለምለም በቀለ ‘ እያደር አዲስ ‘ዳንኤል አማረ ‘አለማየሁ ግርማ ‘ ሰለሞን ግዛው ‘ ሳሙኤል ፍቅሬ ‘ ሲሳይ ዘሪሁን ‘ ጌታሁን ንጋቱ ‘ ምናላቸው ስማቸው ‘ሀ/እየሱስ ወርቁና ጋሻው ተፈራ ነበሩ፡፡

ከዚህ ወዲያ ነበር እነ አሸናፊ ሊጋባ ‘ ነጣነት ፈለቀ ‘ አዲሱ መሸሻ ‘ ሰሎሜ ደስታ ‘ሰኢድ ሙሄ እና ሰለሞን ዮሀንስ የተቀላቀሉን፡፡ ከዜና ክፍል ጋር በስፖርቱ ጋሽ ይንበርበሩ ምትኬ ‘ ጎርፍነህ ይመር ‘ ደምሴ ዳምጤ ‘ ዳዊት ንጉሴ ‘ ዳንኤል ጋሻውና ታደለ ሲጠቀሱ ለፕሮግራም ስራ መስክ በወጡ ቁጥር ዜና ይዘው ከሚመጡት መካከል ደግሞ ሞገስ መኮንን ‘ አስቻለው ጌታቸው እና ነቢያት ገቢሳ አይዘነጉኝም፡፡

በኢኮኖሚያዊ ማህበራዊና ጥበባዊ ዝግጅቶችን በማቅረብም እነ ጋሽ ታደሰ ሙልነህ ‘ንጉሴ አክሊሉ ‘ አዲሱ አበበ ‘አባይነሽ ብሩ ‘ታምራት አሰፋ ‘ጠሀይ ተፈረደኝ ‘ደረጀ ሀይሌ ‘ዳንኤል አያሌው ‘ ጌታቸው ማንጉዳይ ‘ ቤዛዬ ግርማ ‘ ነጋሽ ግዛው ‘ሰለሞን ደስታ ‘ ሂሩት መለሰ ‘ደጀኔ ጥላሁን ‘ አስፋው ገረመው ‘ በልሁ ተረፈ ‘ ልባርጋቸው ሽፈራው ‘ብርሀኑ ገ/ማርያም ‘ ቅድስት በላይ ‘ መስፍን ዘለቀ ‘ አምባዬ አማረ ‘አስካለ ተስፋዬ ‘ ዘውዱ ግርማና መሳይ አለማየሁ ሲሆኑ ከብሄራዊ ሬዲዮ አገልግሎቱ የተዛወሩትንም ለአብነት እንዳልካቸው ፈቃደ ‘ አስቻለው ሽፈራው ‘ ኤልሳቤት ሳሙኤል ‘ ማርታ ጠጋውና አበበ ፈለቀ ሊነሱ ይችላሉ፡፡

ከ1956 ወዲህ ሰፋ ያለ አካባቢን የሚሸፍን በ9 ቦታዎች ማሰራጫ በመትከል ለማሻሻል ታስቦ በገንዘብ ውሱንነትን የየአካባቢው የፖለቲካ ሽፍታ በትንሽ መሳሪያ ጣቢያውን በመቆጣጠር ንጉስ ሆኛለሁ እያለ ስጋት እንዳይጭር በሚል በ3 ቦታ ብቻ ተወስኖ በአዲስ አበባ ጌጃ ዴራ _ በአስመራ አዲ ኡግሪ እንዲሁም በሀረር ሀኪም ጋራ ላይ ተተከለ፡፡ የኢትዮጵያ ሬዲዮ የማሰራጫ አድማሱን በማስፋት ከ1984 ወዲህ የመቱ ማሰራጫ አኙዋክና ኑዌርን ከጨመረ አንስቶ በ11 የመግባቢያ መንገዶች መረጃዎችን ለህዝብ እያቀበለ እንደቀጠለ ነው፡፡ ከ1959 ወዲያ ግርማዊነታቸው በ35ኛው የዘውድ በአላቸው ሰፊ ሽፋን ያለውን ማሰራጫ አስመርቀው የአዲስ አበባ ብቻ በሚል ይጠራ የነበረው የኢትዮጵያ ለመባል በቃ፡፡

በተማከለ መልኩ የሬዲዮ ዜና ማእከል ሁሉንም ዴስኮች ካሰባሰበ ወዲያ ከኦሮምኛ እነ ጋሽ ተስፋዬ ቱጂ ‘ ሀሊማ ኢብራሂም’ ዮሀንስ ዋቆ ‘ፉሪ ቦንሳ ‘ ጋሸ አለማየሁ ‘ ጋሽ ሁሴን ‘በዳሶ ሀጂ ‘ መክብብ ሸዋ ‘ኢሳ ኡመር ‘ ካሳሁን ፈይሳ ‘ራሄል ግርማ ከብዙ በጥቂቱ ሲታወሱ ከትግርኛ ደግሞ እነ ነጋ ‘ተወልደ ‘ ኪሮስ ‘እዮብ ‘ ብርሀነ ‘ትርሀስ ‘ አማን አሊ ‘ ገ/አምላክ ተካ ‘ አክሊሉ ደባልቀው ‘ አሰፋ በቀለ ‘አልማዝ በየነና ዮናስ አይዘነጉም፡፡

ከአንግሊዝኛ ዴስክ ጋዜጠኞች እነ ጋሽ ዮሀንስ ወ/ሩፋኤል ‘ ግሩም ታሪኩ ‘ መለሰ ኢዳ ‘ስለሺ ዳቢ ‘ ባህሩ ተመስገን ‘ፍ/ህይወት ‘ ንግስት ‘ቴዎድሮስ ዘውዴ ‘ ሲሳይ ሀ/ስላሴ ‘ ብሩኬ ከብዙ በጥቂቱ ሲነሱ ከፈረንሳይኛ እነ ጋሽ ጌታቸው ተድላ ‘ ጋሽ ፍራንሲስ ‘ጋሽ ተስፋዬ ‘ ርብቃን እናውሳና ከአረብኛ እነ ጋሽ አደም ኡስማን ‘ሼህ ኢብራሂም ‘ ጋሽ መኮንን ‘ ከድርና ካውሰር ይጠቀሳሉ፡፡ ከሶማሊኛ ጋሽ ጊሬ ‘ ሀሰን እና አብዱላሂን ሳንዘነጋ አፋር ዴስክ ጋ ስንሻገር እነ አብዲና አህመድን ሳንጠቅስ አናልፍም፡፡

ከ1990ዎቹ ወዲያ የመጡትን ደግሞ ከአሸናፊ ሊጋባ በከፊል ወስጄ የሚከተሉትን ለመጥቀስ ያህል ብሩክ ያሬድ ፣ አብዲ ከማል ፣ የትምወርቅ ዘለቀ ፣ ፍትሃወቅ የወንድወሰን ፣ ሀና ተሟሪ ፣ ፋሲል ግርማ ፣ ህይወት ደገፉ ፣ መሰረት ተመስገን ፣ እያሱ ፈጠነ ፣ ሰለሞን ገዳ ፣ ሰይፉ ገብረጻድቅ ፣ እየሩሳሌም ተክለጻዲቅና ሌሎችንም እናንተው አክሉበት፡፡

በመዝናኛው ዛሬ ላይ የሸገር ሬዲዮ ባለቤት የሆኑት እነ መአዛ ብሩና ተፈሪ አለሙ _ የኢትዮ ኤፍ ኤም ሬዲዮ ታላቅ ባለድርሻዎች በአብዬ ዘርጋው የሚታወቀው ሰራዊት ፍቅሬና ሰይፉ ፋንታሁን እንዲሁም የአሻም ቲቪ ባለድርሻዎቹ እነ ሱራፌል ወንድሙ ‘ ግሩም ዘነበ ብሎም በግዞ ተከታታይ የሬዲዮ ድራማ መለያው የነበረው የባላገሩ ቲቪ ባለድርሻው አብረሃም ወልዴ _ እነ አብረሀም አስመላሽና እከ ንብረት ገላውን ጨምሮ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ስራቸው ለምልሞ ያደጉ ናቸው፡፡ በሀገር ቤትና ውጭ ያሉና የነበሩ እነ አሸናፊ ዘደቡብ ‘እሸቴ ከጃን ሜዳ ‘ ዳንዴው ሰርቤሎ ‘ ቀስቶ ከኮተቤ ‘እነ ሀይሉ ጠጋዬ ‘ ተመስገን አፈወርቅ ብቻ ማንን ጠቅሼ ማንን ልተው የዘለልኩትን አክሉበት፡፡

ከቴክኒክ ክፍሉ ከእነ ጋሽ ተካ ወ/ሀዋርያት ‘ ጋሸ ገበየሁ ኑሬሳ ‘ መቅደስ አማረ ‘ ትርሲት ወንድሙ ‘ አቢ ‘ ይትባረክ ‘የአይኔአበባ ተክሌ ‘ በለጥሻቸው ‘ ሰላማዊትና ቤቲ ከብዙ በጥቂቱ እንዲሁም ከማሰራጫ ጋሸ ከበደ ጎበና ‘ጋሽ መላከ ‘ ኢ/ር ዘገየ ‘ጋሽ ካሳ ሚልኮ ‘ ሲሳይ ‘ክንዱ ‘ዘሪሁን ‘ ገረመው ‘ ተስፋዬ ‘ዳዊት ‘ ለዊ በተጨማሪነትም በሞኒተሪንግና ታይፕ እነ ሙሉ ‘ገነት ‘ ቆንጂት ‘ታየች ‘ጥሩዬና ሰናይት ‘ መስፍኔ ‘አስኒ ‘ ብዙዬ እና አሰለፍ አይረሱኝም፡፡

ያኔ ከወረራው ወዲህ በ1934 ኢትዮጵያ ሬዲዮ ተመልሶ እንደገና በቀን የ4 እና 5 ሰአት የቀጥታ ስርጭቱን ሲቀጥል 3 አላማዎች ነበሩት፡፡ ያኔ በጃንሆይ በድልድሉ መሰረት . . . 1 _ ዜናን ኢንፎርማሊያን . . . 2 _ ትምህርታዊ ኢጂኬሽን . . . 3 _ አዝናኝ ኢንተርቴይንመንት ሆነው በምጣኔ ረገድ 60 በመቶው አሳዋቂና አስተማሪ መሆን ሲጠበቅባቸው ቀሪ 40 በመቶው እጅ ደግሞ ለመዝናኛ እንዲሆን ተወስኖ ነበር፡፡ (*የጋዜጠኛ እሸቱ ገለቱ ጽሑፍ)


የኢትዮጵያ ሬዲዮ ትዝታ: በ አርትስ ቲቪ በነገራችን ላይ ክፍል _፩ 

የኢትዮጵያ ሬዲዮ ትዝታ: በ አርትስ ቲቪ በነገራችን ላይ ክፍል _፪

የኢትዮጵያ ሬዲዮ ትዝታ: በ አርትስ ቲቪ በነገራችን ላይ ክፍል _፫




 




Monday, May 3, 2021

ሚሻ ሚሾ (ሙሾ)

 


 ከበዓለ ስቅለት ባህላዊ መገለጫዎች አንዱ በሰሜን ኢትዮጵያ የሚዘወተረው ‹‹ሚሻ ሙሾ›› ነው፡፡

ስለዚህ ባህላዊና ትውፊታዊ ሥርዓት ቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ መታፈሪያ ‹‹መዝገበ በረከት ዘሰሙን ቅድስት›› በተሰኘውና መሰንበቻውን ለንባብ በበቃው መጽሐፋቸው ዘርዘር አድርገው ማስረጃዎች እያጣቀሱ አቅርበውታል፡፡

በደራሲው አገላለጽ፣ ዕድሜያቸው ከ15 ዓመት በታች የሆኑ ወንዶች ሕፃናት ደግሞ ‹‹ሚሻ ሙሾ›› እያሉ እየዘመሩ በየቤቱ እየዞሩ ዱቄት ይለምናሉ፡፡ በዓሉ በቂጣ ስለሚከበር የአይሁድ የቂጣ በዓልን ይመስላል፡፡ አለቃ ታየ ገብረ ማርያም በ1902 ዓ.ም. በታተመው የትብብር ሥራቸው ‹‹ሚሻ ሚሾ›› የሚለው ስያሜ የት መጣ ‹‹ውሾ ውሾ›› ከሚል እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡

ሊቀ ሥልጣናት አባ ሀብተ ማርያም ወርቅነህ ‹‹ማኅበራዊ ኑሮ በኢትዮጵያ›› ብለው በሰየሙት መጽሐፋቸው፣ ይህም አይሁድን ለመስደብ የተሰነዘረ እንደሚመስል ይገልጻሉ፡፡ በሌላ መልኩ መምህር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል ደግሞ ‹‹ሚሻ ሚሾ›› ወዲያ ወዲህ፣ ከዚያ ከዚህ ማለት ነው፡፡ ይህም ከየቤቱ ዱቄቱ የሚሰበሰብ መሆኑን ለማመልከት ነው በማለት ያስረዳሉ፡፡ በተጨማሪም የትውፊቱ ትክክለኛ መጠሪያ ‹‹ሙሾ ሙሾ›› የክርስቶስን ሕማም ለመግለጽ የተሰጠ መሆኑን፣ በጊዜ ሒደት ተለውጦ ‹‹ሚሻ ምሾ›› መባሉንም ይገልጻሉ፡፡

አለቃ ደስታ ተክለ ወልድም የቃሉን ፍች ‹‹ሙሾ (ምሾ) የለቅሶ ዜማ፣ የለቅሶ ቅንቀና፣ ግጥም፣ ዜማ፣ ቁዘማ፣ እንጉርጎሮ፣ ረገዳ፣ ጭብጨባ ያለበት›› በማለት ያስረዳሉ፡፡ ይኼኛው ሐተታ ከክዋኔው ጋር ቀጥታ ቁርኝት አለው፡፡ ሕፃናቱ በየቤቱ መሄዳቸው አይሁድ ሐሙስ ሌሊት ከሐና ወደ ቀያፋ፣ ከቀያፋ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቤት መዞራቸውን ለመዘከር ነው፡፡ ሕፃናት ይህን ዕለት እንዲያስታውሱት በየዓመቱ እንዲዘክሩ በማድረግ ይቻል ዘንድ ሊቃውንት ይህንን ሥርዓት እንደሠሩ ይናገራሉ፡፡

‹‹ሕፃናት ከምሴተ ሐሙስ ጀምረው እስከ በዓለ ስቅለት ምሽት የሚሻ ሙሾን ዝማሬ እያሰሙ በየቤቱ በመዞር ዱቄት የሚያሰባስቡት ትውፊታዊ ክዋኔ አለው፡፡ ሕፃናቱ በየቤቱ ዱቄት ለመሰብሰብ ሲዞሩ በቀለማት ወይም በእሳት ተለብልቦ የተዥጎረጎረ ቀጭን ዘንግ ይይዛሉ፡፡ መሬቱን በዘንግ በመምታት ዱቄት እስኪሰጣቸው ድረስ በተለያዩ ግጥሞች የታጀበ ዝማሬ ያሰማሉ፡፡ ይህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በዘንግ መመታቱን ለማዘከር ነው፡፡

 


 

በዝማሬያቸው

‹‹ሙሻ ሙሾ ስለ ስቅለቱ

አይንፈጉኝ ከዱቄቱ፡፡

ሚሻ ምሾ፣ ሆ ሚሻ ሙሾ

ሳይጋገር መሸ፣

እሜቴ ይውጡ ይውጡ

ይበላዋል አይጡ፣

እሜቴ ይነሱ

ይንበሳበሱ፣

ከቆምንበት

ቁንጫው ፈላበት፣

ስለ አቦ

ያደረ ዳቦ፣

ስለ ስቅለቱ

ዛቅ አድርገው ከዱቄቱ፤››

በማለት ይዘምራሉ፡፡

ሕፃናት ሚሻ ሙሾ ብለው አንድ ቤት ሲጨፍሩ ከቤቱ ዱቄት፣ አዋዜ፣ ቅባኑግ ወይም ጨው ሊሰጣቸው ይችላል፡፡ ይኼንን ሲያገኙ 

‹‹ዕድሜ የማቱሳላን፣

 ጽድቅ የላሊበላን ይስጥልን፤›› ብለው መርቀው ይሄዳሉ፡፡ 

በተጨማሪም ሕፃናት በዚህ ክዋኔ ታላቅ ምርቃት ይሰጣቸዋል፡፡ ሕፃናቱ ለምነው ምንም ነገር ሳይሰጣቸው ከቀረ

‹‹እንደ ሰፌድ ይዘርጋሽ፣ 

እንደ ማጭድ ይቆልምሽ፣ 

ቁመት ያውራ ዶሮ፣ 

መልክ የዝንጀሮ፣ 

ግማት የፋሮ ይስጥሽ፤›› ብለው ተራግመው እንደሚሄዱ አለቃ ታየ ትውፊቱን አስቀምጠዋል፡፡

ሕፃናቱ በልመና ባገኙት ዱቄት ቂጣ ጋግረው ቅዳሜ ምሽት በጋራ ይመገቡታል፡፡ ሊቀ ሥልጣናት አባ ሀብተ ማርያም ወርቅነህ ግን ዳቦውን በትንሣኤ ሳምንት አስጋግረው ጎረቤቶችንና ሽማግሎችን ጋብዘው እንደሚበላ ተናግረዋል፡፡

 ******+++******


 

አርብ ፦ሚሻሚሾ

ሆሆ ሚሻ ሚሾ ሚሻ ሚሾ
አንድ አውራ ዶሮ እግሩን ተሰብሮ
እሜቴ ይነሱ ጉሽጉሻውን ይዳስሱ
ስለ ስቅለቱ ዛቅ አድርገው ከዶቄቱ


እያሉ ህፃናት ተሰብስበው በየቤቱ እየዞሩ የቤቱን ደጃፍ በያዙት ዱላ እየደበደቡ ከላይ ያለውን ግጥም በዜማ ይላሉ። አስቀድመው ግን ዱላ ያዘጋጃሉ ዱላ ሲያዘጋጁም ይልጡትና በልጡ ግማሹን ይሸፍኑትና በእሳት ይለበልቡታል ከዛ ሲወጣ ዝንጉርጉር ይሆናል ነጭና ጥቁር ።በጲላጦስ አደባባይ ጌታችን አጥንቱ እስኪታይ መገረፉን ለማመልከት መሆኑንም ታላላቆቻችን ይናገራሉ.... ሚሻ ሚሾ አንዳንዶች ውሾ ውሾ እያሉ ጌታችንን ማህበራነ አይሁድ መስደባቸውን ለመግለፅ ነው ይላሉ አንዳንዶቹ ደግሞ ዕለቱ የሐዘን ነው አልቅሱ እዘኑ ለማለት ነውም ይላሉ ምሻሚሾ (ሙሾ-ሐዘን ፣ለቅሶ እንዲል ዱቄቱን ከሰበሰቡ በኃላ ደግሞ ድንጋይ እና ድንጋይ በማጋጨት ጫጫ መሰልቀጫ ሚስቴ ወልዳብኝ ጨውና ዘይት ብላብኝ እያሉ ይዞራሉ ለምን ድንጋይ እንደሚይዙ ግን እስካሁን አልገባኝም በኃላም ከተመረጠ ቤት ይሰበሰቡ እና የሰበሰቡት ዱቄት ተቦክቶ ቂጣ ይጋገራል ከዛ ደግሞ የሰበሰቡት ጨው እና ዘይት ይለወስና ቂጣው ይቀባል ከዛ የሚበላው ተቆርሶ ይሰጠዋል ለሚፆመው ደግሞ ይቀመጥለት እና ከቤተ ክርስቲያን መልስ ትልቁም ትንሹም ከተመረጠው ቤት ቡና ተፈልቶ የሚበላው በልተው ጠጥተው የሚያከፍለውም በጨዋታው መሀል ተገኝቶ ተመራርቀው ይለያያሉ

የአርብ ስቅለት በጎንደር እና አከባቢው እንደዚህ ይከበራል እንደሰማሁት በትግራይ አከባቢ ደሞ ልጃገረዶች ሙሉ ቀኑን በባዶ ሆዳቸው ሆዳቸውን በመቀነት አጥብቀው በማሰር ዥዋዥዌ እያሉ ይውላሉ መንገላታቱን ለማሰብ፤ በዋግም እንደዚሁ፤በጎጃም አገዎችም አጎላ ጎሊ ይባላል።


 በጎጃም አገዎችም አጎላ ጎሊ ይባላል:-


 
 
#EBC ሚሻ ሚሾ/አጎላ ጎሌ በአ እንዴት እንደሚጨፈር እና ምን አይነት ሂደቶችና ስርዓቶች እንዳሉት ያስቃኘናል
 


እጅጋየሁ (ጂጂ) ሽባባው አጎላ ጎሌ


***********************************************

ምንጭ:- https://www.ethiopianreporter.com/article/21944

           :- የጥበብ ወሬዎች