ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, June 12, 2014

ካሳየን አጣሁት – አቦነሽ አድነው


 

ለጎንደሩ ጀግና ለጠፋው መቅደላ፣
አብሮ አልቅሱለት ቋራና ኦሜድላ፣
ፍቅሩም ሳይወስነው በትግሬ በወሎ፣
እራሱን የጣለው ጦቢያን አድን ብሎ።
ምንጊዜም ይወራል ዝናው፣
በታሪክ አይሞትም ጀግናው፣
ይጠራል ስሙ በዚህች ምድር፣
ላገሩ ስለዋለው ብድር።

በሰንበት ባውዳመት ተጎድቼ በባል፣
እንግዲህ ምንጠቅሞኝ ተዋበችስ ብባል፣
ከፍቅሬም ካካሌም ባንዴ እየተለየሁ፣
ቀረሁኝ በተስፋ እያልኩ ዓለማየሁ።



 እናቴ ሞሽራ ልትድረኝ ለጀግና፣
ተነስቶ ባገሩ አንድነት ያፀና፣
ሚስት ናት ገረድ ናት ሲለኝ እንዳልኖረ፣
ነፍሱን ላገር ሰጥቶ የኔ ካሳ ቀረ።
ከንግስ ከግርማዊነት ያኮራል ያለው ጀግንነት፣
ወገኔ ጥለህ ተሰደድ እያየው የሱ ጀግንነት።
ዓለማየሁ ብሎ ሀዘንን መቀበል፣
ዕጣው በኔ ሲደርስ እንግዲህ ምን ልበል፣
ጎንደርን ማሳለፍ ምንስ ጎደለብኝ፣
መቅደላ ነው እንጂ ካሳው የቀረብኝ።
 
ሙሉ ቤቴን ሳጣው አላልኩም እየዬ፣
የኑሮ መከታ ባላገር ነው ብዬ፣
ተዋቡ ለሚለኝ ለፍቅሬም ሳይሳሳ፣
ከኔ ለበለጠው ለአገር ሆኗል ካሳ።

ማተብ በጥሶ ቃል ከማጠፍ፣
ይሻላል ቆርጦ ነፍስን መቅጠፍ፣
ሆነልት እንጂ ታሪክ ርስቱ፣
አላጓጓውም ቤተመንግስቱ።
ይሄ ነው ቆራጥ ይሄ ነው ጀግና፣
በታላቅ ስራው ፍቅሩን የሚያፀና።


ስሙ አባታጠቅ የሱ ፈረስ፣
ያውቃል ካሰበው ፈጥኖ መድረስ፣
ቼ እያለ ገስጋሽ ብርቱ ጋላቢ፣
ሜዳነው ሲሉት የሚገኝ ግቢ።
ዘውዱ ነበርኩኝ በሚስትነቴ፣
ንጉሴን አጥታ ጠፋች እናቴ፣
በጎዶሎ ቀን በዕድለ አንካሳ፣
አልኖርም አለች ነፍሴ ያለካሳ።



 


ማተብ በጥሶ ቃል ከማጠፍ፣
ይሻላል ቆርጦ ነፍስን መቅጠፍ፣
ሆነልት እንጂ ታሪክ ርስቱ፣
አላጓጓውም ቤተመንግስቱ።
ይሄ ነው ቆራጥ ይሄ ነው ጀግና፣
በታላቅ ስራው ፍቅሩን የሚያፀና።






https://www.youtube.com/watch?v=ZVKUwPtV5ec 

No comments:

Post a Comment