ከደራሲያን ዓምባ

Wednesday, November 19, 2014

የሚጸልዩ እጆች_እና_አልብሬሽት ዱረር

(እውነተኛ ታሪክ)
*************


ከስድስት ምእት ዓመታት በፊት በጀርመን ኑረምበርግ ከተማ በአንድ ትንሽ መንደር ውስጥ አሥራ ስምንት ልጆች ያሉበት አንድ ቤተሰብ ይኖር ነበር፡፡ አሥራ ስምንት! ለዚህ ሁሉ ማቲ ምግብ ለማቅረብ በሙያው አንጥረኛ የሆነው አባ ወራ በቀን አሥራ ስምንት ሰዓት በሙያውና ከሙያው ውጪ መሥራት ነበረበት፡፡

የቤተሰቡ የኑሮ ሁኔታ የከፋ ቢሆንም ከልጆቹ ውስጥ ሁለቱ ታላላቆች ልዩ ሕልም ነበራቸው ሥነ ጥበብን ማጥናትና ዝነኛ ሠዓሊ መሆን፡፡ አባታቸው ማንኛቸውንም ኑረምበርግ ወደ ሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ ልኮ ሊያስተምራቸው የሚያስችል የገንዘብ አቅም እንደሌለው ግን ሁለቱም ያውቁ ነበር፡፡

አንድ ምሽት በተጨናነቀው አልጋቸው ላይ ሆነው በሕልማቸው ዙሪያ ለረጅም ሰዓት ተወያዩና ወደ አንድ ስምምነት ደረሱ፤ ዕጣ ሊጣጣሉም ወሰኑ፡፡ በዕጣው የተሸነፈው በአቅራቢያቸው ወደ ሚገኝ አንድ የማዕድን ማውጫ ሄዶ እንዲሠራ፣ በሚያገኘውም ገቢ ወደ ከፍተኛ ትምህርት የሚሄደውን ወንድሙን እየረዳ እንዲያስተምር፡፡ ዕጣ የወጣለት ወንድም ደግሞ በኑረምበርግ ከተማ በሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ የአራት ዓመታት ትምህርቱን እንዲማርና ትምህርቱንም ሲጨርስ፣ በሚመረቅበት የሥነ ጥበብ ሙያ ከሚሠራቸው ሥዕሎች ሽያጭ በሚያገኘው ገቢ ወይም አስፈላጊ ከሆነ እርሱም በማዕድን ቁፋሮ ሥራ ተቀጥሮ በተራው ያስተማረውን ወንድሙን ሊያስተምር ወደ ውሳኔ ደረሱ፡፡

አንድ እሑድ ጠዋት ዕጣው ተጣለ፣ ታላቁ አልብሬሽት ዱረር የተባለው ወንድም ዕጣው ወጣለት፡፡ ኑረምበርግ ከተማ ወደ ሚገኘውም የሥዕል አካዳሚ ገባ፡፡

ዕጣ ያልወጣለት ወንድም ወደ አደገኛው የማዕድን ቁፋሮ ሥራ አመራ፣ ለተከታዮቹ አራት ዓመታትም ወንድሙን በገንዘብ እየረዳ አስተማረ፡፡ አልብሬሽት የአካዳሚው የሥዕል ትምህርት ተዋጣለት፡፡ በልዩ ልዩ የሥዕል ሥራዎች የተካነ ሆነ፡፡ የሚሠራቸው የቅብ ሥዕሎች ከመምሕራኖቹ ሥራዎች ይልቅ እየላቁና እይተወደዱ መጡ፡፡ በኮሚሸን ለሚሠራቸውም ሥዕሎች ዳጐስ ያለ ገንዝብ ይከፈለው ጀመር፡፡

ወጣቱ ሠዓሊ ትምህርቱን አጠናቆ ወደ መንደሩ ሲመለስ ቤተሰቡ በድል መመለሱን ምክንያት በማድረገ ድግስ ደግሶ ጠበቀው፡፡ በሙዚቃና በሳቅ በደመቀው ግብዣ መጨረሻ ላይ ሠዓሊው አልብሬሽት ከክብር ወንበሩ ተነሳና ለተወዳጅ ወንድሙ፣ ላመታት ስለከፈለው መስዋዕትነት፣ ሕልሙንም እንዲያሳካ ስለ ረዳው ጽዋ አነሳ፡፡ በመዝጊያ ንግግሩም፣ ‹‹የተባረክህ ወንድሜ አልበርት ሆይ፣ አሁን እንግዲህ ተራው ያንተ ነው፣ ወደ ኑረምበርግ ትሄዳለህ አንተም ሕልምህን ታሳካለህ፣ እኔም በተራዬ እንከባክብሃለሁ›› አለ፡፡

በገበታው የታደሙት ሁሉ አንገታቸውን ከገበታው አንድ ጥግ ላይ ወደ ተቀመጠው የማዕድን ሠራተኛ አልበርት አዞሩ፡፡ በገረጣው ፊቱ ላይ እንባው እየተንከባለለ በጉንጮቹ ላይ እይፈሰሰ ነው፣ ራሱንም ከግራ ወደ ቀኝ እያወዛወዘ፣ ሳግም እየተናነቀው ደጋግሞ፣ ‹‹አይሆንም….. አይሆንም ወንድሜ ሆይ፣….. አይሆንም!›› አለ፡፡

በመጨረሻ ብድግ ብሎ እንባውን ከጉንጮቹ ላይ በማበስ፣ አሻግሮም በገበታው ላይ የታደሙትን የሚወዳቸውን ፊቶች በፍቅር እየተመለከ፣ ሁለት እጆቹን አጣምሮ ወደ ቀኝ አገጩ በማስጠጋት ለስለስ ባለ ድምጽ ‹‹የለም ወንድሜ ሆይ፣ ወደ ኑረምበርግ ልሄድ አልችም፣ ለእኔ ዘግይቷል፣ የአራት ዓመታት የማዕድን ቁፋሮ ሥራ እጆቼን ምን እንዳደረጋቸው ተመልከትማ በጣቶቼ ላይ ያሉ አጥንቶች ሁሉ በቀን ቢያንስ አንድ ጊዜ ይጐዱ ነበር፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በከባድ የቁርጥማት በሸታ እየተሰቃየሁ ነው፣ በእርሳስና በብሩሽ በሸራ ላይ ሥዕሎችን መቀባት ይቅርና፣ አላስተዋልከኝም እንጂ፣ ጽዋችንን እናንሳ ስትል ጽዋውን ለመያዝ እንኳ የቀኝ እጄ አልቻለም፡፡ አሁን ለእኔ ዘግይቷል›› አለ፡፡

ይህ ታሪክ ከተፈጸመ ከ450 ዓመት በላይ አልፈዋል፡፡ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ የአልብሬሽት ዱረር እጹብ ድንቅ ሥራዎች፣ የራስ ምስሎች፣ የእርሳሰና የውኃ ቀለም ቅቦች፣ የቻርኮል ሥራዎች፣ የእንጨት ቅርጻ ቅርጾችና፣ የመዳብ ውቅሮች በመላው ዓለም ባሉ ሙዚየሞች ተሰቅለው ይገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ ብዙ ሰዎች ከሌሎች ሥራዋቹ ይልቅ ‹‹እጆቹ›› የሚለው ሥራውን ቅጅ በየቤቶቻቸውና ቢሮዎቻቸው ግድግዳዎች ላይ አንጠልጥለውታል፡፡

አንድ ቀን ወንድሙ ለከፈለለት መስዋዕትነት አክብሮት ለመስጠት፣ አልብሬሽት ዱረር በከፍተኛ ጥንቃቄ የወንድሙን የተጎዱ እጆች፣ መዳፎቹ ተጋጥመው፣ ቀጫጭን ጣቶቹ ወደ ሰማይ ተዘርግተው የሚታዩበትን ሥዕል ሳለ፡፡ ይህን ድንቅና ኃያል ሥራውንም ‹‹እጆቹ›› የሚል ስያሜ ሰጠው፡፡ ብዙም ሳይቆይ በዓለም ዙሪያ ሥዕሉን የተመለከቱ ሁሉ፣ ለዚህ ታላቅ እጹብ ድንቅ ሥራ ልባቸውን ከፈቱለት፡፡ ይህን ከፍቅር የተነሳ የተሳለ ሥዕልም ‹‹የሚጸልዩ እጆች›› ብለው ሰየሙት፡፡



አልብሬሽት ዱረር (Albrecht Dürer) ማን ነው?
 
Albrecht Dürer (German: 21 May 1471 – 6 April 1528)


ንደ አውሮፓው አቆጣጠር ግንቦት ፳፩ ቀን ፲፬፻፸፬ ኑረምበርግ ጀርመን ተወልዶ በ፶፮ ዓመቱ (ሚያዚያ ፮ ቀን ፲፭፻፳፰) እዛው ኑረምበርግ ከተማ የሞተው አልብሬሽት ዱረር (ከዚህ በኋላ ዱረር ብለን እንጠራዋለን) (German: [ˈalbʁɛçt ˈdyːʁɐ]) የተሳካለት የወርቅ ኣንጥረኛና ከሃንጋሪ ወደ ኑረምበርግ የፈለሰው አባቱና እናቱ ሦስተኛ ልጅ (ሁለተኛው ወንድ) ሲሆን፤ ወላጆቹ ከ፲፬ እስከ ፲፰ ልጆች እንደነበራቸው ይገመታል።
      ዱረር ለጥቂት ዓመታት ትምህርቱን ከተከታተለ በኋላ የወርቅ አንጥረኝነትና የስዕል ሙያ መሰረቶችን ከአባቱ ተማረ። ምንም እንኳን አባቱ በአንጥረኝነቱ እንዲቀጥልበት ቢፈልግም፤ በጣም ላቅ ያለ የስዕል ችሎታ በማሳየቱ ምክኒያት ገና በ፲፬ ዓመቱ በኑረምበርግ ታዋቂ አርቲስትና የኪነ ጥበብ ማዕከል (የአርት ወርክ ሾ) ባለቤት ለነበረው ሚካኤል ዎልጌሙት (Michael Wolgemut) ረዳት ሆነ።
 
 ‹‹የሚፀልዩ እጆች›› /Betende Hände/ በእንግሊዘኛ Praying hands (በጀርመንኛም Studie zu den Händen eines Apostels in German, ወይም "Study of the Hands of an Apostle": የሐዋሪያው እጅ ጥናት) በመባል የሚታወቀው በብዕርና ቀለም በጀርመናዊው የኪነ ጥበብ ሰው አልብሽሬት ዱረር በ፲፭፻፰ የተሰራ ሲሆን፤ ይህ ሥራ ቪየና/ኦስትሪያ (Vienna, Austria) በሚገኘው አልበርቲና (Albertina) ሙዚየም ይገኛል።በብዕርና (እራሱ በሰራው) ሰማያዊ ወረቀት ላይ ዱረር ነጩ ሄይተኒንግ በመባል የሚታወቀውን ቴክኒክ ለዚህ ስራው ተጠቅሟል። ሥዕሉ እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ የሚፀልዩ ሁለት የወንድ እጆች ሲሆን፤ የቀኙ እጅ ሙሉ ክፍል ካለመታየቱ ባሻገር፣ የፀላዩን እጅ የሸፈነው ልብስ (ክሳድ) ጫፍ በጥቂቱ ወደላይ ተቀልብሶ ይታያል። ይህ ሥዕል በ፲፯፳፱ በእሳት የነደደው ባለ ሶስት ክፍሉ የሄለን መስዋዕት ማቅረቢያ (the Heller altar,) በመባል ይታወቅ ለነበረው የዱረር ሥራ መካከለኛው ክፍል ላይ ለተሳለው ሐዋሪያ እጅ (an apostles' hand) እንዲሆን ታስቦ የተነደፈ ነው። ይህ የእጅ ንድፍ ሊደረግ በታሰበበት ሥዕል በመካከለኛው ክፍል በቀኝ በኩል በተመሳሳይ ግን በትንሽ መጠን ተስሎ ይገኛል። በወረቀቱ የሐዋሪያው ራስ ንድፍ የተሰራበት ቢሆንም፤ ሁለቱ የተቀመጡት ተለያይተው ነው። ዱረር ለዚህ (የሄለን መስዋዕት ማቅረቢያ) ስራው በጠቅላላ ፲፰ ንድፎችን ሰርቷል። ቪየና ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሕዝብ ዕይታ በ፲፰፻፸፩ ቀረበ። ሥራው ምናልባት የሰሪው እጅ እንደሆነ ይገመታል።
 
*******************************************************************************

ምንጭ፥ http://www.ethiopianreporter.com/issues/Reporter-Issue-1419.pdf __ኃይል   ከበደ «ምስካይ» (2004)
         :- http://enaseb.blogspot.com/2013/12/blog-post_2986.html 
         :-  የ ኛ ጉ ዳ ይ - Yegna Guday Blog

No comments:

Post a Comment