ከደራሲያን ዓምባ

Tuesday, September 13, 2022

መስከረም ፩ ቀን ለምን የዘመን መለወጫ ሆነ?

~ የአመቱ ወራት ~

ጨለማው ሲጠፋ ዝናቡ ሲያቆም ፥
ያ የለውጥ ወራት መጣ መስከረም
ሰዎች ይነሣሉ ሊሰሠሩ ታጥቀው ፥
መስከረም ነውና ብርሃን ሰጭው ።
ብዙ እህል እሸት ጥቅምት ሲገባ ፥
ሜዳውና ጋራው አጊጦ ባበባ ፥
ህዳር ወር ደርቆ እረገፈ አበባ ፥
የኑግ ፥ የጎመን ዘር የሰሊጥ የተልባ ።
ታኅሣሥ እኩል ነው አዋቂና ልጁ ፥
ሊሠራ ይነሣል ሁሉም በየደጁ ።
ጥር ነው ወራቱ ያጨዳው ክምሩ ፥
ምርትን ለመሰብሰብ ያለው ግርግሩ ።
የካቲት መውቂያ ነው ክምሩ ፈረሰ ፥
ገለባው ተለየ ንፋሱ ነፈሰ ።
መጋቢት መጣልን ዓመት ተጋመሰ ፥
መጋቢት ወራት ሄደ እየቀነሰ ።
ሚያዝያ ተተክቶ መጋቢት አለፈ ፥
በልጉ ዝናብ ጣለ እያርከፈከፈ ።
ግንቦት ደረቅ ወር ነው ፀሐይዋ ከረረች ፥
አቧራው ቦነነ መሬት ተራቆተች ።
ሰኔ ደግሞ መጣ ክረምት አስከትሎ ፥
ገበሬው ተነሣ ማረሻውን ስሎ ።
ሐምሌም ተከተለ ገባ ዝናም ጭኖ ፥
ቀንና ሌሊቱን በዝናብ ጨፍኖ ።
ነሐሴ ተተካ ኅይለኛው ክረምት ፥
ያወርደው ጀመረ የዝናብ መዓት ።
አምስት አምስት ቀን ሦስቱን አመታት ፥
ባራተኛው አንዴ ስድስት ቀን ያላት ፥
መሸጋገሪያዋ የጳጉሜ ወር ናት ።
===============
ምንጭ 📖 ገፅ ፴፬ የ ፫ኛ ክፍል የአማርኛ መፅሃፍ


መስከረም 1 ቀን ለምን የዘመን መለወጫ ሆነ?
መስከረምና የዓመቱ ወራት ትርጉማቸውስ?
ዘመን መለወጫ ለምን መስከረም ወር ላይ እንደሆነ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ሲያትቱም ብርሃናት/ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜን ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ያን ጊዜ ሌሊቱም ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱንም ጠንቀቀው ቢቆጥሩት 364 ቀናት ይሆናል፡፡ ለዘመን መታወቂያ ይሆን ዘንድ ፀሐይና ጨረቃ ከዋክብትን ፈጠረ ይላልና /ሔኖክ.21.49/፡፡ በሌላ በኩልም በዘመነ ኖኅ ዓለምን ውኃ አጥለቅልቋት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ከነበረው ውኃ የተገለጠችበት ወር «በመጀመሪያም ወር በምድር ታየች የንፍር ውኃው ከምድር ደረቀ» የሚለውን መሠረት አድረገው የአቡሻኽር ሊቃውንት የዘመን መለወጫን ታሪካዊ አመጣጥ ያስረዳሉ፡፡/ኩፋ.7.1/
በመሠረቱ ዘመን ተለወጠ ሲባል የሚለወጡት ወራቱ ብቻ አይደሉም፡፡ በወቅቱ የሚከሰቱት/የተከሰቱት/ መልካምም ሆነ ክፉ ነገር /ገጠመኝ/ ሲሆን ወራቶቹ ግን ያው በየዓመቱ እየተፈራረቁ ይመጣሉ፡፡ ዘመን መለወጫ ላይ የሰው ልጆች ሕይወት ሊለወጥ ይገባል፡፡ ተማሪው ተምሮ ወደቀጣዩ ክፍል /ደረጃ/ የሚለወጥበት፣ ገበሬው የክረምቱን ወራት በሚገባ ተጠቅሞ የሚቀጥለውን የበጋ ወራት የሚቀበልበት፣ ሠራተኛው የክረምቱን ዝናብ ታግሶ የፀሐይን ወራት የሚቀበልበት ሌላውም እንደዚያ ሆነው ወራቶቹ በዚያ ዘመን ያለው የተፈጥሮ ክስተቶች የሚለወጥበት ዘመን ተለወጠ እየተባለ ይነገራል፡፡
የቀመር መጀመሪያ የሆነው ዕለት ማክሰኞ ሚያዝያ 1 ቀን ነው። ነገር ግን የሚያዝያን እንዳንጠቀም መዓልቱና ሌሊቱ እኩል አይደለም፡፡
ይህን ተከትሎ በሚዞር ነገር መስማማት እንጂ ሁሉም መነሻ ሆኖ ማገልገል ይችላሉ፡፡ ለመስማማት ደግሞ በቂ ምክንያት ያስፈልጋል፡፡ሊቃውንት ደግሞ ብዙ ምክንያት ያለው መስከረም ስለሆነ መነሻቸው በመስከረም እንዲሆን አድርገዋል፡፡ የመጻሕፍት መምህራን ሌላ ምክንያት ይጨምራሉ፡፡ እስራኤላውያን ከግብጽ በወጡበት የሰባተኛው ወር መባቻ እንደሆነ እግዚአብሔር አዝዟል፡፡ ይኸውም መስከረም ነው ይላሉ፡፡ ክረምት በጨለማ በብሉይ ይመሰላል ፀሐይ የሚወጣበት መስከረም ደግሞ በብርሃን በሐዲስ ኪዳን ይመሰላል፤ ስለዚህ ለዓውደ ዓመት መነሻ ወር መስከረም ነው፡፡

የኢትዮጵያውያን የዘመን መለወጫ መስከረም ነው፡፡ መስከረም 1 ቀን ርእሰ ዓውደ ዓመት ተብሎ ይጠራል፡፡ ትርጉሙም ርዕስ የአንድ ጽሑፍ /ንግግር በር እንደሆነ ሁሉ በዓመት ውስጥ ያሉ ዓውደ ዓመቶች /በዓሎች/ እና አጽዋማት ማወቂያ /ማመላከቻው/ መስከረም 1 ቀን የሚውልበት ነውና፡፡ እንዲሁም የዓመቱ በዓላትና አጽዋማት የሚታወጀው መስከረም 1 ቀን ነው፡፡ በዚሁም ዕለት መዓልቱን /በፀሐይ/ ሌሊቱን /በጨረቃ/ በመቁጠር ምሥጋና ለእግዚአብሔር ይቀርባል፡፡
መስከረም ማለት ምን ማለት ነው ? የመስከረም ወር ትርጓሜስ?
መስከረም ማለት ከግእዝ የመጣ ቃል ሲሆን (ከሪም- ወይም ከሪሞት)
(መዝከረ-ውይም -ከረም) ከሚሉ የግእዝ ቋንቋዋች የተገኘ የውህድ አረፍተ ነገሮች ውጤት ነው ።
1️⃣ ከሪም ወይም ከሪሞት ማለት ምን ማለት ነው ?
ከሪም ወይም ከሪሞት ማለት-በግእዝ የከረመ፣ የቆየ የሰነበተ ማለት ሲሆን ይህም የክረምት ቆይታ የሚገልፅ እና የክረምት መገባደጃ እንደሆነ የሚያመለክት ነው በሌላ ፍቺ የከረመው ክረምት ማለቂያ የመፀው መባቻ መጀመሪያ ማለት ነው ።
2️⃣ ሌላው ደሞ መዝከረ - ከረም ከግእዝ ቃል የተገኝ ቃል የተገኝ ውህድ ሲሆን ትርጓሜውም መዝከር ማለት በግእዝ መዘከር፣ ማስታወስ፣ ማሰብ ማለት ነው።
ከረም ማለት ደሞ የቆየ፣ የከረመ፣ የሰነበተ ማለት ሲሆን በአጠቃላይ
መዝከረ ከረም ማለት የከረመን የቆየን መዘከር ማስታወስ ማለት ነው
ለዚህም ሲባል የቆየውን አመት የምንዘክርበት አዲሱን ዓመት የምንቀበልበት ወር ለማለት መዝከ ከረም(መስከረም) እንለዋለን። በዚህም ምክንያት አውደ ዓመት አዲስ ዓመት ሆነ የከረመውን የቆየውን አሮጌውን ዓመት ተሸኝ የምንቀበልበት ሰናይ ወር መስከረም ሆነ አሮጌው የቆየው ክረምት ተሸኜ ማለት ነው።
መዝከ ከረም ወደ አማርኛ ሲመለስ አንዱን ከግእዝ በመተው
መስከረም ወደሚል አማርኛ ተቀይሮ ይጠራል። የወራቶች መጀመሪያ የአዲስ ዓመት መባቻ የክረምት መገባደጃ ለማለት መስከረም ተባለ።

13ቱ የኢትዮጵያ ወራት አሰያየም
1️⃣. መስከረም
የግእዝ ሥርወ ቃሉ - መስ እና ከረም ሲሆን
ትርጉሙም መስ፣ አለፈ፤
ከረም፣ ክረምት ማለት ሲሆን፤ መስከረም ማለት ክረምት አለፈ ማለት ነው።
2️⃣. ጥቅምት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ጠቀመ።
ትርጉም ሠራ፣ ጠቃሚ ጊዜ ማለት ነው።
3️⃣. ኅዳር
የግእዝ ሥርወ ቃሉ - ኀደረ።
ትርጉም አደረ፣ ሰው በወርሃ አዝመራ ማሳ ውስጥ ለጥበቃ ማደሩን ይገልፃል።
4️⃣. ታኅሣሥ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ኀሠሠ።
ትርጉም መረመረ፣ ፈለገ፣ በመኽር ወቅት የሰብል ምርመራ ያመለክታል።
5️⃣. ጥር
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ነጠረ።
ትርጉም ጠረረ፣ ብልጭ አለ፣ ነጻ በራ የፀሀይን ግለት ወቅት ያሳያል።
6️⃣. የካቲት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ከቲት።
ትርጉም (የእህልን) መክተቻ ማለት ነው።
7️⃣. መጋቢት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ መገበ።
ትርጉም በቁሙ የሚመግብ (በጎተራ የተከተተው የሚበላበት) ማለት ነው።
8️⃣. ሚያዚያ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ መሐዘ።
ትርጉም ጎረመሰ ጎበዘ ሚስት ፈለገ(ወርኀ ሰርግ መሆኑን ሲያጠይቅ)
9️⃣. ግንቦት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ገነበ።
ትርጉም ገነባ፣ ሰራ፣ ቆፈረ፣ ሰረሰረ (ለእርሻ የመሬቱን መዘጋጀት ያሳያል።
1️⃣0️⃣. ሰኔ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ሰነየ።
ትርጉም፣ አማረ ማለት ነው።
1️⃣1️⃣. ሐምሌ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ ሐመለ።
ትርጉም ለቀመ(ለጎመን)
1️⃣2️⃣. ነሀሴ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ አናህስየ።
ትርጉም አቀለለ፣ ተወ የክረምቱን እያደረ መቅለሉን ያመለክታል።
1️⃣3️⃣. ጳጉሜን
ሥርወ ቃሉ ግሪክ ሲሆን ኤጳጉሚናስ።
ትርጉም ተጨማሪ ወር ማለት ነው ።
መልካም አዲስ ዓመት ‼

https://www.facebook.com/petros.kebede




ለምን መስከረም? – ለምን ዕንቁጣጣሽ?


“መስከረም በአበባው ሠርግ በጭብጨባው ይታወቃል” ነው የሚባለው

  • ለንጉሥ ቢኾን ኑሮ “ዕንቁ ፃዕፃኹ” ይባል ነበር እንጂ ዕንቁጣጣሽ አይባልም ነበር  

ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ፣ የመሸጋገሪያው ዕለት “ቅዱስ ዮሐንስ” እየተባለ ሲጠራ፣ በባህላዊና ትውፊታዊ መዘክሩ ደግሞ “ዕንቁጣጣሽ” በመባል ይታወቃል፡፡ ሁለቱም ማለትም ቅዱስ ዮሐንስ እና ዕንቁጣጣሽ መስከረም ፩ ቀን ተደርገው ሲዘከሩም፣ ሃይማኖታዊና ትውፊታዊ ትርጓሜያቸውን ይዘው እንደኾነ መዘንጋት የለበትም፡፡

ሃይማኖት ስንልም ብራና ፍቃ፣ ቀለም አውጥታ፣ ብርዕ ቀርጻ፣ ታሪክን፣ ፍልስፍናን፣ ቁጥርን፣ የሀገር ፍቅርን፣ ነፃነትን፣ ጀግንነትን – መምህርቷ የኢትዮጵያ ተዋሕዶ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ማለታችን እንደኾነ ይታወስልን፡፡ እንግዲህ መስከረም ፩ ቀን ለእኛ ኢትዮጵያውያን የዘመን መለወጫ ወይም ወደ አዲስ ዓመት ተሸጋገርንበት ስንል፣ አዲስነቱ እንዲታወቅ እንደ መጽሐፉ ሥራት፣ እንደ ሊቃውንቱ ትምህርት የገበየነውን ለማካፈል ነው፡፡ ከነይትበሃሉም “መስከረም በአበባው ሠርግ በጭብጨባው ይታወቃል” ነው የሚባለው፡፡

ለምን መስከረም? መስከረም የጨለማው (ክረምት ለማለት) ጊዜ አልፎ ብርሃን የሚታይበት፣ ዕፅዋት፣ አዝርዕት፣ አታከልት፣ የሚያብቡበት፣ የሚያፈሩበት፣ እንስሳት የጠራ ውሃ እየጠጡ፣ ለምለም ሣር እየነጩ የሚቦርቁበት፣ በአጠቃላይ መሬት በልምላሜ አጊጣ፣ ተውባ የምትታይበት በዚሁ በወርኀ መስከረም ነው፡፡ አንዳንድ መምህራንም መስከረምን “የወራት ፊታውራሪ” ይሏታል፡፡

የአቡሻኸር ሊቃውንት እግዚአብሔር ዓለምን የፈጠረው መስከረም ፩ ቀን ነው ሲሉ ያትታሉ፡፡ ሌሎቹም መስከረም በኢትዮጵያ ብቻ ሳይኾን፣ ከዘመነ ሥጋዌ በፊት በዓለም ኹሉ የወርና የዓመት መጀመሪያ እንደነበር ይገልጹና የክረምት ጫፍ መጨረሻ፣ የመፀው መባቻ ከመኾኑም በላይ መዓልቱና ሌሊቱ ትክክል የሚኾንበት ወር ነው ይሉታል፡፡ በነገራችን ላይ መስከረም፡- ከረመ ከሚለው ግስ የተገኘ፣ ትርጓሜውም ቀዳማይ፣ ለዓለም ኹሉ መጀመሪያ፣ ርዕሰ ከራማት፣ መቅድመ አውራኅ ማለት እንደኾነ ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡

መስከረም ሌላም አብነት አለው፡፡ “ርዕሰ-ዓውደ ዓመት”፣ “ዕንቁጣጣሽ” የተባሉትን ምሥጢራት ተሸክሟል፡፡ የምሥጢር አባቶቻችንም ይህንን በአፍም በመጽሐፍም ሲነግሩን ዘመናትን አስቆጥረዋል፣ ነገም እንዲሁ ነው፡፡ እና ለምን መስከረም? ለምን ዕንቁጣጣሽ? በሚሉት ጥያቄዎች ዙሪያ የሊቃውንቱን የቃልና የጽሑፍ አስረጅ እንደሚከተለው እናየዋለን፡፡ የመጀመሪያው አፈሊቅ አክሊሉ ገብረኪሮስ ናቸው፡፡

ሊቁ የኢትዮጵያ ጋዜጦችና መጽሔቶች አቋማቸውን የሚገልጹበትን ቦታ “ርዕስ አንቀፅ” በሚል ስያሜ እንዲጠራ ያደረጉ ዜና ቤተክርስቲያን እና በኋላም የአዲስ ዘመን ጋዜጠኛ የነበሩ ናቸው፡፡ ያልጻፉት ታሪክ፣ የማያውቁት ትውፊት እና ያልተቀኙት የቅኔ ዓይነት የለም ማለት ይቻላል፡፡ ምሉዕ በኩለሄ፡፡

እኚሁ ሊቅ ታዲያ ከዛሬ 56 ዓመት በፊት፣ ማለትም በ1955 ዓ.ም በዚያው በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ስለዘመን መለወጫና ዕንቁጣጣሽ ሲተርኩ፣ “ስለዕንቁጣጣሽ በቃል የተነገረ እንጂ በጽሑፍ የሠፈረ አልተገኘም” ነው ያሉት፡፡ ኾኖም አሉ፤ “…ኾኖም በቃል ሲወርድ ሲወራረድ እንደመጣ ‹ዕንቁ› ብሎ ‹አዕናቁ› ከግእዝ የተወረሰ ቃል ነው፡፡ ዕንቁ ለአንድ፣ አዕናቁ ለብዙ ይነገራል፡፡ ጣጣሽ፡- “ፃዕፃዕ” ከሚለው የግእዙ ቃል የተወረሰ ነው፡፡ በአማርኛ ጣጣ፣ መባዕ፣ ግብር፣ መፍቀደ፣ በረከተ-ገጽ ማለት ይኾናል፡፡ መጽሐፍተ ብሉያት ወደ እግዚአብሔር የሚቀርበውን መባዕ፣ የሚገባውን ግብር “ፃዕፃዕ” ይሉታል፡፡ በየዓመቱ ዕንቁጣጣሽ ማለታችን “የዕንቁጣጣሽ ግብር፣ የዕንቁጣጣሽ በረከተ-ገጽ ነው ብለን የምሥራች ማሰማታችን ነው፡፡

በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ ዕንቁጣጣሽ የተበረከተው፣ ለቀዳማዊ ሚኒሊክ እናት ለንግሥት ማክዳ ነው፡፡ ንግሥት ማክዳ ቀዳማዊ ሚኒሊክን በወለደች ጊዜ ሕዝቡ “ንጉሥ ተወለደ” ብሎ ዕልል ዕያለ፣ የአበባ ዕንቁጣጣሽ ለንግሥት ማክዳ አበረከተ፡፡ ዕንቁጣጣሽ መባሉም መጀመሪያ ለንግሥቲቱ ስለተገበረ ነው፡፡ ለንጉሥ ቢኾን ኑሮ “ዕንቁ ፃዕፃኹ” ይባል ነበር እንጂ ዕንቁጣጣሽ አይባልም ነበር፡፡ በሸዋም ሕዝቡ ግብር አለብኝ ሲል “ጣጣ አለብኝ” ይላል፡፡ ከዚህም በቀር ንጉሥ ሰሎሞን፣ ከደስታው ብዛት የተነሣ ለንግሥቲቱ፣ አስቀድሞ ለጣትሽ መታሰቢያ ይኹንሽ ብሎ የዕንቁ ቀለበት ሰጥቷት ነበር እያሉ ሊቃውንቱ ነግረውናል …” ብለዋል፡፡

ሌሎችም የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት፣ ስለዕንቁጣጣሽ፣ ስለመስከረም እና ዘመን መለወጫ ምሥጢር፣ ከሃይማኖታዊ ትርጓሜው ባሻገር ከሥነ-ቃል ወይም አፍኣዊ ኪነተ ቃል አኳያ አያሌ መጣጥፎችን አኑረውልን አልፈዋል፡፡ በዚህ ረገድ አለቃ አያሌው ታምሩ /ነፍስ ሔር/ ምንጊዜም ሲታወሱ፣ እንደ መምህር ሀብተ ማርያም ተድላ፣ እንደ አለቃ ነቢየ ልዑል ዮሐንስ /ነፍስ ሔር/ እና ቀሲስ ልሳኑ በዛብህ /ነፍስ ሔር/ የምንጠራቸው መምህራነ ቤተክርስቲያን ናቸው፡፡

አለቃ ነቢየ ልዑል ደግሞ ስለዕንቁጣጣሽ ሲተርኩ፣ “ዕንቁጣጣሽ ግጫ ማለት ነው” ይላሉ፡፡ “ግጫ ደግሞ የሣር ዓይነት ነው፡፡ የአበባ እርጥብ ስጦታ መስጠት የተጀመረው በኖኅ ዘመን ነው፡፡ ኖኅ የጥፋት ውሃ በጎደለ ጊዜ፣ መጉደሉን ለማረጋገጥ ርግብን ልኳት የወይራ ቅጠል አምጥታለች፡፡ እርሱም የመርከቡን ጣራ አንስቶ ከወጣ በኋላ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት በማቅረብ፣ ልዩ ልዩ ጸዐዳ ሽታ ያላቸውንም አበቦች አቅርቧል፡፡ ንግሥት ወደ ንጉሥ ሰሎሞን ዘንድ ስትኼድ አምስት መቶ ደናግል ተከትለዋት ነበር፡፡ የእልፍኝ አሽከሮቿም እነሱ ሲኾኑ አበባውም የዕንቁጣጣሹም አሰጣጥ በእነሱ ተፈጽሟል፡፡ ስለዚህ ዛሬ ልጃገረዶች አበባ ቀጥፈው፣ እንግጫ ነቅለው፣ ሸልመው የሚያቀርቡበት ነው፡፡ ይህም በአበው ዘንድ ሲያስመርቃቸው፣ በጎረምሳው ዘንድ ደግሞ የመታጨት ዕድል ያስገኝላቸዋል …” ነው ያሉት፡፡

በነገራችን ላይ ከላይ የጠቀስኳቸው ሊቃውንት፣ ከአለቃ አያሌው በስተቀር ቤተክርስቲያኗ በምታሳትማቸው መጽሔቶችና ጋዜጦች ላይ ሲጽፉ የነበሩ ዓምደኞች እንደነበሩ ላስታውሳችሁ፡፡ እናም ከዛሬ አርባና ሃምሣ ዓመታት በፊት፣ በተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ያሰፈሯቸው መጣጥፎች፣ በመስኩ ጥናትና ምርምር ማድረግ ለሚፈልጉ የጥንታዊ መዛግብትና ኪነቃል ተማሪዎች ግሩም የኾነ ምንጭ እንደሚኾኗቸው እጠቁማለሁ፡፡

እኔም ታዲያ፣ አለቃ አያሌው ታምሩን /ነፍስ ሔር/ መላልሼ ከጠየቅኋቸው ልዩ ልዩ ጉዳዮች መካከል፣ ለዘመን መለወጫ እና ዕንቁጣጣሽ ከ20 ዓመት በፊት “ጦማር” ጋዜጣ ላይ የጠየቅኋቸው ነው፡፡ እርሳቸውም ስለታሪኩ፣ “የኢትዮጵያ እምነት በሦስቱ ሕገጋት” የተሰኘ መጽሐፋቸውን ጠቅሰው ያስረዱኝ የሚከተለው ነው፡፡ “የዘመን መለወጫ የታወቀው በሦስት ዓይነት ነው፡፡

አንደኛ እስራኤል በብሉይ ኪዳን ያከብሩት የነበረው ሚያዚያ ፩ ቀን፣ ሁለተኛ የዓለም ክርስቲያን የክርስቶስን ልደት ተቀዳሚ በማድረግ የሚያከብሩት ጥር ፩ ቀን፣ ሦስተኛ ኢትዮጵያ ጥንተ መሠረትነቱን አውቃ የምታከብረው መስከረም ፩ ቀን ነው፡፡ እስራኤል የዘመን መለወጫ በዓልን በሚያዚያ ማድረጋቸው፣ በዚህ ወር ከግብፅ ባርነት ነፃ ስለወጡና እግዚአብሔር ይህንን የነፃነት በዓል በየዓመቱ እንዲያከብሩት ስለአዘዛቸው ነው፡፡ የዓለም ክርስቲያን ጥር ፩ ቀን ማክበራቸው የክርስቶስን ልደት ምክንያት በማድረግ መኾኑ የታወቀ ነው፡፡

ኢትዮጵያ መስከረም ፩ ቀን የምታከብረው ዘመን መለወጫ የተቀበለችው ከካም ነው፡፡ የተጀመረበትም ካምና ልጁ ኩሳ ወደ ኢትዮጵያ የገቡበት፣ አኵሱም በኩሳ ስም የተመሠረተችበት ጊዜ ነው፡፡ ዘመኑም በኢትዮጵያ ላይ ከ4 ሺህ 900 በላይ ሲኾን፣ ከጥፋት ውሃ በኋላ በኖኅ ዕድሜ 601 ጀምሮ 552 ዓመት አሳልፎ እነሆ ደርሰንበታል፡፡

ኖኅም ሲያከብረው፣ ጥንቱን ዓለም የተፈጠረበት ወር እንደመሆኑ መጠን ከአዳም ጀምሮ ወረደ፣ በአበው እየተላለፈ እስከ እርሱ የደረሰ መኾኑና ኋላም የቀላይ አፎች የተከፈቱበት፣ የጥፋት ውሃ መጉደል የተጀመረበት፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ከጥፋት ውሃ ወዲህ ክረምትና በጋ መፈራረቅ የጀመሩበት፣ ምድር የፍሬ ጽንስ፣ አበባ መልክ ያሳየችበት ስለኾነ ነው፡፡ ፊተኛው ሲጨመር 7 ሺህ 452 ዘመናትን ማሳለፉ ነው፡፡ ስሙም በግእዝ “ርዕሰ-ዐውደ ዓመት”፣ በአማርኛ “ዘመን መለወጫ” “ዕንቁጣጣሽ”፣ “ቅዱስ ዮሐንስ” እየተባለ ይጠራል፡፡

ርዕሰ-ዐውደ ዓመት ማለት፣ የዘመን መለወጫ መጀመሪያ፣ ዕንቁጣጣሽ ማለት “ዕንቁ ዕጽ አወጣሽ ብሎ የአበባውን መፈንዳት ወይም “ዕንቁ ዕጣ ወጣሽ” ብሎ፣ መልካሚቱ ምድር ኢትዮጵያ በዕጣ ለካም መድረሷን የሚያመለክት፣ ቅዱስ ዮሐንስ ማለት፣ በዓሉ ከመጥምቁ ዮሐንስ ዕረፍት ጋር የተደጋገፈ መኾኑን ስለሚገልጥ ነው፡፡

… መስከረም ማለትም፣ እግዚአብሔር ከዚህ እስከ ብሩህ ሰማይ ድረስ ሞልቶ የነበረውን ውሃ ከሦስት ከፍሎ በጠፈር፣ በሐኖስ፣ በውቅያኖስ ከወሰነ በኋላ ደረቁ ይገለጥ ባለ ጊዜ ምድር ገብሬ አርሶ፣ አለስልሶ እንዳከተማት ሁሉ፣ ለዘር የተመቸች ኹና ተገኝታ ነበርና፣ መሀሰ ቆፈረ ከረመ- ከረመ የሚሉትን ሁለቱን ግሶች በማቀነባበርና በማስተባበር መስከረም አጥብቆ፣ ታርሶ፣ ከረመ እንደ ማለት፣ ስሙን ከግብሩ ነስቶ የሚጠራበት ነው፡፡

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም አታሚን – አታኒም የተባለውን ቃል ሲተረጉሙ፣ አታን ወይም ኤታን ማለት ጥንተ ፍጥረት እንደኾነ ዕብራይሰጢውን በማዋሐድ ገልጠው፣ ይኸውም በዕብራውያን ሰባተኛ ወር ጥቅምት፣ በኢትዮጵያውያን በፀሐይ አቆጣጠርና በአቡሻኸር ጠንቃቃ ቁጥር ግን መስከረም መኾኑን አስረድተዋል፡፡

ኢትዮጵያ በአኵሱም መዲናነት የተቀበለችውና ስታከብረው የምትኖረው መስከረም ፩ ቀን የሚውለው፣ ርዕሰ-ዓውደ ዓመቷ የኩሽ ኩሳ መዲናና መቃብር በመኾኗ፣ አኵሱም ርዕሰ አኅጉር ኩሺ /ኩሳ/ አሞን ለአኅጉረ ኩሺ /ኩላ/ ተብላ የምትጠራውን አኵሱምን /አኩሺምን/ ያህል ጥንታዊነቷን ሲመሰክር የሚኖር ነው፡፡ በዓመተ ዓለም፣ በዓመተ ኩነኔ፣ በዓመተ ምሕረት ደመራ፣ ዘርዝራ፣ ዐጥፋ፣ ነጥላ፣ ጠቅልላ፣ ከፍላ የምትሰጠው የዘመን ቁጥርም የጥንትነቷ ፍሬ ነው” ብለዋል አለቃ አያሌው፡፡

እንግዲህ ተደጋግሞ እንደሚገለጸውና እንደሚታወቀውም፣ የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ያለው መኾኑ ነው፡፡ ካስማዋም ከአዳም እስከ ልደተ ክርስቶስ አምስት ሺህ አምስት መቶ የሚለው ኾኖ፣ በ550፣ ክርስቶስ ተወለደ ብላ እነሆ አሁን ፳፻፲፪ /ሁለት ሺህ አሥራ ሁለተኛው/ ዘመን ላይ መኾኗን ልብ ይሏል፡፡

https://ethio-online.com/archives/4924



No comments:

Post a Comment