ከደራሲያን ዓምባ

Wednesday, August 30, 2023

ጆሴፍ ፑልቲዘር

 

የፕሬስ ነጻነት ጠበቃ - ጆሴፍ ፑልቲዘር 

ጋዜጠኛ፣ መርማሪ  ሪፖርተር፣ አሳታሚ፣ የፕሬስ ነጻነት ጠበቃ፣ በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያውን የጋዜጠኝነት ት/ቤት ከፍቷል - በተጨማሪም ለጋዜጠኝነትና ሥነጽሁፍ ዘርፎች፣ ዝነኛውን የፑልቲዘር ሽልማትም ፈጥሯል፡፡

ጆሴፍ ፑልቲዘር፤ የተሻለ የዕይታ ብቃት ይዞ ቢወለድ ወይም ቼዝ መጫወት ባይችል ኖሮ፣ ጋዜጦቻችን ዛሬ ከምናውቃቸው የተለዩ ይሆኑ ነበር፡፡ ጆሴፍ በ1860ዎቹ በሃንጋሪ በታዳጊነት ዕድሜው ሳለ፣ ወታደር የመሆን ብርቱ ፍላጎት ነበረው፡፡ ነገር ግን ዓይኑ (ዕይታው) ደካማ በመሆኑ የተነሳ የትኛውም ሠራዊት ሊቀበለው አልቻለም፡፡ በመጨረሻ ግን የአሜሪካ ቀጣሪዎች፣ በአሜሪካው የእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ እንዲዋጋ መለመሉት፡፡  
በወታደርነት ለአንድ ዓመት ያገለገለው ጆሴፍ፤ ከእርስ በርስ ጦርነት ህይወቱ ተርፎ እዚያ አሜሪካ ተቀመጠ - ያገኘውን  ሥራ እየሰራና እንግሊዝኛ ቋንቋ እየተማረ፡፡ ከዚያም በአጋጣሚ የተከሰተ ድንገተኛ ትውውቅ፣ የራሱንም ህይወት ሆነ የዓለም ጋዜጠኝነትን ታሪክ ለዝንተ-ዓለም ለወጠው፡፡
እንዲህ ነው የሆነው፡፡
ጆሴፍ በቅዱስ ሉዊስ ቤተመጻህፍት ውስጥ እያጠና ሳለ፣ ሁለት ወንዶች ቼዝ ሲጫወቱ ይመለከታል፡፡ ጠጋ ብሎም የአንደኛውን የቼዝ አጨዋወት በማድነቅ ተናገረ፡፡ ከዚያም ሦስቱ ሰዎች መጨዋወት ይጀምራሉ፡፡ ሁለቱ ሰዎች የጋዜጣ አሳታሚዎች ነበሩ፡፡ እናም የሥራ ዕድል ሰጡት - ለጆሴፍ፡፡  

ጆሴፍ ፑልቲዘር ብሩህና ትጉህ ሪፖርተር መሆኑን አስመሰከረ፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላም የጋዜጣ አሳታሚ ሆነ፡፡ ከዚያም  አዋጭ  ድርድሮችን ተራ በተራ  ሲያካሂድ ቆይቶ፣ የከተማው ትልቁን ጋዜጣ በእጁ አስገባ - ”St. Louis Post- Dispach” የተሰኘውን ጋዜጣ ገዛው፡፡


ይሄኔ ነው የፑልቲዘር እውነተኛ የላቀ አዕምሮ  የታየው፡፡ ጋዜጣውን የሰፊው ህዝብ ድምጽ አደረገው፡፡ ህገወጥ የቁማር ተግባራትን፣ የፖለቲካ ሙስናንና ዳጎስ ያሉ የግብር ስወራዎችን መመርመርና  ሃቁን አደባባይ ላይ ማስጣት ያዘ፡፡ ሰዎች ይህን አዲስ የምርመራ ጋዜጠኝነት ስታይል ወደዱለት፤የጋዜጣው ሥርጭትም በእጅጉ አሻቀበ፡፡
ጆሴፍ ፑልቲዘር ከታመመም በኋላ እንኳን ተግቶ መሥራቱን አላቋረጠም፤ እናም የዓይኑን ብርሃን ሊያጣም ደርሶ ነበር፡፡ ፑልቲዘር፤ጋዜጦች የማህበረሰቡን ዓላማ ማገዛቸው እንዲሁም ህዝቡን ከሸፍጥና ሙስና መታደጋቸው አስፈላጊ ነው ብሎ ያምን ነበር፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ ሌላ ጋዜጣ መግዛት ቻለ፡፡ የኒውዮርክን ጋዜጣ፡፡ የህዝበኝነት አቀራረቡንም ለብዙ ተደራሲያን ተገበረ፡፡



እ.ኤ.አ በ1909 ዓ.ም የኒውዮርክ ጋዜጣው፣ በአሜሪካ ታሪክ ታላቁ የፖለቲካ ቅሌት የተባለውን ታሪክ ሰበር ዜና አድርጎ አወጣው - የፓናማ ካናል ስምምነት፣ 40 ሚሊዮን ዶላር ህገወጥ ክፍያን  አጋለጠ፡፡ ይሄን ጊዜ የአሜሪካ መንግሥት ፍ/ቤት ሊያቆመው ሞክሮ ነበር፤ ነገር ግን ፑልቲዘር ”ፍንክች የአባ ቢላዋ ልጅ” አለ፡፡ በጽናት በመቆም፣ ለፕሬስ ነጻነት ትልቅ  ድል አስመዘገበ፡፡


ጆሴፍ ፑልቲዘር፤በዓለም የመጀመሪያው  የጋዜጠኝነት ት/ቤት፣ በኒውዮርክ፣ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ እንዲቋቋም ከሃብቱ ከፊሉን መድቧል፡፡ ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ ለጋዜጠኞችና ጸሃፍት ዓ መታዊ የሽልማት መርሃግብር የሚሆን ገንዘብም ለግሷል፤ ዛሬ ከዝነኞቹ የፑልቲዘር ሽልማቶች አንዱን ማሸነፍ፣ በጸሃፍት ዘንድ እንደ ልዕለ ኮከብ የሚያስቆጥር መሆኑ ይታወቃል፡፡   

ጆሴፍ ፑልቲዘር፤ ምንም እንኳ ወደ  ጋዜጠኝነት  የገባው በአጋጣሚ ቢሆንም ቅሉ፣ ጋዜጦች ዛሬም ድረስ ሊያሳኩት የሚተጉበትን ስታንዳርድ አስቀምጦ ነው ያለፈው፡፡

 ************************

ምን

 https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=31574:%E1%8B%A8%E1%8D%95%E1%88%AC%E1%88%B5-%E1%8A%90%E1%8C%BB%E1%8A%90%E1%89%B5-%E1%8C%A0%E1%89%A0%E1%89%83-%E1%8C%86%E1%88%B4%E1%8D%8D-%E1%8D%91%E1%88%8D%E1%89%B2%E1%8B%98%E1%88%AD&Itemid=209

Thursday, August 24, 2023

የኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን ተሳትፎ

 


የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እ.ኤ.አ. በ1983 በፊንላንድ ሔልሲንኪ ከተማ የተጀመረው በቀድሞ አጠራሩ የዓለም አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር አማካይነት ነው።

ከመጀመሪያው ውድድር በኋላ ሻምፒዮናው እስከ 1991 ድረስ፣ በየአራት ዓመቱ ይደረግ ነበር። ከዚያ በኋላ ግን ውድድሩ በሁለት ዓመት እንዲከናወን ተወሰነ።

በመጀመርያ ሻምፒዮና ከ153 አገሮች የተውጣጡ 1,333 አትሌቶች ተሳትፎ ማድረግ ችለዋል።

እ.ኤ.አ. በ1987 የሴቶች 10,000 ሜትር እና 10 ኪሎ ሜትር ዕርምጃ ተጨምሯል። በ1995 የሴቶች 3000 ሜትር በ5000 ሜትር ሲተካ። በ2005 የሴቶች 3000 ሜትር መሰናከል ተጨምሯል። ዓምና በአሜሪካ ኦሪገን በተከናወነው (2022) የዓለም ሻምፒዮና የ50 ኪሎ ሜትር የወንዶችና የሴቶች፣ የ35 ኪሎ ሜትር ዕርምጃ ተካቷል።

 


ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ

የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ብሔራዊ ቡድን በመጀመርያው ሻምፒዮና 10 አትሌቶች በአምስት የውድድር ዓይነቶች ተሳትፏል። ኢትዮጵያ በወዳጆ ቡልቲ፣ ሥዩም ንጋቱ፣ መሐመድ ከድር፣ በቀለ ደበሌ፣ ግርማ ብርሃኑ፣ እሼቱ ቱራ፣ ግርማ ወልደሃና፣ ከበደ ባልቻና ደረጀ ነዲ ነበር የተወከለችው። አትሌቶቹ በ3000 ሜትር መሰናከል፣ 5000 ሜትር፣ 10 ሺሕ ሜትር፣ ማራቶንና 20 ኪሎ ሜትር የዕርምጃ ውድድሮች ተሳትፈዋል። ከእነዚህ አትሌቶች መካከል ከበደ ባልቻ በወንዶች ማራቶን ለኢትዮጵያ የመጀመርያውን የብር ሜዳልያ አስገኝቷል፡፡

በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ 15ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኢትዮጵያ የዓለም ሻምፒዮና ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በ18ቱም ሻምፒዮናዎች መካፈል ችላለች። እ.ኤ.አ. በ1993 በስቱትጋርት በተደረገው ውድድር ኃይሌ ገብረ ሥላሴ በ10 ሺሕና በ5 ሺሕ ሜትር ወርቅና ብር አግኝቷል፡፡

የኢትዮጵያ ስኬታማ ውጤት

እ.ኤ.አ. በ2009 በጀርመን በርሊን በተከናወነው የዓለም ሻምፒዮና በተለያዩ ርቀቶች የሚሳተፉ 38 አትሌቶችን ይዛ ቀርባለች። ቡድኑ በመካከለኛ ርቀት ጭምር የሚሳተፉ አትሌቶችን ያቀፈ ነበር። በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በተለያዩ ርቀቶች የሚወዳደሩ ተጨማሪ አትሌቶች ይዛ እንድትገባ የተፈቀደላት ሲሆን፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽንም በእነዚህ ውድድሮች ተጠባባቂ አትሌቶችን መርጦ ይዞ ቀርቦ ነበር።

በሻምፒዮናው በወንዶች 5000 ሜትርና 10 ሺሕ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ ሁለት ወርቅ በማምጣት አዲስ ታሪክ ያጻፈበት ክስተት ነበር። ቀነኒሳ በ10 ሺሕ ሜትር 26:46.31 በማጠናቀቅ የቦታውን ክብረ ወሰን ጭምር ማሻሻል ችሏል። በ1500 ሜትር ወንዶች ደረሰ መኮንን የብር ሜዳልያን ሲያሳካ፣ ፀጋዬ ከበደ በማራቶን ሁለተኛውን የብር ሜዳልያ ያስገኝ አትሌት ሆኗል።

በሴቶች መሠረት ደፋር በ5000 ሜትር የነሐስ ሜዳልያ፣ መሰለች መልካሙ በ10 ሺሕ ሜትር ብር፣ ውዴ አያሌው ነሐስ፣ እንዲሁም አሠለፈች መርጋ በማራቶን የነሐስ ሜዳልያ አስገኝተዋል። በዚህም መሠረት ኢትዮጵያ በአጠቃላይ ስምንት ሜዳልያ በመሰብሰብ ከዓለም ስድስተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቅ የቻለችበት ሻምፒዮና ነበር።

ከሁለት ዓመት በኋላ በ2011 በደቡብ ኮሪያ ዴጉ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተካፈለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን 34 አትሌቶችን ይዞ መሳተፍ ችሎ ነበር። ሆኖም በ10 ሺሕ ሜትር ወንዶች በኢብራሂም ጄላን ወርቅ ሲገኝ፣ ደጀን ገብረ መስቀል በ5000 ሜትር፣ ኢማና መርጋ 10 ሺሕ፣ ፈይሳ ሌሊሳ በማራቶን እንዲሁም በ5000 ሜትር ሴቶች በመሠረት ደፋር አራት የነሐስ ሜዳልያ በአጠቃላይ አምስት ሜዳልያዎች ማጠናቀቅ ትችሏል። ይህም ውጤት ኢትዮጵያ በበርሊን ዓለም ሻምፒዮን ከነበረው ውጤት ዝቅተኛው ነበር።

በ2013 በሩሲያ በተሰናዳው የሞስኮ የዓለም ሻምፒዮን ኢትዮጵያ የተሻለ ውጤት ያመጣችበት ነበር። በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በመሠረት ደፋር በ5000 ሜትር ወርቅ፣ በጥሩነሽ ዲባባ 10 ሺሕ ሜትር ወርቅ፣ እንዲሁም በ800 ወንዶች በመሐመድ አማን ወርቅ ማምጣት ተችሎ ነበር። በተለይ ባልተለመደ መልኩ በ800 ሜትር ርቀት በመሐመድ ወርቅ መምጣቱ ሻምፒዮናው ለኢትዮጵያውያን ልዩ አድርጎታል። በሌሎች ርቀቶች ሦስት የብርና ሦስት የነሐስ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ከዓለም ስድስተኛ ደረጃን በመያዝ ማጠናቀቅ ትችሏል።

ሌላው ኢትዮጵያ የደመቀችበት የ2015 ዓለም ሻምፒዮና ይጠቀሳል። የአትሌቲክስ ቡድኑ በሻምፒዮናዎች በረዥም ርቀቶች ብቻ ውጤት ከማምጣት በዘለለ፣ በመካከለኛ ርቀትም የተሻለ ውጤት ማምጣት የቻለበት አጋጣሚም እየተፈጠረ የሄደበት ሁኔታ ነበር። በዚህም መሠረት በቤጂንግ ዓለም ሻምፒዮን ገንዘቤ ዲባባ በ1500 ሜትር ወርቅ ማምጣት ችላ ነበር። ይህም ኢትዮጵያ በመካከለኛ ርቀት በዓለም ሻምፒዮና ተስፋ የሰነቀችበት ነበር።

ኢትዮጵያ በቤጂንጉ የዓለም ሻምፒዮን አልማዝ አያና በ5000 ሜትር ወርቅ፣ ማሬ ዲባባ በማራቶን ወርቅ ሲያሳኩ፣ በሦስት የብርና በሁለት የነሐስ ሜዳልያዎችን  በመሰብሰብ ከዓለም አምስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች።

በ2017 የለንደን ዓለም ሻምፒዮን ሁለት ወርቅና ሦስት የብር ሜዳልያ፣ በ2019 በኳታር ሁለት ወርቅ፣ አምስት ብርና አንድ የነሐስ ሜዳልያ ማምጣት ተችሏል። በኳታር ዓለም ሻምፒዮን ለሜቻ ግርማ በ3000 መሰናክል የብር ሜዳልያ ማሳካት፣ ሌላው ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ተስፋ የተሰነቀበት ድል ያደርገዋል።

ዓለም በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት ዝግ ሆና መቆየቷን ተከትሎ በተለይ አትሌቶች አስቸጋሪ ጊዜ ያሳለፉበት ወቅት ነበር። ይህም ለሁለት ዓመታት ማንኛውም ውድድሮች ሳይከናወኑ መቆየታቸው ይታወሳል። በአንፃሩ ወረርሽኙ አገግሞ የ2022 የኦሪገን ዓለም ሻምፒዮን ለአትሌቶች ተስፋ ያጫረ ሆነ። በልምምድ የዛለው የአብዛኛው አትሌት ጉልበት መፈተሻ መድረክ አገኘ።

የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድንም ስኬታማውን የዓለም ሻምፒዮን ያስባለውን ውጤት አስመዘገበ። ኢትዮጵያ 21 ወንድና 19 ሴት አትሌቶችን በተለያዩ ርቀቶች ማሳተፍ ቻለች። ይህም ቁጥር ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና ካሳተፈቻቸው አትሌቶች ቁጥር ላቅ ያለ ነበር። የቁጥር መጨመር ምክንያትም በየሻምፒዮናው የሚመዘገቡ ውጤቶች አማካይነት ነው። በኦሪገን ዓለም ሻምፒዮን በማራቶን በሁለቱም ፆታ (በታምራት ቶላና ጎተይቶም ገብረ ሥላሴ)  እንዲሁም በ10 ሺሕ ሜትር ሴት ለተሰንበት ግደይና በ5000 ሜትር ሴቶች ጉዳፍ ፀጋይ አራት ወርቅ ማሳካት ተችሏል።

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በማራቶን በሁለቱም ፆታ የቦታውን ክብረ ወሰን ማሻሻል የቻሉበት ሲሆን፣ በ10 ሺሕ ሜትር ለተሰንበት የዓመቱን ምርጥ ሰዓት ማስመዝገብ መቻላቸው ልዩ ያደርገዋል። ኢትዮጵያ በኦሪገኑ ዓለም ሻምፒዮን ከአራቱ ወርቅ በተጨማሪ አራት የብር፣ ሁለት የነሐስ ሜዳልያ በድምሩ 10 ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቅ የቻለችበት ስኬታማው የዓለም ሻምፒዮን ያደርገዋል።

በተለይ ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመት በዘለቀው የሰሜኑ ጦርነት ውስጥ ሆና የተመዘገበ ውጤት መሆኑ የተለየ ቦታ እንዲሰጠው አስችሎታል።

ከኦሊምፒክ ጨዋታና ከእግር ኳሱ የዓለም ዋንጭ ቀጥሎ፣ ምርጡ ውድድር እንደሆነ የሚገለጽለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን፣ ዘንድሮ በቡዳፔስት ። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን ዓምና በአራት ወርቅ የተመለሰው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድኑ ዘንድሮስ ምን ሊያሳካ ይችላል? የሚለው በአብዛኛው ዘንድ በጉጉት የሚጠበቅ ጉዳይ ነው።

https://www.proworksmedia.com/121159/ ዳዊት ቶሎሳ


Wednesday, August 23, 2023

‹‹የሩጫዎች ሙሽሪት›› አትሌት መሰለች መልካሙ ኃይለእየሱስ

 

Written by  ግሩም ሠይፉ(አዲስ አድማስ)

ሰሞኑን ለየት ያለ መልዕክት ደረሰኝ፡፡ በፅሁፍ የተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ ወይንም በመግለጫ ላይ እንድገኝ የሚጋብዝ ጥሪ አልነበረም፡፡ የሙያ ባልደረባዬ በመጀመርያ መልዕክቱን ያደረሰኝ በስልክ ነው፡፡ አትሌት መሰለች መልካሙ ሰርግ ጠርታሃለች በማለት ጥሪው እንዳስደሰተኝ በመግለፅ እዚያው እንገናኝ ብለን ተለያየን፡፡
አዎ የሠርግ ካርዱ ደርሶኛል፡፡ 

“ይድረስ ለወዳጃችን ይላል… እንደምን ሰንብተዋል፡፡ እኛም ባለንበት በእግዚአብሄር ቸርነት በጣም ደህና ነን፡፡ ይኸው እንደ ወግ ልማዳችን ልጃችን አትሌት መሰለች መልካሙ እና አቶ አብርሃም በቀለ የፍቅር አጋር ሊሆኑ ተጫጭተዋል፡፡ እኛም ይሁን ብለን የሰርጉን ቀን ቆርጠናል፡፡…. ሚያዚያ 7 በምናደርገው የእራት ግብዣ ላይ ብቅ ብለው ያዘጋጀነውን ድግስ አብረን ተቋድሰን እንመርቃቸው፡፡ ወዲያውም ስንጫወት እናመሻለን፡፡ ታዲያ እንዳይቀሩ የቀሩ እንደሆነ ግን ማርያምን እንቀየምዎታለን……
አክባሪዎ ወይዘሮ የአለምወርቅ አዘነ
እና አቶ ይታያል መልካሙ
 


በዚህ አጋጣሚ አትሌት መሰለች መልካሙንና ቤተሰቧን በጣም አመሰግናለሁ፡፡ በስፖርት ጋዜጠኝነት እኔም የናንተ ቤተሰብ አክባሪ ነኝ፡፡ በዚህ የስፖርት አድማስ አምድ የታሪክ ማስተወሻ ላይ ስለ አትሌት መሰለች መልካሙ የሩጫ ዘመን ለመፃፍ አጋጣሚውን ስፈልግ ነበር፡፡ በነገው እለት ከአቶ አብርሃም በቀለ ጋር በሠርግ መሞሸሯን ምክንያት በማድረግ የሩጫ ገድሏ እንዲህ አቅርቤላችኋለሁ፡፡

 ሙሉ ስሟ መሰለች መልካሙ ኃይለእየሱስ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ 360 ኪሎሜትሮች ርቃ በምትገኘው ደብረማርቆስ ተወልዳለች። በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ታሪክ ከ18 ዓመታት በላይ በመስራት ከፍተኛ እውቅና እና ክብር አግኝታለች፡፡ ምንም እንኳን የሩጫ ዘመኗን በአገር አቋራጭ ውድድር ብትጀምርም በትራክ ላይ በ5ሺ ሜትር እና 10ሺ ሜትር ውድድሮች ላይ በመሮጥም ከ8 የውድድር ዘመናት በላይ ልምድ አላት፡፡ በቤት ውስጥ አትሌቲክስ፤ በጎዳና ላይ ሩጫ፤ በተራራ ላይ ሩጫዎች በግማሽ ማራቶንና ማራቶኖችም ተወዳዳሪ በመሆን ተሳክቶላታል፡፡
ከ10 ዓመት በፊት በአዲስ አበባ ስታድዬም በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ከታዩ አስደናቂ ውድድሮች የማይረሳው የሴቶች አምስት ሺ ሜትር ውድድር ነበር። በ5ሺ ሜትር የምንግዜም ምርጥ ሯጭ የሆነችውን መሰረት ደፋር በማሸነፍ የአፍሪካ ሻምፒዮን ሆና የወርቅ ሜዳልያውን አትሌት መሰለች ስትጎናፀፍ ሙሉ ስታድዬም ቆሞ ነበር ያጨበጨበላት። በሴቶች 10ሺ ሜትር ደግሞ በ2009 እኤአ ላይ  ያስመዘገበችው 29:53.80 የሆነ ጊዜ ከቻይናዋ የዓለም ሪከርድ ባለቤት ዋንግ ዡንክስያ ቀጥሎ ለ7 ተከታታይ የውድድር ዘመናት በ2ኛ ደረጃ ለመቀመጥ የበቃ የምንግዜም ፈጣን ሰዓት ነበር፡፡ በሪዮ ኦሎምፒክ ይህን ደረጃዋን በኦሎምፒክ ሻምፒዮናዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት አልማዝ አያና 29:53.80 በሆነ ጊዜ የተረከበችውና የኢትዮጰያ ሪከርድ ሆኖ የሚገኝ ነው፡፡ በሴቶች የ10ሺ ሜትር ሩጫ ታሪክ ከ30 ደቂቃ በታች ከገቡ 10 አትሌቶች አንዷ ስትሆን ይህን የሰዓት ገደብ ካስመዘገቡ አምስት የኢትዮጵያ ሴት ሯጮችም አንዷ ናት፡፡ 

ሩጫን ከ18 ዓመታት በፊት የጀመረችው የአባቷን ተቃውሞ በመቋቋም ሲሆን በደብረማርቆስ ከሚገኙ ወጣቶች ጋር ልምምድ በመስራት ነበር፡፡ በደብረማርቆስ ከተማ በተካሄዱ የተለያዩ ውድድሮች በተለይ በአገር አቋራጭ ሩጫዎች ስኬታማ ከሆነች በኋላ ክልሏን በመወከል በኢትዮጵያ የአገር አቋራጭ ሻምፒዮና የምትሳተፍበት እድል ተፈጠረላት፡፡ በወጣቶች ውድድር ጃንሜዳ ላይ ተሳትፎ አድርጋ በ11ኛ ደረጃ ነበር የጨረሰችው፡፡ ከዚህ ውድድር በኋላ ክልሏን በመወከል በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለመሳተፍ በቃች በትራክ የ1500 ሜትር ውድድር ተሳታፎ በመሆን ባሳየችው ልዩ ብቃት በመብራት ሃይል የአትሌቲክስ ክለብ የምትቀጠርበት አጋጣሚ ተፈጠረ፡፡ በዚህ መሰረት ከምትኖርበት የደብረማርቆስ ከተማ የ10ኛ ክፍል ትምህርቷን በማቋረጥ ወደ አዲስ አበባ መጥታ በመብራት ኃይል ክለብ አትሌትነት ሙሉ ለሙሉ ወደሩጫ ስፖርት ገብታለች፡፡ አባቷም ሩጫን ሙያዋ አድርጋ እንደምትዘልቅ በመረዳታቸው ድጋፋቸውን በዚህ ወቅት መስጠት ጀምረዋል፡፡ በማንኛውም ውድድር ለሁሉም ተፎካካሪ ግምት ሰጥታ ለማሸነፍ እንድትወዳደር ነበር የአባቷ ምክር፡፡  በመጀመርያው ዓመት በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ በሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የመካተት ህልም የነበራት ቢሆንም አልተሳካላትም፡፡ ከ2003 እኤአ ጀምሮ ወደ ዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ በወጣቶች ደረጃ መሳተፍ ጀምራለች የመጀመርያ ውድድሯ የነበረው በሉዛን የተደረገው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሲሆን፤ ጥሩነሽ ዲባባ ባሸነፈችበት የወጣቶችውድድር 4ኛ ደረጃ አግኝታ ነበር፡፡ ከዚያም በ2004 እኤአ ላይ በኢትዮጵያ የአገር አቋራጭ ሻምፒዮና በወጣቶችውድድር አሸንፋ በአዋቂዎች የ4ኪሜትር ውድድር ደግሞ 4ኛ ደረጃ በማስመዝገብ ለዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመመረጥ እድሏን አሰፋች፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ መጥቃ የወጣችበት የውድድር ዘመን በ2004 እኤአ ሲሆን በወጣቶች ምድብ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናንና የዓለም ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮናን ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች በድርብ ድል የተቀዳጀችበት ነበር፡፡ በቀጣዩ የውድድር ዘመን በዋናው የአዋቂ ሴቶች አጭር ርቀት 4 ኪሎሜትር ውድድር አራተኛ እንዲሁም በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ደግሞ በ5ሺ ሜትር 4ኛ ደረጃ ነበራት፡፡ይህ ልምዷን በማጠናከር በ2004 እና በ2005 እኤአ የውድድር ዘመናት በአገር አቋራጭ ውድድሮች ብቻ ሳይሆን፤ በትራክ እና የጎዳና ላይ ሩጫዎች ከ1500 ሜትር እስከ 10 ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ከ16 በላይ ውድድሮች አድርጋለች፡፡
ከወጣቶች ምድብ ወደ አዋቂ ደረጃ ከተሸጋገረች በኋላ ከፍተኛ የሜዳልያ ውጤት ለማስመዝገብ የበቃችው በ2006 እኤአ ላይ ነው፡፡ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በአጭር ርቀት 4 ኪሜትር እና በረጅም ርቀት 8 ኪሜትር ውድድሮች ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች እና በቡድን ደግሞ ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችን በመውሰድ ነበር። ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በግሬት አየርላንድ ራን የ10 ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ላይ በስፍራው ሪከርድ 31:41  በማሸነፍ ተሳክቶላታል፡፡
ከጎዳና ላይ ሩጫው በኋላ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ በመመለስ በ2007 እኤአ ላይ በድጋሚ የነሐስ ሜዳልያ ከመውሰዷም በላይ በቡድን ተጨማሪ የወርቅ ሜዳልያ አስገኝታለች፡፡ በተመሳሳይ የውድድር ዘመን ላይ ደግሞ ወደ ትራክ በመግባት በመላው አፍሪካ ጨዋታዎች ላይ አትሌት መሰረት ደፋርን ተከትላ በመግባት በ5ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ አግኝታለች። በዚያው የውድድር ዘመን ማብቂያ ላይ  በ5ሺ ሜትር በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ 6ኛ ደረጃ ነበራት፡፡
በ2007 እኤአ ላይ በአንድ የውድድር ዘመን ከጎዳና ላይ ሩጫ ተነስታ በአገር አቋራጭ ከዚያም በትራክ በመወዳደር የተለየ አቅም ነበር ያሳየችው፡፡ በ2008 እኤአ ደግሞ በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ3ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ አገኘች። የወርቅ ሜዳልያው የአትሌት መሰረት ደፋር ነበር፡፡ በዚያው የውድድር ዘመን ከፍተኛ ልምድ ባካበተችበት የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በዘጠነኛ ደረጃ ብትጨርስም ይህን የሚያካክስ ውጤት ደግሞ አሳክታለች፡፡ በ2008 እኤአ በአዲስ አበባ ስታድዬም በተስተናገደው 16ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ አትሌት መሰረት ደፋርን ቀድማ በመግባት የወርቅ ሜዳልያ በ5ሺ ሜትር የተጎናፀፈችበት ነበር፡፡ ይህ ውጤቷም በቻይናዋ ቤጂንግ ከተማ ለተካሄደው 29ኛው ኦሎምፒያድ ተሳትፎ አብቅቷታል፡፡ በ5ሺ ሜትር በሆነ ጊዜ በስምንተኛ ደረጃ ነበር የጨረሰችው፡፡ ከዓመታት በኋላ በዚሁ ኦሎምፒክ በ5ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ የወሰደችው የቱርኳ ኤልቫን አብይ ለገሰ በዶፒንግ ውጤቷ በመሻሩ፤ አትሌት መሰለች መልካሙ በተሳተፈችበት የመጀመርያ ኦሎምፒኳ በ5ሺ ሜትር የ7ኛ ደረጃ እንዲመዘገብላት ሆኗል፡፡


በ2009 እኤአ ላይ ወደ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ስትመለስ የሜዳልያ ውጤት ነበራት፡፡ በረጅም ርቀት የ8 ኪሎሜትር ውድድር የነሐስ ሜዳልያ ወሰደች፡፡  በጥቂት ወራት ውስጥ ደግሞ በሆላንዷ ኡትርቼት በተካሄደ የ10ሺ ሜትር ሩጫ አዲስ የአፍሪካና የኢትዮጵያ ሪከርድ 29:53.80 በሆነ ጊዜ አስመዘገበች፡፡ አስቀድሞ በጥሩነሽ ዲባባ የተያዘውን የአፍሪካና የኢትዮጵያ ሪከርድ 29:54.66 የሆነ ጊዜ በማሻሻል ነበር፡፡ ያን የውድድር ዘመን የመጀመርያውን የዓለም ሻምፒዮና ከፍተኛ ውጤት በ10ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ በመጎናፀፍ አጠናቀቀች፡፡
በ2010 እኤአ ላይ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በመሳተፍ  የለመደችውን የነሓስ ሜዳልያ በረጅም ርቀት ለመውሰድ የበቃች ሲሆን፡፡ በዚያው የውድድር ዘመን በኬንያ ናይሮቢ በተካሄደ የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ደግሞ በ10ሺ ሜትር አትሌት ጥሩነሽ ዲባባን ተከትላ በመግባት የብር ሜዳልያ ተጎናፅፋለች፡፡ የውድድር ዘመኑን ያገባደደችው በናይጄርያ ኦቡዱ ግዛት በተካሄደ የአፍሪካ ረየተራራ ላይ ሩጫ ጫምፒዮንሺፕ Obudu Ranch International Mountain Race አስደናቂ ድል በማስመዝገብ ነበር፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ትልቁ ውጤታ በጃንሜዳ አገር አቋራጭ ለ4ኛ ጊዜ ማሸነፏ ነበር፡፡
ከ2012 እኤአ ወዲህ ያለፉትን አምስት የውድድር ዘመናት ደግሞ ዋና ትኩረቷ የጎዳና ላይ ሩጫዎች ግማሽ ማራቶንና ማራቶኖች ሆነዋል፡፡ በ2012 እኤአ በጀርመን ፍራንክፈርት ማራቶኑን ስታሸንፍ 2:21:01 በሆነ ጊዜ የግሏን ፈጣን ሰዓት እና የስፍራውን ሪከርድ አስመዝግባለች፡፡ ይህ የመሰለች መልካሙ የማራቶን ሰዓት ከኢትዮጵያ ሴት ማራቶኒስቶች ፈጣን ሰዓቶች አንዱ ነው፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ የራስ አልካሂማህ ግማሽ ማራቶን ስትወዳደር በ7ኛ ደረጃ ብትጨርስም በርቀቱ የግሏን ፈጣን ሰዓት 1:08:05  አስመዝግባለች፡፡
ባለፉት 4 የውድድር ዘመናት  በተሳተፈችባቸው የማራቶን ውድድሮች የተሳካላት ናት፡፡ በ2013 እ.ኤ.አ ላይ ሞስኮ ባስተናገደችው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በማራቶን ብትሳተፍም ውድድሩን ለመጨረስ አልቻለችም፡፡ የመጀመሪያ ማራቶን የሮጠችው በ2012 እኤአ በፍራንክፈርት ማራቶን ሲሆን፣ ውድድሩን ስታሸንፍ 2:21:01 በሆነ ጊዜ ሲሆን  ብርቀቱ የተመዘገበላት ምርጥ ሰዓቷ ነው፡፡ በዱባይ ማራቶን  ሁለት ጊዜ ስትሳተፍ በ2016 እኤአ ላይ በ2፡22፡29 በሆነ ጊዜ ሦስተኛ ደረጃ ማግኘቷ ይታወሳል፡፡  በ2017 እኤአ ደግሞ አልተሳካለትም ከዱባይ ማራቶን ባሻገር በጀርመንና በሆላንድ ከተሞች ሁለት ትልልቅ ማራቶኖችን አሸንፋለች፡፡ በተለይ  በጀርመን ሀምቡርግ ካስመዘገበችው ድል ቀጥሎ ሁለተኛውን የትልቅ ከተማ ማራቶን አሸናፊነት ክብር በአምስተርዳም ለመቀዳጀት መብቃቷ ይጠቀሳል፡፡
በኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ማህበረሰብ፤ በዓመለሸጋነቷ፤ በልምምድ ትጋቷ እና በውድድር ላይ ለቡድን ውጤት በምታበረክተው አስተዋፅኦ የምትከበረው አትሌት መሰለች መልካሙ በአገር አቀፍ እንቅስቃሴዎችም ንቁ ተሳታፊ ናት፡፡ ከ4 ዓመታት በፊት ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ገቢ ማሰባሰቢያ የሚውል 20 ኤል.ሲ.ዲ ቴሌቪዥን በስጦታ ያበረከተች ሲሆን ባለ 32 ኢንች ኤል.ሲ.ዲ ሳምሰንግ ቴሌቪዥኖች  ከ153 ሺህ ብር በላይ ወጪ ተደርጎባቸዋል፡፡ በ2017 ላይ ግን አንድ አሳዛኝ ገጠመኝ ነበር፡፡ አትሌት መሰለች መልካሙን ጨምሮ አምስት አትሌቶች ከ3 ሚሊየን ብር በላይ ደረቅ ቼክ በመጻፍ ማናጀር አታሏቸው መነጋገርያ ሆነው ነበር፡፡ በማታለል ወንጀል የተከሰሰው የአትሌቶች ማናጀር ወላይ አማረ የሚባል ሲሆን በወቅቱ የጠቅላይ አቃቤ ህግ ክስ እንዳመለከተው ተከሳሽ ወንጀሉን በአትሌቶቹ ላይ የፈፀመው ከ2008 እስከ 2009 ዓ.ም ባለው ጊዜ ነው።
ማናጀሩ  ከአምስቱ አትሌቶች በተለያዩ ጊዜና ሀገራት ባደረጉት ውድድር የተሳትፎ የኮንትራት ውል ክፍያን ገንዘብ ሳይኖረው በአዋሽና በሌሎች ባንኮች ሂሳቡ ውስጥ ገንዘብ እንደሌለው እያወቀ ደረቅ ቼክ በመጻፍ ማታለሉ በክሱ ተጠቅሷል። በዚህም መልኩ ለአትሌት አፀደ ፀጋዬ ከ1 ሚሊየን 15 ሸህ ብር በላይ፣ ለአትሌት መሰለች መልካሙ ከ2 ሚሊየን 368 ሺህ ብር በላይ እንዲሁም ለአትሌት በላቸው አለማየሁ 230 ሺህ ብር እና ለሌሎችም አትሌቶች ተመሳሳይ የገንዘብ መጠን ደረቅ ቼክ በመጻፍ የማታለል ተግባር መፈጸሙ በክሱ ተዘርዝሯል፡፡
 የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ አንደኛ ወንጀል ችሎት ተከሳሽ ወላይ አማረ በ10 ዓመት ከ11 ወራት ፅኑ እስራትና በ2 ሺህ 500 ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ ወስኗል።
በአሁኑ ወቅት አትሌት መሰለች መልካሙ ለኢትዮጵያ አትሌቶች ዋና ተምሳሌት ሆና የምትጠቀስ ናት፡፡  የሩጫ መደቦቿ 1500ሜ፤ 3000ሜ፤ 5000ሜ ፤ 10,000ሜ፤ የቤት ውስጥ አትሌቲክስ፤ አገር አቋራጭ፤ የጎዳና ላይ ሩጫዎች፤ ግማሽ ማራቶንና ማራቶን ናቸው፡፡


በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ለረጅም ጊዜ ያገለገለችበት ክለብ  መብራት ኃይል ሲሆን በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ከአሰልጣኝ ዶክተር መስቀል ኮስትሬ እንዲሁም ከዶክተር ይልማ በርታ ጋ ሰርታለች። ለረጅም ጊዜ ማናጀሯ ሆነው ያገለገሏት የግሎባል አትሌቲክስ ኮሚኒኬሽኑ ሆላንዳዊው  ጆስ ሄርማንስ ናቸው፡፡
በዓለም የጎዳና ላይ ሩጫዎች የስታስቲክስ ድረገፅ ኤአርአርኤስ (Arrs) የመረጃ መዝገብ መሰረት አትሌት መሰለች መልካሙ በሩጫ ዘመኗ 41 ውድድሮችን ያሸነፈች ሲሆን በይፋ የሚታወቅ የገንዘብ ሽልማቷ ከ701ሺ 150 ዶላር በላይ ነው፡፡
ፈጣን ሰዓቶቿ
- በ1500 ሜትር – 4:07.52 (2007)
- በማይል ሩጫ– 4:33.94 (2003)
- 2000 ሜትር ቤት ውስጥ - 5:39.2 (2007) 12ኛው የምንግዜም ፈጣን ሰዓት
• በ3000 ሜትር ትራክ- 8:34.73 (2005)
• 3000 ሜትር ቤት ውስጥ - 8:23.74 (2007) 4ኛው የምንግዜም ፈጣን ሰዓት
• 5000 ሜትር ትራክ– 14:31.91 (2010)
• 10,000 ሜትር ትራክ – 29:53.80 (2009) 6ኛው የምንግዜም ፈጣን ሰዓት
• 10 ኪ ሜትር ጎዳና – 31:17 (2013)
• 15 ኪ ሜትር ጎዳና  - 47:54 (2013)
• 20 ኪ ሜትር ጎዳና  - 1:04:32 (2013)
• ግማሽ ማራቶን - 1:08:05 (2013)
• 30 ኪ ሜትር ጎዳና - 1:39.21 (2014)
• ማራቶን – 2:21:01 (2012)
ዋና ዋና ውጤቶቿ
በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና፤ በወጣቶች, በ2003 4ኛ እንዲሁም በ2004 1ኛ፤
በ2004   በዓለም ወጣቶች ሻምፒዮና, 5000ሜ የወርቅ ሜዳልያ
ከ2005 እኤአ ጀምሮ  በ6 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች በመሳተፍ፤  በአጭር 4ኪ.ሜ 6ኛ እንዲሁም በረጅም ርቀት 3 የነሃስ ሜዳልያዎች፤ ሁለት 4ኛ ደረጃዎች እና 9ኛ ደረጃ አስመዝግባለች፡፡
ከ2006 እስከ 2010 እኤአ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5000ሜ 1 የወርቅ ሜዳልያ እና 6ኛ ደረጃ እንዲሁም በ10ሺ 1 የብርና 1 የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝታለች፡፡
በ2007 መላው አፍሪካ ጨዋታዎች በ5000m የብር ሜዳልያ እንዲሁም በ2008 በዓለም አትሌቲክስ ፍፃሜ 5000m የነሐስ እና በየዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና 3000ሜ የብር ሜዳልያ
ከ2005  ጀምሮ እስከ 2011   በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና 5000ሜ 4ኛ፤6ኛ እና 5ኛ ደረጃ በ10ሺ ሜትር ደግሞ የብር ሜዳልያ እና 5ኛ ደረጃ



https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=21677:%E2%80%B9%E2%80%B9%E1%8B%A8%E1%88%A9%E1%8C%AB%E1%8B%8E%E1%89%BD-%E1%88%99%E1%88%BD%E1%88%AA%E1%89%B5%E2%80%BA%E2%80%BA-%E1%8A%A0%E1%89%B5%E1%88%8C%E1%89%B5-%E1%88%98%E1%88%B0%E1%88%88%E1%89%BD-%E1%88%98%E1%88%8D%E1%8A%AB%E1%88%99&Itemid=276

የአትሌት መሰለች መልካሙ የሰርግ ቪዲዮ

https://www.youtube.com/watch?app=desktop&v=A9dkNo-Zzww

 

 

Tuesday, August 8, 2023

የኢትዮጵያና የሩሲያ ወዳጅነት


የኢትዮጵያና የሩሲያ ወዳጅነት 

ከአፄ ምንሊክ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ

በተረፈ ወርቁ (ዲ/ን)


ንደ መንደርደሪያ

የሩሲያንና የኢትዮጵያ ወዳጅነትና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ታሪካዊ ጅማሬው ምን ይመስል ነበር የሚለውን ከታሪክ መዛግብት በጥቂቱ ለመፈተሽ ልሞክር እስቲ፡፡ 

ሩሲያ ከኢትዮጵያ ጋር የጋራ ግንኙነት ለመመሥረት ፍላጎት ማሳየት የጀመረችው በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መባቻ አካባቢ ነው፡፡ የታሪክ መዛግብትና ሰነዶች እንደሚያሳዩት ከዚያ ቀደም ብሎ የሁለቱ አገሮች (የኢትዮጵያና የሩሲያ) ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ምዕመናን ኢየሩሳሌም ለመንፈሳዊ ጉዞ በሚሄዱበት ጊዜ ይገናኙ ስለነበር፣ አንዳቸው ስለአንዳቸው መረጃውና ዕውቀቱ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ነበራቸው፡፡

የታሪክ መዛግብት እንደሚጠቁሙት እ... 1673 ሎሬንቲየስ ሪንሁበር (Laurentius Rinhuber) የተባለ የዛር አሌክሲ አገልጋይ፣ ሩሲያ የኦቶማን ቱርክ ኃይልን ለመቋቋም ከኢትዮጵያ ጋር ትብብር እንደትፈጽምና የሩሲያ ልዑክ ወደ ኢትዮጵያ እንዲላክ ሐሳብ አቅርቦ ነበር፡፡ በወቅቱ ይህ ሐሳብ በሩሲያ መንግሥት ዘንድ ተቀባይነት አግኝቶ የነበረ ቢሆንም፣ በተለያዩ ምክንያቶች ሐሳቡን ዕውን ለማድረግ ሳይቻል ቀርቷል፡፡

ይሁን እንጂ ሩሲያውያን ስለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በይበልጥ ለማወቅ አልቦዘኑም ነበር፡፡ ሩሲያውያን በወቅቱ ስለኢትዮጵያ ጉዳይ ለማጥናት እንደ መረጃ ይጠቀሙባቸው ከነበሩት ጥንታዊ የታሪክ ሰነዶች መካከልም፣ በጀርመናዊው የቋንቋና የታሪክ ሊቅ በሂዮብ ሉዶልፍ (Hiob Ludolf) የተጻፈውን ‹‹Historia Aethiopica›› የተሰኘው መጽሐፍ ይጠቀሳል፡፡

19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ የኢትዮጵያና የሩሲያ ግንኙነት በዋነኝነት በኢትዮጵያ ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ የተለያዩ የሩሲያ ሰዎች ከኢትዮጵያ የተለያ የግዕዝ መዛግብትን ይዘው ወደ ሩሲያ ከመሄዳቸውም ባሻገር፣ ሩሲያውያኑ በአገራቸው የግዕዝን ቋንቋ እስከ ማስተማርም ደርሰዋል፡፡ እ... 1829 እስከ 1836 .. በሩሲያ (University of Kharaov) የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት ይሰጥ ነበር፡፡

የአፄ ምንሊክና የሩሲያ ወዳጅነት

1895 .. አፄ ምንሊክ በፊታውራሪ ዳምጠው የተመራውን የመጀመርያውን የዲፕሎማቲክ ልዑክ ወደ ሩሲያ ላኩ፡፡ ይህ ሲሆን ጣሊያን ኢትዮጵያን በሞግዚነት እንደምታስተዳድር የሚገልጸው የውጫሌ ውል በጣሊያን በኩል ይፋ ሆኖ ነበር፡፡ ምንም እንኳን በኢትዮጵያ በኩል የውጫሌ ውል ተቀባይነት እንደሌለው የተገለጸ ቢሆንም፡፡ ቢሆንም ጣሊያን ይህን በኢትዮጵያ በኩል ውድቅ የተደረገውን የውጫሌ ውል በመጥቀስ የኢትዮጵያውያን ልዑካን ኦፊሴላዊ ጉብኝት ላይ ጥያቄ አንስታ ነበር፡፡

ሩሲያ ግን አፄ ምንሊክ የላኩትን የኢትዮጵያ ልዑክ በሉዓላዊ አገር ልዑክነት ዕውቅና በመስጠት በተገቢው ወግና ማዕረግ በክብር ነበር የተቀበለችው፡፡ በውጭ ጉዳይም ሚኒስትሯ በኩልም ኢትዮጵያን እንደ ሉዓላዊ አገር ብቻ እንደምታውቃትና ግንኙነቷም በዚያ መንገድ መሆኑን ጠቅሳ ለጣሊያን ጥያቄ መልስ ሰጥታ ነበር፡፡

የልደታው ደጃዝማች ባልቻ ሆስፒታል - 1968 ዓ.ም

በፊታውራሪ ዳምጠው ከተመራው ልዑክ በኋላ የሩሲያ መንግሥት በጊዜው የጣሊያን ወረራ ሥጋት ለነበረባት ኢትዮጵያ የመሣሪያ ሽያጭ አድርጋ ነበር፡፡ ምንም እንኳን መሣሪያው በታቀደለት ጊዜ ለዓድዋ ጦርነት ባይደርስም፣ ከመሣሪያ ሽያጩ በተጨማሪ የሩሲያውያን የቀይ መስቀል ማኅበር አባላት የጦርነቱን ቁስለኞች ለመርዳት በጦርነቱ ማግሥት በኢትዮጵያ ተገኝተዋል፡፡

ይህ የሩሲያ የሕክምና ቡድን በዓድዋ ጦርነት ከቆሰሉት ወታደሮች በተጨማሪ፣ በጠቅላላው ከ30,000 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች በአዲስ አበባና በሐረር የሕክምና ዕርዳታ ማድረጉን የታሪክ መዛግብት ይጠቁማሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪም ሩሲያውያን ሐኪሞች ታማኝ የአፄ ምንሊክ የግል ሐኪሞች ሆነው እስከ መመረጥም ደርሰው ነበር፡፡     

ከሩሲያ/ከመስኮብ ወደ ኢትዮጵያ ስለመጡት ልዑካንና አፄ ምኒልክ ወደ ሩሲያ የላኩትን መልዕክተኞቻቸው በተመለከተ፣ የዳግማዊ አፄ ምንሊክ ጸሐፊ ትዕዛዝ የነበሩት አለቃ ገብረ ሥላሴ፣ ‹‹ታሪክ ዘዳግማዊ ምንሊክ›› በሚለው መጽሐፋቸው እንዲህ ተርከውታል፡፡

በዚያን ዘመን የመስኮብ መልዕክተኞች መጥተው ከባህር ጠረፍ ደረሱ የሚል ወሬ ተሰማ፡፡ አፄ ምንሊክም ለራስ መኮንን እነዚያን የመስኮብ መልዕክተኞች አክብረህ ተቀብለህ ስደዳቸው ብለው ላኩ፡፡ እነዚያም መልዕክተኞች አዋሽን ተሻግረው ምንጃር በደረሱ ጊዜ በያደሩበት መስተንግዶ እየተሰናዳላቸው፣ በመስተንግዶ ደስ እያላቸው በጉዟቸው የሚቀመጡበት ሁለት  የተሸለሙና ያጌጡ በቅሎዎች ሰደዱላቸው፡፡

መልዕክተኞቹም መጥተው በአዲስ አበባ ከተማዋ አጠገብ በደረሱ ጊዜ የሚቀበላቸው ሰው ታዞ ተሠልፎ ሂዶ በእንቢልታና በመለከት ተቀበሏቸው፡፡ በታላቅ ክብር በተድላና ደስታ ከጃንሆይ ተገናኙ፡፡ የሚያርፉበትን ቤት አምሮ ተዘጋጅቶ ቆይቶ ነበርና ከዚያ ሄደው ገቡ፡፡ ድርጓቸውም ታዞ ሄደላቸው፡፡ ይኼውም ድርጎ እስኪሄዱ ድረስ አልጎደለባቸውም፡፡


በዚህ ጊዜ የኢትዮጵያና የመስኮብ ፍቅር ተጀመረ፡፡ ነገር ግን የአፄ ምንሊክ ደግነት ሁሉን ያሸንፋል፡፡ በፍቅር ከሆነ የማንም አገር ሰው ቢመጣ ማክበር፣ መውደድና መስጠት ነው እንጂ መሰልቸት የለም፡፡

የመስኮብ መልዕክተኞችም የኢትዮጵያ ቆይታቸውን አጠናቀው ወደ አገራቸው የሚሄዱበት ቀን በደረሰ ጊዜ፣ አፄ ምንሊክ ወደ መስኮብ ንጉሠ ነገሥት የሚሄዱ መልዕክተኞችን አዘዙ፡፡ የታዘዙትም ሰዎች ስማቸው ይህ ነው፡፡ ፊታውራሪ ዳምጠው፣ ቀኝ አዝማች ገነሜ፣ መምህር ገብረ እግዚአብሔር ሌሎችም መኳንንት ተጨምረው እንዲሄዱ ተዘጋጁ፡፡

ለመስኮብ ንጉሠ ነገሥት ለኒቆላዎስ ቄሣር በረከት የሚሄድ ዕፁብ ድንቅ የሆነ ዘውድ፣ ማለፊያ የወርቅ መስቀል፣ አራቱ ወንገጌል መጻሕፍት፣ ሌላም የኢትዮጵያ ብዙ ገፀ በረከት ሰደዱ፡፡ በበኩላቸው ንግሥቲቱ እቴጌ ጣይቱም ለመስኮብ ንግሥት ለአሌክሳንድራ በረከት የሚሄድ ዕፁብ ድንቅ የተባለ በወርቅ አጫዋች ያጌጠ የሐር መሶብ፣ የሴት ወ/ሮ መሣሪያ ወርቅ፣ የእግር ክታብ ወርቅ፣ አልቦ ወርቅ፣ ጠልሰም ወርቅ፣ ድሪ ወርቅ፣ ወለባ ይህን ሁሉ አዘጋጅተው ሰደዱ፡፡

እነዚህም የአፄ ምንሊክ መልዕክተኞች ከመስኮብ መንግሥት በደረሱ ጊዜ በታላቅ ክብር ተቀበሏቸው፡፡ ዓይነተኛውን/የመልዕክተኞቹን መሪ ፊታውራሪ ዳምጠውን በወርቅ ባጌጠ ሠረገላ አስቀምጠው ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ቤት ወሰዷቸው፡፡ ከከተማው በገቡ በአምስተኛው ቀን ለንጉሠ ነገሥቱ ኒቆላዎስ ቄሳር፣ ለንግሥቲቱም ለአሌክሳንድራ የያዙትን ስጦታ/በረከት አቀረቡ የሚል ቃል ወደ አፄ ምንሊክ መጣ፡፡

እንደ መውጫና መደምደሚያ

ከሰሞኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (/) የሩሲያ ጉብኝትና ከአገሪቱ ወሳኝ ሰው ከሆኑት ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር ያደረጓቸው ስምምነቶችና ውይይቶች ትልቅ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆነው ቆይተዋል፡፡ ይህም ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ አንድም ሁለቱ አገሮች ረዥም ዘመን ያስቆጠረ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላቸው መሆናቸው ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ አገራችን የሺሕ ዘመናት ታሪክና ሥልጣኔ ባለቤት፣ የአፍሪካና የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ዓርማ የአፍሪካ መዲና የመሆኗ እውነታ በዓለም አቀፍ መድረክ ልዩ ሥፍራ ስለሚያሰጣት ነው፡፡


ከዚህ የታሪክ ሀቅ ጋር በተያያዘም የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (/) የሩሲያ ጉብኝት፣ በፖለቲካውና በዲፕሎማሲው ዓለም ትልቅ አንድምታ እንዲኖረው አድርጓል፡፡

በሌላም በኩል ደግሞ ምዕራባውያንና አሜሪካ፣ በተቃራኒው ደግሞ ሩሲያ በዲፕሎማሲው መስክና በኃይል አሠላላፍ ረገድ አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት የተያያዙትን የገመድ ጉተታ አገሮችን ከጎናቸው ማሳለፍ ዋነኛ ጉዳያቸው በመሆኑ ነው፡፡ በዚህ ረገድም የአፍሪካ መዲና፣ የአፍሪካውያንና የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ዓርማ፣ የዓላማችን ታላላቅ ሃይማኖቶች ቤት፣ በአፍሪካና በአፍሪካ ቀንድ ወሳኝ የሆነ ጂኦ ፖለቲካዊ አቀማመጥን የያዘች እንደ ኢትዮጵያ ያለ አገርን ኃያላኑ አገሮች ከጎናቸው እንድትሆን/እንድትቆም ማድረግ ትልቅ ዲፕሎማሲያዊ ድል ከመሆኑ እውነታ ጋርም የሚያያዝ መሆኑ ነው፡፡

ይህን የኢትዮጵያንና የሩሲያን ታሪካዊ ግንኙነት አጠናክሮ ለማስቀጠል፣ ባለፈው ዓመት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ በአፍሪካ የአፍሪካ ኅብረት መገኛና መዲና በሆነችው በሆነችው አዲስ አበባ ይፋዊ ጉብኝት አድርገው ነበር፡፡ ይህን የላቭሮቭን ጉብኝት ተከትሎ መቀመጫውን በሩሲያ ያደረገው አሜሪካዊ የፖለቲካ ተንታኝ አንድሩ ኮሪብኮ ባወጣው ጽሑፍ፣ ‹‹የሩሲያ-ኢትዮጵያ ወዳጅነት የባለብዙ አቅጣጫ አጋርነት ማሳያ ሞዴል መሆኑንና የላቭሮቭ ጉብኝት ሩሲያ ከመላው የአፍሪካ አገሮች ጋር ያላትን የጋራና ሁለገብ ግንኙነት አጠናክራ ለመቀጠል ያላትን ፍላጎት ያሳየ መሆኑንም፤›› አትቶ ጽፎ ነበር፡፡


አንድሩ፣ ‹‹አዲስ አበባ የአፍሪካ ኅብረት መቀመጫ ብቻ ሳትሆን የመላው አፍሪካውያን የፀረ ቅኝ ግዛት ተጋድሎ ትእምርት/ሲምቦልና የፓን አፍሪካኒዝም ታሪካዊ መገኛ በመሆኗ የአኅጉሩ መንፈሳዊ መዲና ናት፤›› ብለው በርካቶች እንደሚያምኑም በጽሑፉ አውስቷል፡፡

ሩሲያና ኢትዮጵያ ለቀሪው ዓለም በተለይም ለአፍሪካ አገሮች እንዴት ከቅኝ ግዛት ነፃ መውጣት እንደሚቻል በማሳየት ረገድ ግንባር ቀደም ሆነዋልም ነው ያለው የፖለቲካ ተንታኙና ጸሐፊው አንድሪው፡፡ በጽሑፉ ማጠቃለያም፣ ‹‹ላቭሮቭ ወደ አዲስ አበባ ያደረጉት ጉዞ የሩሲያና የኢትዮጵያ መፃዒ ግንኙነት ጠንካራ እንደሚሆን ከወዲሁ የጠቆመ ነው፤›› ሲል ነበር የደመደመው፡፡

ሰላም ለኢትዮጵያ!

 


SOURCE:- https://www.ethiopianreporter.com/121093/

https://www.dw.com/am/%E1%8D%91%E1%89%B2%E1%8A%95%E1%8A%93-%E1%8A%A2%E1%89%B5%E1%8B%AE%E1%8C%B5%E1%8B%AB%E1%8B%89%E1%8B%AB%E1%8A%91-%E1%89%A0%E1%88%A9%E1%88%B5%E1%8B%AB/a-50043226