ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, April 3, 2014

የሞኞች ቀን(የማምኛ ቀን) April the fool


በየዓመቱ በፈረንጆች ሚያዚያ 1 ቀን የሚውል የአውሮፖውያን የቀልድ ልማድ ቀን ነው በዚህ ዕለት አውሮፖውያን ወዳጅ ዘመድ ጓደኛን በማሞኘት ነው የሚያሳልፉት፡፡ ለመሆኑ የዚህን ዕለት ታሪካዊ አመጣጥ ያሉቃሉ ?
እ.ኤ.አ በ16ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ የኖርዌይ ተወላጅ የሆነው ሉፍ ሊርፖ(Loof Lirpa)የተባለ ሳይንቲስት የበራሪ ምስጢርን ለማወቅ ጥረት ያደርግ ነበር፡፡ አንድ ቀን ሙከራው ስለተሳከለት በወቅቱ የሀገሪቱ ንጉስ ለነበረው ለንጉስ ሄነሪ 8ኛ ደብዳቤ ያፅፍለታል፡፡ የደብዳቤው ፍሬ ሃሳብ የበራሪ ምስጢርን ተመራምሮ ማግኘቱንና አውሮኘላን ሠርቶ መጨረሡን የሚገልፅ ነበር፡፡ የሙከራው ድነቅ ውጤት ለህዝብ በትርኢት መልክ ለማሳየት ስለፈለገም በዚሁ ዕለት ንጉሱ የክብር እንግዳ በመሆን የልፋቱን ውጤት እንዲመለከትለት ይጋብዘዋል፡፡ ትርኢቱም የሚቀርብበት ዕለት እ.ኤ.አ ሚያዚያ 1 ቀን 1545 ነበር፡፡
ንጉሱ የሊርፖን ደብዳቤ ካነበበ በኃላ በሳይንቲስቱ የምርምር ችሎታ በመደሰት ታላላቅ ሹማምንቱን አስከትሎ ወደ ትርኢቱ ሥፍራ ይሄዳል፡፡ ለክብር በተዘጋጀው ሰገነት ላይ በአካባቢው ከተሠበሰበው ህዝብ ጋር ሆኖ ሳይንቲስቱን መጠባበቅ ጀመረ፡፡ ይሁን እንጅ ሊርፖ በወቅቱ ሳይመጣ ቀረ የንጉሱ ባለሟሎች ተጨነቁ ተጠበቡ፡፡ በመጨረሻም ንጉሱም ተናዶ ወደ ቤተ መንግስቱ ተመለሠ፡፡ ለጊዜው የሊርፖ ጉዳይ ምስጢር ሆኖ ቆየ፡፡

ድርጊቱ ሊርፖ ንጉሱን ለማሞኘት ሆነ ብሎ ያደረገው አልነበረም፡፡ ሙከራው ሳይሳካለት ቀርቶም አይደለም፡፡ ከጊዜ በኃላ እንደተረጋገጠው ሉፍ ሊርፖ የበራሪውን ትርኢት ሳያሳይ የቀረዉ እጅግ በማያሳዝን ሁኔታ ነበር፡፡ 

ሊርፖ የክቡር እንግዳውና ህዝቡ ወደ ተሠበሰበበት ቦታ አውሮኘላኑ እያበረረ ለመድረስ ገና ጉዞ እንደጀመረ ከአንድ ትልቅ ዛፍ ጋር ተላትሞ ህይወቱ ያልፋል፡፡ በዚህም የተነሳም ከሚያዚያ 1 ቀን 1545 እ.ኤ.አ ጀምሮ የደረሠውን አጋጣሚ መሠረት በማድረግ ልክ እንደ አንድ ልማድ በመውሠድ ዘመድ ወዳጅና ጓደኞቻቸውን በማሞኘት በተሞኙት ላይም በመሳቅ ቀኑን ማክበር ጀመሩ፡፡ ባሉርፖ ስምም ከአሳ ከሙዝ ከማርማላታና ከቼኮሌት ልዩ ልዩ ኬኮችን በመስራት በመመካብ ያከብሩታል፡፡ አብዛኛዎቹ ግን ቁራን የሚያከብሩት ሰዎችን በሚያስቅና በሚያዝናና ሁኔታ በማሞኘት ነው፡፡
ይህ ልማድ ከግለሠቦች የእርስ በርስ ማሞኘት ሌላ በዜና ማሠራጫዎችም አልፎ አልፎ ይደረጋል፡፡ ግን በማይጐዳ መልኩ ነው፡፡ በአንድ ወቅት የቢቢሲ ቴሌቨዥን ጣቢያ በዚያን ዕለት ያቀረበው ዜና ከማሞኘትም አልፎ የሚያጃጅል ነው፡፡ ጣቢያው እንዳለው ከሜዲትራኒያን የባህር ዳርቻ የነፈሠው ነፋስ በዛፍ ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረሱና የፖስታ ምርት ስለቀነሰ ከፍተኛ የዋጋ ንረት እንዳስከተለ የሚገልፅ ዜና አስተላለፈ፡፡
ይህንን አስከፊ ዜና የሠማው ህዝቡም ከየመደብሮች የቀሩትን ፖስታ ለመግዛት ሰልፍ ያዘ፡፡ ህዝቡ በወቅቱ ፖስታ ከዱቄት እንጅ ከዛፍ እንደማይመረት ለማገናዘብ አልቻለም ነበር፡፡ ከጥቂት ሠዓታት በኃላ ጣቢያው ዕለቱ ኤንሪትል ዘፈል መሆኑን ሲገልፅ ህዝቡ በራሱ ላይ ስቋል፡፡


******************************************************************
ምንጭ:--በታከለ ኩዳን/ቁምነገር መፅሄት ቅፅ 2 ቁጥር 14 መጋቢት 1995 ዓ.ም/

Thursday, March 27, 2014

ዋናው ነገር ጤና


የነጭ ሽንኩርት 34 የጤና በረከቶች

1. የደም ቅዳ (Artery) ግድግዳዎችን በማደደርና በማጥበብ የሚታወቀውን አቲሮስክሊሮሲስ የተሰኘውን በሽታ ይዋጋል፡፡ 
2.የኮልስትሮል መጠንን ይቀንሳል፡፡
3. የደም ግፊትን ይቀንሳል፡፡
4. ጉንፋንንና ሌሎች መሰል የላይኛው የመተንፈሻ አካላት በሽታዎችን ይከላከላል፣ ይፈውሳልም፡፡ 
5.የባክቴሪያ መራባትንና መዛመትን ይከላከላል፡፡
6. ቲቢን ለማከም ይረዳል፡፡
7. መግል የቀላቀለ ቁስልን ለማከም ይረዳል፡፡
8. የብልት በሽታ (Trichomoniasis) የሚሰኘውን የአባላዘር በሽታ ለማከም ይረዳል፡፡ 
9.በህዋሳት ውስጥ የሚካሄደውን ዋንኛውን ኬሚካላዊ ውህደት (Metabolism) ያነቃቃል፡፡ 
10.ከነቀርሳ (Cancer) ዓይነቶች አንዱ የሆነውን የኮለን ካንሰር መስፋፋትን ይገታል፡፡ 
11. የሐሞት ከረጢት ካንሰር መስፋፋትን ይገታል፡፡ 12. የፊንጢጣ ካንሰር መስፋፋትን ይገታል፡፡ 
13. የጡት ካንሰር መስፋፋትን ይገታል፡፡
14. በወንዶች ላይ የሚከሰተውን የፕሮስቴት ካንሰር መስፋፋትን ይገታል፡፡ 
15. ለምግብ መፈጨት ሂደት ይረዳል፡፡
16. በልጆች ላይ የሚከሰተውን የማያቋርጥ ሳል ለመከላከል ይረዳል፡፡ 17. የእርጅናን ሂደትን በተወሰነ መልኩ ለመግታት ይረዳል፡፡
18. የአንጀት ውስጥ ትላትልና ተህዋስያንን ይገድላል፡፡
19. የምግብ ፍላጎትን ይጨምራል፡፡
20 በአብዛኛው በእድሜ ሳቢያ የሚከሰተውን ካታራክት የተሰኘውን የአይን እይታ ችግርን ለማከም ይረዳል፡፡ 
21 . የደም መርጋትን ለማሟሟት ይረዳል፡፡
22 . ለስኳር በሽታ ህክምና ይረዳል፡፡
23 . የጥርስ ህመም ስሜትን ይቀንሳል፡፡
24 . የእንቅልፍ እጦት ችግር ላለባቸው ይመከራል፡፡
25 . የሰውነትን የበሽታ መከላከል አቅም ይገነባል፡፡
26 . የእርሾ ኢንፌክሽንን ለማከም ይረዳል፡፡
27 . የመገጣጠሚያ አካላት በሽታን ለማከም ይረዳል፡፡
28 . በባክቴሪያ አማካኝነት የሚከሰተውን ስታፊሎኮካል ኢንፌክሽንን ለማከም ይረዳል፡፡ 
29 . ኪንታሮትን ለማከም ይረዳል፡፡
30 . የቆዳ ላይ ብጉንጅና እብጠቶችን ለማከም ይረዳል፡፡
31 . አንዳንድ የቆዳ በሽታዎችን ለማከም ይረዳል፡፡
32 . ለአንጀት ጤንነት ተመራጭ ነው፡፡
33 . ፋይቶንሳይድስ የተሰኘ ኬሚካል የሚገኝባቸው የነጭ ሽንኩርት ዓይነቶች የአስም በሽታን ለማከም ይረዳሉ፡፡ 
34 . አደገኛ የብሮንካይተስ ህመምን ለማከም ይረዳል፡፡

Monday, February 3, 2014

ያልተዘመረለት ጀግና – አብዲሳ አጋ



አብዲሳ አጋ ጣልያን በአድዋ የደረሰበትን ሽንፈት ለመበቀል ባደረገው የ1928ዓ.ም ወረራ ወቅት በምርኮኝነት ጣልያን ተወስዶ ከታሰረ በኋላ የተሰጠውን ብርድልብስ ቀዳዶ በመቀጣጠል በመስኮት በኩል ማምለጡ ጎልቶ የሚወሳለት አርበኛ ነበር። ተሳክቶለት ቢያመልጥ እንግዳ የሆነ አገር እንደሚቀላቀል እና ለሃገሩም እሩቅ መሆኑን እያወቀ እንኳን ነጻነቱን አሳልፎ ላለመስጠት በሚል ብልጠት በታከለበት ሁኔታ ያመለጠው አብዲሳ አጋ አስገራሚ ጀግንነቱን ያሳየው ከእስር ቤቱ ካመለጠ በኋላ ነበር።
በኦሮሚያ ወለጋ የተወለደው አብዲሳ የኢትዮጲያን ጦር የተቀላቀለው በ14 አመቱ ሲሆን ጣልያን ኢትዮጲያን ስትወር አገሩን ለመከላከል በሚደረግ ውጊያ ላይ መሳተፍ ጀመረ። እጅግ ዘመናዊ መሳሪያዎች ከታጠቀው የጣልያን ጦር ጋር በሚደረገው ውጊያ ላይ ባጋጠመው የመቁሰል አደጋ ህክምና ላይ ከቆየ በኋላ አዲስ አበባ ውስጥ ፒያሳ አካባቢ በሚገኝ ቤት በቁም እስር ላይ ነበር። በኋላ ጣልያን ኢትዮጲያን እንዲያስተዳድር በሾመችው ግራዚያኒ ላይ የመግደል ሙከራ ከተደረገ በኋላ አብዲሳ አጋ እና ሌሎች 37 የሚሆኑ የቁም እስረኞች ተጠርጣሪ ተብለው በከባድ ስቃይ እስር ቤት ከቆዩ በኋላ በወቅቱ የጣልያን ግዛት በነበረችው በሱማሊያ በኩል ወደ ሲሲሊ ተወስዶ በጣልያን አገር የጦር እስረኛ ተደረገ። በእስር ቤት ጠባዎች ጥብቅ ቁጥጥር የሚደረግበት አብዲሳ እዛው ታስሮ የሚገኝ ሁሊዮ የተባለ የዩጎዝላቪያ ምርኮኛ በጋራ እቅድ በማውጣት ከእስር ቤት ማምለጥ ቻለ።  ከእስር ካመለጡ በኋላ ከፋሺስት ጣልያን ወታደሮች በመደበቅ እና በመሸሽ ፋንታ በአብዲሳ መሪነት እና እቅድ አውጪነት በሌሊት ታስረው ወደነበረበት እስር ቤት ተመልሰው ጠባቂዎቹ ላይ ጥቃት በመፈጸም የታሰሩትን እስረኞች በሙሉ ነጻ በማውጣት የኢትዮጲያውያንን ጀግንነት በአድዋ ብቻ ሳይሆን በጣልያን ምድርም ያስመሰከረ ድንቅ ተዋጊ ነበር።
የአብዲሳ ጀግንነት በዚህ አላበቃም ከእስር ቤት ያስመለጧቸውን ሰዎች በማሰባሰብ የራሱን ጦር ካደራጀ በኋላ ጣልያኖችን በገዛ አገራቸው ያንቆራጥጣቸው ገባ። ከአድዋ ጀምሮ የኢትዮጲያውያንን ወኔ የተረዱት ጣልያኖች የአብዲሳን ጦር በፍርሃት ያዩ የነበረ ሲሆን በተለያዩ ቦታዎች ከጣልያን ጦር ጋር በመዋጋት ብዙ ድሎችን እያስመዘገበ ነበር። ቆራጥነቱን የተረዱት ጣልያኖች የሚያረጉት ግራ ቢገባቸው ከበርካታ ስጦታዎች ጋር ጦሩን ይዞ የጣልያንን ሰራዊት እንዲቀላቀል መማጸን ጀምረው ነበር። ለፋሺስት ጦር መዋጋት አገር መክዳት እንደሆነ አስረግጦ የተናገረው አብዲሳ ትግሉን አፋፍሞ በቀጠለበት ወቅት የሁለተኛው የአለም ጦርነት ተቀሰቀሰ።
የተባበሩት የአሜሪካ እና እንግሊዝ መንግስታት ከጀርመን ጋር ያበረችውን ጣልያንን እየተዋጉ በነበረ ሰዓት ስለ አብዲሳ ዝና ከሰሙ በኋላ ለጦሩ የሚገባውን ድጋፍ በማድረግ የፋሺስት ስርዓቱን ለማዳከም ከሚያግዙ መንገዶች አንዱ ሆኗቸው ነበር። በድጋፉ በመጠናከር ፋሺስቱን ሰራዊት ማርበድበድ የቀጠለው አብዲሳ የጣልያን ጦር ተሸንፎ ዋና ከተማዋ ሮም በአሜሪካን እና እንግሊዝ የሚመራ ጦር እጅ ስር ከወደቀች በኋላ የሚመራቸውን ከተለያዩ አገር የወጡ ወታደሮች በሙሉ ክንዳቸው ላይ የኢትዮጲያን ባንዲራ እንዲያስሩ በማድረግ የሃገሩን ባንዲራ እያውለበለበ ሮም ከተማ ሲገባ በአለም አቀፉ ህብረት ጦር ትልቅ አቀባበል ተደርጎለት ነበር። ከዛም በኋላ ከተጨማሪ ወታደሮች ጋር በአለም አቀፉ ህብረት ስር የሚመራ ጦር መሪ በመሆን ጀርመንን ለማሸነፍ በሚደረገው የመጨረሻ ውጊያ ላይ ተሳትፎ ግዳጁን በሚገባ በመወጣት የኢትዮጲያን ባንዲራ ከእጁ ሳይለይ በርካታ የጀርመን ከተሞችን ነጻ ማውጣት ችሎ ነበር።
ከጦርነቱ መገባደድ በኋላም የእንግሊዝ፣ የካናዳ እና የአሜሪካ መንግስታት ጦራቸውን ተቀላቅሎ እንዲቀጥል በርካታ ጥቅማ ጥቅሞችን አቅርበውለት ነበር። እብዲሳ ግን ኢትዮጲያ ምንም ያህል ድሃ ብትሆንም ህዝቡን እና መንግስቱን ጥሎ እንደማይሄድ አስረግጦ በመናገር ጥያቄውን ውድቅ አደረገ። በዚህ የተናደዱ ምዕራብውያንም በፈጠራ ወንጀል ከሰው ወደ እስር ቤት አስገብተውት ነበር። በኋላም እስሩ ወደ ገንዘብ ቅጣት ተቀይሮ ከተከፈለ በኋላ በክብር ወደ ሃገሩ ሊመለስ ችሏል።
ወደ ኢትዮጲያ ከተመለሰ በኋላ ሰራዊቱን በቅንነት ያገለገለው አብዲሳ በኮረኔልነት ማዕረግ የአጼ ሃይለስላሴ ልዩ ጠባቂ ጦር እየመራ ቆይቶ ንጉሱ ከስልጣን ከወረዱ ከጥቂት አመታት በኋላ ከዚህ አለም በሞት ተለይቷል።  የአብዲሳ አጋን ሙሉ የህይወት ታሪክ በደንብ ማወቅ ከፈለጉ 
 ይችላሉ።

የሃይማኖት አስተማሪዎች በአንድ የስነ ጥበብ ዝግጅት ያደረጉት አዝናኝ ንግግር

በቅርቡ በተዘጋጀ የስነ ጽሁፍ ዝግጅት ላይ የተገኙት የሃይማኖት አስተማሪዎች ከሃይማኖት ውጪ የሆኑ ርእሶች ላይ ሃሳባቸውን ያካፈሉ ሲሆን መጋቢ ሃዲስ እሸቱ ስለ ባህል እና ዘመናዊነት አዝናኝ ንግግር ሲያቀርብ ዲያቆን ዳንኤል ደግሞ አንድ የዩንቨርስቲ መምህር የሚል አነቃቂ ስነ ጽሁፉን አካፍሎ ነበር። ይመልከቱት …
የሃይማኖት አስተማሪዎች በአንድ የስነ ጥበብ ዝግጅት ያደረጉት አዝናኝ ንግግር

Saturday, January 4, 2014

እንኳን ለብርሃነ ልደቱ በዓሉ በሰላም አደረሳችሁ


ገና

***********************
"ታኅሣሥ ገሠገሠ ከተፍ አለ ገና፣
እጠብቅሃለሁ አንተ ልጅ ቶሎ ና፡፡
የታኅሣሥ ትውውቅ በገና ፍቅር፣
ይላል ቅር ቅር፡፡"
ዓመት ጠብቀው፤ ዐውደ ዓመትን ዙረው ከሚመጡት በዓላት አንዱ የገና (ልደት) በዓል ነው፡፡ በያመቱ ታኅሣሥ 29 ቀን ይከበራል፡፡ ሃይማኖታዊ ይዘቱ የክርስቶስ ኢየሱስ 2006ኛ የልደት በዓሉ የሚዘከርበት ነው፡፡
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 29 ቀን 2006 ዓ.ም. የገና በዓል በኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ግብፅ እና በመካከለኛው ምሥራቅና በምሥራቅ አውሮፓ ያሉት ሀገሮች ይከበራል ፡፡

የጁሊያን ቀመር የሚከተሉት ምሥራቅ ኦርቶዶክሳውያን ገናን ሲያከብሩ ዕለቱን ..ዲሴምበር 25.. ብለው ሲሆን፤ ኢትዮጵያና ኤርትራ ታኅሣሥ 29፣ ግብፅ (ኮፕቲክ) ደግሞ ኮያክ 29 ብለው ያከብሩታል፡፡

በ16ኛው ምእት ዓመት ከጁሊያንን ቀመር ተከልሶ የተዘጋጀውን የጎርጎሪያን ቀመር የተከተሉት ምዕራባውያን ደግሞ በነርሱ "ዲሴምበር 25" ባሉት ታኅሣሥ 16 ቀን አክብረውታል፡፡ በዓሉ አንድ ሆኖ የቀኑ ልዩነት የተፈጠረው መሬት ፀሐይን ለመዞር የሚፈጅባት ጊዜ በምሥራቆች 365 ቀን ከ6 ሰዓት ነው በማለታቸው ምዕራቦች ደግሞ 365 ቀን ከ5 ሰዓት 48 ደቂቃ 46 ሰኮንድ ነው በሚል ልዩነት በመፈጠሩ ነው፡፡

"ዮም ተወልደ ቤዛ ኵሉ ዓለም" (ዛሬ የዓለም ቤዛ ተወለደ) እያሉ ኢትዮጵያውያኑ በደማቅ ሥነ ሥርዓት በዓሉን እያከበሩ ነው፡፡ የዛሬውን በዓለ ልደት ለማክበር በመንፈቀ ኅዳር የጀመሩትን ጾም ለ43 ቀኖች አሳልፈዋል፡፡
"ያለም ሁሉ መድኃኒት
ተወለደ በበረት፣
እያሞቁት እንስሳት
ብርሃን ሆነ በዚያች ሌት
ሲዋዥቡ መላእክት
ደስ አሰኙ ለኖሩት" የሚለው ኅብረ ዝማሬ የበዓሉ መገለጫ ሲሆን፤ ቀደም ባለው ዘመንም ተማሪዎች በገና በዓል ፍቅረ ሀገርንም የሚገልጹበት አጋጣሚ ነበር፡፡
"እናታችን ኢትዮጵያ፣
መልካም ቆንጆ ባለሙያ
አቁማለች የውቀት ገበያ፣
ለመንግሥቷ መከላከያ
ሕያው ትሁን ኢትዮጵያ"

በሀገር ውስጥና በውጭ (ድዮስጶራ) በሚገኙ በሁሉም የኢትዮጵያ አብያተ ክርስቲያናት፣ ሌሊቱ ማሕሌት ተቁሞ ቅዳሴ እንዳበቃ፣ የበዓል ፍጻሜ ቢሆንም በተለይ በላሊበላ ግን በተጨማሪ በዕለቱ ጧት ላይ "ቤዛ ኵሉ" የተሰኘው ክብረ በዓል ከአለት ከተፈለፈሉት የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በአንዱ በቤተ ማርያም ካህናቱ ጋራና መሬት ላይ ሆነው ያከብሩታል፡፡

የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶችና ምዕመናን (ነጋድያን-ፒልግሪምስ) ትኩረት የሚስብ ዐቢይ ትርዒት ነው፡፡ የላሊበላው "ቤዛ ኵሉ" አከባበር ትእምርታዊ ነው፡፡ ማሜ ጋር ላይ ያሉት የመላእክት ምሳሌ፣ መሬት ላይ ያሉት ደግሞ የእረኞች ምሳሌ ሆነው ዝማሬውን በሆታና በዕልልታ ያጅቡታል፡፡ የክርስቶስ ኢየሱስን መወለድ መጀመሪያ ያወቁ እረኞች በመሆናቸው በአገር ቤት ትውፊቱ እየተነገራቸው የሚያድጉት እረኞች በተለየ ሁኔታ ያከብሩታል፡፡

የበዓለ ልደቱ ማሕሌቱ በካህናት በሚቀጥልበት ሌሊት ሊቃውንቱ ልደቱን አስመልክተው በየአጥቢያው በቅኔ ማሕሌት ዙርያ ቅኔውን ይዘርፉታል፡፡ አንዱ፣ ከሰባት አሠርት ዓመት በፊት ታላቁ ሊቅ አለቃ ለማ ኃይሉ ወልደ ታሪክ እንዲህ ተቀኝተው ነበር፡፡

"ፍጡራን ላዕለ ፈጣሪ
ኅሊናሆሙ ይግድፉ በሕገ ልቡና ተጽሕፈ
ይእዜሰ እምግብረ ልማዱ ፈጣሪ አዕረፈ
እስመ እንዘ በጎል ይሬኢ ንዴተ ወልዱ ትሩፈ
መንበረ መንግሥት ኢይኅሥሥ ወዘወርቅ አጽፈ
ኅሊናሁ በድንግል ገደፈ፡፡"
(
ፍጡራን ሁሉ፣ ሐሳባቸውን በፈጣሪያቸው
ይጥሉ ዘንድ በሕገ ልቡና ተነግሯል፡፡
ዛሬ ከልማዱ ሥራ ፈጣሪ አረፈ፡፡
የተረፈ የልጁን ድህነት መዋረድ በጎል ሲያይ
የመንግሥት ዙፋን እንዳይሻ የወርቅ ልብስ እንዳይሻ
አሳቡን ከድንግል (ማርያም) ላይ ጣለ፡፡)
ልደት በኢትዮጵያ ዐውድ ከገና ጨዋታ ጋር ተያይዞ በባህላዊ ጨዋታዎች ይከበራል፡፡ የተለያዩ መንፈሳዊና ባህላዊ አከባበር ከሚከበርባቸው ስፍራዎች አንዱ በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው ጃንሜዳ ተብሎ የሚታወቀው ገናን ነው፡፡
በዓሉ በሁለት ቡድኖች መካከል ሚና ለይተው በሚጫወቱበት ጊዜ ተጫዋቾቹም ሆኑ ታዳጊዎች በሆታና በዕልልታ ከሚያዜሟቸው መካከል በዚህ ጽሑፍ መግቢያው ላይ የተጻፈው አንጓ ይጠቀሳል፡፡

የጃንሜዳ ባህላዊና ማኅበራዊ ፋይዳዎች ዙሪያ ጥናት ያደረጉት አቶ አባይነህ ደስታ፣ ጃንሜዳ በከፍተኛ ደረጃ ሕዝብ ተሰብስቦ ከሚያከብራቸው የክርስቲያኖች በዓል ገና እና ጥምቀት ዋነኛ መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡
የገናን ሀገር ባህላዊ ጨዋታን ስንመለከት አስቀድሞ የቡድን አባላት የሚሆኑ ሁለት ሰዎች ይመረጣሉ፡፡ ሁለት ሁለት ተጫዋቾች ወደ አባቶች ይቀርቡና በምርጫው ወደ ቡድን ውስጥ ይገባሉ፡፡ የሚያስፈልገው የተጫዋች ቁጥር ሲሞላ ወገን ወገናቸውን ይዘው በዱላ ቀልጣፋ የሆኑ ተጫዋቾች ጥንጓን ወደፊት እንድትቀጥል ይመቷታል ወይም ይመልሷታል፡፡ ተጫዋቾች ብዙ ጊዜ በጨዋታው ስለሚሰጡ ጥንጓን ከእግር መካከል በገባች ጊዜ ከሰው እግር ጋር ደርበው ስለሚመቱ የእግር መሰበር በዚህም ሳቢያ ወገን ለይተው እስከመፈናከት ይደርሳሉ፡፡ የመኳንንቱም አሽከሮች፣ የንጉሡና የንግሥቲቷ አሽከሮች የጌቶቻቸውን ስም በጉብዝና የሚያስጠሩት በባህላዊው የገና ጨዋታ ነው፡፡  
ጨዋታው በመንደር ልዩነት ከሆነ የታች አምባ ቡድን ሀምሳ ተጫዋቾች ቢሆኑ የላይ አምባ ቡድን ሰባ ሆነው ቢጫወቱ የሚከለክል ደንብ አልነበረም፡፡ ጨዋታው በመጨረሻ ፀብ ስለሚያነሳ ብዙ ጊዜ ጉዳት ያጋጥማል፡፡ ጥንጓም ኃይለኛ ለጊ በመታት ጊዜ ዐይን እስከ ማጥፋት ትደርሳለች፡፡ ተጫዋቾች "በሚና" ብለው በሚጫወቱበት በቆልማማ ዱላ ቢደባደቡም የሚገላግል ዳኛ አልነበረም፤ ጨዋታውን በሚመለከቱ አባቶችም በድብድብ ከመሳቅ በስተቀር ሽምግልናቸው ለገና ጨዋታ አልተለመደም፡፡ "እግር ይብሳል፣ ያንከላውሳል፡፡" እያለ ማስፈራራት፣ ራስን መቀወር ወይም እንቆራቆስ ብሎ እጅና እግርን በዱላው መምታት በገና ጨዋታ የተለመደ ነበር፡፡

የገና ጨዋታ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በሌሎች አገሮች የታወቀውና በኦሊምፒክ የስፖርት በዓል ከሚደረጉ ውድድሮች አንዱ ሆኖ ቆይቷል፡፡ ይህም ጨዋታ ሆኪ በሚል ስም ይጠራል፡፡ ፈረንጆች የፊት አደጋን መከላከያ ዘዴ ይጠቀማሉ፡፡ በኢትዮጵያ ያገር ባህል ገና ጨዋታ በሚደርስ አደጋ ማንም ተጫዋች አይጠይቅም፡፡
በገና ጨዋታ አሸናፊ ለሆኑት ቡድኖች ፊሪዳና ጠጅ ተሰጥቷቸው እየበሉና እየጠጡ፣ እየዘፈኑ ሲሸልሉና ሲያቅራሩ ሜዳውን የጦርነት ድል ያገኙበት ያስመስሉት ነበር፡፡ ከሚዘፍኑትና ግጥሞች ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

"
ማታ ነው ድሌ፣
ይሄ ነው አመሌ፡፡
አሲና በል አሲና ገናዬ፡፡
ኦ! ጉ! አሲና በል አሲና ገናዬ፡፡
ግፋው ግፋው አለኝ እኔ እንደምን ልግፋው፣
የአንድ በሬ ጨጓራ እንደ ቅል የነፋው፡፡
የብብቱ ሽታ፣ የመንፈቅ በሽታ፡፡
የጀርባው መርሬ፣ ያውላል ጥድ በሬ፡፡
ካስር ጋን አተላ፣
አይተርፈው በአንኮላ፡፡
እግርህ የሸረሪት ሆድህ የእንቁራሪት፣
ቀን እንደጠላሁ ና እንዳትመጣ ሌሊት፡፡"
ስድብ ለተራው ሕዝብ ብቻ ሳይሆን በመኳንንቱና በነገሥታቱም ላይ ሊሰነዘር ይችላል፡፡ በሚደርስባቸው ስድብ ግን ምንም ዓይነት ቁጣና ቅጣት አያደርጉም፡፡

"
በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ
በገና ጨዋታ የለም ሎሌ ጌታ፡፡" የሚለው የዘፈን ግጥም ይህን ባህል ይገልፃል፡፡
የገና ጨዋታ ከክርስትና ሃይማኖት በፊት ይዘወተር እንደነበርና በኢትዮጵያ ከታኅሣሥ የመኸር ወቅት ጋር የተያያዘ ባህል እንደሆነ አቶ አባይነህ ያመለክታሉ፡፡ ከበዓሉ ጋር የተያያዘ ብዙ የስነቃል ግጥሞችን ይገኛሉ፡፡

"ታኅሣሥ ገሠገሠ ከተፍ አለ ገና፣
እጠብቅሀለሁ አንተ ልጅ ቶሎ ና፡፡
ይወዘውዘኛል አልጠላኝም ገና፣
ፍቅር ሞገደኛው እየነሳኝ ጤና፡፡
ምግብ አያስበላ አያስለብስ ልብስ፣
ሞገደኛው ፍቅሩ ይዞኝ በታኅሣሥ፡፡
በማለዳ ጀንበር በገና ጨረቃ፣
እኔን እኔን ብላ መጣች ተደብቃ፡፡" ሠናይ በዓል፡፡
**********************************
በሔኖክ ያሬድ
ምንጭ:-http://modersmal.skolverket.se/amhariska/

Tuesday, December 24, 2013

የእንግሊዝኛ - አማርኛ መዝገበ ቃላት አዘጋጅ

                         ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ

                                  (እንግሊዝኛ - አማርኛ መዝገበ ቃላት አዘጋጅ) አረፉ፡፡ 
                         / ነሐሴ 27 ቀን 1922 ዓ.ም.--- ታኅሣሥ 10 ቀን 2006 ዓ.ም./

 በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ (ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ) ለ33 ዓመታት ያገለገሉትና በተለያዩ መጽሐፎቻቸው የእንግሊዝኛ - አማርኛ መዝገበ ቃላትን ጨምሮ ታዋቂ የሆኑት ዶ/ር አምሳሉ አክሊሉ በ84 ዓመታቸው አረፉ::
ከቅርብ ዓመት ወዲህ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት ሕክምናቸውን ሲከታተሉ የነበሩት ዶ/ር አምሳሉ አክሊሉ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ታኅሣሥ 10 ቀን 2006 ዓ.ም. ነው::


የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት የሕዝብ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር የሳይንትፊክ ቡድን ዳይሬክተር ሆነው ለአንድ ዓመት (1954-55) ያገለገሉት ዶ/ር አምሳሉ፣ ከ1955 ዓ.ም. ጀምሮ በጡረታ እስከተገለሉበት እስከ 1985 ዓ.ም. ድረስ በቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲ ከሌክቸረርነት እስከ ተባባሪ ፕሮፌሰርነት ማገልገላቸውን ገጸ ታሪካቸው ያመለክታል:: በተለይ በግእዝ፣ በአማርኛና በዓረብኛ ቋንቋዎች እንዲሁም የኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ታሪክን በማስተማር ይታወቃሉ::
የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሑፍ ትምህርት ክፍል ሊቀመንበር፣ የቋንቋዎች ጥናት ተቋም ዲን፣ የኢትዮጵያ
ቋንቋዎችና ባህሎች አካዴሚ የቦርድ አባልም ሆነው ሠርተዋል:: አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በ1997 ዓ.ም. የፊሎሎጂ (ጥንታዊ ጽሑፎች ጥናት) ትምህርት ክፍል ሲከፈት በድኅረ ምረቃ መርሐ ግብር ስለኢትዮጵያ ፊሎሎጂ፣ ስለግእዝና ዓረብኛ መዋቅር በኮንትራት አስተምረዋል::
ዶ/ር አምሳሉን ስመጥር ካደረጓቸውና ካበረከቷቸው ትምህርታዊ የሕትመት ውጤቶች መካከል 


*‹‹እንግሊዝኛ አማርኛ መዝገበ ቃላት›› (ከጂ.ፒ. ሞስባክ ጋር /1966 ዓ.ም.)፣ 
*‹‹የአማርኛ ፈሊጣዊ አነጋገሮች›› (ከዳኛቸው ወርቁ ጋር/1979 ዓ.ም.) 
*‹‹የእንግሊዝኛና አማርኛ የሳይንስና ቴክኖሎጂ መዝገበ ቃላት›› (ከኢትዮጵያ ቋንቋዎች አካዴሚ ጋር) 
*‹‹ጥሩ የአማርኛ ድርሰት እንዴት ያለ ነው?››  (ከደምሴ ማናህሎት ጋር/1989 ዓ.ም.)፣ 
*‹‹አጭር የኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ታሪክ›› (ያልታተመ)፣
*‹‹አማርኛ-ዓረብኛ መዝገበ ቃላት›› (ከሙኒር አብራር ጋር/1999 ዓ.ም.)፣ 

*‹‹ግዕዝ መማሪያ መጽሐፍ Ge’ez Textbook›› (2003 ዓ.ም.)፣ 
‹‹የአማርኛና ሞክሼ ሆሄያት ጠንቅቆ ያለመጻፍ ችግርና መፍትሔ›› (2002 ዓ.ም.)፣ 
 በጀርመን ሐምቡርግ ዩኒቨርሲቲ በታተሙት ተከታታይ 
*‹‹ኢንሳይክሎፔዲያ ኢትዮፒካ››
እንዲሁም በተለያዩ ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች ጥናታዊ ጽሑፎችን አቅርበዋል::
በቀድሞው አጠራር በወሎ ጠቅላይ ግዛት ደሴ ከተማ
ነሐሴ 27 ቀን 1922 ዓ.ም. የተወለዱት ዶ/ር አምሳሉ፣ ከቄስ ትምህርት ቤት በኋላ መደበኛ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ ቅድስት ሥላሴ ትምህርት ቤት የተከታተሉ ሲሆን፣ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከካይሮ ዩኒቨርሲቲ በነገረ መለኮት (ባችለር ኦፍ ዲቪኒቲ)፣ እንዲሁም ከካይሮው አሜሪካ ዩኒቨርሲቲ ባችለር ኦፍ አርት በተመሳሳይ ዓመት በ1949 ዓ.ም. አግኝተዋል::
የአማርኛ፣ ዓረብኛ፣ እንግሊዝኛና ጀርመንኛ ቋንቋዎች አዋቂ የነበሩት ዶ/ር አምሳሉ፣ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን
ከጀርመን ቱቢንግ ዩኒቨርሲቲ በ1954 ዓ.ም. ሲያጠናቅቁ፣ የመመረቂያ ድርሳናቸውን (ዲዘርቴሽን) የሠሩት በኦገስት ዲልማን የግእዝ መዝገበ ቃላት ላይ ነው::
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል አስተባባሪው ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣
የዶክተር አምሳሉ አክሊሉ ሥርዓተ ቀብር ዛሬ (ታኅሣሥ 13 ቀን 2006 ዓ.ም.) እኩለ ቀን (6 ሰዓት) በየካ ደብረ ሣህል ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ይፈጸማል::

*************************************
ምንጭ:--http://www.ethiopianreporter.com/