ከደራሲያን ዓምባ

Wednesday, October 19, 2022

እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ

 


በቅድሚያ ሦስቱ የኪነት አበባዎች ብዬ የሰየምኳችሁ ቅድስት ይልማ፣ አዜብ ወርቁና ቤዛ ኃይሉ ደራሲነት የሁሉም ተዋንያን ድንቅ ችሎታና ብቃት ለታየበት “እረኛዬ” ተከታታይ ተውኔት ያለኝን አድናቆት ስገልጽ በምሥጋናዬ ውስጥ አገሬና ሕዝባችን እየታዩኝ ነው።

ስለአገራችን ኢትዮጵያና ስለሕዝቧ በርካታ ድምፃውያን፣ ደራሲያን፣ የሥነ ጽሑፍ ሰዎች፣ ሠዓሊያን፣ ተዋንያን እንደየዘርፋቸው አዚመዋል፣ አንጎራጉረዋል።  ከያኒያን አገሬን ብለው ገጥመዋል፣ ሰንደቅ ዓላማዋን ከፍ አርገዋል፣ ወንዞች ተራሮቿን ዳሰዋል፣ ዓባይን ከብዕራቸው አፍስሰው ስንኝ ቋጥረው አድንቀዋል፣ ኢትዮጵያችንን አንድ መጽሐፍ ከሚገልጸው በላይ በሥዕሎቻቸው ተናግረውላታል።

ከአንድ የፖለቲካ ድርጅት፣ ወይም ታዋቂ የፖለቲካ ተንታኝ ነን ብለው እንደ አሸን ከሞሉት ምሁራን በእጅጉ በሚያስንቅ ሁኔታ ድምፃውያን ኢትዮጵያን ከፍ አድርገዋታል። የአገር አንድነት እንዳይዛባ በድምፃቸው ጮኸዋል፣ መድረክ ላይ ወጥተው ጀግኖችን ቀስቅሰዋል፣ አወድሰዋል። ታሪክን አዚመዋል፣ ቅርስን አስተዋውቀዋል።

በዚህ ጽሑፌ በቅርቡ የተጠናቀቀው የ“እረኛዬ” ተከታታይ ተውኔት የዜማ ቅላፄ፣ የቅኔ ዘረፋ፣ የመቼት መረጣ፣ የአብሮነት ዜማ፣ የእናትነት አንጀት፣ የሃይማኖት ክብሩ፣ የዘራፊን ምግባሩ፣ ኢትዮጵያዊነት ክብሩ፣ ደግነቱ፣ አብሮነትን፣ ይቅር ባይነትን፣ የትውልድ፣ የታሪክ፣ የአገር፣ የቋንቋ፣ የባህል፣ የዘር፣ የሃይማኖት፣ የሰው በሰው ሥራ ሌላም ሌላ እውነትን አፍክቶ፣ ማንነትን አውጥቶ፣ ስሜትን ገዝቶ ከመደነቅ አሻግሮ ዛሬም ትውልድ አለ፣ ዛሬም ነገም አገር አለች፣ ያስባለኝን ውስጤን በመጠኑም ቢሆን ለአንባቢያን ላጋራ ፈለግሁ።


“እረኛዬ” አሸንፏል! በዘርና በቋንቋ በተከለለች አገር ዘረኝነት ላይ ዘምቷል፣ በሙስና በተጨማለቀች አገር ሌብነትን አጋልጧል፣ አኩሪ ባህሉን እንዲዘነጋ በተደረገ ትውልድ ላይ “ባህሌን አገሬን” አዚሟል፡፡ በጥላቻ፣ በቂም ላይ ፍቅርን፣ ይቅር ባይነትን ሰብኳል፡፡ በትዳር ውስጥ የእናት ሆድ ዥንጉርጉርነትን ተንተርሶ የእናትነት መንሰፍሰፍን ዳሷል። ሌላም ሌላ፡፡ ከደራሲያኑ ብጀምር የሴቶችን ጠንካራ አመራር ሰጪነትና ኅብረት “እረኛዬ” ይመሰክራል። ዛሬ አንዱ ለአንዱ ምቀኛና ቀናተኛ በሆነበት አገራችን በጋራ ሠርተው የጋር ፍሬያቸውን በጋራ እንድንመለከት፣ እንድንመሰጥ፣ እንድንገረም፣ እንድናለቅስና እድንጓጓ እያደረገ የተጓዘ ተውኔት ነበር ብል አብዛኞች ይጋሩኛልና ልክ ነኝ።

“እረኛዬ” ኪነት ለአገር፣ ኪነት ለኢትዮጵያ፣ ኪነት ለሕዝብ ምን ያህል ጠቀሜታ እንዳለው ከአንድ የፖለቲካ ፓርቲ በላይ ሥር የሰደደ መልዕክት የተላለፈበት ተውኔት ነው። “እረኛዬ” በጨለማ ውስጥ የደመቀ ኮከብ ነው። ደምቆም አላቆመም ተወርዋሪ ሆኖ ሕዝብ ጋ ደርሷል።    

“እረኛዬ” በአብነት መንደር ኢትዮጵያዊነትን ረጭቶ በእማማ ቸርነት ጎጆ መማር ለፈለገ ትህትናን፣ ቀናነትን፣ አብሮነትን አስተምሮ የተጓዘ ተውኔት ነው፡፡ ወግን፣ ጥጋብን፣ ጥበብን፣ ፍቅርን፣ እንባን፣ ዝላይን፣ ጭፈራን፣ ታዛዥነት፣ ትህትናን፣ በእናና አጋጅነት ተሰባስበው የተረጩበት ተውኔት ጎልቶ የታየበት ተመልካችን ያስደመመ ሁሉም ዘር ዓይንና ጆሮ የሰጠው ተውኔት ደራሲያኑንና ከኒያኑን በጥቅሉ በ“እረኛዬ” ላይ አሻራቸውን ላሳረፉ ሁሉ ደስ….ስ ስላለኝ አመሠግናለሁ።

በዚህ አጋጣሚ ስለአገራችን ኢትዮጵያ በርካታ ድምፃውያን አድምቀው አንጎራጉረዋል። ሁሉንም ባይሆን ስሜቴን ከኮረኮሩት ውስጥ ትንሽ ልበልና ላስታውሳቸው፡፡ ዛሬ ከመድረኩ ራቅ ብትልም ሕወሓት/ኢሕአዴግ “ጉሮ ወሸባዬ” ብሎ የዛሬ 31 ዓመት ይዞት የተነሳውን ዘረኝነት ገና ከጅምሩ ‹‹የዘር በሽታ፣ መድኃኒት አለው የማታ ማታ›› ብላ አንጎራጉራ የፍቅር ረሃቧን ለአየር ያበቃችው ጂጂ እምቅ ሥራዎችን መለስ ብዬ እንድቃኝ አድርጎኛል። ‹‹ጎጃም ያረሰውን ወለጋ ካልሸጠ፣ የሸዋ ሰው ልጁን ለትግሬ ካልሰጠ›› ምኑን አገር አለች አገርስ ያሰኛል፡፡ ብላ ቀደምት ሙግቷን ለአገር ያበረከተችው ሥራዋ ዛሬም ነገም ሲታወስ ይኖራል።

ለዓባይ ያላዜመ ድምፃዊ ባይኖርም ስለዓባይ ሲጻፍ፣ ሲተረክ ለአገሩና ለሕዝቡ አገልጋይ ይሆን ዘንድ “ዓባይ ወቶ አዳሪ…” ብላ ዘለዓለማዊ ድምጿን ከሕዝብ አድርሳለች። የስደት ሕይወትን ከአገሯ ባህል ጋር ስትገልጸው በአጭር አገራዊ አገላለጽ “የሰው በግ እያየሁ…” ስትል ቅኔዋን ዘርፋለች። ዛሬ እምን ሁኔታ ላይ እንዳለች ባላውቅም ጂጂ ብልጭ ብላ ድርግም ያለችብኝ አገርን በፍቅር፣ ባህላችንን በወግ አላስነካ ያለች ጎበዝ “ስንት በሠራች” ቁጭት ይወረኛል። “አልወድም ጎበዝ ጀግና ሲረሳ” ብላ ለጀግኖቻችን እስትንፋስ የሰጠች ኪነት ለኢትዮጵያ ያበረከተች፣ ኢትዮጵያዊነት መሠረት ውሉ እንዳይበጠስ አጥብቃ የተውረገረገች ዜመኛ ሥራዋ ሁሌም ይጠራታል።

ወያኔ/ሕወሓት ሕዝብ ሆነበትና ባይገድለውም የምሬት ዳርቻቸው ለእስር የዳረገው የኢትዮጵያ ልጅ ቴዲ አፍሮ ዕውን ማን እንደ እሱ ለአገር ሞገተ? ማን እንደ እሱ ስለአንድነት ሰበከ? ማን እንደ እሱ ኢትዮጵያዊነትን አነቃነቀ? ማን እንደ እሱ ምኒልክ፣ ቴዎድሮስ ላይ ስቅታ ለቀቀ ቢባልለት ሲያንሰው ነው።

የዛሬ 17 ዓመት ከ1997 ዓ.ም. የምርጫ ዋዜማ ለአየር በቅቶ ፖለቲከኞቻችን ገደል ቢከቱትም፣ ምርጫው በድል ይጠናቀቅ ዘንድ ፊት ለፊት የተጋፈጠው “ያስተሰርያል” ዜማው አንድነትን ፈጥሯል፣ ሕዝባዊነትን አቀናጅቷል፣ ፍቅርን አንግሷል፣ ወያኔን አርበድብዷል፣ ኢሕአዴግን ዘርሯል። ፖለቲከኞቻችንና ምሁሮቻችን መጠቀም አቃታቸው እንጂ ኦሮሞን፣ ከአማራ፣ ከትግራይ፣ ከጉራጌ፣ ከጋምቤላ፣ ከሐረሪ፣ ከወላይታ፣ ከሲዳማ ሁሉን ኢትዮጵያዊ እጅ ለእጅ ያያያዘ ነበር። “ይቅር እንባባል” ብሎ ፍቅርን የሰበከ፣ ማማዬ፣ ኢትዮጵያዬ ብሎ መድረክ ላይ የተፋለመ፣ በሚሊዮኖች ያነቃነቀ ፖለቲካውን በዜማ ቅላጼው የተቆጣጠረ ብርቅዬ ነበር ዛሬም ነው። 

የቴዲ ሥራዎች በተለይ በወጣቱ ትውልድ ኢትዮጵያዊነት እንዳይሳሳ፣ ሰንደቅ ዓላማ እንዳይረሳ፣ ጀግኖች እንዳይደበዝዙ፣ አዚሟል “ኡ ኡ ታዬ” ብሎ እሪ ብሏል። ምኒልክን አንግሦ፣ ቴዎድሮስን አሞግሶ ትውልድን ቀስቅሷል፣ አነቃቅቷል። እስላም ክርስቲያኑን አንድ ነው ቤታችን ብሎ አስተቃቅፏል። ፍቅርን፣ ይቅርታን፣ አንድነትን፣ ኅብረትን በጠነከረ ዜማው ከሕዝብ አዋህዷል። ኢትዮጵያዬ ብሎ ኢትዮጵያዊነትን አሳይቷል። ዘመን ከፈጠራቸው የትውልድ ጀግና፣ አዋጊ ዜመኛ፣ ድምፃዊ ፓርቲ ቢባል ይገባዋል። 

“እረኛዬ”  ወደ ሌላ ተዛማጅ ጉዳዮች ቢወስደኝም አንኳሩ ኪነት ምን ያህል ለአገር፣ ለሕዝብ፣ ለትውልድ ያላትን እምቅ ችሎታ ለማስመር ነው። የ“እረኛዬ” አባላትንም ሆነ ሌሎች ባለሙያዎች ሌላም የፈጠራ ሥራዎቻችሁን አሳዩን እያልኩኝ፣ የምሥጋና ድምፄን በአንድ ቃልና በአራት ነጥብ ላብቃ። በርቱ።

በነሲቡ ስብሐት

https://www.ethiopianreporter.com/110256/

ባህልን በምልዓት ያንፀባረቀው ‹‹እረኛዬ››


የኢትዮጵያ ባህል፣ እሴት፣ ወግና ሌሎች ነገሮች ተካተውበት ከተሠሩ ተከታታይ ድራማዎች መካከል ‹‹እረኛዬ›› ይጠቀሳል፡፡

ይኼው በሳምንት ሦስት ቀናት በአርትስ ቲቪ ለሕዝብ ይተላለፍ የነበረው ተከታታይ ድራማ በኅብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነትን አትርፏል፡፡ ድራማው እንዲወደድ ካደረጓቸው ነገሮች መካከል የቦታ አመራረጥ፣ አቀራረፁ፣ ተዋናዮቹ፣ ድርሰቱ፣ የቪዲዮ ጥራትና በብዙ ማኅበረሰቦች ውስጥ ያለውን አገራዊ ይዘት ያለው በመሆኑ ነው የሚሉ አልታጡም፡፡

እረኛዬ ድራማ ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በኋላ ብቅ ካሉ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች አንዱ ነው፡፡ ከወረርሽኙ በኋላ የፊልም ኢንዱስትሪው እየተነቃቃ እንደሚገኝ፣ እነዚህ መነቃቃቶች ከታዩባቸው መካከል እረኛዬ አንዱ መሆኑንና የድራማው ደራሲዎች ደግሞ ሦስቱም ሴቶች (ቤዛ ኃይሉ፣ ቅድስት ይልማና አዜብ ወርቁ) መሆናቸው ድራማውን ይበልጥ አጉልቶታል፡፡

በዚህ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ ለረዥም ዓመታት ከቴሌቪዥን መስኮት የጠፉ ዕውቅ አርቲስቶች ብቅ ያሉበት በመሆኑም ለየት ያደርገዋል፡፡

በድራማውም መሉዓለም ታደሰ፣ ሳያት ደምሴ፣ ድርብ ወርቅ ሰይፉ፣ ቃል ኪዳን ጥበቡ፣ አበበ ተምትምና ሰለሞን ቦጋለን ጨምሮ በርካታ አዲስና ነባር ተዋናዮች ተሳትፈውበታል፡፡

በአርትስ ቴሌቪዥን ሲቀርብ የነበረው እረኛዬ ድራማ ለሦስት ተከታታይ ምዕራፍ ለዕይታ ቀርቦ መቋረጡ ይታወሳል፡፡ በግንቦት መጨረሻና ሰኔ መጀመርያ ይጀመራል የተባለውን የቴሌቪዥን ድራማ በተመለከተ፣ ቅዳሜ ሚያዝያ 29 ቀን 2014 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሳይንስ አካዴሚ ቅጥር ግቢ ውስጥ የድራማው ተዋናዮች፣ ደራሲዎቹና ታዳሚዎች በተገኙበት የፓናል ውይይት ተካሄዷል፡፡ የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የሥነ ጥበብ ማዕከል ባዘጋጀው መድረክ በተውኔቱ ላይ ሙያዊ ዳሰሳ ያቀረቡት የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ መምህሩ ሰለሞን ተሾመ (ዶ/ር)፣ የእረኛዬ ድራማ ከባህል አንፃር እንዴት ይታያል የሚለውን ሁኔታ በአምስት ነገሮች በመከፋፈል አቅርበውታል፡፡

የእረኛዬ ድራማ የገጸ ባህርይ አሣሣል፣ የቦታ መረጣ፣ ርዕስ፣ በድራማ ውስጥ ያለው ይዘትና አጠቃላይ የቀረበበት መንፈስ ምን ይመስላል የሚለውን ማየታቸውን የተናገሩት ሰለሞን (ዶ/ር) ከዚህ አንፃርም ‹‹የተዋጣለት ድራማ›› መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በትንታኔያቸውም እንዳከሉት፣ ‹‹ይህ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ የታሪክ አወቃቀሩ፣ የገጸ ባህሪዎቹ አመራረጥ፣ የትወና ብቃት፣ የቦታ አመራረጥ፣ ዳይሬክቲንግና ቀረፃው የሙያውን ደረጃ ከፍ ያደረገና አገራዊውን የፊልም ገጽታ የቀየረ ነው፡፡››

የእረኛዬ ድራማ ዋናው ጭብጥ ‹‹የኢትዮጵያን ችግር በኢትዮጵያ ባህል እንፍታ›› የሚል እንደነበር፣ ድራማው በሚቀረፅበት ወቅት የተመረጡት ቦታዎችና ተዋናዮቹ ብቃት ብርሃን የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል፡፡

በድራማው ውስጥ የተለያዩ ተፋላሚ ኃይሎች፣ በተቃራኒ ጎራ፣ በተቃራኒ ሐሳብ፣ በተቃራኒ ፍላጎት ተወዳድረው ሲፋተጉና ሲጋጩ እንደሚታዩ፣ ይህም የሚያሳየው የእኛነት ስሜትን ያንፀባርቃል ሲሉ ሰለሞን (ዶ/ር) አብራርተዋል፡፡

በድራማው ውስጥ የነበሩ ተቃርኖዎች ቅንነትን በእማማ ቸርነት፣ በዳዊትና በእናና፣ አለመታመንን በጣሰው ላይ የታየ ሲሆን፣ ባለቤትና ባይተዋርነት ፍቅርና ጥላቻን ያሳያል የሚሉት ዶ/ር ሰለሞን፣ በተፈለገው ልክ ኢትዮጵያ ያለችበትን ሁኔታ በድራማው ላይ ማየት ተችሏል፡፡

በተለይም በእንጉርጉሮ መልክ የሚቀርቡ መልዕክቶች ልብ ይነኩ እንደነበር፣ የተስፋና የተስፋ ቢስነት ግጭትን የሚያሳይ መሆኑን በዳዊትና በጣሰው ገጸ ባህርያት ላይ ማየት እንደተቻለ አክለዋል፡፡

ድራማው የተጀመረ ሰሞን የነበረው የገጸ ባህርይ ሁኔታ መተሳሰብና መቻቻልን የሚያሳይ ነው የሚሉት ሰለሞን (ዶ/ር)፣ ድራማውም በአጠቃላይ ኋላቀር የሆነ የፖለቲካ ባህልን እንደሚያንፀባርቅ፣ ዓብይ ትግሉም ከኋላቀር የፖለቲካ አስተሳሰብ ተላቅቆ ወደ ሠለጠነ አስተሳሰብ የሚደረግ የሽግግር ሒደትን ይጠቁማል ብለዋል፡፡

የእረኛዬ ድራማ ርዕስ ‹‹እግዚአብሔር እረኛዬ ነው›› ከሚለው መዝሙራ ዳዊት ክፍል የተወሰደ መሆኑን የተናገሩት የድራማው ደራሲ ወ/ሮ ቅድስት ይልማ ናቸው፡፡

የእረኛዬ ድራማ ከጽሑፍ ጀምሮ ወደ ዕይታ ለማምጣት አምስት ዓመታት እንደፈጀ፣ አብዛኛውን የድራማው ጭብጥ አንድ ኢትዮጵያን ያሳየ ነውም ብለዋል፡፡

በድራማውም የነበሩ ይዘቶች መልካምነትን የሚያንፀባርቁ፣ በተቃራኒው ደግሞ ጥላቻን የሚፈጥሩ ታሪኮችን የያዘ እንደነበር ገልጸው፣ የድራማው ጥንስስ የኢትዮጵያን ትውፊቶችን የሚያሳይ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

የድራማው አዘጋጅና ደራሲ ቅድስት ይልማና ደራሲዎቹ አዜብ ወርቁና ቤዛ ኃይሉ ድራማው የኢትዮጵያን ባህል፣ ሥነ ልቦና፣ ትውፊቶችንና እሴቶችን የተላበሰና ሳቢ እንዲሆን በማድረግ ትውልድን ከባህል ብረዛና ከማንነት ቀውስ ለመታደግ ታልሞ እንደተሠራ ገልጸዋል።

በአብዛኛው ደራሲዎች ፊልሞች ላይ ሴቶችን ሲመድቡ (ካስት ሲያደርጉ) የግድ ቆንጆ መሆን አለባት የሚል እምነት እንዳላቸው፣ በእረኛዬ ድራማ ላይ ግን ይህንን ችግር በማስወገድ ለድራማው የሚሆኑ ተዋናዮች ተመርጠው ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጋቸውን ደራሲዎቹ አብራርተዋል፡፡


እረኛዬ ከመጽሐፍ ይልቅ በድራማ እንዲቀርብ የተደረገው፣ አብዛኛውን ጊዜም የፊልም ኢንዱስትሪው በቃና የታበጀ በመሆኑና የተከታታይ ድራማን መንፈስ ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት በማለም መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

የእረኛዬ ድራማ ዋናው ዓላማ ትንሿን ኢትዮጵያ መፍጠር እንደሆነ፣ በድራማው ከዚህ ቀደም የነበሩ የመተሳሰብን፣ አብሮ የመብላት መንፈስን በመገንባት ኢትዮጵያ አሁን ያለችበትን ገጽታ ለማሻሻል የታሰበ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

የእረኛዬ ድራማ ላይ የተሳተፉ ተዋናዮች የተሰጣቸውን ኃላፊነት በአግባቡ እየተወጡ እንደሆነ፣ በአሁኑ ወቅትም በማኅበረሰቡ ዘንድ ተቀባይነትን ማግኘት እንደተቻለ በወቅቱ ተገልጿል፡፡

በቴሌቪዥን ድራማው አብዬ በቃሉን ሆነው የተወኑት የ‹‹የወዲያነሽ›› እና ‹‹ጉንጉን›› ተወዳጅ ልብ ወለዶቻቸውና ‹‹እንካ ሰላምቲያ›› በተሰኘው ድርሰታቸው የሚታወቁት ኃይለ መለኮት መዋዕል፣ እማማ ቸርነትን ሆና የተወነችው ድርብ ወርቅ ሰይፉ በድራማው ላይ ስለነበራቸው ተሳትፎ አብራርተዋል።

የመድረኩ ታዳሚዎች በሰጡት አስተያየት ድራማው የበርካታ ተመልካቾችን ቀልብ የሳበ፣ በትርጉም ከሚቀርቡ የውጭ አገር ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች ዓይናችንን ወደ አገርኛ የመለሰ ተከታታይ ድራማ ነው ሲሉ አሞካሽተውታል። ድራማው ከሰፊ ማኅበራዊ ጠቀሜታው ባሻገር ጉልህ ፖለቲካዊ ፋይዳ እንዳለውም ተጠቁሟል።

የድራማው ተከታታይ ክፍሎች መቼ እንደሚጀምሩ ከታዳሚዎች ለቀረበላቸው ጥያቄ ደራሲና ዳይሬክተሯ ቅድስት ይልማ በሰጡት ምላሽ፣ የቀጣይ ክፍሎች ቀረፃ ተጠናቆ ቅንብር ላይ እንደሚገኝና በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለዕይታ እንደሚበቃ አሳውቀዋል።

ተመስገን ተጋፋው

https://www.ethiopianreporter.com/82463/

እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማን እንዲወደድ ያደረጉ ምክንያቶች


እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ በአርትስ ቴሌቭዥን በአራት ምዕራፎች በ48 ክፍሎች ሲተላለፍ ቆይቶ አርብ ነሐሴ 13/2014 ዓ.ም. ተጠናቋል።

ይህ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ በአዜብ ወርቁ፣ በቤዛ ኃይሉ እንዲሁም በቅድስት ይልማ የተጻፈ ሲሆን፣ ያዘጋጀችው ደግሞ ከደራሲዎቹ መካከል አንዷ የሆነችው ቅድስት ይልማ ነች።

እነዚህ ሦሰት ደራሲያን ለፊልም ጽሁፍ እንዲሁም ዝግጅት እንግዳ አይደሉም። በስማቸው በርከት ያሉ ሥራዎች ሰፍረው ይገኛሉ።

በጥምረት ግን ሲሰሩ ይህ የመጀመሪያቸው ነው።

እረኛዬ ተከታታይ የቴሌቭዥን ድራማ መቼቱን ያደረገው ከከተማ ግርግር ርቆ፣ ሕይወት ስክን ብላ በምትፈስበት ገጠር ውስጥ ነው።

ይህ አብነት የተሰኘ የገጠር መንደር በምናብ የተፈጠረ ነው።

ይህች የገጠር መንደር ኢትዮጵያን እንድትመስል ተደርጋ ነው የተሳለችው።

በዚህ መንደር በፍቅር ተሳስበው የሚኖሩ ዘመዳሞች እና ጎረቤታሞች ፍቅራቸውን የሚነቀንቅ ተቀናቃኝ መጥቶባቸዋል።

ይህ ተቀናቃኝ ባለሀብት ነው።

በሀብቱ ብዛት መሬታቸውን ሊነጥቅ የቋመጠ፣ ለዚህም በቀኝ በግራው፣ በፊት በኋላው ግለሰቦችን ያሰለፈ ነው።

ይህ ባለሀብት የሚነጥቃቸው መሬት ይምሰል እንጂ ከመሬቱ ጋር የተሰፋ ማንነት፣ ባሕል እና ትውፊት አብሮ አለ።

የአብነት መንደር ነዋሪዎች ይህንን የኖረ ባሕላቸውን፣ ማንነታቸውን ለመከላከል በገበሬ አቅማቸው ይውተረትራሉ።

በድራማው የመጀመሪያ ክፍል ላይ የምናያቸው እና በኋላም በታሪኩ ውስጥ በተደጋጋሚ በአርዓያ ሰብነት የሚጠቀሱት አብዬ በቃሉ ከአካባቢው ሁሉ የተለዩ ግለሰብ ነበሩ።

መለየታቸው ለመልካም ነው። ሕብረት ይወዳሉ፤ ድንበር አይፈልጉም። አገራዊ እውቀቶች ከአንዱ ሰው ወደ ሌለው እንዲተላለፉ አጥብቀው ይሻሉ። ለእርሱም ትምህርት ቤት ከፍተው የአብነትን ነዋሪዎች ያስተምሩ ነበር።

ነገር ግን ልጃቸው ከጋብቻ ውጪ አርግዛ የሠርጓ ዕለት በመውለዷ በድንጋጤ ሕይወታቸው አለፈ።

አገሬው ጉድ አለ፤ የአቶ በቃሉ ሕልም ተዳፈነ። ቤተሰቡ አንገቱን ደፋ። ልጃቸው ወጋየሁም ጨርቄን ማቄን ሳትል ሌሊቱን ማንም ወደማያውቃት አገር ተሰደደች።

የአብነት መንደር ወግ ባሕል ልማድ የተጣሰው ዋነኛ ተቆርቋሪ በሆኑት አብዬ በቃሉ ልጅ፣ ወጋየሁ ነው።

በኋላ ግን የጠፋው ወግ ባሕል ልማድ በእርሳቸው የልጅ ልጅ እንደ አዲስ ሲያንሰራራ እንመለከታለን።

በአንድ ማህጸን ያደሩት ዳዊት እና መንግሥቱ በተለያዩ ወላጆቻቸው እጅ ማደጋቸው፣ የተለያየ ባሕርይ እና ማንነት ሰጥቷቸው የማይግባቡ ዥንጉርጉሮች አድርጓቸዋል።

ያደሩበት ማህፀን፣ ተካፍለው የጠቡት ጡት ያቆየላቸው እንጥፍጣፊ ፍቅር ያለ አይመስልም።

እረኛዬ በእነዚህ ገፀ ባሕሪያት በኩል የአገርኛ እውቀቶች እንዲያብቡ፣ ባሕል ወግ ልማድ እንዳይጣስ፣ ፍቅር ይቅርታ የኑሮ አምድ እንዲሆኑ ደጋግሞ ይወተውታል።

በበርካቶች ዘንድ ትኩረትን ያገኘው ለዚህ ይሆን? ድራማውን የተከታተሉ ሁለት ግለሰቦች አነጋግረናል።

ገሸሽ ያደረግነውን ማንነት ፍለጋ

በእረኛዬ ድራማ ላይ የምናያቸው የማምረቻ መሳሪያዎቹ፣ አልባሳቱና ጌጣጌጦቹ፣ ወዘተ የራሳቸው የሆነ ቱባ ሥነ ውበታዊ ገጽታ አላቸው።

በአሰራራቸው የአገርኛ ጥበብ አሻራ ታትሞባቸው ይገኛል።

በድራማው ላይ የሚታዩት የሰላምታ ልውውጦች፣ የግብይት ልማዶች፣ የጋብቻ ሥርዓቶች፣ የአምልኮ ትውፊቶች፣ የለቅሶ ልማድ ሁሉ የየራሳቸው ውበትና መስህብ እንዲኖራቸው ተመልካችን እንዲያማልሉ ሆነው ተቀርፀዋል።

በድራማው ላይ በእረኞች እና በኮማሪቷ ማስረሻ፣ የሚገጠሙ ግጥሞች የማኅበረሰቡን ማንነትና ስሜት ከማንጸባረቅ ትይዩ የቆሙ፣ ሥነ ጽሑፋዊ ቴክኒክ ተላብሰው የቀርቡ ናቸው።

ይህም የማዝናናት ለዛቸውን አጉልቶ፣ አይረሴና ተጨባጭ አድርጓቸዋል።

ድራማው አካብቶ ያቀርብልን የማኅበረሰቡ ጠቅላላ የተሞክሮ ዕውነታ ባሕላዊ ማንነትን የሚያጎሉ ቅርሶች የተዝናኖት ፋይዳ ጨምረውለታል።

የደራሲዎቹ የተጠባቢነት አቅም ልኩ የሚመዘነው ደግሞ እነዚህን አጣጥሞ በማቅረብ ብቃቱ ላይ የተመሰረተ መሆኑን የባላገሩ ቴሌቪዥን የፕሮግራም ዳይሬክተር የሆነው ሲራክ ተመስገን ይናገራል።

የትያትር እና የፊልም መምህር የሆነው አንተነህ ሠይፉ በበኩሉ እረኛዬን የወደድንበትን ምክንያት ሲያነሳ አስቀድሞ የሚጠቅሰው መቼቱን ነው።

በኢትዮጵያ የፊልም እና የተከታታይ ድራማ ታሪክ መቼታቸውን በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ያደረጉ ሥራዎች በቀላሉ በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት እና ተወዳጅነት ማግኘታቸውን በማንሳት እረኛዬም ይህ እንደረዳው ይገልጻል።

የዚህ ተከታታይ ድራማ ደራሲና አዘጋጅ የሆነችው ቅድስት ይልማ ቀዳሚ ሥራ የሆነው ‘ረቡኒ’ን በምሳሌነት ያነሳው አንተነህ፣ በተመሳሳይ መልኩ መቼቱን ገጠር በማድረጉ ተወዳጅነትን አትርፎ እንደነበር ያስታውሳል።

አንተነህም ሆነ ሲራክ፣ እረኛዬ ተከታታይ ድራማ፣ ያነሳው ታሪክ ወደ ጥንታዊ ማንነት፣ ገሸሽ ወዳደረግናቸው ባሕላዊ እሴቶቻችን መመልከቱ በተመልካች ዘንድ ተወዳጅነት ለማግኘቱ አስተዋጽኦ ማድረጉ ላይ ይስማማሉ።

አክለውም ታሪኩ የተዋቀረበት እና ገጸ ባህሪያቱ የመጡበት ዓለም፣ ከማኅበራዊ ከሌሎች እሴቶቻችን ጋር መሳ ለመሳ መሆኑ ተቀባይነት ለማግኘት አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ይናገራሉ።

ዳይሬክተሯም ገጸ ባህሪያቱ የተቀዱበት ማኅበረሰብን ማንነት ለማጉላት የተጠቀመችባቸው ነባር እሴቶችም አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አንተነህ አክሎ ይገልጻል።

ኢትዮጵያ ያለችበት ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ሁኔታ



እረኛዬ ድራማ በአገሪቱ ካለው እውናዊ ሕይወት በትይዩ ይሳል እንጂ፣ የማኅበረሰቡን ስምና አድራሻ በቅጂነት ከነምግባሩ አያነሳም።

ገጸ ባህሪያቱ በምናብ በተፈጠረ መንደር፣ አብነት፣ ልቦለዳዊ ኑሯቸውን መስርተዋል።

የማኅበረሰቡን ኑሮ አይኑሩ እንጂ፣ ለኑሮው መስታወት ሆነው የራሱ የዕለት ተለት ገመና መልሶ እንዲመለከት አድርገውናል።

በድራማው ውስጥ የማኅበረሰቡን እንከን፣ ሠላም የማጣት፣ የመናቆር፣ ይቅር ማለት አለመቻል ፍጥጥ ብሎ እንዲታይ አድርጓል።

ለዚህም እንቆቅልሽ ብሎ በመጠየቅ ከራስ መልስ እንደመጠየቅ አይነት ነው።

ደራሲዎቹ በገጸ ባህርያቱ ሕይወት በኩል እንቆቅልሽ ብለው ይጠይቃሉ። ተመልካቹም ፍንጮቹን እየተከተለ የሕይወትን እንቆቅልሽ የመፍታት ድርሻን ይወስዳል።

አንተነህ ይህንን ሃሳብ ሲያጠናክር “ወቅቱን የሚገልፁ፣ ሰዉ ልብ ውስጥ ያለውን፣ በአደባባይ መተንፈስ መናገር የማይችለውን ነገር በድራማ መልክ ስለማንነታችን፣ ስለ እርስ በእርስ ግንኙነታችን ስለአናኗራችን አሁን ስላለው ፖለቲካዊ ሁኔታ፣ በጥሩም ይሁን በመጥፎ ያነሳሳል” ይላል።

ላለው ወቅታዊ ፖለቲካዊ ሁኔታ ጥያቄ ነው ያለውን ድራማው ያነሳል፤ እንደ ታምራት ገለፃ መልስ ነው መፍትሔ ይሆናል ያለውንም እዚያው ይጠቁማል፤ ይመልሳል።

ሲራክም ሆነ አንተነህ በድራማው በኩል የራሳችን ገበና፣ ከአደባባይ ርቀን በማጀታችን የምናወራው ነገር ሲቀርብልን፣ መተንፈሻ ፉካ ሆኖን በማገልገል ተወዳጅነትን አትርፏል ይላሉ።

ሲራክ አክሎም ዳይሬክተሯ ቅድስት አገሪቷ ያሉባትን ችግሮች፣ አገር በቀል በሆነ እውቀት ውስጥ መፍትሔ መፈለግን እንደ ስልት ይዛዋለች ይላል።


ጀግኒት ፀሐፊያን እና አዘጋጅ

የኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ የወንዶች ዓለም ነው በሚለው ሀሳብ አንተነህና ሲራክ ይስማማሉ።

አብዛኞቹ ታሪክ ነጋሪዎችና ፀሐፊዎች ወንዶች በመሆናቸው በወንድ ዐይን ነው ዓለሙን የሚያሳዩን ይላል አንተነህ።

የምንኖረውን የአባታዊ ሥርዓት፣ በምንታደመው የጥበብ መድረክ ላይም የምናየው ሕይወት የወንዶች ምናብ ውጤት ነው በማለት ያክላል ሲራክ።

“ዓለሙን፣ ሕይወትን፣ አገርን የሚተረጉሙት በወንድ መነጽር ነው” ይላል አንተነህ።

የእረኛዬ ደራሲዎች ግን ከዚህ ተቃራኒ ዕድል ነበራቸው።

እንዲህ ሴቶች በድርሰትም በዝግጅትም ሰብሰብ ብለው መምጣታቸው እንደ እረኛዬ አይነት በሥርዓተ ጾታ ላይ ጥንቁቅ የሆነ ድራማ እንድናገኝ ረድቶናል ይላል ሲራክ።

ለዚህም ነው የእረኛዬ ሴት ገጸባህሪያት የድራማው ደምና አጥንት ሆነው ነው የተሳሉት።

የአብነት መንደር ሕይወት በጫንቃቸው ነው። የአብዬ በቃሉ አደራ በደም ሥራቸው ይፈሳል።

የትምህርት ቤት ደጃፍ ባይረግጡም፣ የፊደል ዘር ባይለዩም ሕይወትን፣ በዙሪያቸው የተንሰራፋውን ዓለም በገባቸው ልክ የሚተረጉሙ እና እርሱንም አጽንቶ ለማቆም የሚታገሉ ናቸው።

የእረኛዬ ሴት ገጸ ባህሪያት ለከተማ ሕይወት ባዳ ሆነው፣ የቀለም ዘር ሳይለዩ ለመብታቸው የሚቆሙ ናቸው የሚለው ደግሞ አንተነህ ነው።

በዚህ ሃሳብ ሲራክም ይስማማል። “በእረኛዬ ድራማ ላይ ልፍስፍስ ሴት አትታይም፤ ከወንዶች እኩል የምትገዳደር ሴት እናገኛለን” ሲል ያክላል።

አንተነህ ሲያክልበት ደግሞ “ለእህቷ ለጓደኛዋ መብት የምትቆም ሴት. . .ልጆቿን ሕልውናዋን ለመመለስ የምትታገል ሴት. . .ቤቷን ብቻ ሳይሆን አካባቢዋን አጽንቶ ለማቆም የምትታገል እናት” ማየታችን በሴት ደራሲያን የመጻፉ ትሩፋት መሆኑን ያስረዳል።

የድራማው ደራሲያን ሴት መሆናቸው ወንዶች የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ሲጽፉ የሚያጎዱሉት ነገር ቁጭት እና እልህ አለባቸው የሚለው አንተነህ፣ ጠንካራ ሴት ገጸ ባህሪያትን በመሳል ረገድ እንደተዋጣላቸው ይመሰክራል።

ደራሲያኑ እንዲሁም ዳይሬክተሯ ሴቶች መሆናቸው “ለሚገባቸው ሚና የሚታመኑ ጠንካራ ገጸ ባህሪያትን” ጠንካራ ሴቶች እንድናይ አድርጎናል ሲል ይገልጻል።

የእረኛዬ ሴት ገጸ ባህሪያት ከእነርሱ ሕይወት ይልቅ የሚኖሩበት ማኅበረሰብ ሕልውና ያሳስባቸዋል።

በዋና ገጸ ባህሪይነት የተሳሉት ሴቶች ሁሉ ከራሳቸው በላይ ሰንደቅ ሆኖ የሚውለበለብ ዓላማ አላቸው።

የእናና ገጸ ባህሪ ደግሞ ለሞቷ ሰበብ የሆነውን የጥቅም ፈላጊዎች ጠብ፣ ለመኖሪያ ቀዬዋ ነዋሪዎች ቀጣይ የጠብ ጥንስስ መነሻ እንዳይሆን በመመሸግ፣ መስዋዕት እስከመሆን ትደርሳለች።

ጎምቱ እና ተወዳጅ ተዋንያን መሳተፋቸው



በእረኛዬ ድራማ ላይ የተሳተፉት ተዋንያንም ቢሆኑ ስምና ዝና ያላቸው፣ ክህሎትም ቢሆን ጠንቅቀው የተካኑ መሆናቸው ለተወዳጅነቱ አስተዋጽኦ ማድረጉን አንተነህ እና ሲራክ የሚስማሙበት ጉዳይ ነው።

“ከእረኛዬ ድራማ የተመቸኝ አንድ ነገር ቢኖር ገጸ ባህሪ አሳሳሉ እና ተዋናይ መረጣው ነው” ይላል ሲራክ።

እረኛዬ ድረማ “የደርቢ ስብስብ ይመስላል” የሚለው ደግሞ አንተነህ ነው። ለዚህ ደግሞ ምክንያቱ በድራማው ላይ ወሳኝ ስፍራ የያዙት ተዋንያን ስምም ዝናም ያላቸው መሆናቸውን ነው።

በእርግጥ በድራማው ላይ አዳዲስ ፊቶች የታዩ ቢሆንም እንደ አበበ ባልቻ፣ ሙሉዓለም ታደሰ፣ ድርብ ወርቅ ሠይፉ፣ ሳያት ደምሴ፣ ኩራባቸው ደነቀ፣ አማኑኤል ሐብታሙ፣ ቃልኪዳን ጥበቡ እንዲሁም ሠለሞን ቦጋለ ያሉ ተዋንያንን ማሳተፉ አድናቂዎቻቸውን ወደ ድራማው በመጥራት ረገድ አስተዋጽኦ ማድረጉን ይጠቅሳል።

ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ ተዋንያኑ የተወከሉበትን ገጸ ባህሪ በሚገባ መጫወታቸው፣ ተደራሲያንን ወደ ታሪኩ ጎትቶ በማስገባት ረገድ የላቀ ሚና እንደነበረው ያነሳል።

ከተለመደው አቀራረብ ወጣ ማለቱ

የእረኛዬ ገጸ ባህሪያት ከሚኖሩበት አብነት መንደር ርቀው አይሄዱም። ወደ ተለያዩ ከተሞች ልጇን ፍለጋ የምትባዝነው ወጋየሁም ብትሆን ትንንሽ የገጠር ከተሞችን ታካልላለች እንጂ ሕንጻ ወደተንጠለለበት ከተማ ጎራ አትልም።

ይህ ግን ተደራሲው ላይ ያጎደለው ነገር የለም። ድራማው የሚያነሳው አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን በየቀኑ የሚውሉበትን፣ የሚወጡ የሚወርዱበትን በመሆኑ በታሪኩ ላይ ጉድለት አልፈጠረም።

እረኛዬ ታሪኩን የመሰረተው ከከተማ ውጪ ያለ ሕይወት ላይ መሆኑ፣ ተመልካቹ ከለመደው ውጪ ነገር ይዞ መቅረቡ ለተወዳጅነቱ አስተዋጽኦ ማድረጉን አንተነህ ያነሳል።

ይህ የታሪክ አቀራረቡ በተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ እንዲሁም ፊልም ከተለመደው ውጪ መሆኑ የራሱ ድርሻ ነበረው።

ሲራክ በበኩሉ በበርካታ የፊልም ባለሙያዎች ዘንድ ኢትዮጵያዊ ፊልም መስራት የሚለው አጀንዳ ሲነሳ እሰማለሁ በማለት ኢትዮጵያዊ ድራማ ማለት ገጠር ውስጥ የሚከወን ብቻ መሆኑ ላይ ጥያቄ ያነሳል።

የእረኛዬ ድራማ በአብነት የገጠር መንደር መኖራቸው፣ ከተማ ጠል መሆናቸው ባይጎረብጠውም ኢትዮጵያዊ ለማድረግ ብቻ ግን ገጠሩን መምረጥ አዋጭ ሃሳብ አለመሆኑን አንስቶ ይሞግታል።

በማጠቃለያውም ላይ ከተሜ ሆኖ ኢትዮጵያዊ ወግ ባሕል የሚታይበት ኑሮ እኮ አለ ሲል ያክላል።

https://www.bbc.com/amharic/articles/cv2l9y818q2o

<ልንለው የምንፈልገው አለን> ከእረኛዬ ተከታታይ የቴሌቭዥን ድራማ


Thursday, October 13, 2022

እነሆ መንገድ ለኢትዮጵያ__የፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው መጽሐፍ

 የፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው እነሆ መንገድ ለኢትዮጵያ . . . መጽሐፍ __ሔኖክ ያሬድ



‹‹ስለ ሀገሬ ኢትዮጵያ ባሰብኩ ቁጥር ስለ ጥንታዊቷ አገር ያነበብኳቸው የታሪክ መጻሕፍትና አሁን ያለንበት ሁኔታ አልገጣጠም ይለኝና ‹ለምን ይህ ሆነ?› እያልኩ ብቻዬን እነጋገራለሁ፤ እተክዛለሁ በተመስጦም ዝም ብዬ ቁጭ እላለሁ፡፡ ቀድሞ የነበርንበትን የከበረ ወንበርና አሁን ደግሞ ያለንበትን ከባድ ጉስቁልና ሳስብ ውስጤ በቁጭት ይሞላል፡፡ ብዙ ጊዜ በጥሞና ውስጥ ሆኜ አዲሲቱንና የምንመኛትን አገሬን በዓይነ ሕሊናዬ አያታለሁ፡፡ ታዲያ እንደገና መለስ ብዬ አሁን ያለንበትን ሁኔታ ሳስብ ወደምንመኛት፣ ማርና ወተት ወደምታፈስ አገር ለመድረስ ምን መደረግ አለበት? ብዬ ሳውጠነጥን መያዣ መጨበጫው ይጠፋኛል፡፡ ችግሮቹ እጅግ የበዙ ናቸውና፡፡››

መሰንበቻውን የኅትመት ብርሃን ባየው የፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው ‹‹እነሆ መንገድ ለኢትዮጵያ . . .›› መጽሐፍ መግቢያ ላይ ደራሲ የተንደረደሩበት እሳቦት ነው፡፡ ቀድሞ ገናና የነበረች አገር በዚህ ዘመን ምን ዱብዳ ወድቆባት ነው ጭራ የሆነችው? የሚለውን የኅብረተሰብ ቁጭት መርምረው መፍትሔ ነው የሚሉትን ሐሳቦች በመጽሐፉ ላይ አስፍረውታል፡፡

የአስተሳሰብ የማያቋርጥ ዕድገት ለአገሮች ብልፅግና መሠረት መሆኑን  ያመለከቱት ደራሲው፣ ሐሳባቸውን ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት ለአገሪቱ ዕድገት የኢትዮጵያውያን የልቦና ውቅር መለወጥ (ፓራዳይም ሺፍት/Paradigm Shift) እንዳለበት ያመለክታሉ፡፡

መጽሐፉ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሲመረቅ የምሕንድስና ፕሮፌሰሩ እንደተናገሩት፣

 ‹‹የምንመኛትን ኢትዮጵያ በማየት እዚያ እንዴት ነው መድረስ የምንችለው? አስተሳሰባችን አመለካከታችን ልንቀይር ይገባል፡፡ አሁን ያለን አመለካከት ድሮ በኖርንበት ከሆነ የትም መድረስ አንችልም፡፡ ዓለም እየተቀየረች ነው፡፡ በፖለቲካ፣ በጂኦግራፊ፣ በኢኮኖሚ በሁሉም አቅጣጫ እየተቀየረች ሲሆን እኛ ደግሞ ሐሳባችንና አመለካከታችን መቀየር አለበት፡፡››

ይህንኑ መሠረተ ሐሳባቸውን በመግቢያቸው እንዲህ አብራርተውታል፡፡  

‹‹ኢትዮጵያን ስናስብ በራቀው የታሪካችን ምዕራፍ ውስጥ ምን ያህል ገናና ታላቅ አገር እንደነበረች እንረዳለን፡፡ ጥቂትም ቢሆኑ ትንግርት መስለው የቆሙ ምስክሮቻችን ለቀድሞ ትውልድ ማንነት ማስታወሻ፣ ለአሁኖቹ የጥያቄዎቻችን ምንጭ፣ ለሌሎቹ ደግሞ የግርምታቸው ዘሀ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ታዲያ ከዓለም በፊት ቀድመን፣ ሰው ተኝቶ ሳያልም እኛ ርዕይ አይተን እንዳልነበር ለምን አሁን የሀገራት ጭራ ሆንን? ጥያቄው የሁላችንም፣ ምክንያቱ ፈርጀ ብዙ ይሆናል፡፡

‹‹ይሁን እንጂ አሁንም እንደትውልድ ለቀጣዩ እንድናስተላልፍ ያልተቀበልነው ዱላ፣ እንደታሪክ ያልተሻገርነው ክፍተት አለ ማለት ነው፡፡ አገራችን እጅግ ከባድና መራራ ጊዜ ብታሳልፍም፣ የቱንም ያህል ጠላቶቻችን ቢበዙና ቢያይሉ ከሥራ ለዘብተኛነትና ቸልተኝነት በላይ የሚጎዳን፣ ከፍቅርና ኅብረት ማጣታችን የባሰ የሚያሸንፈን ነገር አይኖርም፡፡ በመሆኑም በአገር ደረጃ ከፍ ብለን ለመታየትና፣ የምንመኛትንም ዓይነት የበለፀገችና ጠንካራ አገር በሁላችንም ጥረትና ሥራ ለማምጣት የጋራ ርዕይ ያስፈልገናል፡፡ ይህን ርዕይ ደግሞ ሁላችንም ልንደርስበት የምንችለው በእያንዳንዳችን ልብ ውስጥ የታተመ ሲሆን ነው፡፡››

ሌላው ተናጋሪ፣ 

‹‹አገርን ለመውደድ መጀመርያ ራስን መውደድ ያስፈልጋል የሚል ነገር አለ፡፡ እዚህ ላይ ነው የልቦና ውቅር የሚመጣው፡፡ ኢትዮጵያውያን በየጊዜው ያለፉበት መንገድ አለ፤››

 

የሚሉት በመጽሐፉ ላይ አስተያየት የሰጡት የሥነ ልቦና ምሁሩ ዶ/ር መስፍን አርአያ ናቸው፡፡  

እንዲሀም አብራሩት፣ በአንድ ወቅት ካሜራ ኢትዮጵያ ሲገባ ለአፄ ምኒልክ እንዴት እንደሚሠራ ሲያሳዩዋቸው በአካባቢያቸው የነበሩት በጣም ነበር የነቀፉት፡፡ ለምን ይህ የሰይጣን ሥራ ነው የሚል አመለካከት ነበራቸውና፡፡ እንዲህ ያለ ነገር አገራችን መግባት የለበትም፤ መኪና ፈቀዱ፣ ሰላቢ የሆነ በሽቦ ውስጥ የሚሄድ ድምፅ እንዲሠራ ፈቀዱ፤ በአገራችን መከራ አሳር ያመጣል፡፡ በዚያን ጊዜ የነበረውን የልቦና ውቅር ያሳያል፡፡ አርቆ አሳቢው መሪ ግን ራሳቸው እንዳሳዩት ካሜራውን መጠቀም፣ መኪናውን መንዳት ነበረባቸው ራሳቸው በስልክ መነጋገር ነበረባቸው፡፡

‹‹እንደዚህ ዓይነቱን ውቅር ለውጥ እስካላመጣን ድረስ በአገሪቱ በአንድ ቦታ ላይ የምንሰቃይ ከሆነ መራመድ አንችልም፤ ወሳኝ የሆነ ነገር ነውና የልቦና አወቃቀር ጽንሰ ሐሳብን ሁላችንም መያዝ እንዳለብን በሚገባ መጽሐፉ ያመለክታል፤›› ያሉት ዶ/ር መስፍን፣ ሙሉ ሰዎችን ለማፍራት ትክክለኛ የልቦና ውቅር ለውጥ መምጣት እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተውበታል፡፡ በየትውልድ ላይ የሚቀየሩ ነገሮች እንደሚስተዋሉ ያመለከቱት አንድ ዘለላ ምሳሌ በማምጣት ነው፡፡

‹‹በአሁን ሰዓት የአሜሪካን ሕዝብ መዝሙር ለማጥናት የሚተጉ ወጣቶችን አስተውላለሁ፡፡ አንፃሩ ደግሞ የኢትዮጵያ ሕዝብ መዝሙር ከ‹ኢትዮጵያ ሆይ› ጀምሮ እስካሁን እስካለው ‹የዜግነት ክብር› ድረስ ያለውን መዝሙር የምናውቀው ስንት ነን? ብንል በጣም ጥያቄ ውስጥ የምንገባ ነው የሚሆነው፡፡ የልቦና ውቅር ሰፊ ነው ወደ ሚለው ይወስደናል፡፡

የምንመኛት ኢትዮጵያን በተመለከተ በልማቱ ዘርፍ ምርታማነትና ጥራት ላይ ብዙ ጽፈዋል፡፡ ወደዚያ ለመድረስ ከፈለክ ግን መጀመርያ ያለውን የልቦና አወቃቀራችንን ለመቀየር መዘጋጀት አለብን የሚለው ከዚህ መጽሐፍ ላይ የምወስደው ነው፡፡››

በዶ/ር መስፍን አርአያ አገላለጽ፣ የልቦና ውቅርን ከሰብእና ጋር የሚገናኝ ነው፡፡ ሰብእና አንድ ሰውን ሲያመለክት ልቦና ውቅር ደግሞ በዚያ ሰውና በአካባቢው የሚቀረፁ ሒደቶችን ያመላክታል፡፡

‹‹እነሆ መንገድ ለኢትዮጵያ. . .›› መንግሥታዊና ግላዊ ተቋማት እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትስስር የተሻለ እንዲሆን ይመክራል፡፡ ምርታማነት እንዲጨምር ያሠራር መንገዶችን በቀጣይነት ስለማሻሻል ያትታል፡፡ በተለይም የሐሳቦች ዋነኛ አትኩሮቱ ጥራት ላይ ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ዕድገት ያገልግሎትና ምርት ጥራት ጉዳይ የሁሉም ኃላፊነት መሆኑንም አስረግጦ ይናገራል፡፡ ይህንኑ  ፕሮፌሰር ዳንኤል ሲያመለክቱ፣ ‹‹ጥራት ሒደት ነው፤ ጥራት የዕድገት ደረጃ ነው፡፡ አሜሪካኖቹ አውሮፓውያኑን በሰባት ዓመት ይበልጧቸዋል ይላል ሊትሬቸሩ፤ አውሮፓውያኑ ደግሞ እኛን በብዙ ዓመት ይበልጡናል፡፡ ስለዚህ ይህን የጥራት ባህል የምናመጣው እያንዳንዳችን ከልጅነት ጀምሮ ስንማር ነው፤›› ብለዋል፡፡

በመድረኩ እንደታወሰው፣ አገሪቱ አማካይ ነገር ላይ ነች፡፡ በድህነትና በብልፅግና፡፡ እኩልነት የሰፈነባት ኢትዮጵያን ለማምጣት ‹‹እነሆ መንገድ ለኢትዮጵያ . . .›› አንድ ማሳያ ነው፡፡ ‹‹የመንግሥተ ሰማያት መንገድ ቀጭን ነች፡፡ የኢትዮጵያን ቀጭን መንገድ ሁላችን ልንጓዝበት ይገባል፡፡ በሩ እየሰፋ ይሄዳል፡፡ የኢትዮጵያችን በር መስፋት አለበት፡፡ ጥቂቶች የሚበለፅጉበት ሌሎች መናጢ የሚሆንበት መንገድ መኖር የለበትም፡፡ የልቦና ውቅር ለውጥ መምጣት አለበት፤›› በመድረኩ ተስተጋባ፡፡

በአገሪቱ መተባበርና መወዳደር (Cooperative and Competition) ለዕድገት እንደሚበጅ ደራሲው ያሰመሩበት ቁም ነገር በምሳሌ የታጀበ ነው፡፡ ‹‹አቅርቦት (Delivery)›› በተሰኘው ምዕራፋቸው ያነሱት ነጥብ እዚህ ላይ ይነሳል፡፡

‹‹የጫማ ፋብሪካ የሚጠይቀው የአቅርቦት መጠን እራሱ ካለው የአቅርቦት አቅም በላይ ከሆነ፣ እሱን መሰል ከሆኑ ሌሎች ፋብሪካዎች ጋር በመተባበር የተጠየቀውን የአቅርቦት መጠን ማሟላት ይችላል፡፡ ተመሳሳይ ድርጅቶች በጋራ ሆነው መሥራት፣ ሲያስፈልግም ደግሞ እርስ በርስ መወዳደራቸው ክላስተሪንግ በመባል ይታወቃል፡፡ ይህን ክላስተሪንግ የተሰኘ ጽንሰ ሐሳብ ማስተማሪያ የሚሆን ምሳሌ ሳስብ እ.ኤ.አ. 2003 የተካሄደው የፓሪሱ የዓለም ሻምፒዮና የ10,000 ሜትር ሩጫ ውድድር ወደ አዕምሮዬ ይመጣል፡፡

‹‹በዚያ ፈታኝና እጅግ እልህ አስጨራሽ ውድድር ላይ ኢትዮጵያውያኑ ኃይሌ ገብረ ሥላሴ፣ ቀነኒሳ በቀለና ስለሺ ስሕን ተወዳድረዋል፡፡ ሦስቱ ጀግና አትሌቶቻችን ከመነሻው ጀምሮ በመተባበር ሌሎቹን ተወዳዳሪዎች ካዳከሟቸው በኋላ ሦስቱም ብቻቸውን አፈትልከው ወጥተዋል፡፡ ዓለም በአንድ ሳንባ የሚተነፍስ እስኪመስል ድረስ ትንፋሽ አሳጥቶ የነበረው ውድድር ላይ ተነጥለው የወጡት አትሌቶች ቀሪው ሥራቸው እርስ በርስ መወዳደር ነበር፡፡ እናም ሦስቱ ብርቱዎች እርስ በርስ ተፎካክረው ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ወጡ፡፡

‹‹እነዚህ ጀግኖች ተመሳሳይ ስልት ተጠቅመው እ.ኤ.አ. 2004 በአቴና ኦሊምፒክ ከዚያም እ.ኤ.አ. 2008 በቤጂንግ ኦሊምፒክ የ10,000 ሜትር ሩጫ ውድድሮች ላይ በተደጋጋሚ አስደናቂ ውጤት አግኝተዋል፡፡ ይህ ነው እንግዲህ በመተባበርና በመወዳደር አንፀባራቂ ድል ማስመዝገብ፡፡ ኢንዱስትሪዎቻችንም አንዱ ብቻውን አከናውኖ ማቅረብ የማይችለውን በመተባበር ቢሠሩ በድል አድራጊነት መወጣት ይችላሉ፡፡››

-----------------------------------------------------

SOURCE :- https://www.ethiopianreporter.com/49545/

                  www.henockyared.com/2016/08/blog-post_20.html

አውደ ሰብ - ፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው ክፍል - 1 EBC /EthiopianBroadcastingCorporation/


አውደ ሰብ - ፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው ክፍል - 2


የልቦና ውቅር - በሃገራችን በአስተሳሰብ በአመለካከት እንዴት መለወጥ ይቻላል ከፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው ጋር ቆይታ


የንባብ ክሊኒክ - ቆይታ ከፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው ጋር ክፍል 1 ESAT


የንባብ ክሊኒክ - ቆይታ ከፕሮፌሰር ዳንኤል ቅጣው ጋር ክፍል 2 ESAT






Wednesday, October 12, 2022

አንጋፋው የስፖርት ሰው ፍቅሩ ኪዳኔ ሲታወሱ

 


1927 ዓ.ም - 2015 ዓ.ም 

በኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኝነት ታሪክ በዋናነት የሚነሱት ጋዜጠኛና ደራሲ ፍቅሩ ኪዳኔ የተወለዱት በ1927 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ነው።

አባታቸው የቅዱስ ጊዮርጊስ ደጋፊ የነበሩ ሲሆን፣ የክለቡን ተጫዋቾች ከትምህርት ቤት ወደ ስታዲየም ይዞ በመሄድ ይታወሳሉ፡፡

በእነዚህ ጊዜያት ሁሉ ከአባታቸው ጋር የመሆን ዕድል የነበራቸው አቶ ፍቅሩ በኋላ የስፖርት አስተማሪ ሆነዋል።

በኢትዮጵያ ሬዲዮና የተለያዩ የአገር ውስጥ የሕትመት ውጤቶች ስለ አገር ውስጥ ስፖርት መዘገብ የጀመሩት አቶ ፍቅሩ በ1943 ዓ.ም በሱዳን እና ኢትዮጵያ መካከል የተደረገውን ጨዋታ በቀጥታ በሬዲዮ ማስተላለፍ የቻሉ የመጀመሪያው የስፖርት ጋዜጠኛ ናቸው።

አቶ ፍቅሩ የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር በ1961 ዓ.ም ሲመሰረት የመጀመሪያው ፕሬዝደንት የነበሩ ሲሆን በብስክሌት ፌዴሬሽን፣ቴኒስ ፌዴሬሽን እና በኢትዮጵያ የኦሊምፒክ ኮሚቴ በዋና ፀሐፊነት፣ በኢትዮጵያ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን የሕዝብ ግንኙነት በመሆን አገራቸውን አገልግለዋል፡፡

በዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ እና የአፍሪካ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ውስጥም በአመራርነት ፣ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) የቀድሞ ፕሬዝደንት የነበሩት የኢሳ ሃያቱ አማካሪ ጭምር የነበሩ ፡፡

ከ1969 ዓ.ም ጀምሮ ኑሯቸውን በፈረንሳይ መዲና ፓሪስ ያደረጉት አቶ ፍቅሩ በአገሪቷ ለሚገኘው ዕለታዊ የስፖርት ጋዜጣ ለኪፕ እና ሳምንታዊ የእግር ኳስ መጽሔት ፉትቦል ፍራንስ፣ ዶቼቬሌ (የጀርመን ድምፅ) እና ሌሎች የአለም አቀፍ ታዋቂ መገናኛ ብዙሃን መስራት ከመቻላቸው በተጨማሪ “የፒያሳ ልጅ” እና “የስፖርት ጨዋነት ምንጮች” የተሰኙ መጻሕፍት መጻፍ ችለዋል፡፡

ጋዜጠኛና ደራሲ ፍቅሩ ኪዳኔ አንድ ልጅ ያላቸው ሲሆን ሁለት የልጅ ልጆችንም አይተዋል።

ደራሲ -  ፍቅሩ ኪዳኔ

አከፋፋይ - ዓይናለም የመጻሕፍት መደብር

ዋጋ - 70 ብር

የታተመበት ዓመት - 2001 ዓም

የፒያሳ ልጅ በአስራ ስድስት ምእራፋት ተከፋፍሎ፤ 456 ገፆች ሲኖሩት፤ 
ከሃምሳ በላይ በሚሆኑት ገፆቹ “እንዴት አይናገር ይናገራል ፎቶ…” እንዲሉ፤ 
ማራኪና ታሪካዊ የሆኑ የፎቶግራፍ ማስረጃዎች ያካተተ ሲሆን የህትመት ዘመኑም 2009 ዓ.ም  

አንጋፋው የስፖርት ሰው ፍቅሩ ኪዳኔ ሲታወሱ


በኢትዮጵያ የተለያዩ ስፖርቶች ውስጥ አሻራቸውን ካሳረፉ ሰዎች መካከል በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ አቶ ፍቅሩ ኪዳኔ።

በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያውን የእግር ኳስ ግጥሚያ በሬዲዮ ከማስተላለፍ አንስቶ፣ በሬዲዮና በጋዜጣ ላይ ስፖርትን የሚመለከቱ ዘገባዎች ቦታ እንዲያገኙ አድርገዋል።

በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ የስፖርት ተቋማት ውስጥ ጉልህ ሚና ካላቸው ጥቂት ኢትዮጵያውያን መካከል በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። በ87 ዓመታቸው ያረፉት አቶ ፍቅሩ ኪዳኔ እንዴት ይታወሳሉ?

መስመር

በኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኝነት ሙያ የመጀመሪያው የእግር ኳስ ግጥሚያ በሬዲዮ ከማሰራጨት እስከ ፀሐፊ እና የስፖርት ሕትመቶች ዋና አርታዒነት ደርሰዋል።

በስፖርት እውቀታቸው ዓለም አቀፍ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ሴክሬታሪያት ፀሐፊ ሆነው አገልግለዋል። በዘረፉ ለስመዘገቡት አስተዋጽኦ በዓለም አቀፉ የስፖርት ፕሬስ ማኅበር የሕይወት ዘመን ስኬት ሽልማትን ተቀብለዋል።

ጥቅምት 01/2015 ዓ.ም. ፈረንሳይ ውስጥ በ87 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩትን አንጋፋውን የስፖርት ሰው ፍቅሩ ኪዳኔን ታዋቂው የስፖርት ጋዜጠኛው ገነነ መኩሪያ “የሕይወት ዘመናቸውን በሙሉ ለኢትዮጵያ ስፖርት ያዋሉ” ሲል ይገልጻቸዋል።

የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠ ታዋቂው ፍቅሩ ኪዳኔ ከቀድሞው የ IOC ፕሬዝዳንት ሁዋን አንቶኒዮ ሳምራንች ጋር


ፍቅሩ ኪዳኔከኔልሰን ማንዴላ ጋር

የመጀመሪያው የእግር ኳስ ግጥሚያ በሬዲዮ

አቶ ፍቅሩ ኪዳኔ እአአ 2016 ላይ ለሲቢሴስ አማርኛ ሲናገሩ፤ በኢትዮጵያ የሕትመት ውጤቶች እና የሬዲዮ ስርጭት ውስጥ የስፖርት ፕሮግራሞች እንዲከፈቱ ጥረት ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል።

አቶ ፍቅሩ እርሳቸው በጀመሩት የመጀመሪያው የሬዲዮ ፕሮግራም የኢትዮጵያ እና የሱዳን ብሔራዊ ቡድኖችን የእግር ኳስ ግጥሚያ ለመጀመሪያ ጊዜ ማሰተላለፋቸውን ይገልጻሉ።

አቶ ፍቅሩ ይህን ጨዋታ እንዴት በሬዲዮ እንዲያስተላለፉ የተደረገው በድንገትና ሳያስቡት ነበር። ይህም ጨዋታውን ለሕዝብ ጆሮ እንደሚያደርሱ ሳይነገራቸው እና ምንም አይነት ዝግጅት ሳያደርጉ ነበር የመጀመሪያውን የቀጥታ ሥርጭት ያስተላለፉት።

አቶ ፍቅሩ ይህን ጨዋታ እንዴት በሬዲዮ እንዲያስተላለፉ የተደረገው በድንገትና ሳያስቡት ነበር። ይህም ጨዋታውን ለሕዝብ ጆሮ እንደሚያደርሱ ሳይነገራቸው እና ምንም አይነት ዝግጅት ሳያደርጉ ነበር የመጀመሪያውን የቀጥታ ስርጭት ያስተላለፉት።

ሱዳኖች የእግር ኳስ ጨዋታውን ከአዲስ አበባ በቀጥታ በሬዲዮ እንደሚያስተላልፉ የተረዱት አቶ ይደነቃቸው ተስማ፣ እኛስ ለምን አናስተላልፍም? በማለት ሐሳቡን በድንገት እንዳመጡት ጋዜጠኛ ገነነ ይናገራል።

ከዚያም ከኢትዮጵያ ሬዲዮ ኃላፊዎች ጋር በመነጋገር የቀጥታ ሥርጭቱ በመፈቀዱ ጨዋታው ከመጀመሩ ከደቂቃዎች በፊት አቶ ፍቅሩ እንደሚፈለጉ በድምጽ ማጉያ ተጠርተው ነበር በድንገት ተጠርተው የቀጥታ ሥርጭት ማይክሮፎን የቸበጡት ይላል ገነነ።

አቶ ፍቅሩም “ጨዋታው ሊጀመር 10 ደቂቃዎች ብቻ ሲቀሩት ትፈለጋለህ ተብዬ ተጠርቼ ስሄድ፣ አቶ ይድነቃቸው አንተ እኮ ነው የምትፈለገው ብሎ የተጫዋቾችን አሰላለፍ ሰጥቶ ጨዋታውን እንዳስተላልፍ ነገረኝ” ሲሉ አስታውሰዋል።

“ጨዋታው ሊጀመር 10 ደቂቃዎች ብቻ ሲቀሩት ትፈለጋለህ ተብዬ ተጠርቼ ስሄድ፣ አቶ ይድነቃቸው አንተ እኮ ነው የምትፈለገው ብሎ የተጫዋቾችን አሰላለፍ ሰጥቶ ጨዋታውን እንዳስተላልፍ ነገረኝ።”

ከዚያ በኋላ በኢትዮጵያ የስፖርት ውድድር ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ከአዲስ አበባ ስታዲዮም (በ1948 ዓ.ም.) የእግር ኳስ ጨዋታ በሬዲያ በቀጥታ በሬዲዮ በማስተላከፍ አቶ ፍቅሩ ቀዳሚው ሆኑ።

በሕትመት ውጤቶች ላይም ቢሆን ስፖርታዊ ጉዳዮችን መዘገብ የተጀመሩት በአቶ ፍቅሩ ጥረት ነበር። ጋዜጠኛ ገነነ መኩሪያ ለቢቢሲ ሲናገር፤ “በጋዜጦች ላይም ስፖርት የሚባል አይታወቅም ነበር። ከ1950 በኋላ ፍቅሩ ነበር መጻፍ የጀመረው።”

ጫማ ለአበበ ቢቂላ

ገነነ እንደሚለው በባዶ እግሩ የኢሊምፒክ ማራቶንን በማሸነፍ የሚታወቀው የዓለማችን ታላቁ የማራቶን ሯጭ አበበ ቢቂላ በጫማ እንዲሮጥ ያደረጉት አቶ ፍቅሩ ኪዳኔ ናቸው።

“ፍቅሩ ከአንድ ጫማ አምራች ድርጅት ጋር ተነጋግሮ ለአበበ በነጻ የመሮጫ ጫማ እንዲሰራለት አስደርጓል። ጫማ አምራቹም በአበበ ስም ታዋቂነትን ለማግኘት ችሏል።”

በኒውዮርክ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ውስጥ ሲሰሩ የቆዩት አቶ ፍቅሩ፣ ወታደራዊው መንግሥት ወደ ሥልጣን በመጣበት ጊዜ እንደወጡ ቀርተው ለበርካታ ዘመናት በተለያዩ አገራት ውስጥ ኖረዋል።

ነገር ግን ባሉበት ሆነው በኢትዮጵያ የተለያዩ ስፖርቶች እንዲጎለብቱ የሚችሉትን አስተዋጽኦ ሲያበረክቱ ቆይተው፤ አብዛኛውን እድሜያቸውን በቆዩባቸው የውጭ አገራት ውስጥ ሆነው እንኳን ለኢትዮጵያ ስፖርት ሲሰሩ እንቆዩ ገነነ ገልጿል።

አቶ ፍቅሩ በኢትዮጵያ የተለያዩ ስፖርቶች ውስጥ ፍቅሩ ያልገቡበት ዘርፍ የለም የሚለው ገነነ፣ አሁን ትኩረትን እየሳበ ያለው የሴቶች እግር ኳስ እንዲጎለበት የአቶ ፍቅሩ ሚና ጉል እንደነበር ይጠቅሳል።  

ፍቅሩ ከእግር ኳስ ባሻገር በተለያዩ የስፖርት አይነቶች ውስጥ ኢትዮጵያ ውክልና እንዲኖራት በግሉ የቻለውን ሁሉ ሲያደርግ እንደቆየ የሚናገረው ጋዜጠኛ ገነነ፤ ብዙም አቅም የሌላቸው የስፖርት ፌዴሬሽኖችን በመወከል በእራሱ ወጪ በዓለም አቀፍ ስብሰባዎች ላይ ይሳተፍ ነበር።

እንዲሁም በደቡብ አፍሪካ የነበረውን የዘር መድልዎ (አፓርታይድ) ሥርዓት በመቃወም አገሪቱ ከዓለም አቀፍ የስፖርት ውድድሮች እንድትታገድ ከአቶ ይድነቃቸው ተሰማ ጋር ከፍተኛ ጥረት ከማድረግ ባሻገር፤ በዓለም አቀፍ ሕትመቶች ላይ ፀረ አፓርታይ የቅስቀሳ ጽሁፎችንም ያቀርብ እንደነበር ገነነ አስታወሷል።

የዓለም ዋንጫን በፕሮጀክተር

አቶ ፍቅሩ ስፖርት በመገናኛ ብዙኃን ላይ ቦታ እንዲያገኝ ከመጣራቸው ባሻገር፣ ቴሌቪዥን ባልተስፋፋበት በዚያ ዘመን ከአዲስ አበባ ውጪ ያለው ስፖርት አፍቃሪ ታላላቅ የእግር ኳስ ጨዋታዎችን እንዲመለከትም አስችለዋል።

ለዚህም እአአ 1958 በስዊዲን አገር ተካሂዶ የፔሌ ትውልድን የያዘው የብራዚል ብሔራዊ ቡድን ዋንጫ የወሰደችበትን ግጥሚያ አቶ ፍቅሩ በክፍለ አገር ከተሞች እየተጓዙ በፕሮጀክተር ጨዋታውን ያሳዩ እንደነበረ ጋዜጠኛ ገነነ ይናገራል።  

“እኛ ፔሌ፣ ጋሪንቻ የሚባሉትን በስም እንኳ አናውቃቸውም ነበር። እሱ በየክፍለ አገሩ ዞሮ ካሳየ በኋላ ነው ተጫዋቾቹ ኢትዮጵያ ውስጥ የታወቁት።”

አቶ ፍቅሩ ኪዳኔ በስፖርት ጋዜጠኝነት ሙያ ከማገልገላቸው በተጨማሪ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውስጥ፣ የማስታወቂያ ባለሙያ ሆነውም ሠርተዋል።

በተጨማሪም በመንግሥታቱ ድርጅት በኩል ኢትዮጵያ ወደ ኮንጎ ጦሯን ባሰማራችበት ወቅት ጦሩን የሚመሩት የኢትዮጵያ ጄኔራሎች ፈረንሳይኛ የሚናገር ወጣት በመፈለጋቸው፣ ፍቅሩ የመቶ አለቃ ማዕረግ ይዘው ወደ ኮንጎ መዝመተውም ነበር።

ይህ አጋጣሚ ነበር አቶ ፍቅሩ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውስጥ የሥራ ዕድል በር ከፍቶላቸው የማስታወቂያ ባለሙያ ሆኖ የመስራት ዕድልን እንደከፈተላቸው ጠቅሰው ነበር።

ኦሊምፒክ እና አቶ ፍቅሩ

አቶ ፍቅሩ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ስለኦሊምፒክ ጨዋታዎች ያለው እውቀት እምብዛም ባልነበረበት ወቅት ውድድሩን ለአገሬው ለማስተዋወቅ መጽሐፍ እስከ ማሳተም ደርሰው ነበር።

“የኦሊምፒክ ጨዋታ የሚል መጽሐፍ በ1960 አሳተምኩ። ይህን መጽሐፍ ያዘጋጀሁት ሕዝቡ ስለ ኦሊምፒክ ጨዋታዎች እውቀት እንዲኖረው ነው።”

ይህን መጸሐፍም ለትምህርት ሚኒስቴር በመስጠት በአገሪቱ ባሉ ትምህርት ቤቶች እንዲታደሉ በማድረግ ወደ ወጣቶች እንዲደርስ አድርገዋል።

አቶ ፍቅሩ ከስፖርት ጋር በተቆራኘው ሕይወታቸው በበርካታ ኃላፊነቶች ላይ አገልግለዋል። በኢትዮጵያ የወቅቱ የማስታወቂያ ሚኒስቴር ውስጥ ተቀጥተው የኢትዮጵያ የብስክሌት ፌዴሬሽን፣ የቴኒስ ፌዴሬሽን፣ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሆነው አገልግለዋል።

አቶ ፍቅሩ የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማኅበርን አቋቁመው የማኅበሩ ፕሬዝዳንት በመሆንም ሠርተዋል።

ከኢትዮጵያም ውጪ አቶ ፍቅሩ ከኦሊምፒክ ውድድር ጋር ባላቸው ቁርኝት ትልቅ የሥልጣን ደረጃ ላይ መድረስም ችለው ነበር።

ጋዜጠኛ ገነነ መኩሪያ አቶ ፍቅሩ የመጀመሪያው ጥቁር የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ እና የፕሬዝዳንቱ ልዩ አማካሪ ሆነው ተሹመው እንደነበረ ይገራሉ።

የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን የፕሬዝዳንቱ ልዩ አማካሪ፣ የአፍሪካ የሰፖርት ጋዜጠኞች ማኅበር ዋና ፀሐፊ በመሆን አገልግለዋል።

የፊፋ የፕሬስ ኮሚቴ አባል የነበሩ ሲሆን እንደ ቢቢሲ፣ የአሜሪካ ድምጽ፣ ሬዲዮ ፍራንስ ኢንተርናሽናል ላሉ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘገባዎችን ይሰሩም ነበር።

ጋሽ ፍቅሩ ኪዳኔ የፒያሳ ልጅ ከጥቂት ዓመታት በፊት 
ፓሪስ በሚገኘው ቤታቸው ተቀብለውኝ  በሙያቸው፣ 
በእውቀታቸው፣ በፍቅራቸው ለሃገራቸው ለኢትዮጵያ እና
 ለኢትዮጵያውያን ካበረከቱት ከታሪካቸው በጥቂቱ ጨልፈው አጫውተውኝ ነበር አዜብ ወርቁ

የዛሬ 6 ዓመት ከጋሽ ፍቅሩ ኪዳኔ ጋር ሩዋንዳ ኪጋሊ ሻይ ጠጡበት ብለው ለእያንዳንዳችን 50 ዶላር ሰጥተውን ነበር ሰይድ ኪያር


ጋሽ ፍቅሩ ኪዳኔ ከስፓርት ጋዘጠኞች ዬናስ ተሾመ እና አረጋ ከፈለው

ጥር 17፡2008 ዓ.ም ከጋዜጠኛ ፍቅሩ ኪዳኔ ጋር የተደረገ ቆይታ ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጋር



ጋዜጠኛ ፍቅሩ ኪዳኔ SBS Amharic 

Life and Legacy: Fikrou Kidane – Pt 1 - SBS Amharic



Life and Legacy: Fikrou Kidane – Pt 2 - SBS Amharic

ፍቅሩ ኪዳኔ፤ በክፍል ሁለት የስፖርቱ መስክ ግለ-ሕይወት ትረካቸው፤ ከኮንጎ ዘመቻ ተሳትፎአቸው ተነስተው የቀድሞው የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚደንት ኹዋን አንቶኒዮ ሳማራንች ጽህፈት ቤት ዋና ዳይሬክተርነት ዘመናቸው ድረስ ያወጋሉ።


Life and Legacy: Fikrou Kidane – Pt 3 - SBS Amharic

ፍቅሩ ኪዳኔ፤ የአፓርታይድ አገዛዝ የዓለምን ኅሊና እየሞገተ በነበረበት ወቅት በስፖርቱ ዘርፍ እንደምን የፀረ-አፓርታይድ ትግሉ አካል ለመሆን እንደበቁ፤ የመጀመሪያው የዓለም አቀፍ ኦሎምፒክ ኮሚቴ የስፖርት ተጠሪ ሆነው ከኔልሰን ማንዴላ ጋር እንደተገናኙ፤ በዓለም አቀፍ የሚዲያ አውታሮች እንዴት እንደሠሩ፤ ስለ አቶ ይድነቃቸው ተሰማና የውቤ በረሃ ትዝታዎቻቸውን አካትተው ያነሳሉ።



ሔኖክ ያሬድ

http://www.danielkibret.com/2010/11/blog-post_21.html

https://ghion-meg.com/2021/09/03/%E1%89%B5%E1%88%9D%E1%88%85%E1%88%AD%E1%89%B5-%E1%89%A0%E1%8A%A2%E1%89%B5%E1%8B%AE%E1%8C%B5%E1%8B%AB-%E1%8D%8D%E1%89%85%E1%88%A9-%E1%8A%AA%E1%8B%B3%E1%8A%94/

https://amharic.voanews.com/a/ethiopian-fikru-kidane-honored-with-sport-award-for-his-contribution-in-athletics/3276632.html

http://www.tadias.com/index.php?s=60th

https://www.aipsmedia.com/aips/pages/articles/2018/23368.html

https://www.aipsmedia.com/aips/pages/articles/2022/32933.html

https://ethiopiazare.com/amharic/images/doc/pdf/books/2011/1105ye-piassa-lij-by-mesfin-mammo.pdf


********************************

ምንጭ:-- https://www.bbc.com/amharic/articles/cx76v13n28eo