ከደራሲያን ዓምባ

Friday, October 2, 2015

የሙዚቃ ጣዕም

በሰባ ደረጃ
ቴዲ አፍሮ /ቴዎድሮስ ካሳሁን

******************
ግጥምና ዜማ፡- ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)
ሙዚቃ ቅንብር፣ ሚክሲንግ፣ ኪቦርድ እና ቤዝ ጊታር፡-  ዳግማዊ ዓሊ
ናሙና ዝግጅት፡-  አብርሃም ዘዉዴ
ክራር፡-  ታመነ መኮንን
ድምጵ ቀረጳ፡-  ክብረት /ኪዮስ
ፕሮዲዩስድ፡-  በቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)
******************************
Teddy Afro's Be Seba Dereja Wins Leza Radio Show Best Single of the Year Award
http://www.diretube.com/teddy-afros-be-seba-dereja-wins-leza-radio-show-best-single-of-the-year-award_16d01931c.html
********************

አርቲስት: ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)
ርእስ: በሰባ ደረጃ [2006]
************************************
ከመኮንን ድልድይ: ከንጨት ፎቁ በላይ
ሲመሽ እንገናኝ
መጣሁ አንችን ብዬ: ሳይከብደኝ እርምጃው
በሰባ ደረጃው
በሳሪያን ኮት ላይ: ያንን ቀጭን ኩታ
ጣል አድርጌ
በመኮንን ድልድይ: ልምጣ በደረጃው
በፒያሳ አርጌ
በፍቅር ማነቂያው: ዶሮ እንዳይል በከንቱ
እሪ አንችን ወዶ
ክራሩን ስትሰሚ: ብቅ በይ ቆሚያለሁ
ከበርሽ ማዶ
ሲመሽ ወደማታ: ማታ ማታ
አቤት ያንቺ ፍቅር ሲበረታ
ሲመሽ ወደማታ: ማታ ማታ
ብቅ በይ ሲገረፍ: ክራር ሲመታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ
አምጧት ከጎኔ: ትቀመጥ
እንጀራ አይቀርብም: ካለወጥ
አቅፎ ገላዋን: አልጠግብ ያለው
ማነው ካላችሁ: ማነው ማነው
ልቤ ልቤ ነው: ልቤ እረሃብተኛው
እሷን ወዶ: ሌት እማይተኛው
ይውጣ ይውጣ: እግሬ ይዛል በርምጃው
ከሷ አይብስም: ሰባ ደረጃው
ዎይ… ዘበናይ: ነይ ዘበናይ
ዘበናይ ዘበናይ
ሲመሽ ወደማታ
ሁሉ ዘግቶ በሩን
ታም ታራም ሳረገው
ብቅ በይ ክራሩን
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
ሳረገው ክራሩን
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
ፀጉሯን ተተኩሳው: እንዳርምዴ ሜሪ
ዘበናይ ናት ፍቅሯን: በክራር ነጋሪ
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
በክራር ነጋሪ
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
ሄዶ ከኮሪያ: ዘማች ሲመለስ
ዘማች ሲመለስ
ያወሳል ናፍቆቱን: ብክራሩ ድምፅ
ብክራሩ ድምፅ
ፍቅርሽ አስጨንቆ: መላዎስ አቃተኝ
መላዎስ አቃተኝ
ተደናበርኩልሽ: ጥይት እንደሳተኝ
ጥይት እንደሳተኝ
ሳተና ነበርኩኝ: ተኳሽ በመውዘሬ
ተኳሽ በመውዘሬ
ለዘበናይ ብቻ: እጄን ሰጠሁ ዛሬ
እጄን ሰጠሁ ዛሬ
ዎይ…ዘበናይ: ነይ ዘበናይ
ዘበናይ ዘበናይ
በሳሪያን ኮት ላይ: ያንን ቀጭን ኩታ
ጣል አድርጌ
በመኮንን ድልድይ: ልምጣ በደረጃው
በፒያሳ አርጌ
እንዳውራ ዶሮ ክንፍ: ኮቴን እየሳብኩት
መሬት ለመሬት
በዞርኩት ገላሽን: ሳትወጣብኝ ፀሐይ
ሳይነጋብኝ ሌት
ሲመሽ ወደማታ: ማታ ማታ
አቤት ያንቺ ፍቅር ሲበረታ
ሲመሽ ወደማታ: ማታ ማታ
ብቅ በይ ሲገረፍ: ክራር ሲመታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ: ማታ ማታ
ማታ ማታ
ሞልቶ ባራዳ: ያርመን ዳቦ
ሳሳ አከላቴ: ሰው ተርቦ
አቅፎ ገላዋን: አልጠግብ ያለው
ማነው ካላችሁ: ማነው ማነው
ልቤ ልቤ ነው: ልቤ እረሃብተኛው
እሷን ወዶ: ሌት እማይተኛው
ይውጣ ይውጣ: እግሬ ይዛል በርምጃው
ከሷ አይብስም: ሰባ ደረጃው
ዎይ… ዘበናይ: ነይ ዘበናይ
ዘበናይ ዘበናይ
አይወጣም ደረጃ: ቢፈጥር ሴሸኝቶ
እንደኔ ካልሄደ: በፍቅር ተገፍቶ
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
በፍቅር ተገፍቶ
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
መድፈሪያሽ ወርቅ ነው
ብርም አይገዛሽ
ልብ የሌለው ሀብል: ግድም አይሰጥሽ
ኬረዳሽ
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
ግድም አይሰጥሽ
ታም-ታራራም ታራራም ታራራም
ካንገትሽ ላይ አርጊኝ
እንደማር ተሬዛ
እንደማር ተሬዛ
ወዲህ ወዲያ እንዳልል
አደብ እንድገዛ
አደብ እንድገዛ
ተከለከለ አሉ: የንጉሥ አዳራሽ
የንጉሥ አዳራሽ
የክት ያለበሰ: አይገባም በጭራሽ
አይገባም በጭራሽ
መጣሁ ከኮሪያ: ይዤልሽ ሰዓት
ይዤልሽ ሰዓት
በፓሪ ሞድሽ ላይ: አምረሽ ታይበት
አምረሽ ታይበት
ዎይ… ዘበናይ: ነይ ዘበናይ
ዘበናይ ዘበናይ
ዘናይ እናናዬ: ተይ አሁን ነይ
አሁን ነይ
ዘናይ እናናዬ: ተይ አሁን ነይ
አሁን ነይ አሁን ነይ
ዘናይ እናናዬ: ተይ አሁን ነይ
አሁን ነይ አሁን ነይ
ዘናይ እናናዬ: ተይ አሁን ነይ
አሁን ነይ አሁን ነይ
************************
ግጥምና ዜማ፡ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)
ሙዚቃ ቅንብር፣ ሚክሲንግ፣ ኪቦርድ እና ቤዝ ጊታር፡ ዳግማዊ ዓሊ
ናሙና ዝግጅት፡ አብርሃም ዘዉዴ
ክራር፡ ታመነ መኮንን
ድምጵ ቀረጳ፡ ክብረት ዘ/ኪዮስ
ፕሮዲዩስድ፡ በቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)
*****************************

‹‹ከመኮነን ድልድይ …ከንጨት ፎቁ በላይ … ሲመሽ እገናኝ ››
(አሌክስ አብርሃም)
****************************************
አንድ ቁመቱ መለል ያለ ወጣት በሳርያን ኮት ላይ ባለቀጭን ጥለት ኩታውን ጣል አድርጎ በሰባ ደረጃ ዱብ ዱብ እያለ ሽቅብ … ቆንጅትን ፍለጋ … ስንጠረጥር በግራ እጁ ክራር ይዟል ….ሰባዋን ደረጃ እንደጨረሰ ተረረም ሊያደርጋት ….እናም የክራሩን ተረረም ቅኔ እንደመጥሪያ ደውል በተጠንቀቅ የምትጠብቅ አንዲት ቆንጁ…ዘበናይ የቤት ልጅ አለች …እዛው አካባቢ …እንግዲህ አስቡት ሲመሽ ወደማታ ሁሉም ዘግቶ በሩን …አንድ ሰው ውጭ ላይ ክራሩን ተረረም ሲያደርገው …አንድ ተረረም ለአድማጮቹ የተለያየ ትርጉም ይሰጣል ….የተኙትና የክራሩ ተረረም ያልገባቸው ‹‹የማነው አዝማሪ በዚህ ምሽት ክራር …›› ይላሉ ….በፍቅር ለምትጠብቀው ኮረዳ ግን (ያውም እንደሜሪ አርሚዴ ፀጉሯን ተተኩሳ) በዚች ምድር ላይ ካሉ ድምፆች ሁሉ ምርጥ የፍቅር ጥሪ ደውል ነው …. አንድን ጉዳይ በተፈጥሮዋዊ እውነቱ ለመስማት ከስጋዊ ጆሮ በላይ ከፍ ያለ የፍቅር ጆሮ ያሻል !
እና ሲመሽ ወደማታ ክራሩ ተረረም ሲል አንዳንዶች ‹‹አዝማሪ ›› እያሉ ሲያሽጓጥጡ አንዳንዶቹም እንቅልፋቸውን ሲለጥጡ …እኛ ግን የፍቅር ቅኔዋ ስለምትገባን ጉዳይ አለንና ሰባውን የፍቅር ደረጃ ወጥተን … ያው ባለቅኔው እንዳለው
አይወጣም ደረጃ ቢፈጥን ሴሸንቶ 
እንደኔ ካልሄደ በፍቅር ተገፍቶ ….
የመኮነን ድልይን የፍቅር ድልድይ እድርገን ‹‹በፍቅር ተገፍተን›› ወደፍቅር ከተሻገርን በኋላ ….ከእንጨት ፎቁ በላይ ተም ተረረም ! በነገራችን ላይ ይሄ ዘፈኑ ውስጥ የምትሰሙት አፍቃሪ ገፀ ባህሪ ተራ ሰው እንዳይመስላችሁ …ሰባ ደረጃን ከመውጣቱ በፊት …ተረረም ከማድረጉም በፊት …ልጅቱ ክራሩን ሰምታ ከመውጣቷ በፊት ሳሪያን ኮቱን ለብሶ ለቆንጅትም የእጅ ሰዓት ስጦታ ይዞ ከመከሰቱ በፊት …ኮሪያ ነበር!! ምን ሊሰራ ኮሪያ ሄደ ማለት ተገቢ ነው …የቴዲ አፍሮ ዘፈኖች ውስጥ የሚከሰቱ የፍቅር ገፀ ባህሪያት ተራ አፍቃሪዎች አይደሉም ….ወደፊት እመለስበታለሁ ወንዱም ሴቱም በቴዲ ዘፈኖች ውስጥ ያሉ ገፀ ባህሪያት የአገርና የወገን አደራን ጥንቅቅ አድርገው የሚወጡ አገር ወዳድ መሆናቸውን ታያላችሁ …..
እና ይሄንኛውም አፍቃሪ ኮሪያ ከፍ ባለ የአገር ሃላፊነት ላይ ከርሞ አረፍ እንኳን ሳይል መሳሪያውን አስቀምጦ ክራሩን ያነሳ ትንታግ ወጣት ነው …. ቆይማ ይሄ ምርጥ አፍቃሪ፣ ይሄ የሳሪያን ኮት ለባሽ ለምን ኮሪያ እንደሄደ ላስታውሳችሁ ….ከዛ በፊት ግን ጥያቄ... ከእናተ መካከል የሳሪያን ኮት የማያውቅ ካለ እጁን ያውጣ …እሽ ሳሪያን ኮት ማለት ከታች ፎቶውን የለጠፍኩላችሁ ነው …ከዛ በዚህ ኮት ላይ ባለቀጭን ጥለት ኩታ ጣል አድርጎበት ማለት ነው ….ኩታ ምንድነው የሚል የለም መቸም (አሁንስ አበዛችሁት ) እሽ ኩታ የማያውቅ ሰው ካለ ቢፈልግ ከቤቱ ወጥቶ እናቶችን ይመልከት ዘመናዊ እናቶች ያሉበት ሰፈር ያለ ሰው ሽሮ ሜዳ ይሂድና ኩታ አይቶ ይመለስ !!
እንግዲህ ከ1945 ዓ/ም ማለትም ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት መጠናቀቅ ቀደም ብሎ .... አሁን የምናውቃቸው ዓለም ላይ አንዴ ኒውክሌር አንዴ ምናምን እያሉ ‹‹የሚያነጅቡት›› ሁለቱ ኮሪያዎች (ሰሜንና ደቡብ ኮሪያ ) …በጃፓን ቅኝ ግዛት ስር ነበሩ…ጃባን እንአብረት ቀጥቅጣ ገዝታቸዋለች ! ታዲያ ይህ ቅኝ ግዛት ይበቃል ያሉ ወገኖች አገራቱን ከጃፓን ቅኝ ግዛት ነፃ ለማድረግ ጦር አዘመቱ የቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት እና ቻይና ከሰሜን ኮሪያ ጎን ፤ አሜሪካ እንግሊዝና ፈረንሣይ ደግሞ ከደቡብ ኮሪያ ጋር ተሰልፈው ቅኝ ገዢዋን ጃፓን ከኮሪያ ምድር ለማባረር ዘመቱ …ዘመቻው ሰምሮላቸው በሰሜኑ በኩል የተሰለፈው ኃይል ቅኝ ገዥዋን ጃፓንን ወደ ደቡብ ….በደቡብ በኩል የተሰለፈው ኃይል ደግሞ ወደ ሰሜን አቅጣጫ እያባረረ ሄደው ሁለቱን ኮሪያዎች በሚያለያየው 38ኛው በሚባለው መስመር ላይ ደረሱ ….አሁን ጃፓን የለችም …ነፃ እናውጣ ብለው የዘመቱት አገራት ተፋጠጡ ይታያችሁ በሰው አገር !
ይህ ከሆነ በኋላ በደቡብና በሰሜን የተሰለፉት አገሪቷን ለቅቀው እንዲወጡና ሁለቱ ኮሪያዎች በሚፈልጉት መልክ ይተዳደሩ የሚል ስምምነት ላይ ተደረሰ …የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ነበር ውሳኔውን ያሳለፈው … በደቡብ የተሰለፈው የውጭ ኃይል ማለትም እንግሊዝ ፈረንሳይና አሜሪካ በስምምነቱ መሠረት ለቀው ወጡ ….በሰሜን የተሰለፉት ቻይናና ሶቬት ግን ሲቆዩ ደንበሩ የራሳቸው መሰላቸው መሰል ለቀን አንወጣም ብለው ሙጭጭ !! እንደውም ጭራሽ መስመሩን አልፈው ደቡቦቹ የለቀቅትን አንዳንድ ቦታዎች በጉልበት ያዙ 
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተበሳጨ ‹‹እንዴ የሰው አገር ልቀቁ እንን ‹ሸም› ነው …አላቸው …እናጅሬ በስሚያችን ጥጥ ነው !! የሰሜኑ ኃይል ወርሮ ከያዘው የደቡብ ክልል ወጥቶ ቀድሞ ወደነበረበት ቦታ እንዲመለስ ውሳኔ አስተላለፈ ….ይሁንና እነዛንኞቹ ብንሞት ወደነበርንበት አንመለስም ማነው ወንዱ የሚያስለቅቀን አሉ!! ስለዚህ የሰሜኑ ሃይል ደቡቡን የያዙትን በሃይል እንዲያስለቅቅ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ወሰነ!
ታዲያ እነዚህን የሰው መሬት ይዘው አንለቅም ያሉ ጥጋበኞች ለማስተንፈስ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን አላማ የሚደግፉ አገራት ወታደር እንዲልኩ ሲጠየቁ በወቅቱ ከአፍሪካ ብቸኛ የሆነው እና ጀግናው የቃኘው ሻለቃ ሠራዊትን ከ1943 ዓ.ም. እስከ 1945 ዓ.ም. ድረስ በተባበሩት መንግስታት እዝ ስር ሁኖ ወደኮሪያ ዘመተ ...መዝመት ብቻ አይደለም ኢትዮጲያው ቃኘው ሻለቃ ጦር ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሌሎች አገራት ዘማቾች ጋር በመሆን እነዛን ጥጋበኞች ጠራርጎ እያንከሳከሰ ከምድረ ኮሪያ አስወጣቸው !!

ያኔ ኢትዮጲያችን ያዘመተችው ጦር 6037 (ስድስት ሽ ሰላሳ ሰባት) ወታደሮች እንደነበር ነው አንዳንድ የታሪክ መዛግብት የሚነግሩን …ከእነዚህ ውስጥ 120 ወታደሮቻችን ሲሰው 530 ወታደሮች ቆስለዋል …ታዲያ ያኔ አለምን ያስደመመው የኢትዮጲያዊያን ጀግንነት ምን መሰላችሁ ኢትዮጲያዊ ወታደሮች ቢሞቱ እጃቸውን አይሰጡም ….እንኳን በህይዎት ቀርቶ የቆሰሉና የተሰው ጓደኞቻቸውንም አሳልፈው አይሰጡም ነበር ኢትዮጲያዊያኑ ወታደሮች ! ጦርነቱ ተጠናቆ የእስረኛ ልውውጥ ሲደረግም የታየው ይሄ ነው ኢትዮጲያ የተማረከ አንደም ወታደር አልነበራትም !!አንድም !! ልውውጡ እንዴት መሰላችሁ ….በዚህ በኩል የየአገራቱ ባንዲራ ይተከልና የተማረከው ወታደር ሲለቀቅ ባንዲራው አጠገብ ይቆማል …ታዲያ ሁሉም ባንዲራወች ስር በመቶና በሽ የሚቆጠር እስረኛ እንደንብ ሲሰፈር የኢትዮጲያ ባንዲራ ብቻዋን በክብር ስትውለበለብ ነበር ..!! በቃ ኢትዮጲያዊ እጁን አይሰጥማ !!

እንግዲህ የዛሬዋ ደቡብ ኮሪያ እንዲህ ወታደሮቻችን ከቀን ጅቦቹ ወራሪዎች ታደጓት አገር ናት …በደም የተሳሰርን ህዝቦችም ሁነናል !! ወደቴዲ አፍሮ ስንመለስ እንግዲህ ይሄ ሰባ ደረጃ ላይ ክራሩን ተረረም ሲያደርግ ያየነው ወታደር ከእዛ አለም አቀፍ እሳት እጁን ጠላት ሳይነካው ሃሎቹን አፈር ከድቤ አስበልቱ የተመለሰ ትንታግ ከአገሩ አልፎ የሰው አገር ድንበር አስጠብቆ የተመለሰ ጀግና ነው …ስንቱን አገር አዳርሰው የመጡ ወላፈን እግሮች ሰባ ደረጃን ያውም በፍቅር መውጣት ምናቸው ነው ….ይሄ ሰው ድል ካደረገም በኋላ ጀብዱውን እያወራ መሳሪያ ተሸክሞ የሚጃጃል በጠብመንጃው የሚመካ ሰው አልነበረም ….በቦታው ጠላትን አገላብጦ ሲመለስ መውዚሩን አስቀምጦ ስለፍቅር ክራሩን ይዞ ተረረም ! ይታያችሁ የኢትዮጲያ ወታደር ለጠላቱ ቢሞት እጅ አይሰጥም ብያችኋለሁ …ለፍቅር ግን ….እንዲህ አለ ቴዲ …
ሳተና ነበርኩኝ ተኳሽ በመውዚሬ 
ለዘበናይ ብቻ እጀን ሰጠሁ ዛሬ !!
ስለፍቅር እጅ መስጠት ለፍቅር ሰዎች ብቻ የተሰጠ ፀጋ ነው !በፍቅር ጦርነት የፍቅር ባንዲራችን ስር ተማርኮ መቆምም ውርደት አይደለምና …ገጭ ያውም ከወታደራዊ ሰላምታ ጋር፡) ጃ ….ወደፊት ብያለሁ !! የመውዚርም ፎቶ ያውላችሁ ከታች ….የኮሪያም ዘማቾች ለፍቅረኞቻቸው ያመጡላቸው ከነበሩት ሰዓቶች የአንዷ ፎቶ ይቻትላችሁ !
መጣሁ ከኮሪያ ይዠልሽ ሰዓት 
በፓሪሞድሽ ላይ አምረሽ ታይበት …..አይደል ያለው …ሃሃ እንግዲህ የቴዲን ‹‹ ሰባ ደረጃ ›› ባለፍ ገደም እንዲህ አየሁት !
*****************************************************************************

ቴዲ አፍሮ በሰባ ደረጃ ነጠላ ዜማ ማህበራዊ ድረገጾችን ተቆጣጠረ
*****************************************
ድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) “በሰባ ደረጃ” በሚል ስም ሰሞኑን የለቀቀው ነጠላ ዜማ በተለይ እንደፌስ ቡክ ባሉ ማህበራዊ ድረገጾች ላይ ከፍተኛ አድናቆትን በማግኘት ላይ እንደሚገኝ የሚሰጡ አስተያየቶች አመለከቱ።
     ቴዲ ነጠላ ዜማውን በዩቲዮብ ለተለቀቀ በኋላ የተለያዩ የኢትዮጵያዊን ድረገጾች የተቀባበሉት ሲሆን በፌስቡክ ላይ በሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵዊን ዘፈኑን መውደዳቸውን ለመግለጽ “like” በማድረግ አድናቆታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።
     ደራሲና ገጣሚ በዕውቀቱ ሥዩም በፌስቡክ ድረገጽ በሰጠው አስተያየት “ሣልሳዊ ቴዎድሮስ ወይም “ቴዲ አፍሮ” በሰባ ደረጃ የተባለ(ች) ነጠላ ዘፈን ለቆልናል። “በሰባ ደረጃ”ን እኔ ስሰማው እልም ያለ የፍቅር ዘፈን ነው። ፍቅርን ልዩ በሆነ ቦታና ልዩ በሆነ ሥፍራ የሚያሳይ ዘፈን። በአማርኛ ዘፈን ባህል ውስጥ ቦታን ማስጎብኘት የተለመደ ነው። “የሐረር ልጅ ነች ወጣቷ/ጀጎል ነው ቤቷ” አይነት ዘፈን ሞልቶናል። አብዛኛው ያገራችን ዘፋኝ፣ ያስጎብኝነት ሚናም ደርቦ ሲጫወት ኖሯል። በዚህ ምክንያት ተፈቃሪዋ ሴት ሁሌም ከታሪካዊ ቦታ አጠገብ ለመወለድ ትገደዳለች። ቴዲ በዚህ ዜማው ባልተሄደበት መንገድ ሄዷል። ሲጀምር፣ እዚህ ግባ የማይባል፣ ለዓይን የማይሞላ ቦታ መረጠ። ብዙ ጊዜ፣ ታሪካዊ ቦታ ሲባል፣ አክሱም ላሊበላ፣ ፋሲል ሶፍኡመር ጀጎል እንላለን። ካሜራው በኒህ ቅርሶች ላይ አፍጥጦ ኖሯል። ታሪክ አክሱም ላይ ጀምሮ ጀጎል ላይ የተጠናቀቀ ይመስል። ብዙዎቻችን በሸገር ላይ አድልኦ ስንፈጽም ኖረናል። አዲስ አበባ ለአቅመ ቅርስ የምትበቃ ከተማ አትመስለንም። ሸገር ታሪክ ሲሠራባትና ሲሠራላት እንደኖረች አናውቅም። ወይም ለማወቅ አንፈልግም። ቴዲ ይህንን እይታ ቀየረው” ብሏል። 
     አያይዞም “ሁለተኛ፣ ከላይ የጠቀስኳቸው ቅርሶች የጌቶች መታሰቢያ ናቸው። የምድራዊና ሰማያዊ መሪዎችን የሚወክሉ ናቸው። የስም የለሹን፣ የተርታውን ሰው ኑሮ የሚያሳዩ ቅርሶች ግን ደምቀው አልወጡም። አይተን እንዳላየን፣ ቸል ብለናቸው ቆይተናል። ቴዲ ግን ማንም ሲወጣበትና ሲወርደበት ለኖረው አንድ መንገድ ዘፈነለት። መዝፈን ቢሉህ ዝም ብሎ መዝፈን ብቻ አይደለም፤ አንድ ውብ የሆነ የፍቅር ታሪክ ተረከበት። ነጠላ ዜማው ከተለቀቀበት ጊዜ አንስቶ ሰባ ደረጃን በድሮ ዓይናችን አናየውም። አሪፍ ጥበብ ዓይን ገላጭ ነው የሚባለው ለዚህ ነው።
     ሦስተኛው ነጥብ፣ ዘፋኞች ልዩ ቦታን ሲያሳዩ ኖረዋል። ቴዲ ደግሞ አንድን ልዩ ዘመን ለማሳየት ሞክሯል። የቴዲን ዘፈን ስሰማ፣ በካሳሁን ግርማሞ ዘመን የኖረ አንድ ሮሚዎ ይታየኛል። ሸዋ ዳቦ ሳይቋቋም፣ ከአርመን ሱቅ ፉርኖ በሚሸመትበት ዘመን፣ ምኒባስ ሳይገባ፣ ሰዎች ሴቼንቶ የሚሳፈሩበት ዘመን፣ ከጄኔራሎች በላይ ሴቼንቶ ነጂዎች ስመጥር የነበሩበት ዘመን፣ ሴቶች የጥላቸውን ቁመት አይተው ሰአት ከመገመት ወጥተው፣ ክንዳቸው ላይ ሰአት ማሰር የጀመሩበት ዘመን -
     በዚያ ዘመን የኖረ አፍቃሪ ይታየኛል። አንድን ልዩ ዘመን በሲኒማና በልቦለድ ማሳየት የተለመድ ነው። በጣም አጭር ቆይታ ባለው ዘፈን ውስጥ ዘመንን ለማሳየት በመሞከር ግን ቴዲ ፋና -ወጊ ይመስለኛል።
     ዜመኛ ስላልሆንሁ ስለቴዲ ዜማ ምንም ማለት አልችልም። ያም ሆኖ ፣ግጥሙ የተዋጣለት እንደሆነ መመስከር እችላለሁ። አንድ ቦታ ላይ ‹‹አንደ አርሚዴ ሜሪ›› የሚል ሐረግ ሰምቻለሁ። ዜመኛው፣ ሜሪ አርምዴን፣ አርምዴ መሪ ብሎ መጥራት የገጣሚነት ነጻነቱ ይፈቅድለታል። ገጣሚ እንደ ህጻን ልጅ፣ እንደ እብድና እንደ ቅዱሳን ከቋንቋ ሕግ በላይ ነው። እንደ ጋዜጠኛ፣ በሰዋስው ህግ አይታሠርም። እንዲያውም ሳይራቀቁ መግጠም፣ ፈሳሽ ውስጥ ሳይገቡ መስጠም አይታሰብም። በነገራችን ላይ በድሮ ዘመን በኢትዮጵያ የአባት ስም ከልጅ ስም ቀድሞ ይጻፍ ነበር።ቴዲን ትውፊትም ያግዘዋል ለማለት ፈልጌ ነው” ሲል አድናቆቱን ጽፎአል። 
     ትብለጥ በሚል ስም የምትታወቅ አድናቂ “ለእኔ ሁሌም ቴዲ አዲስ ነው። እግዚአብሄር ይባርከው” በማለት አድናቆቷን ሰጥታለች።
     አንዳንድ የማህበራዊ ገጽ ታዳሚዎች ቴዲ በተለይ ግጥም በራሱ ብቻ እየሠራ የመምጣቱ ጉዳይ ጥበቡን ሊጎዳው ይችላል በሚል ሥጋታቸውን ጽፈዋል።
**************************************************************************
ምንጭ:----https://www.facebook.com/alex.abreham.31/posts/1640063316276878
         ----http://ethiozeima.com/tag/teddy-afro-lyrics/
        ----http://www.addislive.com/teddy-afro-beseba-dereja/
       ----http://www.sendeknewspaper.com/news-sendek/item/

Tuesday, August 25, 2015

ፋኖስና ብርጭቆ

 
 
 
 
አንድ የፋኖስ መብራት በግብሩ የኮራ፤
እንዲህ ሲል ተጣላ ከብርጭቆ ጋራ፡፡
‹‹እኔ ነኝ መብራቱ ብርሃን የምሰጥ፤
ጨለማን አጥፍቼ የምገላልጥ፡፡
አንተ ግን ከፊቴ እንዲህ ተደንቅረህ፤
ዙሪያዬን ከበኸኝ እንዲያው ተገትረህ፡፡
አልገባኝም ከቶ የምትሰራው ስራ፤
ብርሃኔ ሩቅ ደርሶ ደምቆ እንዳያበራ፤
አንተን ፈጠረብኝ መንገድ የምትዘጋ፡፡
እንቅፋት እየሆንክ ስራዬን አታጥፋ
ገለል በል ከፊቴ ብርሃኔ ይስፋፋ፡፡››
‹‹አገልግሎቴማ ከሆነብኝ ጥፋት፤
እውነት ላንተ ከሆንኩህ እንቅፋት፡፡
ልሂድልህ›› ብሎ ሲለቅለት ቦታ፤
ከጎን የነፈሰ የንፋስ ሽውታ፣
መጣና መብራቱን አጠፋው ባንዳፍታ፡፡
አጭር እየሆነ ተመልካችነቱ፣
መለየት አቅቶት ጥቅሙን ከጉዳቱ፣
እወቁኝ እወቁኝ እያለ ሲነሳ
ሰውም እንደዚሁ ያመጣል አበሳ፡፡

(/ ከበደ ሚካኤል)

ታላቁ ደራሲ ብርሃኑ ዘሪሁን ከ1925-1979

ከ1925-1979 ዓ. ም.
==============
ኢትዮጵያ ውስጥ በ1925 ዓ.ም አንድ ታላቅ ሰው ተወለደ። ይህ ሰው እያደገ ሲመጣ የብዙ ሚሊዮን ህዝቦችን ታሪክ፣ ባህል፣ እምነትና አስተሳሰብ የሚገልፅ ደራሲ ለመሆንም በቃ። ብዕሩ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ላይ በሰፊው ያተኩራል። የዚህችን ሀገር ታላላቅ ጀግኖች ታሪክ እያነበበ እና እየመረመረ ለትውልድና ለእናት ምድራቸው ያበረከቱትን አስተዋፅኦ ውበትና ለዛ ባላቸው የገለፃ ጥበቦቹ እየፃፈ የሚሊዮኖችን መንፈስ ሲያረካ ኖሯል። ኢትዮጵያም ታላላቅ ደራሲዎቿን ማነሳሳት ስትጀምር ስሙ እና ተግባሩ ከፊት ከሚሰለፉት የብዕር አርበኞች መካከል ያደርገዋል። አንዳንድ ሃያሲያን ደግሞ የተዋጣለት የድርሰት ገበሬ ነው ይሉታል። በኢትዮጵያ ሥነ-ፅሁፍ ታሪክ ውስጥ ለዘላለም እንደ ከዋክብት ሲያበሩ ከሚኖሩት ደራሲያን እና ፀሐፊ- ተውኔቶች ውስጥ ታላቁን የሊትሬቸር ሰው ብርሃኑ ዘሪሁንን በጥቂቱ አነሳሳላችኋለሁ።
ብርሃኑ ዘሪሁን የተወለደው ድሮ የበጌምድር ጠቅላይ ግዛት ርዕሰ ከተማ በሆነችው እና በተለይም የ17ኛው እና የ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የስልጣኔ ማዕከል እንደነበረች በሚገለፅበት በሰሜናዊቷ ክፍለ -ግዛት በጎንደር ከተማ ነው። ዘመኑም 1925 ዓ.ም ነበር። አባቱ መሪ ጌታ ዘሪሁን መርሻ የሚባሉ ሲሆን እናቱ ደግሞ ወ/ሮ አልጣሽ አድገህ ይባላሉ። አባቱ መሪ ጌታ ዘሪሁን የቤተ-ክህነት ሰው ስለነበሩ እና በዘመናቸውም የተማሩ ስለሆኑ ለልጃቸው ትምህርት የሚጨነቁ ነበሩ። እናም አራት ዓመት ሲሆነው እቤት ውስጥ ከርሳቸው ዘንድ የሚማረው ትምህርት ተጨምሮ የቤተ-ክህነትን ትምህርት ተማረ።
ብርሃኑ ዘሪሁን ጎንደር ውስጥ የሚሰጠውን የቤተ-ክህነት ትምህርት ከተከታተለ በኋላ ወደ ዘመናዊ ት/ቤት ገባ። ይህ ዘመናዊ ት/ቤት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ት/ቤት በመባል ይጠራ ነበር። ብርሃኑ ዘሪሁን የሀገሩ ኢትዮጵያን ባህላዊ፣ ታሪካዊና ኃይማኖታዊ ትምህርቶችን በቤተ-ክህነት ውስጥ ከተከታተለ በኋላ ወደ ዘመናዊ ት/ቤት ሲገባ ልዩ ተሰጥኦው ብቅ አለ። ይህም አንባቢነት ነው። ፈረንጆቹ “Book Worm” እንደሚሉት መፅሐፍን የሚያነብ ብቻ ሳይሆን እንደ ምግብም የሚጠቀምባቸው አይነት ሰው እንደነበር የህይወት ታሪኩ ያወሳል።
ብርሃኑ ዘሪሁንን ቀልቡን ከሚከቡት ታሪኮች መካከል ደግሞ የኢትዮጵያ ታሪክ ነው። ኢትዮጵያን በመፃህፍቶቿ አማካይነት እያነበባት አወቃት። እርሱ ያልነበረበትን ዘመን በሰፊ ንባቡ እና ጠያቂነቱ የማንነቱን ክፍተት ሞላው። እናም ሙሉ ኢትዮጵያዊ እየሆነ መምጣት ጀመረ።
የብርሃኑ ዘሪሁንን ቀልብ ከሳቡት ታላላቅ መፃህፍት ውስጥ ደብተራ ዘነብ የፃፏቸው ታሪኮች ናቸው። አንደኛው የአፄ ቴዎድሮስ ታሪክን የሚያወጣው መፅሀፍ ነው። ደብተራ ዘነብ በቴዎድሮስ ቤተ-መንግስት ውስጥ የነበሩ እና ከቴዎድሮስ ጎን የማይጠፉ የዚያን ዘመን ሊቅ ብሎም ፈላስፋ ናቸው። ታዲያ እርሳቸው የፃፉትን የአፄ ቴዎድሮስን ታሪክ ብርሃኑ ዘሪሁን ይወደው ነበር። ከዚህ መፅሀፍ በተጨማሪም ደብተራ ዘነብ “መፅሀፈ ጨዋታ ስጋዊ ወመንፈሳዊ” የተሰኘች መፅሐፍ አለቻቸው። ይህች መፅሃፍ ሃይማኖት ላይ መሰረት አድርጋ የተዘጋጀት ከኢትዮጵያ የፍልስፍና ጽሁፎች መካከል አንዷ ናት። ብርሃኑ ዘሪሁን ይህችን መፅሀፍ የመፅሀፎች ሁሉ ቁንጮ አድርጓት በየጊዜው ያነባት ነበር። በነገራችን ላይ ይህች መፅሃፍ ጨዋታ ስጋዊ ወመንፈሳዊ በውስጧ ምን ቢኖር እንዲህ የተወደደችው ለሚል ሰው ሁለቱን ነጥቦች ብቻ ጠቅሼ ልለፍ።
መፅሃፏ በዋናነት አላማዋ ሃይማኖትን ማስተማር ቢሆንም፣ የተጻፈችበት ቴክኒክ ግን ፍፁም በተለየ አቀራረብ ነው። ለምሳሌ ፈጣሪን የምትወቅስ እየመሰለች የፈጣሪን ታላቅነት የምታስተምር ናት። እንዲህ የሚል ሃሳብ አለባት “እየሱስ ስራብ አላበላችሁኝም፣ ስጠማ አላጠጣችሁኝም፣ ስታረዝ አላለባሰችሁኝም ይለናል። ለመሆኑ ከርሱ የበለጠ ሃብታም አለ ወይ? ለምን ይጨቀጭቀናል. . .” እያሉ ደብተራ ዘነብ ጽፈዋል። የደብተራ ዘነብ አፃፃፍ በዚህ ብቻም አያቆምም። እንዲህም የሚል ሃሳብ ያንፀባርቃል። “እንደ አይሁድ ጅል አላየሁም” የአለሙን ጌታ በ30 ዲናር ሸጠው። ወየሁ እኔ ባገኘሁት” እያለ ከተለመደው የስብከት መንገድ ወጥቶ ሌላ የአፃፃፍ እና የአተያይ መንገድ የከፈተ መጽሐፍ ነው። ብርሃኑ ዘሪሁን ደብተራ ዘነበን አእምሮው የተሳለ ፈላስፋ ይላቸው ነበር። እናም ደብተራ ዘነብ የብርሃኑ ዘሪሁንን አእምሮ ገና በልጅነቱ ስለውለታል ማለት ይቻላል።
በነገራችን ላይ ደብተራ ዘነብ የአፄ ቴዎድሮስን ልጅ ልዑል አለማየሁን በቤት ውስጥ የሚያስተምሩ መምህርም ነበሩ።
ብርሃኑ ዘሪሁን በንባብ ልምዱ ላይ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች ከሚላቸው መካከል ነጋድራስ /ፕሮፌሰር/ አፈወርቅ ገ/እየሱስን ነው። እርሳቸውም በኢትዮጵያ የታሪክ እና የልቦለስ ጽሁፍ ውስጥ ከከፍተኛ ተዕዕኖ ፈጣሪ በመሆናቸው የብርሃኑ ዘሪሁንን የልጅነት እውቀት በመፃፍቶቻቸው አስፍተውለታል። የነ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወ/ስላሴ እና የክብር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል መፃህፍት ኢትዮጵያዊ እውቀቱን በከፍተኛ ደረጃ እንዳጎለመሱለት ይነገራል።
ብርሃኑ ዘሪሁን በ1945 ዓ.ም ላይ ብዙ እውቀቶችን ከገበየበት ጎንደር ከተማ ተነስቶ አዲስ አበባ መጣ። በአዲስ አበባም ቆይታው ተግባረ ዕድ ት/ቤት ገብቶ የሬዲዮ ቴክኒሻንነት በመማር በ1948 ዓ.ም ላይ በዲፕሎማ ተመረቀ። ታዲያ በዚያ በምረቃ ወቅት ከተማሪዎቹ ሁሉ አንደኛ ወጥቶ ተሸላሚ የነበረው ብርሃኑ ዘሪሁን ነው።
ብርሃኑ ዘሪሁን ተግባረ ዕድ ት/ቤት ሲማር የታላላቅ የአለማችንን ደራሲያን ስራዎችን ለማንበብ ዕድሉን አገኘ፡ የነ ዊሊያም ሼክስፒርን፣ የአሌክሳንደር ዱማስ ፔሬን፣ የቻርልስ ዲክነስን፣ የነ አሌክሳንደር ፑሽኪንን እና የሌሎችንም መፃህፍት አነበበ። እውቀቱንም እያስፋፋ መጣ። በንባብ የተከማቸው እውቀቱም በፅሁፍ መውጣት ጀመረ። እዚያው ተግባር-ዕድ ት/ቤ ሲማር የት/ቤቱ ልሳን የነበረችውን “ቴክኒ-ኤኮ” የምትሰኘውን መፅሄት አዘጋጅ ሆኖ ሰርቷል። ከዚህ በተጨማሪም እዚያው ተማሪ ሳለ በ1947 ዓ.ም ተውኔት ጽፎም አሳይቷል። እናም እንግዲህ በኢትዮጵያ ሥነ-ፅሁፍ ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ ሊወስድ ብርሃኑ ዘሪሁን የሚባል ብዕረኛ ወደ አደባባይ ብቅ ማለት ጀመረ።
ብርሃኑ ዘሪሁን ተግባረ ዕድ ውስጥ ውጤቱ ከፍተኛ ስለነበር እዚያው ት/ቤት ውስጥ ተቀጠረ። ከት/ቤቱ ውስጥም ሆኖ ለተለያዩ ጋዜጦች ይፅፍ ነበር። ከተግባረ ዕድ ት/ቤት በመልቀቅ በወቅቱ አጠራር የጦር ሚኒስቴር በአሁኑ መከላከያ ሚኒስቴር በሚባለው መስሪያ ቤት በአስተርጓሚነት ተቀጥሮ መስራት ጀመረ። እዚያም ብዙ ሳይሰራ 1952 ዓ.ም ወደ ማስታወቂያ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ተዘዋወረ።
ብርሃኑ ዘሪሁን ማስታወቂያ ሚኒስቴር ውስጥ ወዲያው “የኢትዮጵያ ድምጽ” ተብሎ በሚታወቀው ጋዜጣ ላይ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ሰራ። ታዲያ በዚህ ወቅት ጋዜጣዋን ታዋቂ ከማድረጉም በላይ በብዙዎች ዘንድ የሚነበቡ መጣጥፎችን እና ታሪኮችን በመፃፍ ዝነኛ እየሆነ መጣ። ቀጥሎም የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ተዘዋወረ። ብርሃኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ በኢትዮጵያዊያን አንባቢያን ልብውስጥ ሰተት ብሎ ገባ። በአንድ ጊዜ ስሙ እና ዝናው እየናኘ መጣ።
ብርሃኑ ዘሪሁን በድርሰት ዓለም ውስጥ በተለይ በ1958 ዓ.ም አዲስ የታሪክ አብዮት ማቀጣጠል ጀመረ። “የቴዎድሮስ ዕንባ” የሚሰኝ መፅሐፍ አሳተመ። መፅሀፉ የአፄ ቴዎድሮስን አነሳስ እና ለኢትዮጵያ ያላቸውን ርዕይ ብሎም የመጨረሻውን የህይወት ፍፃሜ የሚያሳይ ነበር። በወቅቱ ማለትም ብርሃኑ ይህን መፅሀፍ ከማዘጋጀቱ በፊት የአፄ ቴዎድሮስ ታሪክ በጭካኔያቸው ላይ ተመስርቶ ብቻ የሚዘጋጅ በመሆኑ የቴዎድሮስን ውስጣዊ ስብዕና ያን ያህል ጎልቶ አይነገርም ነበር። እናም ብርሃኑ ዘሪሁን አፄ ቴዎድሮስ ብሔራዊ ጀግና መሆናቸውን የሚገልፅ ድርሰት ፅፎ በማቅረቡ በዘመኑ በጣም ታዋቂ ሆነ። ይህን “የቴዎድሮስ ዕንባ” የተሰኘውን ታሪክ መስፍን አለማየሁ ወደ መድረክ ቀይሮት በኢትዮጵያ የቴአትር አለም ውስጥም ከታላላቅ ቴአትሮቹ ተርታ የሚሰለፍ አድርጎታል።
በቴአትሩ ውስጥ የእንግሊዙ ቆንሲል አፄ ቴዎድሮስን እንዲህ ይላቸዋል “ጃንሆይ እኔ ተልኬ የመጣሁት ከታላቋ የብሪታኒያ የጦር ጀነራል ከናፒር ዘንድ ነው” ይላቸዋል።
ቴዎድሮስም “እና ምን ይዘህ መጣህ” አሉት።
መልዕክተኞች “ጃንሆይ ጦርነቱ እየከፋ ስለመጣ በሰላም እጅዎን ለታላቋ የብሪታኒያ መንግስት እንዲሰጡ ነው። እጅዎን በሰላም ከሰጡ የእንግሊዝ መንግስት በእንክብካቤ ይይዝዎታል” ይላቸዋል።
ቴዎድሮስም “ኧ ኧ ኧ ኧ ብለው የምፀት ሳቅ ከሳቁ በኋላ “ስማ! እኔ እንደ ፈረንጅ ጅል አላየሁም! መንጋ መሳፍንት እና መኳንንት ያንቀጠቀጠ ነበልባል እጄን ልያዘው አለ? የሚፋጅ የእሳት አሎሎ ነው በለው! ደግሞ . . . እጅህን ብትሰጥ በክብር ትያዛለህ ይለኛል። በየት አገር ነው እስረኛ በክብር የሚያዘው? ወይስ በሌላ የአፍሪካ ሀገር እንደለመዱት እኔን እስረኛ አድርገው ሀገሬ ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ሊይዙ? እኔ እንደሁ ህይወቴ እያለች ሀገሬ ኢትዮጵያን ከጥቁር ዘራፊ አውጥቼ ለነጭ ዘራፊ አልሰጥም ብሎሃል በለው! ሂድ ንገረው! ውጣ!” እያሉ ቴዎድሮስ ለኢትዮጵያ ያላቸውን ፍቅር የሚገልፁበት ታሪካዊ ተውኔት ነው።
አፄ ቴዎድሮስ ወታደሮቻቸውን ሁሉ ከነ መሳሪያቸው ካሰናበቱ በኋላ ራሳቸውን ሊያጠፉ በሚወስኑበት ወቅት ባለቤታቸው እቴጌ ጥሩወርቅ እንዲህ አሏቸው።
“ኧረ በአማየሁ፣ በአለማየሁ ይሄን ሃሳብዎን ይተው!” ይሏቸዋል።
ቴዎድሮስም፡- “ለአለማየሁ ምንም የማወርሰው ነገር የለኝም። ብቻ ሲያድግ አባትህ አንዲት ኢትዮጵያ በአይኑ እንደዞረች ሞተ ብለሽ ንገሪው”
በእንዲህ አይነት ሀገራዊ ፍቅር የታጀቡት የብርሃኑ ዘሪሁን የአፃፃፍ ቴክኒኮች ዘመን ሰበር ታሪኮች ሆነው ዛሬም እናወጋቸዋለን።
ብርሃኑ ዘሪሁን በድርሰት ዓለም ውስጥ ሲያዥጎደጉዳቸው ከነበሩት መፃሐፍት መካከል በ1961 ዓ.ም “የእንባ ደብዳቤዎች” በሚል ርዕስ ያሳተመው በሰፊው የተነበበለት ሲሆን ከዚያም በመለጠቅ “ድል ከሞት በኋላ ነው” የሚለውም መፅሐፉ እንዲሁ በወቅቱ ይቀነቀን የነበረውን ተራማጅ እንቅስቃሴ የሚያቀጣጥል ነበር። “የበደል ፍፃሜ” እንዲሁም “ጨረቃ ስትወጣ” የተሰኙትም መፅሐፍቶቹ በኢትዮጵያ ስነ-ፅሁፍ ውስጥ የብርሃኑ ዘሪሁንን ስም እናማንነት እየገነቡ የመጡ ስራዎቹ ናቸው። ብርአምባር ሰበረልዎ የተሰኘው መፅሐፉም ታትማ ስትወጣ አምራች ደራሲነቱን /Productive Author/ የሚል ቅፅል አሰጥታዋለች።
በአንድ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ሶስት ተከታታይ የሆኑ መፃሐፍትን በማሳተም ረገድ ብርሃኑ ዘሪሁን በኢትዮጵያ ሥነ-ጽሑፍ አለም ውስጥ ፈር ቀዳጅ ሆኖ ይጠቀሳል። በ1970ዎቹ ውስጥ ብርሃኑ ዘሪሁንን በሥነ-ፅሁፍ ታሪክ ውስጥ የማዕዘን ድንጋይ ሆኖ ስሙ እንዲነሳለት ያደረጉት እነዚህ ሶስት መፅህፍቶቹ “ማዕበል የአብዮቱ ዋዜማ”፣ “ማዕበል የአብዮቱ መባቻ” እና “ማዕበል የአብዮቱ ማግስት” ይሰኛሉ። መፅሐፎቹ በአንድ ወቅት በሰሜን ኢትዮጵያ ወሎ ውስጥ ተከስቶ በነበረው የረሃብና የድርቅ አደጋ ላይ ተመስርቶ የፃፋቸው ውብ መፅሀፎቹ ናቸው። እንዲህ አይነት ሶስት መፃህፍትን ፈረንጆቹ /Trilogy/ ይሏቸዋል። እናም በኛ ሀገር ደግሞ “ስልስ ድጉስ” ብለው የተረጎሙት ሰዎች አሉ። ብርሃኑ ዘሪሁን የስልስ ድጉስ መፃሐፍትም ደራሲ ነው።
ብዙም ሳይቆይ ደግሞ በኢትዮጵያዊያን የመፃህፍት አንባቢያን ዘንድ በእጅጉ የተወደደውን እና በተደጋጋሚ የታተመውን መጽሐፍ በ1978 ዓ.ም አሳተመ። መፅሀፉ “የታንጉት ምስጢር” ይሰኛል። በአፄ ቴዎድሮ ዘመድ በታንጉት እና በቴዎድሮስ የጦር አበጋዝ በሆነው በፊታውራሪ ገብርዬ ጎሹ መካከል ያለውን ፍቅር እና የዘመኑን ታሪክ የፃፈበት ውብ ድርሰት ነው። ሶስቱን ማዕበሎች እና የታንጉት ምስጢርን በኢትዮጵያ ሬዲዮ ላይ ድንቅየው ተዋናይ ወጋየሁ ንጋቱ በመተረኩ ከህዝብ አእምሮ እና ልቦና ውስጥ ለዘላለም እንዲኖሩ አድርጓቸዋል።
ብርሃኑ ዘሪሁን ከደራሲነቱ ባሻገር ፀሐፊ-ተውኔት ነው። የቴአትር ፅሁፎችን በማዘጋጀት እና በኢትዮጵያ መድረክ ላይ ግዙፍ ሰብዕና የሰጡትን ስራዎች አቅርቧል። ከቴዎድሮስ እንባ በኋላ በ1972 ዓ.ም “ሞረሽ” የተሰኘ ተውኔት በብሔራዊ ቴአትር ቤት አቅርቧል። በ1975 ዓ.ም ደግሞ “ጣጠኛው ተዋናይ” የተሰኘ ተውኔት በሐገር ፍቅር ቴአትር ቤት አቅርቧል። በ1976 ደግሞ “የለውጥ አርበኞች” የተሰኘ ተውኔት ጽፏል። በኢትዮጵያ የታሪክ ተውኔቶች አለም ውስጥ በዘመን አይሽሬነታቸው ከሚጠቀሱት ቴአትሮች መካከል “ባልቻ አባነፍሶ” የተሰኘው ቴአትር ነው። ይህን ቴአትር በ1977 ዓ.ም የፃፈው ይኸው ጎምቱ ደራሲ ብርሃኑ ዘሪሁን ነው።
ብርሃኑ ዘሪሁን ከደራሲነቱ እና ከፀሐፊ ቴውኔትነቱ ባሻገር ሃያሲም ነበር። የተለያዩ ደራሲያንን ስራዎችን ፅሁፎችን እየተከታተለ ሂሳዊ መጣጥፎችን ያቀርብ ነበር። ከዚህ በላይ ደግሞ የተዋጣለት ጋዜጠኛ ሆኖ በዘመኑ በብዕሩ የናኘ ስብዕና የተጎናፀፈ ሰው ነበር።
     ይህ የድርስት ገበሬ ስራዎቹ በበርካታ የስነ-ጽሁፍ እና የታሪክ ተመራማሪ በሆኑ ምሁራን ጥናት ተደርጎባቸዋል። የዩኒቨርስቲ የመመረቂያ ጽሁፎችም ሆነው በርካቶችን አስመርቀዋል። ሞልሸር የተባለው የኖርዌይ ዜጋ እና የኢትዮጵያን ደራሲዎች ታሪክ Black lions በሚል ርዕስ የፃፍው ደራሲ ብርሃኑ ዘሪሁንን ከኢትዮጵያ ታላላቅ ደራሲያን ተርታ ያስቀምጠዋል። ብርሃኑ ዘሪሁን ተግቶ በማንበቡ እና በመመራመሩ በኢትዮጵያ ሥነ -ጽሁፍ ታሪክ ውስጥ ለትውልድ ውለታ ውለው ካለፉ ጥበበኞች መካከል አንዱ ሆኖ ይጠራል። ሀገርን እና ትውልድን በብዕሩ ቀለማት ሲዘክር የኖረው ይህ ሰው ሚያዚያ 16 ቀን 1979 ዓ.ም በ54 ዓመቱ ከዚህ አለም በሞት ተለየ። ቀብሩም በባለወልድ ቤተ-ክርስቲያን ተፈፀመ። ዛሬ በአፀደ ስጋ ከኛ ጋር ባይኖርም ስራዎቹ ግን ዘመንን እየተሻገሩ ገና ወደፊትም ስሙን ያስጠሩታል።

ምንጭ:--በጥበቡ በለጠ ___http://www.sendeknewspaper.com/arts-sendek/item/559
****************************************************************************************************



ብርሃኑ ዘሪሁን እና “ድል ከሞት በኋላ”

**** ******************** ****

ባዩልኝ አያሌው 

  የአንዳንድ ፀሐፍቶቻችንን ብርታትና ትጋት፣ በዚህም ያበረከቱልንን ረብ ያላቸው ፍሬዎቻቸውን ሳስብ በመደነቅ ውስጤ ይሞላል፡፡ ሆኖም ብዙም ሳይቆይ እነዚህ ጠቢባንና ስራዎቻቸው እውቅና እና ትኩረት ማጣታቸውን ሳስብ ልቤ በቁጭት ይጨመቃል፡፡ እናም “እድል እና ቲፎዞ አቦ ላትመለሱ እንጦሮንጦስ ውረዱ!” ብዬ እራገማለሁ። የፀሐፊ ክፍያው መነበብ በመሆኑ አለመነበብ መከፋትን ቢጭርም ቅሉ የምር ፀሐፊ ይህንንም ቸል ብሎ መጻፉን ይቀጥላልና ስሜቱ የወል አይሆን ይሆናል፡፡ የምር እውቅና መስጠትስ መረዳትን የግድ ይል የለ። እንደዛ!
ብዙ ተግተው ብዙ ቢሰጡንም፣ ብዙም “ካልዘመርንላቸው” ብርቱ ደራሲዎቻችን አንዱ ብርሃኑ ዘሪሁን ይመስለኛል፡፡ ስለደራሲውና ስራዎቹ በጋዜጣ አምድ ላይ ለማውሳት መሞከር “ሆድ ላይሞሉ አጉል ማላስ” ቢሆንም፣ ካለማለት ጥቂት ማለት ያተርፋልና በዚህ ጽሑፌ ስለደራሲ ብርሃኑ ዘሪሁንና አስተዋጽኦዎቹ፣ እንዲሁም “ድል ከሞት በኋላ” ስለተባለው ድርሰቱ ጥቂት አወሳለሁ፡፡
በኢትዮጵያ ስነጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ቦታ ሊሰጣቸው የሚገቡ ስራዎችን ካበረከቱ ደራሲያን አንዱ ብርሃኑ ዘሪሁን ነው፡፡ የአጭርና የረዥም ልቦለድ ደራሲ፣ ጸሐፌ ተውኔት እና ጋዜጠኛ የነበረው ብርሃኑ ከ1952 ጀምሮ ከዚህ ዓለም በሞት እስካለፈበት 1979 ዓ.ም ድረስ 11 ልቦለድ ድርሰቶችንና 3 የሙሉ ጊዜ ተውኔቶችን ለተደራሲያኑ እንካችሁ ያለ ብርቱ ብዕረኛ ነው፡፡
በ1952 ዓ.ም “የእንባ ደብዳቤዎች” የተባለ ድርሰቱን እንካችሁ በማለት ጉዞውን አንድ ያለው ብርሃኑ፤ በኋላም “ድል ከሞት በኋላ”፣ “አማኑኤል ደርሶ መልስ”፣ “የበደል ፍጻሜ”፣ “ጨረቃ ስትወጣ” እና “ብር አምባር ሰበረልዎ” የተባሉትን ድርሰቶቹን አበርክቶአል፡፡ እንዲሁም “የቴዎድሮስ እንባ” እና “የታንጉት ምስጢር” የተባሉ ሁለት ታሪካዊ ልቦለዶችንና በወሎ ክፍለ ሀገር ተከስቶ የነበረውን ድርቅና የመንግስቱን ቢሮክራሲ ህያው አድርጎ የከተበባቸውን “ማዕበል የአብዮት ዋዜማ”፣ “ማዕበል የአብዮት መባቻ” እና “ማዕበል የአብዮት ማግስት” የተባሉ 3 ልቦለዶችን አስነብቦአል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ “ጣጠኛው ተዋናይ”ን እና “አባ ነፍሶ”ን የመሰሉ ተውኔቶችንም ጽፎ ለመድረክ አብቅቶአል፡፡
የብርሃኑን ድርሰቶች በጥሞና ለመረመረ አንባቢ አንድ ነገር አይሸሸገውም፡፡ ይኸውም ደራሲው ከጊዜ ጊዜ እያደገና እየበሰለ መሄዱ ነው፡፡ ደራሲው በገፀ ባህርያት አሳሳል፣ በግጭት አፈጣጠር እና በአተራረክ ጥበብ እንዲሁም በአጻጻፍ ብልሀቱ እየሰላ ሲሄድ በድርሰቶቹ በጉልህ ይስተዋላል፡፡ ምንም እንኳን ሲመሰከር ባይሰማም ብርሃኑ አጭር፣ ቀጥተኛና ግልጽ አረፍተ ነገሮችን በድርሰቶች ውስጥ በመጠቀም፣ እንዲሁም ቀድሞ የነበረውን ተረታዊ የታሪክ መንገሪያ ስልት በመቀየር ፈር ቀዳጅ ከሆኑ የሀገራችን ደራሲያን አንዱ ነው፡፡ ድርሰቶቹን የሚጽፈው እጅግ ቀላል እና ግልጽ በሆነ ስልት ነው፡፡ ከይዘት አንጻር አብዛኞቹ ድርሰቶቹም የሚያተኩሩት ማህበራዊና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ነው፡፡
የብርሃኑ ድርሰቶች ከቅርጽም ሆነ ከይዘት አንጻር ብዙ ሊባልላቸው የሚችሉ ናቸው፡፡ ሁሉም ድርሰቶቹ ማለት ይቻላል እጅጉን ለመነበብ የማይጎረብጡ ናቸው፡፡ ታሪክ ሲተርክም ሆነ መዋቅር ሲያበጅ ያውቅበታል፡፡ በየድርሰቶቹ የምናገኛቸው ገጸ ባህሪያቱ የቅርብ ሰዋችን ያህል የሚሰሙን ናቸው፡፡ የዚህም ምክንያቱ ምናልባት ማንነታቸው ከእኛ እንደ አንዱ ስለሆነ ታሪካቸውም እኛው የምንኖረው ያልራቀን፣ ያልረቀቀን አይነት ስለሆነ ይሆናል፡፡ በመሆኑም ስሜታቸውን ሁሉ እንድንጋራ እንሆናለን፡፡ የብዙዎቹ ድርሰቶቹ ጭብጦችም እንዲሁ ኑሮአችንና የየእለት ጉዳያችን ናቸው፡፡
ብርሃኑንና ድርሰቶቹን ሳስብ ሁሌም የሚደንቀኝ አንድ እውነት አለ፡፡ ያለኝ መረጃ እርግጥ ከሆነ ብርሃኑ ለብዙ ዓመታት ጋዜጠኛ፣ በኋላም የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነበር፡፡ የጋዜጣ ስራ ደግሞ ምን ያህል ጊዜን እንደሚወስድ ብቻ ሳይሆን አድካሚና የአፍታ ረፍት የለሽ መታተር እንደሆነ እናውቃለን። ዛሬ ለነገ ሰርቶ ዛሬውኑ ለቀጣዩ ቀን ማሰብን፣ መሮጥን ያለ ረፍት መድከምን… ይጠይቃል፡፡ ጋዜጣው እለታዊ ሲሆን ደግሞ አስቡት፡፡ የጋዜጣው አዘጋጅ ሲኮንስ? ሌላ ሌላውን ትተን ዋና አዘጋጁ ቢያንስ በየእለቱ ርዕሰ አንቀጽ መጻፍ ይጠበቅበታል። እንግዲህ በዚህ ሁሉ ውጥረት ውስጥ ሆኖ ነው ብርሃኑ በቁጥር የበዙ በጥራትም የላቁ ድርሰቶችን የጻፈው፡፡ ይህ ሁሌም ያስገርማኛል፡፡
“ድል ከሞት በኋላ” ብርሃኑ ዘሪሁን “የእንባ ደብዳቤዎች”ን ካቀረበ ከ3 ዓመታት በኋላ በ1955 ዓ.ም ያሳተመው ሁለተኛው ልቦለዱ ነው፡፡ ብርሃኑ ልቦለዱን የጻፈው በወቅቱ በደቡብ አፍሪካ ይካሄድ በነበረው የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ትግል ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ የድርሰቱ ጭብጥ የነጻነት ትግል፣ ትኩረቶቹም በወቅቱ ነጻ ያልወጣችው ደቡብ አፍሪካ እና በነጮች ስር ሆነው በመሰቃየት ላይ የሚገኙት ህዝቦቿ ናቸው፡፡ የታሪኩ ስፍራ ደቡብ አፍሪካ፣ የልቦለዱ ገጸ ባህሪያትም ለነጻነት የሚታገሉት ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን እና ገዢዋቻቸው የሆኑት ነጮች ናቸው፡፡
ልቦለዱ የሚተርከው የደቡብ አፍሪካ ጥቁር ህዝቦች በነጮች ስለሚደርስባቸው ጭቆና እና ይህንን ጭቆና ለማስወገድ ጥቁሮቹ ስለሚያደርጉት ትግል ነው፡፡ በዘመኑ በደቡብ አፍሪካ የነበረው ጨቋኝ የነጮች አገዛዝ፣ የጥቁሮቹ በገዛ ሀገራቸው በባርነት መገዛት በዚህም ይደርስባቸው የነበረው ግፍና መከራ ሁሉ በልቦለዱ ግሩም በሆነ መልኩ ቀርቦአል፡፡
የልቦለዱ ዋና ገጸ ባህሪ የዙሉ ጎሳ አባል የሆነው ድኩማ ነው፡፡ የድኩማ አባት ኪሙይ በሚሰራበት የነጮች ንብረት በሆነው የዱቄት ፋብሪካ ውስጥ ከሌሎች የስራ ባልደረቦቹ ጋር ባነሱት የህክምና አበል ጥያቄ ምክንያት በነጮች ላይ ትልቅ ሤራ ጠንስሰዋል በሚል በሀሰት ተወንጅሎ ይታሰራል። አባቱ በመታሰሩ ምክንያት የቤተሰቡ ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ በድኩማ ትከሻ ላይ ይወድቃል፡፡ ዘሩ ነጭ ቢሆንም የነጮቹን የግፍ አገዛዝ የሚቃወመውና ለጥቁሮቹ የሚቆረቆረው ዶክተር እስቴዋርድ ድኩማን የቆዳ ፋብሪካ ውስጥ በጉልበት ሰራተኛነት ያስቀጥረዋል፡፡
 ድኩማ በፋብሪካው እየሰራ ቤተሰቡን ለማስተዳደር ጥረት ቢያደርግም አባቱ በወንጀለኛነት ስለተፈረደበት ብቻ የወንጀለኛ ልጅ ነህ በሚል ምክንያት ከቆዳ ፋብሪካው ይባረራል፡፡ በድኩማ ቤተሰብ ላይም ከፍተኛ ችግር ይወድቃል። በዚህም ድኩማ የመከራው ጥልቀት እያንገሸገሸው ይመጣል።
ቆይቶም ሲያግዘው የቆየው እስቴዋርድ ዱርባን በምትባልና ጥቁሮች በሚኖሩባት ከተማ ለሚኖር አባ አሊንጎ ለተባለ ወዳጁ ድኩማን ላይ የደረሰበትን ችግር ሁሉ ገልጾ ደብዳቤ በመጻፍ እንዲረዳው ድኩማን ይልከዋል፡፡ ሆኖም አሊንጎ ስራ ሊያገኝለት ባለመቻሉ ድኩማ አሊንጎ ቤት መኖር ይጀምራል፡፡ በአሊንጎ መኖሪያ ቤት ማታ ማታ በየአካባቢው የሚኖሩ የጥቁሮች ተወካዮች ስለተጫነባቸው የመከራ ሕይወትና እንዴት ነጻ መውጣት እንደሚችሉ ያደርጉት የነበረው ውይይት ድኩማን እየሳበው ይመጣል፡፡ በሂደትም የውይይቱ አካል ይሆናል፡፡
ምክክሩና እቅዱ ቀጥሎ እነ አሊንጎ አመጹን ለማንሳት ምቹ ጊዜን እየጠበቁ ባሉበት ወቅት ድኩማ በፖሊስ ተይዞ ይታሰራል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ለጥቁሮች ወደ ተከለከለው ኮከብ አደባባይ ገብቶ መገኘቱ ነበር። የድኩማ መታሰርም አመጹ ተጠንቶ እና ምቹ ሁኔታ ሲገኝ ያለ ደም መፋሰስ ነው መደረግ ያለበት የሚል አቋም የነበረውን አሊንጎን ተስፋ ያስቆርጠዋል። ስለዚህም አመጹ መካሄድ እንዳለበት ይወስናል፡፡ በመሆኑም ድኩማ ፍርድ ቤት በሚቀርብበት ሰዓት 50 ሺ ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በሰልፍ ሆነው የተቃውሞ መዝሙር በመዘመር ወደ ፍርድ ቤቱ ያመራሉ። ሆኖም የነጭ ፖሊሶች ጥይት በመተኮስ የአመጹን መሪዎች ጨምሮ ብዙ ጥቁሮችን ይገድላሉ፡፡  ከፍርድ ቤቱ በመውጣት አመጹን የተቀላቀለው ድኩማ እና የትግሉ መሪ የነበረው አሊንጎም ከፖሊሶቹ በተተኮሰ ጥይት ይገደላሉ፡፡ የጀመሩት ትግል እንደሚቀጥል ተስፋ አድርገው፣ ሞታቸውን በጸጋ እንደተቀበሉት ተገልጾ ታሪኩ ይቋጫል፡፡
ታሪኩ እጅግ አጓጊና የማይሰለች፣ አተራረኩም ውብ ነው፡፡ እነ ድኩማና አባቱ ኪሙይ፣ አሊንጎ፣ ዶክተር እስቴዋርድ የመሳሰሉት የታሪኩ ባለቤቶች በውብ መንገድ የተቀረጹና ቅርባችን ያሉ ያክል የሚሰሙን አይረሴ ገጸ ባህሪያት ናቸው፡፡
ብርሃኑ ዘሪሁን ብዙዎቹን ታሪካዊ ልቦለዶቹን የጻፈው ታሪኩ የተፈጸመበት ቦታ በአካል ተገኝቶ መረጃዎችን በመሰብሰብና የሁነቱን መንፈስ ለመላበስ በመሞከር ነው፡፡ “የቴዎድሮስ እንባ”ን ሲጽፍ ጎንደርና መቅደላ፣ 3ቱን “ማዕበሎች” ሲጽፍ ደግሞ ከወሎ የገጠር ቀበሌዎች ደሴ እስከነበረው የስደተኞች ካምፕ ድረስ ተዘዋውሮ በድርቅ የተጠቁትን ሰዎች በማየትና በማነጋገር መረጃዎችን ሰብስቦአል፡፡ “ድል ከሞት በኋላ”ን ለመጻፍ ግን ደቡብ አፍሪካ አልሄደም፡፡ ያም ሆኖ ባለመሄዱ ከመቼትም ሆነ ከታሪክ አንጻር ምንም እንዳላጎደለና  የወቅቱን የደቡብ አፍሪካን ጥቁሮች የመከራ ህይወትና የነጻነት ትግል በጥሩ አቀራረብ ለአንባቢያን ማሳየቱን ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡
ልቦለዱን ከራሱ ከደራሲው ስራዎችም ሆነ ከሌሎች በዘመኑና ከእሱም ቀድመው ከታተሙ ልቦለድ ድርሰቶች የሚለየው አንድ ጉዳይ አለ፡፡ ይኸውም የሌሎች ሕዝቦችን ታሪክ መተረኩ ነው፡፡
ቀደም ሲል ለድርሰቶቻቸው በእውኑ ዓለም የሌሉ መቼቶችን እየፈጠሩና ሰው ያልሆኑ ገጸ ባህሪያትን እየቀረጹ ጭምር የጻፉ ደራሲያን ቢኖሩም የሌላ ሀገርን ታሪክና መቼት በሙሉ ጊዜ በድርሰቱ ውስጥ በመገልገል፣ በአጠቃላይ የሌሎች ሕዝቦችን ጉዳይ የድርሰቱ አቢይ ትኩረት አድርጎ የጻፈ ደራሲ አላጋጠመኝም፡፡ ይህንን ለማንሳት የወደድኩት ደራሲው ይህንን ልቦለድ መጻፍን ለምን ፈለገ? ወደሚለው ጥያቄ ስለሚመራኝ ነው፡፡
ደራሲው ስለመጽሐፉ የመጻፍ ምክንያት በከተበበት መግቢያ ላይ “መጽሐፉን የጻፍኩት ስለ ነጻነትና ስለመብት ለተሰዉ ሰዎች እና ወደፊትም በመታገል ላይ ለሚገኙት ሕዝቦች ሁሉ መታሰቢያ የምትሆን አንዲት ድርሰት ማበርከት እዳዬ ሆኖ ስለተሰማኝ ነው” ይላል፡፡ ሆኖም መጽሐፉ የታተመበትን ጊዜ (1955 ዓ.ም) እና በልቦለዱ የተነሱ ጉዳዮችን ይዘን ስናስብ አማራጭ የለንም ብለን እጅ ካልሰጠን በቀር ብርሃኑ ድርሰቱን ለመጻፍ ምክንያቴ ነው ያለንን ለማመን እንቸገራለን፡፡ ወቅቱ ምንም እንኳን የብዙ የአፍሪካ ሀገሮች የነበሩበትን መንፈስ ያህል ባይሆንም በኢትዮጵያም የለውጥ ነፋስ መንፈስ የጀመረበት ጊዜ ነው፡፡ እርግጡን መናገር ቢቸግርም ደራሲው ልቦለዱን ሲጽፍ ሌላ ዓላማ ያለው ይመስላል፡፡ ምናልባትም የደቡብ አፍሪካውን የነጻነት ትግል መንፈስ በዚህች ሀገር ወጣቶች ላይ ማጋባት፣ እኛም የተጫነን ቀንበር አለና ከተቀመጥንበት እንነቃነቅ የማለት… የመሳሰሉት አይነት ዓላማዎች፡፡
አስገራሚው ጉዳይ ታዲያ ይህንን የመሰለ የነጻነት ትግልን ጭብጡ ያደረገ ይህንንም በበርካታ  ሁነቶች ማሳየት የቻለ ልቦለድ፣ የለውጥ ነፋስ እየመጣባት ባለች ሀገርና ነፋሱን እየጠሩት ባሉት የዘመኑ ወጣቶች ሳይቀር ብዙም አለመነበቡ ነው፡፡ በወቅቱ ልቦለዱ 2,000 ኮፒ እንደታተመና ብዙም እንዳልተሸጠ፣ ለዚህም ምክንያቱ የዘመኑ አንባቢያን ለደቡብ አፍሪካ ታሪክ ብዙም ፍላጎት ያልነበራቸው በመሆኑ እንደሆነ ደራሲው (ብርሃኑ) ገልጾልኛል፤ በማለት የብርሃኑን የህይወት ታሪክ እና ስራዎቹን ያጠናው ሪዱልፍ ኬ. ሞልቬር Black Lions- The Creative Lives of Moderen Ethiopia’s Literary Giants and Pioneers (1997) በተባለው መጽሐፉ አስፍሮአል፡፡ መተላለፍ ይሉታል ይሄ ነው።

ምንጭ:--http://www.addisadmassnews.com/
*************************************************************************** 

Friday, November 21, 2014

የባንዲራ ታሪክ_በኑረዲን ዒሣ

የግጥም ጣዕም 

የባንዲራ ታሪክ_ኑረዲን ዒሣ

 

በሃበሻ ምድር
እንዲህ እንደዛሬው ዋጋው መሣ ሳይሆን
እኩል ከእራፊ ጨርቅ
ለሃገር ክብር ሲባል
ከባንዲራ በፊት – ሰው ነበር የሚወድቅ።
መሣፍንቱ በጎጥ ሸንሽኖ ከፋፍሎ
የማሽላ ዳቦ ያረጋትን ሃገር
ገብርዬ ሲለካት – እንቅጯን ሁለት ክንድ
በሆነች ባንዲራ ገጣጥሞ በማሰር
አንድን ሕዝብ አንድ አርጎ
ማኖር እንደሚችል ከተዋበች በቀር
ሕዝቡም፣ ሹማምንቱም፣ እራሱ ቴዎድሮስም – ከቶ አያውቅም ነበር።
የዛን ቀን ለሊት ግን
እንደ ነገ ጠዋት፣ ደረስጌ ማርያም ላይ
ንግሥና ሊቀባ፣ ክፉኛ ሃሳብ ይዞት
እንቅልፍም እንደሰው ሙልጭ አርጎ ክዶት
እልፍኙ ውስጥ ሆኖ….
ስለአንዲት ሃገሩ፣ ስለአንዲት ወዳጁ
እቋፍ ላይ ስላለች
ላሳቡ ማሰሪያ አጥቶ – እግር ተወርች
እንዲህ ሲንጎራደድ
ሌላኛ ወዳጁ
የሴት ባለመላ – ተዋበች አሊ ግን ልታነቃው አለች።
«ካሣ መከታዬ»
ሃሳብ ለምን ገባህ አልልም የኔ አባት
ቅድምም አየውህ – ማዱን ስትገፋው
አልዋጥ ብሎ፣ ባፍህ ሲንከራተት የጎረስከው እራት።
አውቃለሁ ጌታዬ
የእንቅልፍህ፣ የእረፍትህ፣ ያንዠትህም ጠላት
ይቺው ሃገርህ ናት።
ደሞ ምናባቱ…እንቅልፍስ ይቅርብህ – ወዴት ታውቀውና
እጣህን የመንቃት አድርጎት ሲያበቃ…
ምኑን ታርፈዋለህ
ይኼው ጎበጥክ አይደል – ሃገር ስታቀና።
እንቅልፍስ ይቅርብህ ወዴት ታውቀውና።
ቁስሉን ነካችበት
ብሶቱ ልፋቱን – መከራውን አልፋ ሕልሙን አየችበት።
ካሣ አንገቱን ደፋ
እሷ ፊቷን ዞረች።
እንዲህ የሆነ ዕለት – ከሱና እሷ በቀር – ባዕድ የማያውቃት
ያይኑን ገደብ አልፋ – የምትፈስ እንባ አለች
ያቺ ዕንባ ጠብ አለች።
እንግዲህ አለ መይሳው
እንግዲህ…
በእኔ ልፋትና በኔ ድካም ሳይሆን
በእግዜር ይሁን ማለት
ለዚህ ማዕረግ መርጦ – ሰጥቶኛል ይኽን ሹመት
እኔ ስሰነዝር እሱ ከኔ ቀድሞ ባላንጦቼን እየጣለ
ወሰኔን እያሰፋ – የታጠቅ ጉልበት እንደቻለ
ሞገሴን እያገዘፈ….
እንደልቤ መሻት—እርከኔን እያከለ።
እግዛቤር ይመስገን
ይኼው … ለዚህ በቅቻለሁ
ተመስገን ከማለት ውጪ
ለስለት እከፍለውስ—ምን የከበረ አስገባለሁ።
ግን አለ መይሳው!
ግን ነገ ማለዳ…ቅባቱን ተቀብዬ – ዘውዱን ስደፋ
ሕዝቡ!
ይጠብቃልና…እገባለት ኪዳን – ፈቅደህ ስጠኝ ስለው ይቺን ትልቅ ሃገር
ምን ይዤ ልማልለት – ምን ጨብጬ ልቁረብለት
ምንስ ብዬ ልናገር
እስኪ መላ ካለሽ – ተዋቡ – ካንቺ እንኳን ልበደር።
በማተቤ እንዳልምል
የባለሌጣ አንገቱም የእስላሙም ናት ይቺ ሃገር
በጊዮን እንዳልምል
ኦሞ፣ ጉደር፣ አዋሽ፣ ቦርከና፣ ባሮ፣ ተከዜ፣ ጉማራ በይው ሎኒያ
ሁሉም ገንዘቧ ነው
የቱ ከየትኛው በልጦብኝ – በየትኛው ልማልላት ለኢትዮጵያ!
ሽናሻ፣ ጋምቤላ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ፣ አገው፣ ወላይታ
ትግሬ በይው አማራ፣
በምድሯ የተቀነበበ ሁሉ በስሟ ነው የሚጠራ።
እህም…አለች ተዋቡ
እህም…አሁን እስላም ስትል – ሸማኔው ትዝ አለኝ
እጀ ወርቅ የሚሉት – አህመዴ ቦጋለ
በል ቶሎ በል ካሣ – አሽከር አስጠራልኝ – ገብርዬ የታለ
ገብርዬን አስጠራው
እሱ ነው የልቤ – ሲጋልብ የሚነፍስ
ከጎህ ቅዳጅ በፊት – መልዕክቴን ይዞልኝ – ከደጁ የሚደርስ።
ካሣን ግራ ገባው፣ ግን አይጠይቃትም፣
አምስት ስድስት ጊዜም እንደዚህ አዋክባው
እሷው ነድፋ፣ እሷው አባዝታ
እሷው አድርታ፣ እሷው ፈትላ
ባመጣችው ሃሳብ፣ ባሳየችው መላ
ብትንትን ሃሳቡን ገጣጥማ ስትሰፋው – አይቷልና ባይኑ
ለምን ማለት ትቶ፣ እንዴት ማለት ትቶ
«ገብርዬ ይጠራ» አለ ወዲያውኑ።
ገብርዬ
ከታንጉት ሙቅ እቅፍ
በውድቅት ተላቆ – ከነ ጋሻ ጃግሬው ገና እንደደረሰ
«እሰይ የኔ አንበሳ» ስትለው ተዋበች
ገና እንኳን በወጉ የወጉን እጅ መንሳት ሰጥቶም አልጨረሰ።
«እሰይ የኔ አንበሳ…
እንትፍ ይቺ ምራቅ ምድር መጥጧት ሳትከር
ስትገሰግስ ሄደህ…ደገኞቹ መንደር
አህመዴ ለሚባል
እጀ ወርቅ ሸማኔ … ቃሌን ቃል ሳትጨምር፣ እንዲህ ብለህ ንገር።
ባገር ሠማይ ስትፈልቅ
የቅርቡም የሩቁም እኩል እንደሚያያት የማሪያም መቀነት፣
በዚህ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ጥለት
አንተ ስትለካት – ሁለት ክንድ የሆነች – ጥብቅ ምት ባንዲራ፣
ሁነኛ አርጎ ሰርቶ
ነገ ማሪያም ድረስ – ይዟት እንዲመጣ – አጥብቀህ … አርቀህ ንገረው አደራ።
በማለት ተዋበች…
ግብጦች ለእጅ መንሻ – ከላኩላት መሐል -
የሃር የሆነውን ጥለት ጥድፍ ብላ
ለገብርዬ ሰጥታው – እሱም ጥድፍ ብሎ
ከነጀሌዎቹ ከወጣ በኋላ
ካሣ ፈገግ አለ፣
የጥድፈቷ ሚስጥር ቋጠሮው ተፈትቶ፣ ብትንትን ሃሳቡን
ባንድ ስላዋለ
ካሣ ፈገግ አለ።
ሺህ ስምንት መቶ አርባ አምስት – ዓመተ ምህረት
የተራራው አናት – ገና ሳይላቀቅ
ካድማስ ጥቁር እግር
ባህመዴ አማርኛ – ሠማዩ ሳይቀላ ባግባቡ ሳይፈጅር
አህመዴ ቦጋለ
የንጋት ስግደቱን – አስላምቶ አብቅቶ
ልክ! ፊቱን እያበሰ
ፊታውራሪ ገብርዬ
ከነጀሌዎቹ ደጁ ላይ ደረሰ።
የፈረሶች ኮቴ – ደጁን ሲረመርም የሰማው አህመዴ
ልቡ ድንግጥ አለ፣
«እንዲህ በማለዳ – የሚደርስ ከደጄ
መርዶ ነጋሪ ነው
ደሞ ማን ተለየኝ – የትኛው ዘመዴ?
ከቶ የኔ ሐዘን ዳርም የለው እንዴ
«እንዴት አደራችሁ…ቤቶች»
ይበልጥ ተረበሸ ይኼን ድምፅ ያውቀዋል፣
ምላሽም አልሰጠ፣ በርም አልከፈተ
ድርቅ ብሎ ቁሞ – ወይ ወንድሜን አለ
ክተት ሲባል ከቶ ከመይሣው ጋራ አብሮ የዘመተ
አንድ ወንድም ነበረው… ያ ወንድሙ ሞተ?
«ቤቶች…ቤቶች
ገብርዬ ጥሪውን እንዲህ ሲደጋግም
ገፋ አድርጎ ወጥቶ የጎጆውን ግርግም
ድሮ አውቄዋአለሁ
ለደግም አልነበር አደባባይ ቆሜ
ሸማ ሳውለበልብ ያየሁት በህልሜ
ወይ ወንድሜን ወንድሜ!
«የለ እንደሱም አይደል» ገብርዬ አቋረጠው
«ተዋበች ልካን ነው»
አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ጥለቱን ሰጠው።
አስከትሎ ደግሞ
ቃሌን ቃል ሳትጨምር – ያለችውን መልዕክት
ቃሏን ቃል ሳይጨምር – ረግጦ ሲነግረው
የመናቡ ተፍሲር – ብስራት ሆኖለት
እጀ ወርቅ ደስ አለው።
አለም፦
እንዴት ያንድ እናት ሆድ፣ አንድ ላይ ያበቅላል፣ አንድ ደህና አንድ ጠፍ
ብረገም ነው እንጂ
ክተት ሲል ከትቼ – እንደዚያ ወንድሜ – ከመይሣው ጋራ ጎኑ ማልሰለፍ፣
ብዬ እቆጭ ነበር፣… ይኼው ዛሬ ግና
አላህ ያለ ለታ፣ ላገር ሥራ ሲለኝ ረብ ያለው ሥራ
ያውም የመይሳውን ያውም የኢትዮጵያን … ያውም ያገሬን ባንዲራ
ያውም በኔ ጥበብ…
ያውም በሰው እጆች … ከሰውም በኔ እጆች … በሸማ እንድሰራ
ታሪክ እድል ሰጠኝ፣ ብሞትም አይቆጨኝ ከዚህስ በኋላ!
አህመዴ ሸለለ፣
አህመዴ ፎከረ … በደስታ ሰከረ፣ በደስታ አለቀሰ
ሩጦ ቤቱ ገባ፣ ሦስቱንም ልጆቹን – ሚስቱን ቀሰቀሰ።
ነገራት ለሚስቱ፣
ከምርጥ ዘሃ መሀል – ምርጡን ዘሃ መርጣ
እንድታቀርብለት – ቶሎ ብላ አዝግታ።
አዘዘ ልጆቹን
ቱባ ተከፋፍለው – ከየአንዳንዱ ጥለት
አሥር አሥር ቀለም – እንዲያዳውሩለት።
ሦስት ሰዓትም አልፈጀ
መቀነት ሸማቃው ከኖረበት ወርዶ
ዝግ ዘሃው ተቋጥሮ
ጥለቱ ተጥሎ.. ድምድሙ ተመትቶ – ባንዲራው ሲቆረጥ
በቅሎው ከጋጥ ወጥቶ
በጌጥ ተሸልሞ አህመድ ተነሚስቱ እጋማው ላይ ወጥቶ
እሱ – ሲኮለኩል – በቅሎው ንሮ ሲሮጥ … ሲሮጥ … ሲሮጥ
ደረስጌ ማሪያም ላይ ደርሰው ሆታው ሲቀልጥ
በዚያ መሀል አልፈው አህመድ ለመይሣው ባንዲራውን ሲሰጥ
ሰዓትም አልፈጀ
መይሣው ደስ አለው
የወርዱ ምጣኔ፣ የጠርዙ ጥብቅነት፣
የጥለቱ አጣጣል፣ ጥበቡ ደነቀው፣
ቁርጥማት አይንካህ
በሆዱ መረቀው
ካሣ ዞሮ ሄደ።
አህመዴ ተጣራ
መይሳው ዞር አለ
ባንዲራው ሲሰራ
ተርፎ ስለነበር ብዙ የሃር ጥለት ካቁማዳው አውጥቶ … እጁን ዘረጋለት።
ካሣ….!!
የዚህን ደሃ ሰው – ፍፁም ታማኝነት፣ ገራገር ልቦና ባስተዋለ ጊዜ፣
የጎንደር አዝማሪ ያቀነቀናትን በልቡ እያዜማት
በልቡ ያላትን … ያቺኑ ምርቃት…
ተባረክ እጅህን አይንካው ቁርጥማት
በአፉም ደገማት።
የጎንደር አዝማሪ በእነ አህመዴ ዘመን፣
«እስላም አልኩሽ እንጂ – እጁ የሚታመን
ሸማኔማ ሞልቷል ደሞ ለመሸመን»
ይል ነበር።                        

https://www.youtube.com/watch?v=rekboLUx2wI

Wednesday, November 19, 2014

የሚጸልዩ እጆች_እና_አልብሬሽት ዱረር

(እውነተኛ ታሪክ)
*************


ከስድስት ምእት ዓመታት በፊት በጀርመን ኑረምበርግ ከተማ በአንድ ትንሽ መንደር ውስጥ አሥራ ስምንት ልጆች ያሉበት አንድ ቤተሰብ ይኖር ነበር፡፡ አሥራ ስምንት! ለዚህ ሁሉ ማቲ ምግብ ለማቅረብ በሙያው አንጥረኛ የሆነው አባ ወራ በቀን አሥራ ስምንት ሰዓት በሙያውና ከሙያው ውጪ መሥራት ነበረበት፡፡

የቤተሰቡ የኑሮ ሁኔታ የከፋ ቢሆንም ከልጆቹ ውስጥ ሁለቱ ታላላቆች ልዩ ሕልም ነበራቸው ሥነ ጥበብን ማጥናትና ዝነኛ ሠዓሊ መሆን፡፡ አባታቸው ማንኛቸውንም ኑረምበርግ ወደ ሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ ልኮ ሊያስተምራቸው የሚያስችል የገንዘብ አቅም እንደሌለው ግን ሁለቱም ያውቁ ነበር፡፡

አንድ ምሽት በተጨናነቀው አልጋቸው ላይ ሆነው በሕልማቸው ዙሪያ ለረጅም ሰዓት ተወያዩና ወደ አንድ ስምምነት ደረሱ፤ ዕጣ ሊጣጣሉም ወሰኑ፡፡ በዕጣው የተሸነፈው በአቅራቢያቸው ወደ ሚገኝ አንድ የማዕድን ማውጫ ሄዶ እንዲሠራ፣ በሚያገኘውም ገቢ ወደ ከፍተኛ ትምህርት የሚሄደውን ወንድሙን እየረዳ እንዲያስተምር፡፡ ዕጣ የወጣለት ወንድም ደግሞ በኑረምበርግ ከተማ በሚገኘው የሥነ ጥበብ አካዳሚ የአራት ዓመታት ትምህርቱን እንዲማርና ትምህርቱንም ሲጨርስ፣ በሚመረቅበት የሥነ ጥበብ ሙያ ከሚሠራቸው ሥዕሎች ሽያጭ በሚያገኘው ገቢ ወይም አስፈላጊ ከሆነ እርሱም በማዕድን ቁፋሮ ሥራ ተቀጥሮ በተራው ያስተማረውን ወንድሙን ሊያስተምር ወደ ውሳኔ ደረሱ፡፡

አንድ እሑድ ጠዋት ዕጣው ተጣለ፣ ታላቁ አልብሬሽት ዱረር የተባለው ወንድም ዕጣው ወጣለት፡፡ ኑረምበርግ ከተማ ወደ ሚገኘውም የሥዕል አካዳሚ ገባ፡፡

ዕጣ ያልወጣለት ወንድም ወደ አደገኛው የማዕድን ቁፋሮ ሥራ አመራ፣ ለተከታዮቹ አራት ዓመታትም ወንድሙን በገንዘብ እየረዳ አስተማረ፡፡ አልብሬሽት የአካዳሚው የሥዕል ትምህርት ተዋጣለት፡፡ በልዩ ልዩ የሥዕል ሥራዎች የተካነ ሆነ፡፡ የሚሠራቸው የቅብ ሥዕሎች ከመምሕራኖቹ ሥራዎች ይልቅ እየላቁና እይተወደዱ መጡ፡፡ በኮሚሸን ለሚሠራቸውም ሥዕሎች ዳጐስ ያለ ገንዝብ ይከፈለው ጀመር፡፡

ወጣቱ ሠዓሊ ትምህርቱን አጠናቆ ወደ መንደሩ ሲመለስ ቤተሰቡ በድል መመለሱን ምክንያት በማድረገ ድግስ ደግሶ ጠበቀው፡፡ በሙዚቃና በሳቅ በደመቀው ግብዣ መጨረሻ ላይ ሠዓሊው አልብሬሽት ከክብር ወንበሩ ተነሳና ለተወዳጅ ወንድሙ፣ ላመታት ስለከፈለው መስዋዕትነት፣ ሕልሙንም እንዲያሳካ ስለ ረዳው ጽዋ አነሳ፡፡ በመዝጊያ ንግግሩም፣ ‹‹የተባረክህ ወንድሜ አልበርት ሆይ፣ አሁን እንግዲህ ተራው ያንተ ነው፣ ወደ ኑረምበርግ ትሄዳለህ አንተም ሕልምህን ታሳካለህ፣ እኔም በተራዬ እንከባክብሃለሁ›› አለ፡፡

በገበታው የታደሙት ሁሉ አንገታቸውን ከገበታው አንድ ጥግ ላይ ወደ ተቀመጠው የማዕድን ሠራተኛ አልበርት አዞሩ፡፡ በገረጣው ፊቱ ላይ እንባው እየተንከባለለ በጉንጮቹ ላይ እይፈሰሰ ነው፣ ራሱንም ከግራ ወደ ቀኝ እያወዛወዘ፣ ሳግም እየተናነቀው ደጋግሞ፣ ‹‹አይሆንም….. አይሆንም ወንድሜ ሆይ፣….. አይሆንም!›› አለ፡፡

በመጨረሻ ብድግ ብሎ እንባውን ከጉንጮቹ ላይ በማበስ፣ አሻግሮም በገበታው ላይ የታደሙትን የሚወዳቸውን ፊቶች በፍቅር እየተመለከ፣ ሁለት እጆቹን አጣምሮ ወደ ቀኝ አገጩ በማስጠጋት ለስለስ ባለ ድምጽ ‹‹የለም ወንድሜ ሆይ፣ ወደ ኑረምበርግ ልሄድ አልችም፣ ለእኔ ዘግይቷል፣ የአራት ዓመታት የማዕድን ቁፋሮ ሥራ እጆቼን ምን እንዳደረጋቸው ተመልከትማ በጣቶቼ ላይ ያሉ አጥንቶች ሁሉ በቀን ቢያንስ አንድ ጊዜ ይጐዱ ነበር፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በከባድ የቁርጥማት በሸታ እየተሰቃየሁ ነው፣ በእርሳስና በብሩሽ በሸራ ላይ ሥዕሎችን መቀባት ይቅርና፣ አላስተዋልከኝም እንጂ፣ ጽዋችንን እናንሳ ስትል ጽዋውን ለመያዝ እንኳ የቀኝ እጄ አልቻለም፡፡ አሁን ለእኔ ዘግይቷል›› አለ፡፡

ይህ ታሪክ ከተፈጸመ ከ450 ዓመት በላይ አልፈዋል፡፡ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ የአልብሬሽት ዱረር እጹብ ድንቅ ሥራዎች፣ የራስ ምስሎች፣ የእርሳሰና የውኃ ቀለም ቅቦች፣ የቻርኮል ሥራዎች፣ የእንጨት ቅርጻ ቅርጾችና፣ የመዳብ ውቅሮች በመላው ዓለም ባሉ ሙዚየሞች ተሰቅለው ይገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ ብዙ ሰዎች ከሌሎች ሥራዋቹ ይልቅ ‹‹እጆቹ›› የሚለው ሥራውን ቅጅ በየቤቶቻቸውና ቢሮዎቻቸው ግድግዳዎች ላይ አንጠልጥለውታል፡፡

አንድ ቀን ወንድሙ ለከፈለለት መስዋዕትነት አክብሮት ለመስጠት፣ አልብሬሽት ዱረር በከፍተኛ ጥንቃቄ የወንድሙን የተጎዱ እጆች፣ መዳፎቹ ተጋጥመው፣ ቀጫጭን ጣቶቹ ወደ ሰማይ ተዘርግተው የሚታዩበትን ሥዕል ሳለ፡፡ ይህን ድንቅና ኃያል ሥራውንም ‹‹እጆቹ›› የሚል ስያሜ ሰጠው፡፡ ብዙም ሳይቆይ በዓለም ዙሪያ ሥዕሉን የተመለከቱ ሁሉ፣ ለዚህ ታላቅ እጹብ ድንቅ ሥራ ልባቸውን ከፈቱለት፡፡ ይህን ከፍቅር የተነሳ የተሳለ ሥዕልም ‹‹የሚጸልዩ እጆች›› ብለው ሰየሙት፡፡



አልብሬሽት ዱረር (Albrecht Dürer) ማን ነው?
 
Albrecht Dürer (German: 21 May 1471 – 6 April 1528)


ንደ አውሮፓው አቆጣጠር ግንቦት ፳፩ ቀን ፲፬፻፸፬ ኑረምበርግ ጀርመን ተወልዶ በ፶፮ ዓመቱ (ሚያዚያ ፮ ቀን ፲፭፻፳፰) እዛው ኑረምበርግ ከተማ የሞተው አልብሬሽት ዱረር (ከዚህ በኋላ ዱረር ብለን እንጠራዋለን) (German: [ˈalbʁɛçt ˈdyːʁɐ]) የተሳካለት የወርቅ ኣንጥረኛና ከሃንጋሪ ወደ ኑረምበርግ የፈለሰው አባቱና እናቱ ሦስተኛ ልጅ (ሁለተኛው ወንድ) ሲሆን፤ ወላጆቹ ከ፲፬ እስከ ፲፰ ልጆች እንደነበራቸው ይገመታል።
      ዱረር ለጥቂት ዓመታት ትምህርቱን ከተከታተለ በኋላ የወርቅ አንጥረኝነትና የስዕል ሙያ መሰረቶችን ከአባቱ ተማረ። ምንም እንኳን አባቱ በአንጥረኝነቱ እንዲቀጥልበት ቢፈልግም፤ በጣም ላቅ ያለ የስዕል ችሎታ በማሳየቱ ምክኒያት ገና በ፲፬ ዓመቱ በኑረምበርግ ታዋቂ አርቲስትና የኪነ ጥበብ ማዕከል (የአርት ወርክ ሾ) ባለቤት ለነበረው ሚካኤል ዎልጌሙት (Michael Wolgemut) ረዳት ሆነ።
 
 ‹‹የሚፀልዩ እጆች›› /Betende Hände/ በእንግሊዘኛ Praying hands (በጀርመንኛም Studie zu den Händen eines Apostels in German, ወይም "Study of the Hands of an Apostle": የሐዋሪያው እጅ ጥናት) በመባል የሚታወቀው በብዕርና ቀለም በጀርመናዊው የኪነ ጥበብ ሰው አልብሽሬት ዱረር በ፲፭፻፰ የተሰራ ሲሆን፤ ይህ ሥራ ቪየና/ኦስትሪያ (Vienna, Austria) በሚገኘው አልበርቲና (Albertina) ሙዚየም ይገኛል።በብዕርና (እራሱ በሰራው) ሰማያዊ ወረቀት ላይ ዱረር ነጩ ሄይተኒንግ በመባል የሚታወቀውን ቴክኒክ ለዚህ ስራው ተጠቅሟል። ሥዕሉ እርስ በርሳቸው የተጋጠሙ የሚፀልዩ ሁለት የወንድ እጆች ሲሆን፤ የቀኙ እጅ ሙሉ ክፍል ካለመታየቱ ባሻገር፣ የፀላዩን እጅ የሸፈነው ልብስ (ክሳድ) ጫፍ በጥቂቱ ወደላይ ተቀልብሶ ይታያል። ይህ ሥዕል በ፲፯፳፱ በእሳት የነደደው ባለ ሶስት ክፍሉ የሄለን መስዋዕት ማቅረቢያ (the Heller altar,) በመባል ይታወቅ ለነበረው የዱረር ሥራ መካከለኛው ክፍል ላይ ለተሳለው ሐዋሪያ እጅ (an apostles' hand) እንዲሆን ታስቦ የተነደፈ ነው። ይህ የእጅ ንድፍ ሊደረግ በታሰበበት ሥዕል በመካከለኛው ክፍል በቀኝ በኩል በተመሳሳይ ግን በትንሽ መጠን ተስሎ ይገኛል። በወረቀቱ የሐዋሪያው ራስ ንድፍ የተሰራበት ቢሆንም፤ ሁለቱ የተቀመጡት ተለያይተው ነው። ዱረር ለዚህ (የሄለን መስዋዕት ማቅረቢያ) ስራው በጠቅላላ ፲፰ ንድፎችን ሰርቷል። ቪየና ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሕዝብ ዕይታ በ፲፰፻፸፩ ቀረበ። ሥራው ምናልባት የሰሪው እጅ እንደሆነ ይገመታል።
 
*******************************************************************************

ምንጭ፥ http://www.ethiopianreporter.com/issues/Reporter-Issue-1419.pdf __ኃይል   ከበደ «ምስካይ» (2004)
         :- http://enaseb.blogspot.com/2013/12/blog-post_2986.html 
         :-  የ ኛ ጉ ዳ ይ - Yegna Guday Blog

Thursday, September 25, 2014

የመስቀል በዓል


ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ እንዴት መጣ? የመስቀል በዓል እንጨት ተደምሮ እሳት ተቀጣጥሎ ለምን ይከበራል? ለመስቀሉ መገኘት የሮሙ ንጉስ ቆስጠንጢኖስ እና የንግስት ዕሌኔ ሚና ምን ነበር?

***********************************************************************************

ፎቶ -በዩኔስኮ በዓለም ቅርስነት የተመዘገበው የመስቀል ደመራ በዓል  በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ

ዕሌኒና ተርቢኖስ


ዕሌኒና ተርቢኖስ የሚባሉ ሁለት ደጋግ ክርስቲያኖች ተጋብተው ይኖሩ ነበር፡፡ተርቢኖስና ዕሌኒ ኑሮአቸው ፍቅርና ሰላም የሰፈነበት በመሆኑ ለብዙ ሰዎች እንደ ምሳሌ ሆነውይኖሩ ነበር፡፡ ተርቢኖስ ነጋዴ ነበር፡፡ከዕለታትአንድቀን ራቅ ወዳለ ሀገር በመርከብለንግድ ሄደ፡፡ ዕሌኒም ባለቤቷ ተርቢኖስ ለንግድ ወጥቶ እስኪመለስ ስለባሏ ከመጸለይና ከማሰብ በቀር ከግቢዋ አትወጣም ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ተርቢኖስ ለንግድ ሄዶ ብዙ ዓመታትን ቆይቶ ከጓደኞቹ ጋር ወደሀገሩ ሲመለስ ከነጋዴዎች አንዱ በእግዚአብሔር ፈቃድ ከሽፍታና ከማዕበል ከልዩ ልዩ አደጋ ተርፈን በሰላም ተመልሰን ግን ሚስቶቻችን ሌላ ሳይወዱ ሳይለምዱ እናገኛቸው ይሆን? ብሎጠየቀ፡፡ ተርቢኖስ ግን "እንኳን በሰላም አደረሰን እንጂ ሚስቴን በዚህ አልጠረጥራትም" ብሎ ሲመልስ ሌላው ጓደኛው "ያንተሚስት ከማን ትበልጣለችና ነው አሁን ሄጄ ከሚስትህ ጋር ለምዳኝ ወዳኝ ወድጃት ብመጣስ ምን ይቅጣህ?" አለው፡፡


ተርቢኖስም በሚስቱ እሌኒ ተማምኖና ይህንን ብታደርግ ይህን ያህል ዓመት የለፋሁበት ሀብት ከነትርፉ ውሰድ አንተም ብታደርግ እንዲሁ ሀብትህ ከነትርፉ ለእኔ ይሁን ተባብለው ተወራረዱ፡፡ከዚያም መርከቡ ወደብ ከመድረሱ በፊት ነጋዴው ወደ ዕሌኒ ቤት ደረሰና በሩን አንኳኩቶሠራተኛይቱን ዕሌኒን ማነጋገር እፈልጋለሁና ንገሪልኝ ብሎ ጠየቃት፡፡ እሷም እያፈረችየተላከችውን ለዕሌኒ ነገረቻት ዕሌኒም ተቆጥታ ከመች ወዲህ ነው እንግዳ የማነጋግረው ብላ አሳፈረቻት፡፡

ሠራተኛይቱም ለነጋዴው መልሱን ስትነግረው ነጋዴው እንደማይሆንለት ከተረዳበኋላ ሌላ ተንኮል አቀደና ለሠራተኛይቱ ባልና ሚስቱ ብቻ የሚያውቁትን አንድ ነገር ብቻብትሰጪኝ ብዙ ገንዘብ ወርቅ እሰጥሻለሁ ብሎ ወርቅ ሰጣት፡፡ ሠራተኛይቱም ሁለቱ ብቻ የሚያውቁትን የእመቤቴ ሀብል አለ ያንን እመጣልሀለሁ መጀመርያ አንተ በከተማው ውስጥ እየዞርህነጋዴዎችን መጡ የብስ ረገጡ እያልክ አስወራ ከዚያም ተመልሰህ እንድትመጣ ብላ ሰደደችው፡፡ነጋዴውም እንደተመከረው የነጋዴዎቹን መምጣት በከተማይቱ እንዳወራ የነጋዴዎቹ ቤተሰቦችነጋዴዎችን ለመቀበል ዝግጅት ማድረግ ጀመሩ፡፡ የዕሌኒም ሰራተኛ እመቤቴ ነጋዴዎች መጡተብሎ ይወራልና፡፡ ባለቤትዎ በሰላም ስለመጡ ይዘገጃጁ ገላዎን ይታጠቡ ብላ መከረቻት፡፡ዕሌኒም ገላዋን ስትታጠብ ያንገቷን ሐብል ቁጭ ካደረገችበት ቦታ ሠራተኛይቱ አንስታ ለነጋዴውበተቃጠሩበት ዕለት ሰጣች፡፡ ነጋዴውም ለሠራተኛይቱ የውለታዋን ብዙ ገንዘብ ሰጥቶአት ደስእያለው ወደ ጓደኞቹ ሄደ፡፡ ለተርቢኖስ ሚስትህን ለምጃት ወድጃት መጣሁ አለው ተርቢኖስምውሸት ነው ለዚህ ምን ምልክት አለህ ብሎ ጠየቀው፡፡ ተንኮለኛውም ነጋዴ ያንን ሐብል አውጥቶይህ ሐብል የሚስትህ አይደለምን ብሎ ሰጠው ተርቢኖስም ደነገጠ የሚናገረውን አጣ፡፡በውርርዱምመሰረት ሀብቱን ሁሉ አስረከበና ባዶ እጁን ወደቤቱ እያዘነ እየተቆጨ ሔደ፡፡


ባለቤቷንበናፍቆትና በታማኝነት ስትጠብቅ የከረመችው ዕሌኒ በተርቢኖስ ያልተለመደ ሀዘንና ብስጭት ግራተጋብታ ወንድሜ ምን ሆነሀል? ለወትሮው እንኳን ይህን ያህል ዘመን ተለያይተን ቀርቶ ለጥቂትቀናት ተለያይተን እንኳ ለጥቂት ቀናት ተለያይተን ስንገናኝ እንነፋፈቃለን፡፡ አሁን ግን ከመጣህበትጊዜ ጀምሮ አዝነህ አይሀለሁ ብላ ጠየቀችው፡፡ ተርቢኖስም ብዙ የደከምኩበትና የለፋሁበት ሀብትንብረቴ እንዳለ ማዕበል አጠፋብኝ እኔ ያላዘንኩ ማን ይዘን አላት፡፡ እሌኒም የተማረች ናትናእግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሣ የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን እንዳለ ኢዮብን አስበውአንተ እንኳን በሰላም መጣህ እንጂ ሀብቱ ውሎ አድሮ ይመጣል፡፡ እያለች አጽናናችው፡፡ተርቢኖስም እንግዲህ በተከበርኩበት ሀገር ተዋርጄ፣ በሰጠሁበት ሀገር ለምኜ ለመኖር አልችልምናወደሌላ ወደማያውቁኝ ሀገር እሔዳለሁ አንቺ ግን ሁሉ ይወድሻል ያከብርሻል ከወደድሸው ጋር ኑሪአላት፡፡ ዕሌኒም በደስታ ጊዜ አብሬህ እንደሆንኩ በችግርም ጊዜ ልለይህም የኔንና ያንተን አንድነትችግር አይፈታውም ከአንተ ተለይቼ ወዴት እቀራለሁ ወደምትሄድበት አብሬህ እሄዳለሁ ብላተነሳች፡፡

ሁለቱም ቤታቸውን ጥለው ሲሄዱ በመንገድ ላይ ተርቢኖስ በልቡናው ይዞት የነበረውን ምሥጢርአወጣው "ዕሌኒ ስወድሽ የጠላሽኝ ሳምንሽ የከዳሽኝ ምን አድርጌሽ ነው?" ብሎ ጠየቃት፡፡ ዕሌኒምእኔ አንተን አልጠላሁም አልከዳሁምም ይህንን ሐሳብ እንዴት አሰብህ ብትለው ከኪሱ አውጥቶሐብሉን አሳያትና የሆነውን ሁሉ ነገራት፡፡ ዕሌኒም ያልጠበቀችው ነገር ስለተፈጸመ አዝና የሆነውንእውነተኛ ታሪክ በሙሉ ነገረችው፡፡

ተርቢኖስ ግን አላመናትም፡፡ ከባህር ዳር በደረሱ ጊዜ በቁመቷልክ ሳጥን አሠርቶ ዕሌኒን በውስጡ አስገባትና ብታደርጊውም ባታደርጊውም እንደሥራሽ ሥራሽያውጣሽ ብሎ ወደ ባህሩ ወረወራት፡፡ ዕሌኒ ያለችበት ሳጥን በፈቃደ እግዚአብሔር እየተንሳፈፈከወደብ ደረሰ በዚያ ወደብ አካባቢ ምዕራብ ሮምን ያስተዳደር የነበረው ኮስታንዲዮስ /ቁንስጣ/የተባለው ንጉሥ ነበርና ሳጥኑን አይቶ አውጥቶ እንዲከፍቱት ወታደሮችን አዘዘ፡፡ ሳጥኑንአውጥተውም ሲከፍቱት እጅግ የተዋበች ሴት ሆና አገኟት ንጉሡም ዕሌኒን ወስዶ ሚስቱአደረጋት፡፡ ኮስታንዲዮስ /ቁንስጣ/ የመክስምያኖስ ቄሳር ሆኖ ምዕራብ ሮምን ያስተዳደር ነበር፡፡ንግስት ዕሌኒም በ272.ም ታላቁ ቆስጠንጢኖስን ወለደችለት ቆስጠንጢኖስም ገና በወጣትነቱየአባቱ እንደራሴ ሆኖ እንደሠራ አባቱ ሞተ፡፡ የአባቱ ባለሟሎችና ህዝቡ ተስማምተው የ18ዓመቱን ቆስጠንጢኖስን በአባቱ ቦታ ሐምሌ 25 ቀን 316 .ም በሮም ምዕራብ ክፍል በገላትያአነገሡት፡፡ በጦር ሜዳዎች ብዙ የጀግንነት ሥራዎች ስለሰራ በሠራዊቱ ዘንድ ይወደድ ነበር፡፡

ንግሥት ዕሌኒ ልጅዋን ቆስጠንጢኖስን ከልጅነቱ ጀምሮ ስለክርስትና ሃይማኖትና ስለክርስቲያኖችመከራ ታስተምረው ስለነበር በክርስቲያኖች ላይ የነበረው አመለካከት በሮም ከነገሡት ቄሣሮች ሁሉየተሻለ ነበር፡፡ በተለይም በ312.ም ከጠላቱ ከመክስምያኖስ ጋር ለመዋጋት ምታ ነጋሪት ክተትሠራዊት ብሎ ለዘመቻ እንደተሰለፈ በራዕይ በሰማይ ላይ "በዚህ መስቀል /ምልክት/ ጠላትህን ድልታደርጋለህ" የሚል መስቀልና ጽሑፍ ስላየ ለሠራዊቱ የመስቀል ምልክት በመሳሪያቸው እናበሰንደቅ ዓላማው ላይ እንዲያደርጉ አዘዘ፡፡ ወደያው ጦርነት ቢገጥም በቲቤር ወንዝ ድልድይ ላይጠላቱን ድል ነስቶ በጠቅላላው የሮም መንግስት ግዛቶች ሁሉ ገዥሆነ፡፡

ታላቁ ቆስጠንጢኖስ የሮም ንጉሠ ነገሥት

ታላቁ ቆስጠንጢኖስ የሮም ንጉሠ ነገሥት ከሆነ በኋላ በ300 ዓመታት ውስጥ ለመጀመርያ ጊዜለክርስቲያኖች የነጻነት ዐዋጅ ዐወጀ፡፡ ክርስትናም ብሔራዊ ሃይማኖት ተባለች፡፡ ንግሥት እሌኒምበተፈጠረላት አመች ሁኔታ በመጠቀም የጌታችን መስቀል ከተቀበረበት ለማውጣት በ327.ም ወደኢየሩሳሌም ሔደች፡፡ ዕሌኒ ልጅዋ ቆስጠንጢኖስ ክርስቲያን ከሆነላት ወደ ኢየሩሳሌም ሔዳመስቀሉን ለመፈለግ እንዲሁም በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳት መካናትንና አብያተ ክርስቲያናትንለማሳነጽ ለእግዚአብሔር ተሳለች፡፡ ከዚህ በኋላ ቆስጠንጢኖስ አምኖ በ337.ም ተጠመቀ፡፡ቅድስት ዕሌኒ ወደ ኢየሩሳሌም ሔደች ከእርሷም ጋር ብዙ ሠራዊት ነበር፡፡ እንደደረሰችም ስለከብረ መስቀል መረመረች ጠየቀች፡፡ ቦታውን የሚያስረዳት አላገኘችም፡፡ የአይሁድ ወገን እንቢቢሉም በኋላ ግን ባደረገችው ጥረት አረጋዊው ኪራኮስ የጎልጎታን ኮረብታ አመለከታት አስቆፍሪውብሎ ነገራት ኪራኮስም ዘመኑ ከመርዘሙ ጋር ተያይዞ እውነተኛው ተራራ ይህ ነው ብሎ ማሳየትባለመቻሉ ከሦስቱ ተራሮች አንዱ ነው ስላላት አይሁድ ተራሮቹን ይቆፍሩ ዘንድ አዘዘቻቸው፡፡የጌታችን ቅዱስ መስቀል ከጌታ ሞት እያመነ በተቸገሩ ግዜ ማንም እንዳያገኘው የኢየሩሳሌም ነዋሪሁሉ የእቤቱን ቆሻሻ የከበረ መስቀል ባለበት ቦታ እንዲጥል አይሁድ አዝዘው ስለነበር ከሁለት መቶዓመት በላይ ጥራጊ ስለጣሉበት ታላቅ ተራራ ሆነ፡፡

ንግስት ዕሌኒ እና የመጀመርያው ደመራ

ዕሌኒ ተራሮቹን ለማስቆፈር ከሦስቱ ተራሮች የቱ እንደሆነ ለመለየት ደመራ አስደምራ ብዙእጣንም በመጨመርና በማቃጠል ከአኢየሩሳሌም ወጣብለውያሉትንኮረብቶች አሳያት፡፡ የእጣኑ ጢስ ወደ ሰማይ በመውጣት በቀጥታ ተመልሶ መስቀሉ ባለበት ተራራ ላይ በማረፍናበመስገድ መስቀሉ ያለበትን ትክክለኛ ስፍራ አመለከታት፡፡ ቅዱስ ያሬድም "ሰገደ ጢስ" ጢሱሰገደ ብሎታል፡፡ ከዚያም መስከረም 16 ቀን ቁፋሮው እንዲጀመር አዘዘች፡፡ ሰባት ወር ያህልከተቆፈረ በኋላ መጋቢት 10 ቀን ሦስት መስቀሎች በአንድነት ተገኙ፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችንየተሰቀለበት የትኛው እንደሆነ ለማወቅ ተቸገሩ፡፡ የሞተ ሰው አምጥተው በሁለቱ መስቀሎች ላይበተራ ቢያስቀምጡት አልተነሣም፡፡ በመጨረሻ በአንዱ መስቀል ላይ ቢያስቀምጡት ያን ጊዜየሞተው ሰው ተነሣ፡፡ በዚህም የጌታን መስቀል ለዩት፡፡ ዕሌኒም የጌታ መስቀል እንደሆነ አወቃሰገደችለት፡፡ ክርስቲያኖች ሁሉ ሰገዱለት፡፡ በየሀገሩ ያሉ ክርስትያኖች ሁሉ የመስቀሉን መገኘትበሰሙ ግዜ መብራት አብርተው ደስታቸውን በመግለጥ ለዓለም እንዲታወቅ አደረጉ፡፡ በዚህምምክንያት ይህ ታላቅ የድኅነት ምልክት የሆነው መስቀል የኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ደመራበመደመር በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ታከብረዋለች፡፡


 
ንግሥትዕሌኒ መስከረም 16 ቀን 320.ምበዕጣን ጢስ ምልክት ቁፋሮ አስጀምራ መጋቢት 10ቀን አግኝታ በማውጣት ታላቅ ቤተመቅደስ ጎልጎታ ላይ ሠርታ በክብር አስቀመጠችው ይህመስቀልም ከዚያ ዕለት ጀምሮ እንደ ፀሐይ እያበራ ድውይ እየፈወሰ አጋንንት እያባረረ ልዩ ልዩተአምራት እየሰራ ሙት እያነሳ ዕውር እያበራ ተአምራቱን ቀጠለ፡፡ ይህንንም ከኃያላን ነገሥታትመካከል የፋርስ ንጉሥ መስቀሉን ማርኮ ፋርስ ወስዶ አስቀመጠው፡፡ በዚህ ጊዜ የአየሩሳሌምምዕመናን የድሉን ዜና ሰምተው ስለነበር የአንድ ቀን መንገድ ያህል ሄደው በመቀበል ካህናቱበዝማሬና በቸብቸቦ ወንዱ በሆታ ሴቱ በእልልታ ሆ! እያሉና ችቦ አብርተው ተቀብለዋቸዋል፡፡የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንም ለመስቀል ችቦ እያበሩ በዓሉን በሆታ በእልልታበስብሐተ እግዚአብሔር የምታከብረው ይህንን ታሪካዊ ትውፊት በመከተል ነው፡፡ ብዙየቤተክርስቲያን አባቶች እንደሚሉት ንጉሡ ሕርቃል ይህንን ታላቅ ድል ለማግኘትና የጌታን ቅዱስመስቀል ከአሕዛብ /ከፋርሶች/ እጅ ለማስመለስ የቻለው በዚያን ጊዜ አብያተ ክርስቲያንናት ሁሉለአንድ ሳምንት /አንድ ሱባዔ/ ባደረጉት ጾም ጸሎት ነው፡፡ ይህንንም ለማስታወስና ጌታንለማመስገን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንና የግብጽ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያንበየዓመቱ የዐቢይ ጾም /የጌታ ጾም/ ከመጀመሩ አስቀድሞ "ጾመ ሕርቃል" ብለው አንድ ሳምንትይጾማሉ፡፡

የጌታ መስቀል ለብዙ ግዜያት ኢየሩሳሌም ከቆየ በኋላ ነገሥታት ይህን መስቀል እኔ ልውሰድ እኔልውሰድ በማለት ጠብ ፈጠሩ፡፡ በዚህ ጊዜ የአንጾኪያ፣ የኤፌሶን፣ የአርማንያ፣ የግሪክ፣የእስክንድርያ፣ የመሳሰሉት የሃይማኖት መሪዎች ጠቡን አበረዱት ከዚያም አያይዘው በኢየሩሳሌምየሚገኘውን የክርስቶስን መስቀል ከ4ት ከፍለው በዕጣ አድርገው በስምምነት ተካፍለው ከሌሎችታሪካዊ ንዋያተ ቅዱሳት ጋር በየሀገራቸው ወስደው በክብር አስቀመጡት የቀኝ ክንፉ የደረሰውለአፍሪቃ ስለነበር ከታሪካዊ ንዋየ ቅዱሳት ጋር በግብጽ የሚገኘው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ተረክቦወስዶ በክብር አስቀመጠው፡፡


ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ እንዴት መጣ?


ግማደ መስቀሉ ለብዙ ዘመን በእስክንድርያ ሲኖሩ በግብጽ ያሉ እስላሞች እየበዙ ኃይላቸውእየጠነከረ ሲሔድ በእስክንድርያ የሚኖሩ ክርስትያኖች ላይ ሥቃይ ያጸኑባቸው ጀመር፡፡ክርስቲያኖቹም አንድ ሆነው መክረው ለኢትዮጵያዊው ዓጼ ዳዊት እንዲህ የሚል መልእክት ላኩ"ንጉሥ ሆይ! በዚህ በግብጽ ያሉ እስላሞች መከራ አጽንተውብናልና ኃይልህን አንሥተህአስታግስልን ብለው ጠየቁት ዳግማዊ ዓጼ ዳዊትም ለመንፈሳዊ ኃይማኖት ቀንተው የክርስቶስ ፍቅርአስገድዷቸው 20,000 ሠራዊት አስከትለው ወደ ግብጽ ዘመቱ በዚህ ጊዜ በግብጽ ያሉ ኃያላን ፈሩተሸበሩ ንጉሡ ዳግማዊ ዳዊትም እንዲህ የሚል መልዕክት ለእስላሞቹ ላከ በተፈጥሮ ወንድሞቻችሁከሆኑት ክርስቲያኖች ካልታረቃችሁ ሀገራችሁን መጥቼ አጠፋለሁ" የሚል ማስጠንቀቂያ ላከ፡፡የንጉሡ መልዕክትም ለእስላሞቹ እንደደረሳቸው ፈርተው እንደ ጥንቱ በየሃይማታቸው ጸንተውበሰላም እንዲኖሩ ከክርስቲያን ወንድሞቻቸው ጋር ታረቁ፡፡ መታረቃቸውን ዓጼ ዳዊት ሰሙበዚህም ጉዳይ ንጉሡ ደስ አላቸው፡፡

እግዚአብሔርንም አመሰገኑ በግብጽ የሚኖሩ ክርስቲያኖችምከ12,000 ወቄት ወርቅ ጋር ደስታቸውን ለኢትዮጵያዊው ንጉሥ ለዳግማዊ ዳዊት በደብዳቤአድርገው ላኩላቸው፡፡ ንጉሡም የደስታውን ደብዳቤ ተመልክተው ደስ አላቸው ወርቁን ግንመልሰው በመላክ እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጻፉ፡፡ በግብጽ የምትኖሩ የክርስቶስ ተከታዮች ሁሉ እንኳን ደስ አላችሁ የላካችሁልኝ 12,000 ወቄት ወርቅ መልሼ ልኬላችኋለሁ፡፡ የእኔ ዓላማ ወርቅፍለጋ አይደለም የክርስቶስ ፍቅር አስገድዶኝ በተቻለኝ ችግራችሁን ሁሉ አስወገድኩላችሁ አሁንምየምለምናችሁ በሀገሬ ኢትዮጵያ ረሀብና ቸነፈር ድርቅ ስለወረደብኝ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስየተሰቀለበት ቅዱስ መስቀልና የቅዱሳን አጽም ከሌሎች ክቡራን ዕቃዎች ጋር እንድትልኩልኝ ነውየሚል ነበር፡፡

በእስክንድርያም ያሉ ምዕመናን ይህ መልዕክት እንደደረሳቸው ከሊቃነ ጳጳሳትና ከኤጲስ ቆጶሳቱጋር ውይይት በማድረግ ይህ ንጉሥ ታላቅ ክርስቲያን ነው፡፡ ስለዚህ ልቡን ደስ እንዲለውየፈለገውን የጌታችንን ግማደ መስቀል ከቅዱሳን አጽምና ንዋየ ቅዱሳት ጋር አሁን በመለሰው ወቄትወርቅ የብርና የነሐስ የመዳብና የወርቅ ሣጥን አዘጋጅተን እንላክለት ብለው ተስማምተው በክብርበሥነ ሥርዓት በሠረገላና በግመል አስጭነው ስናር ድረስ አምጥተው ባስረከቧቸው ጊዜ በእጃቸውእያጨበጨቡ በእግራቸው እያሸበሸቡ በግንባራቸው እየሰገዱ በክብር በደስታ ተቀበሏቸው፡፡

ግሸን ደብረ ከርቤ ግማደ መስቀሉ የሚገኝበት
 
ግማደ መስቀሉ ወደ መካከለኛው ኢትዮጵያ ሳይደርስ በድንገት ዓጼ ዳዊት ስናር በሚባልበረሀ ላይአረፉ፡፡ ግማደ መስቀሉም የግድ በዚያው በስናር መቆየት አስፈለገው፡፡ ከዚህ በኋላ የሟቹየዳግማዊ ዳዊት ልጅ ዓጼ ዘርዓ ያዕቆብ እንደነገሠ ወደ ስናር ሔደው ግማደ መስቀሉን ከሌሎቹንዋያተ ቅዱሳት ጋር አምጥተው በመናገሻ ከተማቸው በደብረ ብርሃን ላይ ቤተመቅደስ ሠርተውለማስቀመጥ ሲደክሙ በሕልማችው ‘’ አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል‘’ ወዳጄ ዘርዐ ያዕቆብሆይ መስቀሌን በመስቀለኛ ቦታ ላይ አስቀምጥ የሚል ሕልም አዩ፡፡

ከእስክንድርያሀገር ከመስቀሉ ጋር በልዩ ልዩ ሣጥን ተቆልፈው የመጡትም ዝርዝር ስማቸው ጌታ በዕለተ ዓርብ ለብሶት የነበረው ቀይ ልብስ፣ ከሮም የመጣው ከለሜዳው፣ ሐሙት የጠጣበት ሰፍነግ /ጽዋ/፣ ዮሐንስ የሳለው ኩርዓተ ርዕሱ ስዕል እንዲሁም የተለያዩ የቅዱሳን አጽም፣ ከግብጽ ታላላቅ ገዳማት የተቆነጠረአፈር፣የዮርዳኖስውሃይገኛል፡፡ ንጉሡም መስቀለኛ ቦታ እየፈለጉ በኢትዮጵያ አውራጃዎች ሁሉበመፈለግ ከብዙ ቦታ አስቀምጠውት ነበር፡፡ ለምሳሌ በሸዋ በደብርቅዱስደብረጽጌ ማርያምገዳም፣ በማናገሻ ማርያም፣ በወጨጫ መስቀሉን አሳርፈውት ነበር፡፡ ነገር ግን የመጨረሻውን ቦታባለማግኘታቸው በራዕይ እየደጋገመአንብርመስቅልየበዲበመስቅል መስቀሌን በመስቀለኛ ሥፍራአስቀምጥ እያለ ይነግራቸው ነበር፡፡ ዓጼ ዘርዓ ያዕቆብም ለሰባት ቀን ሱባዔ ገቡ፡፡

በዚያምየተገለጸላቸው መስቀለኛውን ቦታ የሚመራህ ዓምደብርሃን ይመጣል አላቸው፡፡ እርሳቸውም ከዚያእንደወጡ መስቀለኛውን ቦታ የሚመራ የብርሃን ዓምድ ከፊታቸው መጥቶ ቆመ፡፡ በዚያ መሪነትወደ ወሎ ክፍለ ሀገር አምባሰል አውራጃ ውስጥ ግሸን ከምትባል አምባ መርቶመስከረም21ቀን1440ዓም አደረሳቸው፡፡ በእውነትም ይህች ግሸን የተባለችው አምባ ጥበበኛ ሰው እንደቀረጻትየተዋበች መስቀለኛ ቦታ ሆና ስላገኟት የልባቸው ስለደረሰ ደስ አላቸው፡፡ በዚያም አምባ ታላቅቤተመቅደስ ሰርተው መስቀሉንና ሌሎች ንዋየ ቅዱሳቱን በየመዓረጋቸው የክብር ቦታ መድበውአስቀመጡዋቸው፡፡ ዘመኑም በ14ኛው ክፍለ ዘመን ነው፡፡


የመስቀል በዓል በኢትዮጵያ


በሀገራችን በኢትዮዽያ የመስቀል በዓል የሚከበረው አበቦች በሚፈኩበት የጥቢ ወራት መግቢያ በመኾኑ ጸሎቱም (መስቀል ኣብርሃ በከዋክብት አሠርገወ ሰማየ እምኵሉሰ ፀሐየ አርኣየ) ሲሆን ሕዝባዊ ዜማውም (ኢዮሀ አበባዬ ÷ መስከረም ጠባዬ)በማለት የመስቀልን ክብር ሳይለቅ ነው፡፡

በተያያዘም በወሎ ክፍለ ሀገር በአንባሰል አውራጃ ውስጥ ግሸን ማርያም የምትባል ደብር ትገኛለች፡፡ግሸን አምባ ከአዲስ አበባ 480 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ቅድስት ሥፍራ ናት። ይህች ደብር በሐይቅና በመቅደላ በደላንታ በየጁ መካከልና በበሽሎ ወንዝ አዋሳኝ በርዋ አንድ ዙርያውን በገድል የተከበበች አምባ ናት፡፡ በበርዋ ከተገባ በኋላ ግቢዋ፣ ከላይ ሜዳና መስቀለኛ ቦታ ነው፡፡ ወደዚህች ደብር ለመሔድ በረሃን አቋርጦ ተለያየን ወንዝና በሽሎን በመሻገር የተጠማዘዘ አስፈሪ ገደሉን ማለፍ ግድ ይላል፡፡ ግሸን የመጀመርያ ስሟ ደብረ እግዚአብሔር በመባል ይጠራ ነበር፡፡

ይህ ደብረ እግዚአብሔር የሚለው ስያሜም በጻድቁ ንጉሥ ላሊበላ እጅ ከቋጥኝ ድንጋይ ተፈልፍሎ
 
የተሠራ ቤተመቅደስ በእግዚአብሔር አብ ስም ስለነበረ ደብረ እግዚአብሔር ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ ከዚያም በዓጼ ድግናዥን ዘመነ መንግሥት የሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም ሲመሰረት ሐይቅ ደብረ ነጐድጓድ ተብሎ ሲሰየም ግሸን የሐይቅ ግዛት ስለሆነች ደብረ እግዚአብሔር ተብላለች፡፡ ከዚያም በ14ኛው መቶ ከፍለ ዘመን ላይ በዓጼ ዘርአያዕቆብ ዘመነ መንግስት ግማደ መስቀሉ ግሸን ገብቶ ሲቀመጥ ደብረ ነጐድጓድ የሚለው ደብረ ከርቤ በማለትተቀይሮአል፡፡ በጊሸንደብረከርቤ አምባ በሁሉም ማዕዘንአብያተ ክርስቲያናት የታነፁ ሲሆን ከመስቀሉ ራስጌ የእመቤታችን፣ ከመስቀሉ ግርጌ የቅዱስሚካኤል ከቀኝ ክንፉ ላይ ቅዱስ ገብርኤል ከግራ ክንፉ ደግሞ ቅዱስ ዑራኤል ሲሆኑ መካከሉ ላይመስቀሉ የተቀበረበት የእግዚአብሔር አብ ቤተክርስቲያን ይገኛል፡፡
***************************************************************************ምንጭ:--ጉዳያችን(http://gudayachn.blogspot.no/2013/09/blog-post_22.html)