ከደራሲያን ዓምባ

Thursday, November 16, 2023

የምስኪኖቹን መንደር በስካቫተር ያፈረሰው ሚሊየነር

የምስኪኖቹን መንደር በስካቫተር ያፈረሰው ሚሊየነር

Chinese Millionaire Bulldozes This Village’s Run Down Huts And Builds Free Houses For Residents

በደቡባዊ ቻይና ግዛት የምትገኘው የደሳሳዋ ዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎች ፡ ሸቀጣሸቀጥ ጭነው ከሚመጡ አሮጌ ከባድ መኪኖች ውጭ አንድም መኪና ወደመንደራቸው ዘልቆ አይተው አያውቁም ። ዛሬ ግን እጅግ ዘመናዊ ፡ መርሰዲስ መኪና መጥታ ቆማለች ።

እናም ነዋሪዎች ፡ በመኪናዋ እዚህ መገኘት በመገረም ዙሪያውን ከበው በማየት ላይ እያሉ ፡ አንድ በጠባቂዎች የታጀበ እድሜው በሀምሳዎቹ የሚገመት ሰው ከመኪናው ወጣ ። ማንም ደፍሮ ሰላም ሊለው ወይም ሊያናግረው የመጣ ሰው ግን አልነበረም ። እናም ሰውየው መንደሩን ለደቂቃዎች ከተመለከተ በኋላ ተመልሶ ወደመኪናው ገብቶ ሄደ ።


ይህ በሆነ በማግስቱ ወደዛች ደሳሳ መንደር ሌላ መኪና መጣ ። ከመጡት ሰወች ውስጥ የትናንቱ ሰውዬ አልነበረም ። በቁጥር በዛ የሚሉ መሀንዲሶች ነበሩ የመጡት ። በዚህ ጊዜ ነዋሪዎቹ ነገሩ ገባቸው ፡ የትናንቱ ሰው ባለሀብት መሆኑን በሁኔታው አውቀዋል ፡ እናም ይህን መንደር ሊያፈርስ መሀንዲሶች ልኳል ።


እነዚህ ነዋሪዎች ፡ ይህም ኑሮ ሆኖ ፡ ደሳሳ ጎጇቸውን የሚያፈርስ ሰው ይመጣል ብለው መቼም አስበው አያውቁም ነበር ። እና ሽማግሌዎች ቀርበው መሀንዲሶቹን አናገሯቸው ። ፍርሀታቸው ልክ ነበር ፡ ትናንት የመጣው ባለሀብት እዚህ መንደር ላይ ሪል ስቴት መገንባት ፈልጓል ፡፡ ለዚህም ከመንግስት ፍቃድ እንዳገኘ ፡ ከሰባ በላይ ለሚሆኑት ለመንደሩ ነዋሪዎችም ካሳ እና መኖሪያ ቤት የሚገነቡበት ገንዘብ እንደሚሰጣቸው እስከዛ ግን በመጠለያ መቆየት እንደሚችሉ ፡ እስከነገ ድረስም እቃቸውን አውጥተው በተዘጋጀላቸው ማረፊያ እንዲያስቀምጡ ነግረዋቸው ሄዱ ።

ከቀናት በኋላም ፡ ብዛት ያላቸው ግሪደሮች እና የህንጻ ሰራተኞች ትንሿን መንደር አጥለቀለቋት ።

ያለቻቸውን አሮጌ እቃ አውጥተው ከቤታቸው አቅራቢያ በተዘጋጀላቸው መጠለያ ውስጥ የገቡት የዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎች ፡ ቆመው እያዩ ለዘመናት የኖሩባቸው ደሳሳ ጎጆዎች በስካቫተር ፈረሰ ።


ቃል የተገባላቸው ቤት መስሪያ ቦታም ሆነ ካሳ ሳይሰጣቸው ለወራት በመጠለያ እየተረዱ ቆዩ ። ከአመታት በፊት ከነሱ ብዙም በማይርቅ ቦታ የሚገኙ መንደሮች ልክ እንደነሱ በጨካኝ ባለሀብት ተፈናቅለው ፡ መሰደዳቸውን እያሰቡ ፡ እጣ ፈንታቸውን መጠባበቅ ጀመሩ ።

ይህ በሆነ በጥቂት ወራት ውስጥም የባለሀብቱ ዘመናዊ ቪላዎች ተገንብተው ተጠናቀቁና ፡ ነዋሪዎቹ በስነስርአቱ ላይ እንዲገኙ ፡ በፕሮግራሙም ላይ ለነሱም ቃል የተገባላቸው ካሳ እንደሚሰጥ ተነገራቸው ። ብዙዎች ነዋሪዎች ግብዣውን ተቃወሙ ።


ትንሿ የዦንኪንግ መንደር ዛሬ በልዩ ሁኔታ ደምቃለች ። ከሰባ በላይ ዘመናዊ መኖሪያዎችን ለመመረቅ የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል ። ያቺ የድሆች መንደር ፡ አይታ በማታውቀው ሁኔታ በዘመናዊ መኪኖችና በሀብታሞች ተጥለቅልቃለች ።

የምረቃው ፕሮግራም ተጀመረ ።

 

ያ ፡ በመጀመሪያ ቀን መርሰዲስ መኪና ይዞ ወደዚህ መንደር የመጣው ባለሀብት ፡ ንግግር ለማድረግ ወደ መድረኩ ወጣ ።
ክቡራንና ክቡራት የዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎችና ፡ ክቡራን እንግዶች ዛሬ ልዩ የሆነውን ይህን የዘመናዊ መኖሪያ ቤት ፕሮጀክት ለመመረቅ ስለተገኛችሁ አመሰግናለሁ ።

እኔ የማየው ዛሬ ሚሊየነር መሆኔን አይደለም ። የኔ ስብእና የኔ የሀብት ምንጭ ይሄ መንደር ነው ።. ... እኔ ..... ትንሽ ልጅ ሆኜ የምታውቁኝ Xiong Shuihua ነኝ ። 


በርግጥ ከዚህ መንደር ከወጣሁ ብዙ አመታት ተቆጥረዋልና ፡ አላወቃችሁኝም ። እኔ ግን ሁላችሁንም አስታውሳለሁ ።

ለኔና እጅግ ድሆች ለነበርነው ቤተሰቦቼ በየወሩ ቀለብ ይቆርጥልን የነበረው ሚስተር ዣይን ፡ ከልጆቻቸው እኩል ልብስ ይገዙልኝ የነበሩት የሚስ ታዮኒ ቤተሰቦች ፡ ሲርበን የሚያበሉን የዚህ መንደር ነዋሪዎች ሁላችሁንም አስታውሳለሁ ።

የኔ የአሁን ህይወት ላይ የመሰረት ድንጋይ ያስቀመጣችሁ እናንተ ናችሁ ። ለዚህም ነው መንደሩን ለመለወጥ በተሻለ ህይወት እንድትኖሩ ለማሰብ የተገኘሁት ።


 

እናም እነዚህ ቤቶች የተሰሩት ለናንተ ነው ። ያለምንም ክፍያ በነዚህ ቤቶች ትኖራላችሁ ። ቤቶቹ ንብረቶቻችሁ ናችሁ ። በነጻ የተሰጧችሁ አይደሉም ፡ ከአመታት በፊት ለኔና ለቤተሰቦቼ መልካም ነገር በማድረግ ኢንቨስት አድርጋችሁበታል ።

እያለ እንባ እየተናነቀው ሲናገር የመንደሩ ሰወች በሙሉ በታላቅ ድንጋጤ ውስጥ ሆነው ይሰሙት ነበር ።
ባለሀብቱ ንግግሩን ቀጥሏል ።


 

እናም ከሀምሳ ሚሊየን ዶላር በላይ ወጭ ተደርጎባቸው የተሰሩት ፡ እነዚህ ቤቶች በፈረሱት ቤቶቻችሁ ቁጥር ልክ የተሰሩ ናቸው ፡ ነገ አዳዲስ የቤት እቃ የጫኑ መኪኖች ይደርሳሉ ። መብራትና ውሀም አትከፍሉም ። መስራት ለምትችሉ የስራ እድል ይዘጋጃል ፡ ለአቅመ ደካሞችና ማብሰል ለማይችሉ ደግሞ ዘመናቸውን ሙሉ የሚፈልጉትን መርጠው የሚመገቡበት መመገቢያ አዳራሽም ተገንብቷል ። 

 

የናንተ ውለታ ከዚም በላይ ነው አላቸውና ፡ ከመድረኩ ወረደ ።

 

 


 

ከመጻሕፍት ዓለም - Book shelf 📗📚📖
© Wasihune Tesfaye

https://www.atchuup.com/xiong-shuihua-acts-of-kindness/

https://www.dailymail.co.uk/news/article-2850436/Millionaire-Chinese-businessman-bulldozes-run-huts-village-grew-builds-luxury-flats-residents-instead-free.html




Wednesday, August 30, 2023

ጆሴፍ ፑልቲዘር

 

የፕሬስ ነጻነት ጠበቃ - ጆሴፍ ፑልቲዘር 

ጋዜጠኛ፣ መርማሪ  ሪፖርተር፣ አሳታሚ፣ የፕሬስ ነጻነት ጠበቃ፣ በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያውን የጋዜጠኝነት ት/ቤት ከፍቷል - በተጨማሪም ለጋዜጠኝነትና ሥነጽሁፍ ዘርፎች፣ ዝነኛውን የፑልቲዘር ሽልማትም ፈጥሯል፡፡

ጆሴፍ ፑልቲዘር፤ የተሻለ የዕይታ ብቃት ይዞ ቢወለድ ወይም ቼዝ መጫወት ባይችል ኖሮ፣ ጋዜጦቻችን ዛሬ ከምናውቃቸው የተለዩ ይሆኑ ነበር፡፡ ጆሴፍ በ1860ዎቹ በሃንጋሪ በታዳጊነት ዕድሜው ሳለ፣ ወታደር የመሆን ብርቱ ፍላጎት ነበረው፡፡ ነገር ግን ዓይኑ (ዕይታው) ደካማ በመሆኑ የተነሳ የትኛውም ሠራዊት ሊቀበለው አልቻለም፡፡ በመጨረሻ ግን የአሜሪካ ቀጣሪዎች፣ በአሜሪካው የእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ እንዲዋጋ መለመሉት፡፡  
በወታደርነት ለአንድ ዓመት ያገለገለው ጆሴፍ፤ ከእርስ በርስ ጦርነት ህይወቱ ተርፎ እዚያ አሜሪካ ተቀመጠ - ያገኘውን  ሥራ እየሰራና እንግሊዝኛ ቋንቋ እየተማረ፡፡ ከዚያም በአጋጣሚ የተከሰተ ድንገተኛ ትውውቅ፣ የራሱንም ህይወት ሆነ የዓለም ጋዜጠኝነትን ታሪክ ለዝንተ-ዓለም ለወጠው፡፡
እንዲህ ነው የሆነው፡፡
ጆሴፍ በቅዱስ ሉዊስ ቤተመጻህፍት ውስጥ እያጠና ሳለ፣ ሁለት ወንዶች ቼዝ ሲጫወቱ ይመለከታል፡፡ ጠጋ ብሎም የአንደኛውን የቼዝ አጨዋወት በማድነቅ ተናገረ፡፡ ከዚያም ሦስቱ ሰዎች መጨዋወት ይጀምራሉ፡፡ ሁለቱ ሰዎች የጋዜጣ አሳታሚዎች ነበሩ፡፡ እናም የሥራ ዕድል ሰጡት - ለጆሴፍ፡፡  

ጆሴፍ ፑልቲዘር ብሩህና ትጉህ ሪፖርተር መሆኑን አስመሰከረ፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላም የጋዜጣ አሳታሚ ሆነ፡፡ ከዚያም  አዋጭ  ድርድሮችን ተራ በተራ  ሲያካሂድ ቆይቶ፣ የከተማው ትልቁን ጋዜጣ በእጁ አስገባ - ”St. Louis Post- Dispach” የተሰኘውን ጋዜጣ ገዛው፡፡


ይሄኔ ነው የፑልቲዘር እውነተኛ የላቀ አዕምሮ  የታየው፡፡ ጋዜጣውን የሰፊው ህዝብ ድምጽ አደረገው፡፡ ህገወጥ የቁማር ተግባራትን፣ የፖለቲካ ሙስናንና ዳጎስ ያሉ የግብር ስወራዎችን መመርመርና  ሃቁን አደባባይ ላይ ማስጣት ያዘ፡፡ ሰዎች ይህን አዲስ የምርመራ ጋዜጠኝነት ስታይል ወደዱለት፤የጋዜጣው ሥርጭትም በእጅጉ አሻቀበ፡፡
ጆሴፍ ፑልቲዘር ከታመመም በኋላ እንኳን ተግቶ መሥራቱን አላቋረጠም፤ እናም የዓይኑን ብርሃን ሊያጣም ደርሶ ነበር፡፡ ፑልቲዘር፤ጋዜጦች የማህበረሰቡን ዓላማ ማገዛቸው እንዲሁም ህዝቡን ከሸፍጥና ሙስና መታደጋቸው አስፈላጊ ነው ብሎ ያምን ነበር፡፡ ከጥቂት ዓመታት በኋላ ሌላ ጋዜጣ መግዛት ቻለ፡፡ የኒውዮርክን ጋዜጣ፡፡ የህዝበኝነት አቀራረቡንም ለብዙ ተደራሲያን ተገበረ፡፡



እ.ኤ.አ በ1909 ዓ.ም የኒውዮርክ ጋዜጣው፣ በአሜሪካ ታሪክ ታላቁ የፖለቲካ ቅሌት የተባለውን ታሪክ ሰበር ዜና አድርጎ አወጣው - የፓናማ ካናል ስምምነት፣ 40 ሚሊዮን ዶላር ህገወጥ ክፍያን  አጋለጠ፡፡ ይሄን ጊዜ የአሜሪካ መንግሥት ፍ/ቤት ሊያቆመው ሞክሮ ነበር፤ ነገር ግን ፑልቲዘር ”ፍንክች የአባ ቢላዋ ልጅ” አለ፡፡ በጽናት በመቆም፣ ለፕሬስ ነጻነት ትልቅ  ድል አስመዘገበ፡፡


ጆሴፍ ፑልቲዘር፤በዓለም የመጀመሪያው  የጋዜጠኝነት ት/ቤት፣ በኒውዮርክ፣ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ እንዲቋቋም ከሃብቱ ከፊሉን መድቧል፡፡ ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ ለጋዜጠኞችና ጸሃፍት ዓ መታዊ የሽልማት መርሃግብር የሚሆን ገንዘብም ለግሷል፤ ዛሬ ከዝነኞቹ የፑልቲዘር ሽልማቶች አንዱን ማሸነፍ፣ በጸሃፍት ዘንድ እንደ ልዕለ ኮከብ የሚያስቆጥር መሆኑ ይታወቃል፡፡   

ጆሴፍ ፑልቲዘር፤ ምንም እንኳ ወደ  ጋዜጠኝነት  የገባው በአጋጣሚ ቢሆንም ቅሉ፣ ጋዜጦች ዛሬም ድረስ ሊያሳኩት የሚተጉበትን ስታንዳርድ አስቀምጦ ነው ያለፈው፡፡

 ************************

ምን

 https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=31574:%E1%8B%A8%E1%8D%95%E1%88%AC%E1%88%B5-%E1%8A%90%E1%8C%BB%E1%8A%90%E1%89%B5-%E1%8C%A0%E1%89%A0%E1%89%83-%E1%8C%86%E1%88%B4%E1%8D%8D-%E1%8D%91%E1%88%8D%E1%89%B2%E1%8B%98%E1%88%AD&Itemid=209

Thursday, August 24, 2023

የኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን ተሳትፎ

 


የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እ.ኤ.አ. በ1983 በፊንላንድ ሔልሲንኪ ከተማ የተጀመረው በቀድሞ አጠራሩ የዓለም አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር አማካይነት ነው።

ከመጀመሪያው ውድድር በኋላ ሻምፒዮናው እስከ 1991 ድረስ፣ በየአራት ዓመቱ ይደረግ ነበር። ከዚያ በኋላ ግን ውድድሩ በሁለት ዓመት እንዲከናወን ተወሰነ።

በመጀመርያ ሻምፒዮና ከ153 አገሮች የተውጣጡ 1,333 አትሌቶች ተሳትፎ ማድረግ ችለዋል።

እ.ኤ.አ. በ1987 የሴቶች 10,000 ሜትር እና 10 ኪሎ ሜትር ዕርምጃ ተጨምሯል። በ1995 የሴቶች 3000 ሜትር በ5000 ሜትር ሲተካ። በ2005 የሴቶች 3000 ሜትር መሰናከል ተጨምሯል። ዓምና በአሜሪካ ኦሪገን በተከናወነው (2022) የዓለም ሻምፒዮና የ50 ኪሎ ሜትር የወንዶችና የሴቶች፣ የ35 ኪሎ ሜትር ዕርምጃ ተካቷል።

 


ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ

የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ብሔራዊ ቡድን በመጀመርያው ሻምፒዮና 10 አትሌቶች በአምስት የውድድር ዓይነቶች ተሳትፏል። ኢትዮጵያ በወዳጆ ቡልቲ፣ ሥዩም ንጋቱ፣ መሐመድ ከድር፣ በቀለ ደበሌ፣ ግርማ ብርሃኑ፣ እሼቱ ቱራ፣ ግርማ ወልደሃና፣ ከበደ ባልቻና ደረጀ ነዲ ነበር የተወከለችው። አትሌቶቹ በ3000 ሜትር መሰናከል፣ 5000 ሜትር፣ 10 ሺሕ ሜትር፣ ማራቶንና 20 ኪሎ ሜትር የዕርምጃ ውድድሮች ተሳትፈዋል። ከእነዚህ አትሌቶች መካከል ከበደ ባልቻ በወንዶች ማራቶን ለኢትዮጵያ የመጀመርያውን የብር ሜዳልያ አስገኝቷል፡፡

በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ 15ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኢትዮጵያ የዓለም ሻምፒዮና ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በ18ቱም ሻምፒዮናዎች መካፈል ችላለች። እ.ኤ.አ. በ1993 በስቱትጋርት በተደረገው ውድድር ኃይሌ ገብረ ሥላሴ በ10 ሺሕና በ5 ሺሕ ሜትር ወርቅና ብር አግኝቷል፡፡

የኢትዮጵያ ስኬታማ ውጤት

እ.ኤ.አ. በ2009 በጀርመን በርሊን በተከናወነው የዓለም ሻምፒዮና በተለያዩ ርቀቶች የሚሳተፉ 38 አትሌቶችን ይዛ ቀርባለች። ቡድኑ በመካከለኛ ርቀት ጭምር የሚሳተፉ አትሌቶችን ያቀፈ ነበር። በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በተለያዩ ርቀቶች የሚወዳደሩ ተጨማሪ አትሌቶች ይዛ እንድትገባ የተፈቀደላት ሲሆን፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽንም በእነዚህ ውድድሮች ተጠባባቂ አትሌቶችን መርጦ ይዞ ቀርቦ ነበር።

በሻምፒዮናው በወንዶች 5000 ሜትርና 10 ሺሕ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ ሁለት ወርቅ በማምጣት አዲስ ታሪክ ያጻፈበት ክስተት ነበር። ቀነኒሳ በ10 ሺሕ ሜትር 26:46.31 በማጠናቀቅ የቦታውን ክብረ ወሰን ጭምር ማሻሻል ችሏል። በ1500 ሜትር ወንዶች ደረሰ መኮንን የብር ሜዳልያን ሲያሳካ፣ ፀጋዬ ከበደ በማራቶን ሁለተኛውን የብር ሜዳልያ ያስገኝ አትሌት ሆኗል።

በሴቶች መሠረት ደፋር በ5000 ሜትር የነሐስ ሜዳልያ፣ መሰለች መልካሙ በ10 ሺሕ ሜትር ብር፣ ውዴ አያሌው ነሐስ፣ እንዲሁም አሠለፈች መርጋ በማራቶን የነሐስ ሜዳልያ አስገኝተዋል። በዚህም መሠረት ኢትዮጵያ በአጠቃላይ ስምንት ሜዳልያ በመሰብሰብ ከዓለም ስድስተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቅ የቻለችበት ሻምፒዮና ነበር።

ከሁለት ዓመት በኋላ በ2011 በደቡብ ኮሪያ ዴጉ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተካፈለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን 34 አትሌቶችን ይዞ መሳተፍ ችሎ ነበር። ሆኖም በ10 ሺሕ ሜትር ወንዶች በኢብራሂም ጄላን ወርቅ ሲገኝ፣ ደጀን ገብረ መስቀል በ5000 ሜትር፣ ኢማና መርጋ 10 ሺሕ፣ ፈይሳ ሌሊሳ በማራቶን እንዲሁም በ5000 ሜትር ሴቶች በመሠረት ደፋር አራት የነሐስ ሜዳልያ በአጠቃላይ አምስት ሜዳልያዎች ማጠናቀቅ ትችሏል። ይህም ውጤት ኢትዮጵያ በበርሊን ዓለም ሻምፒዮን ከነበረው ውጤት ዝቅተኛው ነበር።

በ2013 በሩሲያ በተሰናዳው የሞስኮ የዓለም ሻምፒዮን ኢትዮጵያ የተሻለ ውጤት ያመጣችበት ነበር። በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በመሠረት ደፋር በ5000 ሜትር ወርቅ፣ በጥሩነሽ ዲባባ 10 ሺሕ ሜትር ወርቅ፣ እንዲሁም በ800 ወንዶች በመሐመድ አማን ወርቅ ማምጣት ተችሎ ነበር። በተለይ ባልተለመደ መልኩ በ800 ሜትር ርቀት በመሐመድ ወርቅ መምጣቱ ሻምፒዮናው ለኢትዮጵያውያን ልዩ አድርጎታል። በሌሎች ርቀቶች ሦስት የብርና ሦስት የነሐስ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ከዓለም ስድስተኛ ደረጃን በመያዝ ማጠናቀቅ ትችሏል።

ሌላው ኢትዮጵያ የደመቀችበት የ2015 ዓለም ሻምፒዮና ይጠቀሳል። የአትሌቲክስ ቡድኑ በሻምፒዮናዎች በረዥም ርቀቶች ብቻ ውጤት ከማምጣት በዘለለ፣ በመካከለኛ ርቀትም የተሻለ ውጤት ማምጣት የቻለበት አጋጣሚም እየተፈጠረ የሄደበት ሁኔታ ነበር። በዚህም መሠረት በቤጂንግ ዓለም ሻምፒዮን ገንዘቤ ዲባባ በ1500 ሜትር ወርቅ ማምጣት ችላ ነበር። ይህም ኢትዮጵያ በመካከለኛ ርቀት በዓለም ሻምፒዮና ተስፋ የሰነቀችበት ነበር።

ኢትዮጵያ በቤጂንጉ የዓለም ሻምፒዮን አልማዝ አያና በ5000 ሜትር ወርቅ፣ ማሬ ዲባባ በማራቶን ወርቅ ሲያሳኩ፣ በሦስት የብርና በሁለት የነሐስ ሜዳልያዎችን  በመሰብሰብ ከዓለም አምስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች።

በ2017 የለንደን ዓለም ሻምፒዮን ሁለት ወርቅና ሦስት የብር ሜዳልያ፣ በ2019 በኳታር ሁለት ወርቅ፣ አምስት ብርና አንድ የነሐስ ሜዳልያ ማምጣት ተችሏል። በኳታር ዓለም ሻምፒዮን ለሜቻ ግርማ በ3000 መሰናክል የብር ሜዳልያ ማሳካት፣ ሌላው ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ተስፋ የተሰነቀበት ድል ያደርገዋል።

ዓለም በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት ዝግ ሆና መቆየቷን ተከትሎ በተለይ አትሌቶች አስቸጋሪ ጊዜ ያሳለፉበት ወቅት ነበር። ይህም ለሁለት ዓመታት ማንኛውም ውድድሮች ሳይከናወኑ መቆየታቸው ይታወሳል። በአንፃሩ ወረርሽኙ አገግሞ የ2022 የኦሪገን ዓለም ሻምፒዮን ለአትሌቶች ተስፋ ያጫረ ሆነ። በልምምድ የዛለው የአብዛኛው አትሌት ጉልበት መፈተሻ መድረክ አገኘ።

የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድንም ስኬታማውን የዓለም ሻምፒዮን ያስባለውን ውጤት አስመዘገበ። ኢትዮጵያ 21 ወንድና 19 ሴት አትሌቶችን በተለያዩ ርቀቶች ማሳተፍ ቻለች። ይህም ቁጥር ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና ካሳተፈቻቸው አትሌቶች ቁጥር ላቅ ያለ ነበር። የቁጥር መጨመር ምክንያትም በየሻምፒዮናው የሚመዘገቡ ውጤቶች አማካይነት ነው። በኦሪገን ዓለም ሻምፒዮን በማራቶን በሁለቱም ፆታ (በታምራት ቶላና ጎተይቶም ገብረ ሥላሴ)  እንዲሁም በ10 ሺሕ ሜትር ሴት ለተሰንበት ግደይና በ5000 ሜትር ሴቶች ጉዳፍ ፀጋይ አራት ወርቅ ማሳካት ተችሏል።

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በማራቶን በሁለቱም ፆታ የቦታውን ክብረ ወሰን ማሻሻል የቻሉበት ሲሆን፣ በ10 ሺሕ ሜትር ለተሰንበት የዓመቱን ምርጥ ሰዓት ማስመዝገብ መቻላቸው ልዩ ያደርገዋል። ኢትዮጵያ በኦሪገኑ ዓለም ሻምፒዮን ከአራቱ ወርቅ በተጨማሪ አራት የብር፣ ሁለት የነሐስ ሜዳልያ በድምሩ 10 ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቅ የቻለችበት ስኬታማው የዓለም ሻምፒዮን ያደርገዋል።

በተለይ ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመት በዘለቀው የሰሜኑ ጦርነት ውስጥ ሆና የተመዘገበ ውጤት መሆኑ የተለየ ቦታ እንዲሰጠው አስችሎታል።

ከኦሊምፒክ ጨዋታና ከእግር ኳሱ የዓለም ዋንጭ ቀጥሎ፣ ምርጡ ውድድር እንደሆነ የሚገለጽለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን፣ ዘንድሮ በቡዳፔስት ። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን ዓምና በአራት ወርቅ የተመለሰው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድኑ ዘንድሮስ ምን ሊያሳካ ይችላል? የሚለው በአብዛኛው ዘንድ በጉጉት የሚጠበቅ ጉዳይ ነው።

https://www.proworksmedia.com/121159/ ዳዊት ቶሎሳ


Wednesday, August 23, 2023

‹‹የሩጫዎች ሙሽሪት›› አትሌት መሰለች መልካሙ ኃይለእየሱስ

 

Written by  ግሩም ሠይፉ(አዲስ አድማስ)

ሰሞኑን ለየት ያለ መልዕክት ደረሰኝ፡፡ በፅሁፍ የተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ ወይንም በመግለጫ ላይ እንድገኝ የሚጋብዝ ጥሪ አልነበረም፡፡ የሙያ ባልደረባዬ በመጀመርያ መልዕክቱን ያደረሰኝ በስልክ ነው፡፡ አትሌት መሰለች መልካሙ ሰርግ ጠርታሃለች በማለት ጥሪው እንዳስደሰተኝ በመግለፅ እዚያው እንገናኝ ብለን ተለያየን፡፡
አዎ የሠርግ ካርዱ ደርሶኛል፡፡ 

“ይድረስ ለወዳጃችን ይላል… እንደምን ሰንብተዋል፡፡ እኛም ባለንበት በእግዚአብሄር ቸርነት በጣም ደህና ነን፡፡ ይኸው እንደ ወግ ልማዳችን ልጃችን አትሌት መሰለች መልካሙ እና አቶ አብርሃም በቀለ የፍቅር አጋር ሊሆኑ ተጫጭተዋል፡፡ እኛም ይሁን ብለን የሰርጉን ቀን ቆርጠናል፡፡…. ሚያዚያ 7 በምናደርገው የእራት ግብዣ ላይ ብቅ ብለው ያዘጋጀነውን ድግስ አብረን ተቋድሰን እንመርቃቸው፡፡ ወዲያውም ስንጫወት እናመሻለን፡፡ ታዲያ እንዳይቀሩ የቀሩ እንደሆነ ግን ማርያምን እንቀየምዎታለን……
አክባሪዎ ወይዘሮ የአለምወርቅ አዘነ
እና አቶ ይታያል መልካሙ
 


በዚህ አጋጣሚ አትሌት መሰለች መልካሙንና ቤተሰቧን በጣም አመሰግናለሁ፡፡ በስፖርት ጋዜጠኝነት እኔም የናንተ ቤተሰብ አክባሪ ነኝ፡፡ በዚህ የስፖርት አድማስ አምድ የታሪክ ማስተወሻ ላይ ስለ አትሌት መሰለች መልካሙ የሩጫ ዘመን ለመፃፍ አጋጣሚውን ስፈልግ ነበር፡፡ በነገው እለት ከአቶ አብርሃም በቀለ ጋር በሠርግ መሞሸሯን ምክንያት በማድረግ የሩጫ ገድሏ እንዲህ አቅርቤላችኋለሁ፡፡

 ሙሉ ስሟ መሰለች መልካሙ ኃይለእየሱስ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ 360 ኪሎሜትሮች ርቃ በምትገኘው ደብረማርቆስ ተወልዳለች። በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ታሪክ ከ18 ዓመታት በላይ በመስራት ከፍተኛ እውቅና እና ክብር አግኝታለች፡፡ ምንም እንኳን የሩጫ ዘመኗን በአገር አቋራጭ ውድድር ብትጀምርም በትራክ ላይ በ5ሺ ሜትር እና 10ሺ ሜትር ውድድሮች ላይ በመሮጥም ከ8 የውድድር ዘመናት በላይ ልምድ አላት፡፡ በቤት ውስጥ አትሌቲክስ፤ በጎዳና ላይ ሩጫ፤ በተራራ ላይ ሩጫዎች በግማሽ ማራቶንና ማራቶኖችም ተወዳዳሪ በመሆን ተሳክቶላታል፡፡
ከ10 ዓመት በፊት በአዲስ አበባ ስታድዬም በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ከታዩ አስደናቂ ውድድሮች የማይረሳው የሴቶች አምስት ሺ ሜትር ውድድር ነበር። በ5ሺ ሜትር የምንግዜም ምርጥ ሯጭ የሆነችውን መሰረት ደፋር በማሸነፍ የአፍሪካ ሻምፒዮን ሆና የወርቅ ሜዳልያውን አትሌት መሰለች ስትጎናፀፍ ሙሉ ስታድዬም ቆሞ ነበር ያጨበጨበላት። በሴቶች 10ሺ ሜትር ደግሞ በ2009 እኤአ ላይ  ያስመዘገበችው 29:53.80 የሆነ ጊዜ ከቻይናዋ የዓለም ሪከርድ ባለቤት ዋንግ ዡንክስያ ቀጥሎ ለ7 ተከታታይ የውድድር ዘመናት በ2ኛ ደረጃ ለመቀመጥ የበቃ የምንግዜም ፈጣን ሰዓት ነበር፡፡ በሪዮ ኦሎምፒክ ይህን ደረጃዋን በኦሎምፒክ ሻምፒዮናዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት አልማዝ አያና 29:53.80 በሆነ ጊዜ የተረከበችውና የኢትዮጰያ ሪከርድ ሆኖ የሚገኝ ነው፡፡ በሴቶች የ10ሺ ሜትር ሩጫ ታሪክ ከ30 ደቂቃ በታች ከገቡ 10 አትሌቶች አንዷ ስትሆን ይህን የሰዓት ገደብ ካስመዘገቡ አምስት የኢትዮጵያ ሴት ሯጮችም አንዷ ናት፡፡ 

ሩጫን ከ18 ዓመታት በፊት የጀመረችው የአባቷን ተቃውሞ በመቋቋም ሲሆን በደብረማርቆስ ከሚገኙ ወጣቶች ጋር ልምምድ በመስራት ነበር፡፡ በደብረማርቆስ ከተማ በተካሄዱ የተለያዩ ውድድሮች በተለይ በአገር አቋራጭ ሩጫዎች ስኬታማ ከሆነች በኋላ ክልሏን በመወከል በኢትዮጵያ የአገር አቋራጭ ሻምፒዮና የምትሳተፍበት እድል ተፈጠረላት፡፡ በወጣቶች ውድድር ጃንሜዳ ላይ ተሳትፎ አድርጋ በ11ኛ ደረጃ ነበር የጨረሰችው፡፡ ከዚህ ውድድር በኋላ ክልሏን በመወከል በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለመሳተፍ በቃች በትራክ የ1500 ሜትር ውድድር ተሳታፎ በመሆን ባሳየችው ልዩ ብቃት በመብራት ሃይል የአትሌቲክስ ክለብ የምትቀጠርበት አጋጣሚ ተፈጠረ፡፡ በዚህ መሰረት ከምትኖርበት የደብረማርቆስ ከተማ የ10ኛ ክፍል ትምህርቷን በማቋረጥ ወደ አዲስ አበባ መጥታ በመብራት ኃይል ክለብ አትሌትነት ሙሉ ለሙሉ ወደሩጫ ስፖርት ገብታለች፡፡ አባቷም ሩጫን ሙያዋ አድርጋ እንደምትዘልቅ በመረዳታቸው ድጋፋቸውን በዚህ ወቅት መስጠት ጀምረዋል፡፡ በማንኛውም ውድድር ለሁሉም ተፎካካሪ ግምት ሰጥታ ለማሸነፍ እንድትወዳደር ነበር የአባቷ ምክር፡፡  በመጀመርያው ዓመት በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ በሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የመካተት ህልም የነበራት ቢሆንም አልተሳካላትም፡፡ ከ2003 እኤአ ጀምሮ ወደ ዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ በወጣቶች ደረጃ መሳተፍ ጀምራለች የመጀመርያ ውድድሯ የነበረው በሉዛን የተደረገው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሲሆን፤ ጥሩነሽ ዲባባ ባሸነፈችበት የወጣቶችውድድር 4ኛ ደረጃ አግኝታ ነበር፡፡ ከዚያም በ2004 እኤአ ላይ በኢትዮጵያ የአገር አቋራጭ ሻምፒዮና በወጣቶችውድድር አሸንፋ በአዋቂዎች የ4ኪሜትር ውድድር ደግሞ 4ኛ ደረጃ በማስመዝገብ ለዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመመረጥ እድሏን አሰፋች፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ መጥቃ የወጣችበት የውድድር ዘመን በ2004 እኤአ ሲሆን በወጣቶች ምድብ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናንና የዓለም ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮናን ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች በድርብ ድል የተቀዳጀችበት ነበር፡፡ በቀጣዩ የውድድር ዘመን በዋናው የአዋቂ ሴቶች አጭር ርቀት 4 ኪሎሜትር ውድድር አራተኛ እንዲሁም በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ደግሞ በ5ሺ ሜትር 4ኛ ደረጃ ነበራት፡፡ይህ ልምዷን በማጠናከር በ2004 እና በ2005 እኤአ የውድድር ዘመናት በአገር አቋራጭ ውድድሮች ብቻ ሳይሆን፤ በትራክ እና የጎዳና ላይ ሩጫዎች ከ1500 ሜትር እስከ 10 ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ከ16 በላይ ውድድሮች አድርጋለች፡፡
ከወጣቶች ምድብ ወደ አዋቂ ደረጃ ከተሸጋገረች በኋላ ከፍተኛ የሜዳልያ ውጤት ለማስመዝገብ የበቃችው በ2006 እኤአ ላይ ነው፡፡ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በአጭር ርቀት 4 ኪሜትር እና በረጅም ርቀት 8 ኪሜትር ውድድሮች ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች እና በቡድን ደግሞ ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችን በመውሰድ ነበር። ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በግሬት አየርላንድ ራን የ10 ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ላይ በስፍራው ሪከርድ 31:41  በማሸነፍ ተሳክቶላታል፡፡
ከጎዳና ላይ ሩጫው በኋላ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ በመመለስ በ2007 እኤአ ላይ በድጋሚ የነሐስ ሜዳልያ ከመውሰዷም በላይ በቡድን ተጨማሪ የወርቅ ሜዳልያ አስገኝታለች፡፡ በተመሳሳይ የውድድር ዘመን ላይ ደግሞ ወደ ትራክ በመግባት በመላው አፍሪካ ጨዋታዎች ላይ አትሌት መሰረት ደፋርን ተከትላ በመግባት በ5ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ አግኝታለች። በዚያው የውድድር ዘመን ማብቂያ ላይ  በ5ሺ ሜትር በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ 6ኛ ደረጃ ነበራት፡፡
በ2007 እኤአ ላይ በአንድ የውድድር ዘመን ከጎዳና ላይ ሩጫ ተነስታ በአገር አቋራጭ ከዚያም በትራክ በመወዳደር የተለየ አቅም ነበር ያሳየችው፡፡ በ2008 እኤአ ደግሞ በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ3ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ አገኘች። የወርቅ ሜዳልያው የአትሌት መሰረት ደፋር ነበር፡፡ በዚያው የውድድር ዘመን ከፍተኛ ልምድ ባካበተችበት የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በዘጠነኛ ደረጃ ብትጨርስም ይህን የሚያካክስ ውጤት ደግሞ አሳክታለች፡፡ በ2008 እኤአ በአዲስ አበባ ስታድዬም በተስተናገደው 16ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ አትሌት መሰረት ደፋርን ቀድማ በመግባት የወርቅ ሜዳልያ በ5ሺ ሜትር የተጎናፀፈችበት ነበር፡፡ ይህ ውጤቷም በቻይናዋ ቤጂንግ ከተማ ለተካሄደው 29ኛው ኦሎምፒያድ ተሳትፎ አብቅቷታል፡፡ በ5ሺ ሜትር በሆነ ጊዜ በስምንተኛ ደረጃ ነበር የጨረሰችው፡፡ ከዓመታት በኋላ በዚሁ ኦሎምፒክ በ5ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ የወሰደችው የቱርኳ ኤልቫን አብይ ለገሰ በዶፒንግ ውጤቷ በመሻሩ፤ አትሌት መሰለች መልካሙ በተሳተፈችበት የመጀመርያ ኦሎምፒኳ በ5ሺ ሜትር የ7ኛ ደረጃ እንዲመዘገብላት ሆኗል፡፡


በ2009 እኤአ ላይ ወደ የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ስትመለስ የሜዳልያ ውጤት ነበራት፡፡ በረጅም ርቀት የ8 ኪሎሜትር ውድድር የነሐስ ሜዳልያ ወሰደች፡፡  በጥቂት ወራት ውስጥ ደግሞ በሆላንዷ ኡትርቼት በተካሄደ የ10ሺ ሜትር ሩጫ አዲስ የአፍሪካና የኢትዮጵያ ሪከርድ 29:53.80 በሆነ ጊዜ አስመዘገበች፡፡ አስቀድሞ በጥሩነሽ ዲባባ የተያዘውን የአፍሪካና የኢትዮጵያ ሪከርድ 29:54.66 የሆነ ጊዜ በማሻሻል ነበር፡፡ ያን የውድድር ዘመን የመጀመርያውን የዓለም ሻምፒዮና ከፍተኛ ውጤት በ10ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ በመጎናፀፍ አጠናቀቀች፡፡
በ2010 እኤአ ላይ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በመሳተፍ  የለመደችውን የነሓስ ሜዳልያ በረጅም ርቀት ለመውሰድ የበቃች ሲሆን፡፡ በዚያው የውድድር ዘመን በኬንያ ናይሮቢ በተካሄደ የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ደግሞ በ10ሺ ሜትር አትሌት ጥሩነሽ ዲባባን ተከትላ በመግባት የብር ሜዳልያ ተጎናፅፋለች፡፡ የውድድር ዘመኑን ያገባደደችው በናይጄርያ ኦቡዱ ግዛት በተካሄደ የአፍሪካ ረየተራራ ላይ ሩጫ ጫምፒዮንሺፕ Obudu Ranch International Mountain Race አስደናቂ ድል በማስመዝገብ ነበር፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ትልቁ ውጤታ በጃንሜዳ አገር አቋራጭ ለ4ኛ ጊዜ ማሸነፏ ነበር፡፡
ከ2012 እኤአ ወዲህ ያለፉትን አምስት የውድድር ዘመናት ደግሞ ዋና ትኩረቷ የጎዳና ላይ ሩጫዎች ግማሽ ማራቶንና ማራቶኖች ሆነዋል፡፡ በ2012 እኤአ በጀርመን ፍራንክፈርት ማራቶኑን ስታሸንፍ 2:21:01 በሆነ ጊዜ የግሏን ፈጣን ሰዓት እና የስፍራውን ሪከርድ አስመዝግባለች፡፡ ይህ የመሰለች መልካሙ የማራቶን ሰዓት ከኢትዮጵያ ሴት ማራቶኒስቶች ፈጣን ሰዓቶች አንዱ ነው፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ የራስ አልካሂማህ ግማሽ ማራቶን ስትወዳደር በ7ኛ ደረጃ ብትጨርስም በርቀቱ የግሏን ፈጣን ሰዓት 1:08:05  አስመዝግባለች፡፡
ባለፉት 4 የውድድር ዘመናት  በተሳተፈችባቸው የማራቶን ውድድሮች የተሳካላት ናት፡፡ በ2013 እ.ኤ.አ ላይ ሞስኮ ባስተናገደችው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በማራቶን ብትሳተፍም ውድድሩን ለመጨረስ አልቻለችም፡፡ የመጀመሪያ ማራቶን የሮጠችው በ2012 እኤአ በፍራንክፈርት ማራቶን ሲሆን፣ ውድድሩን ስታሸንፍ 2:21:01 በሆነ ጊዜ ሲሆን  ብርቀቱ የተመዘገበላት ምርጥ ሰዓቷ ነው፡፡ በዱባይ ማራቶን  ሁለት ጊዜ ስትሳተፍ በ2016 እኤአ ላይ በ2፡22፡29 በሆነ ጊዜ ሦስተኛ ደረጃ ማግኘቷ ይታወሳል፡፡  በ2017 እኤአ ደግሞ አልተሳካለትም ከዱባይ ማራቶን ባሻገር በጀርመንና በሆላንድ ከተሞች ሁለት ትልልቅ ማራቶኖችን አሸንፋለች፡፡ በተለይ  በጀርመን ሀምቡርግ ካስመዘገበችው ድል ቀጥሎ ሁለተኛውን የትልቅ ከተማ ማራቶን አሸናፊነት ክብር በአምስተርዳም ለመቀዳጀት መብቃቷ ይጠቀሳል፡፡
በኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ማህበረሰብ፤ በዓመለሸጋነቷ፤ በልምምድ ትጋቷ እና በውድድር ላይ ለቡድን ውጤት በምታበረክተው አስተዋፅኦ የምትከበረው አትሌት መሰለች መልካሙ በአገር አቀፍ እንቅስቃሴዎችም ንቁ ተሳታፊ ናት፡፡ ከ4 ዓመታት በፊት ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ገቢ ማሰባሰቢያ የሚውል 20 ኤል.ሲ.ዲ ቴሌቪዥን በስጦታ ያበረከተች ሲሆን ባለ 32 ኢንች ኤል.ሲ.ዲ ሳምሰንግ ቴሌቪዥኖች  ከ153 ሺህ ብር በላይ ወጪ ተደርጎባቸዋል፡፡ በ2017 ላይ ግን አንድ አሳዛኝ ገጠመኝ ነበር፡፡ አትሌት መሰለች መልካሙን ጨምሮ አምስት አትሌቶች ከ3 ሚሊየን ብር በላይ ደረቅ ቼክ በመጻፍ ማናጀር አታሏቸው መነጋገርያ ሆነው ነበር፡፡ በማታለል ወንጀል የተከሰሰው የአትሌቶች ማናጀር ወላይ አማረ የሚባል ሲሆን በወቅቱ የጠቅላይ አቃቤ ህግ ክስ እንዳመለከተው ተከሳሽ ወንጀሉን በአትሌቶቹ ላይ የፈፀመው ከ2008 እስከ 2009 ዓ.ም ባለው ጊዜ ነው።
ማናጀሩ  ከአምስቱ አትሌቶች በተለያዩ ጊዜና ሀገራት ባደረጉት ውድድር የተሳትፎ የኮንትራት ውል ክፍያን ገንዘብ ሳይኖረው በአዋሽና በሌሎች ባንኮች ሂሳቡ ውስጥ ገንዘብ እንደሌለው እያወቀ ደረቅ ቼክ በመጻፍ ማታለሉ በክሱ ተጠቅሷል። በዚህም መልኩ ለአትሌት አፀደ ፀጋዬ ከ1 ሚሊየን 15 ሸህ ብር በላይ፣ ለአትሌት መሰለች መልካሙ ከ2 ሚሊየን 368 ሺህ ብር በላይ እንዲሁም ለአትሌት በላቸው አለማየሁ 230 ሺህ ብር እና ለሌሎችም አትሌቶች ተመሳሳይ የገንዘብ መጠን ደረቅ ቼክ በመጻፍ የማታለል ተግባር መፈጸሙ በክሱ ተዘርዝሯል፡፡
 የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ አንደኛ ወንጀል ችሎት ተከሳሽ ወላይ አማረ በ10 ዓመት ከ11 ወራት ፅኑ እስራትና በ2 ሺህ 500 ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ ወስኗል።
በአሁኑ ወቅት አትሌት መሰለች መልካሙ ለኢትዮጵያ አትሌቶች ዋና ተምሳሌት ሆና የምትጠቀስ ናት፡፡  የሩጫ መደቦቿ 1500ሜ፤ 3000ሜ፤ 5000ሜ ፤ 10,000ሜ፤ የቤት ውስጥ አትሌቲክስ፤ አገር አቋራጭ፤ የጎዳና ላይ ሩጫዎች፤ ግማሽ ማራቶንና ማራቶን ናቸው፡፡


በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ለረጅም ጊዜ ያገለገለችበት ክለብ  መብራት ኃይል ሲሆን በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ከአሰልጣኝ ዶክተር መስቀል ኮስትሬ እንዲሁም ከዶክተር ይልማ በርታ ጋ ሰርታለች። ለረጅም ጊዜ ማናጀሯ ሆነው ያገለገሏት የግሎባል አትሌቲክስ ኮሚኒኬሽኑ ሆላንዳዊው  ጆስ ሄርማንስ ናቸው፡፡
በዓለም የጎዳና ላይ ሩጫዎች የስታስቲክስ ድረገፅ ኤአርአርኤስ (Arrs) የመረጃ መዝገብ መሰረት አትሌት መሰለች መልካሙ በሩጫ ዘመኗ 41 ውድድሮችን ያሸነፈች ሲሆን በይፋ የሚታወቅ የገንዘብ ሽልማቷ ከ701ሺ 150 ዶላር በላይ ነው፡፡
ፈጣን ሰዓቶቿ
- በ1500 ሜትር – 4:07.52 (2007)
- በማይል ሩጫ– 4:33.94 (2003)
- 2000 ሜትር ቤት ውስጥ - 5:39.2 (2007) 12ኛው የምንግዜም ፈጣን ሰዓት
• በ3000 ሜትር ትራክ- 8:34.73 (2005)
• 3000 ሜትር ቤት ውስጥ - 8:23.74 (2007) 4ኛው የምንግዜም ፈጣን ሰዓት
• 5000 ሜትር ትራክ– 14:31.91 (2010)
• 10,000 ሜትር ትራክ – 29:53.80 (2009) 6ኛው የምንግዜም ፈጣን ሰዓት
• 10 ኪ ሜትር ጎዳና – 31:17 (2013)
• 15 ኪ ሜትር ጎዳና  - 47:54 (2013)
• 20 ኪ ሜትር ጎዳና  - 1:04:32 (2013)
• ግማሽ ማራቶን - 1:08:05 (2013)
• 30 ኪ ሜትር ጎዳና - 1:39.21 (2014)
• ማራቶን – 2:21:01 (2012)
ዋና ዋና ውጤቶቿ
በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና፤ በወጣቶች, በ2003 4ኛ እንዲሁም በ2004 1ኛ፤
በ2004   በዓለም ወጣቶች ሻምፒዮና, 5000ሜ የወርቅ ሜዳልያ
ከ2005 እኤአ ጀምሮ  በ6 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች በመሳተፍ፤  በአጭር 4ኪ.ሜ 6ኛ እንዲሁም በረጅም ርቀት 3 የነሃስ ሜዳልያዎች፤ ሁለት 4ኛ ደረጃዎች እና 9ኛ ደረጃ አስመዝግባለች፡፡
ከ2006 እስከ 2010 እኤአ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5000ሜ 1 የወርቅ ሜዳልያ እና 6ኛ ደረጃ እንዲሁም በ10ሺ 1 የብርና 1 የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝታለች፡፡
በ2007 መላው አፍሪካ ጨዋታዎች በ5000m የብር ሜዳልያ እንዲሁም በ2008 በዓለም አትሌቲክስ ፍፃሜ 5000m የነሐስ እና በየዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና 3000ሜ የብር ሜዳልያ
ከ2005  ጀምሮ እስከ 2011   በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና 5000ሜ 4ኛ፤6ኛ እና 5ኛ ደረጃ በ10ሺ ሜትር ደግሞ የብር ሜዳልያ እና 5ኛ ደረጃ



https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=21677:%E2%80%B9%E2%80%B9%E1%8B%A8%E1%88%A9%E1%8C%AB%E1%8B%8E%E1%89%BD-%E1%88%99%E1%88%BD%E1%88%AA%E1%89%B5%E2%80%BA%E2%80%BA-%E1%8A%A0%E1%89%B5%E1%88%8C%E1%89%B5-%E1%88%98%E1%88%B0%E1%88%88%E1%89%BD-%E1%88%98%E1%88%8D%E1%8A%AB%E1%88%99&Itemid=276

የአትሌት መሰለች መልካሙ የሰርግ ቪዲዮ

https://www.youtube.com/watch?app=desktop&v=A9dkNo-Zzww

 

 

Tuesday, August 8, 2023

የኢትዮጵያና የሩሲያ ወዳጅነት


የኢትዮጵያና የሩሲያ ወዳጅነት 

ከአፄ ምንሊክ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ

በተረፈ ወርቁ (ዲ/ን)


ንደ መንደርደሪያ

የሩሲያንና የኢትዮጵያ ወዳጅነትና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ታሪካዊ ጅማሬው ምን ይመስል ነበር የሚለውን ከታሪክ መዛግብት በጥቂቱ ለመፈተሽ ልሞክር እስቲ፡፡ 

ሩሲያ ከኢትዮጵያ ጋር የጋራ ግንኙነት ለመመሥረት ፍላጎት ማሳየት የጀመረችው በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መባቻ አካባቢ ነው፡፡ የታሪክ መዛግብትና ሰነዶች እንደሚያሳዩት ከዚያ ቀደም ብሎ የሁለቱ አገሮች (የኢትዮጵያና የሩሲያ) ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ምዕመናን ኢየሩሳሌም ለመንፈሳዊ ጉዞ በሚሄዱበት ጊዜ ይገናኙ ስለነበር፣ አንዳቸው ስለአንዳቸው መረጃውና ዕውቀቱ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ነበራቸው፡፡

የታሪክ መዛግብት እንደሚጠቁሙት እ... 1673 ሎሬንቲየስ ሪንሁበር (Laurentius Rinhuber) የተባለ የዛር አሌክሲ አገልጋይ፣ ሩሲያ የኦቶማን ቱርክ ኃይልን ለመቋቋም ከኢትዮጵያ ጋር ትብብር እንደትፈጽምና የሩሲያ ልዑክ ወደ ኢትዮጵያ እንዲላክ ሐሳብ አቅርቦ ነበር፡፡ በወቅቱ ይህ ሐሳብ በሩሲያ መንግሥት ዘንድ ተቀባይነት አግኝቶ የነበረ ቢሆንም፣ በተለያዩ ምክንያቶች ሐሳቡን ዕውን ለማድረግ ሳይቻል ቀርቷል፡፡

ይሁን እንጂ ሩሲያውያን ስለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን በይበልጥ ለማወቅ አልቦዘኑም ነበር፡፡ ሩሲያውያን በወቅቱ ስለኢትዮጵያ ጉዳይ ለማጥናት እንደ መረጃ ይጠቀሙባቸው ከነበሩት ጥንታዊ የታሪክ ሰነዶች መካከልም፣ በጀርመናዊው የቋንቋና የታሪክ ሊቅ በሂዮብ ሉዶልፍ (Hiob Ludolf) የተጻፈውን ‹‹Historia Aethiopica›› የተሰኘው መጽሐፍ ይጠቀሳል፡፡

19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ የኢትዮጵያና የሩሲያ ግንኙነት በዋነኝነት በኢትዮጵያ ቋንቋና ሥነ ጽሑፍ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ የተለያዩ የሩሲያ ሰዎች ከኢትዮጵያ የተለያ የግዕዝ መዛግብትን ይዘው ወደ ሩሲያ ከመሄዳቸውም ባሻገር፣ ሩሲያውያኑ በአገራቸው የግዕዝን ቋንቋ እስከ ማስተማርም ደርሰዋል፡፡ እ... 1829 እስከ 1836 .. በሩሲያ (University of Kharaov) የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት ይሰጥ ነበር፡፡

የአፄ ምንሊክና የሩሲያ ወዳጅነት

1895 .. አፄ ምንሊክ በፊታውራሪ ዳምጠው የተመራውን የመጀመርያውን የዲፕሎማቲክ ልዑክ ወደ ሩሲያ ላኩ፡፡ ይህ ሲሆን ጣሊያን ኢትዮጵያን በሞግዚነት እንደምታስተዳድር የሚገልጸው የውጫሌ ውል በጣሊያን በኩል ይፋ ሆኖ ነበር፡፡ ምንም እንኳን በኢትዮጵያ በኩል የውጫሌ ውል ተቀባይነት እንደሌለው የተገለጸ ቢሆንም፡፡ ቢሆንም ጣሊያን ይህን በኢትዮጵያ በኩል ውድቅ የተደረገውን የውጫሌ ውል በመጥቀስ የኢትዮጵያውያን ልዑካን ኦፊሴላዊ ጉብኝት ላይ ጥያቄ አንስታ ነበር፡፡

ሩሲያ ግን አፄ ምንሊክ የላኩትን የኢትዮጵያ ልዑክ በሉዓላዊ አገር ልዑክነት ዕውቅና በመስጠት በተገቢው ወግና ማዕረግ በክብር ነበር የተቀበለችው፡፡ በውጭ ጉዳይም ሚኒስትሯ በኩልም ኢትዮጵያን እንደ ሉዓላዊ አገር ብቻ እንደምታውቃትና ግንኙነቷም በዚያ መንገድ መሆኑን ጠቅሳ ለጣሊያን ጥያቄ መልስ ሰጥታ ነበር፡፡

የልደታው ደጃዝማች ባልቻ ሆስፒታል - 1968 ዓ.ም

በፊታውራሪ ዳምጠው ከተመራው ልዑክ በኋላ የሩሲያ መንግሥት በጊዜው የጣሊያን ወረራ ሥጋት ለነበረባት ኢትዮጵያ የመሣሪያ ሽያጭ አድርጋ ነበር፡፡ ምንም እንኳን መሣሪያው በታቀደለት ጊዜ ለዓድዋ ጦርነት ባይደርስም፣ ከመሣሪያ ሽያጩ በተጨማሪ የሩሲያውያን የቀይ መስቀል ማኅበር አባላት የጦርነቱን ቁስለኞች ለመርዳት በጦርነቱ ማግሥት በኢትዮጵያ ተገኝተዋል፡፡

ይህ የሩሲያ የሕክምና ቡድን በዓድዋ ጦርነት ከቆሰሉት ወታደሮች በተጨማሪ፣ በጠቅላላው ከ30,000 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች በአዲስ አበባና በሐረር የሕክምና ዕርዳታ ማድረጉን የታሪክ መዛግብት ይጠቁማሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪም ሩሲያውያን ሐኪሞች ታማኝ የአፄ ምንሊክ የግል ሐኪሞች ሆነው እስከ መመረጥም ደርሰው ነበር፡፡     

ከሩሲያ/ከመስኮብ ወደ ኢትዮጵያ ስለመጡት ልዑካንና አፄ ምኒልክ ወደ ሩሲያ የላኩትን መልዕክተኞቻቸው በተመለከተ፣ የዳግማዊ አፄ ምንሊክ ጸሐፊ ትዕዛዝ የነበሩት አለቃ ገብረ ሥላሴ፣ ‹‹ታሪክ ዘዳግማዊ ምንሊክ›› በሚለው መጽሐፋቸው እንዲህ ተርከውታል፡፡

በዚያን ዘመን የመስኮብ መልዕክተኞች መጥተው ከባህር ጠረፍ ደረሱ የሚል ወሬ ተሰማ፡፡ አፄ ምንሊክም ለራስ መኮንን እነዚያን የመስኮብ መልዕክተኞች አክብረህ ተቀብለህ ስደዳቸው ብለው ላኩ፡፡ እነዚያም መልዕክተኞች አዋሽን ተሻግረው ምንጃር በደረሱ ጊዜ በያደሩበት መስተንግዶ እየተሰናዳላቸው፣ በመስተንግዶ ደስ እያላቸው በጉዟቸው የሚቀመጡበት ሁለት  የተሸለሙና ያጌጡ በቅሎዎች ሰደዱላቸው፡፡

መልዕክተኞቹም መጥተው በአዲስ አበባ ከተማዋ አጠገብ በደረሱ ጊዜ የሚቀበላቸው ሰው ታዞ ተሠልፎ ሂዶ በእንቢልታና በመለከት ተቀበሏቸው፡፡ በታላቅ ክብር በተድላና ደስታ ከጃንሆይ ተገናኙ፡፡ የሚያርፉበትን ቤት አምሮ ተዘጋጅቶ ቆይቶ ነበርና ከዚያ ሄደው ገቡ፡፡ ድርጓቸውም ታዞ ሄደላቸው፡፡ ይኼውም ድርጎ እስኪሄዱ ድረስ አልጎደለባቸውም፡፡


በዚህ ጊዜ የኢትዮጵያና የመስኮብ ፍቅር ተጀመረ፡፡ ነገር ግን የአፄ ምንሊክ ደግነት ሁሉን ያሸንፋል፡፡ በፍቅር ከሆነ የማንም አገር ሰው ቢመጣ ማክበር፣ መውደድና መስጠት ነው እንጂ መሰልቸት የለም፡፡

የመስኮብ መልዕክተኞችም የኢትዮጵያ ቆይታቸውን አጠናቀው ወደ አገራቸው የሚሄዱበት ቀን በደረሰ ጊዜ፣ አፄ ምንሊክ ወደ መስኮብ ንጉሠ ነገሥት የሚሄዱ መልዕክተኞችን አዘዙ፡፡ የታዘዙትም ሰዎች ስማቸው ይህ ነው፡፡ ፊታውራሪ ዳምጠው፣ ቀኝ አዝማች ገነሜ፣ መምህር ገብረ እግዚአብሔር ሌሎችም መኳንንት ተጨምረው እንዲሄዱ ተዘጋጁ፡፡

ለመስኮብ ንጉሠ ነገሥት ለኒቆላዎስ ቄሣር በረከት የሚሄድ ዕፁብ ድንቅ የሆነ ዘውድ፣ ማለፊያ የወርቅ መስቀል፣ አራቱ ወንገጌል መጻሕፍት፣ ሌላም የኢትዮጵያ ብዙ ገፀ በረከት ሰደዱ፡፡ በበኩላቸው ንግሥቲቱ እቴጌ ጣይቱም ለመስኮብ ንግሥት ለአሌክሳንድራ በረከት የሚሄድ ዕፁብ ድንቅ የተባለ በወርቅ አጫዋች ያጌጠ የሐር መሶብ፣ የሴት ወ/ሮ መሣሪያ ወርቅ፣ የእግር ክታብ ወርቅ፣ አልቦ ወርቅ፣ ጠልሰም ወርቅ፣ ድሪ ወርቅ፣ ወለባ ይህን ሁሉ አዘጋጅተው ሰደዱ፡፡

እነዚህም የአፄ ምንሊክ መልዕክተኞች ከመስኮብ መንግሥት በደረሱ ጊዜ በታላቅ ክብር ተቀበሏቸው፡፡ ዓይነተኛውን/የመልዕክተኞቹን መሪ ፊታውራሪ ዳምጠውን በወርቅ ባጌጠ ሠረገላ አስቀምጠው ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ቤት ወሰዷቸው፡፡ ከከተማው በገቡ በአምስተኛው ቀን ለንጉሠ ነገሥቱ ኒቆላዎስ ቄሳር፣ ለንግሥቲቱም ለአሌክሳንድራ የያዙትን ስጦታ/በረከት አቀረቡ የሚል ቃል ወደ አፄ ምንሊክ መጣ፡፡

እንደ መውጫና መደምደሚያ

ከሰሞኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (/) የሩሲያ ጉብኝትና ከአገሪቱ ወሳኝ ሰው ከሆኑት ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር ያደረጓቸው ስምምነቶችና ውይይቶች ትልቅ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆነው ቆይተዋል፡፡ ይህም ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ አንድም ሁለቱ አገሮች ረዥም ዘመን ያስቆጠረ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላቸው መሆናቸው ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ አገራችን የሺሕ ዘመናት ታሪክና ሥልጣኔ ባለቤት፣ የአፍሪካና የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ዓርማ የአፍሪካ መዲና የመሆኗ እውነታ በዓለም አቀፍ መድረክ ልዩ ሥፍራ ስለሚያሰጣት ነው፡፡


ከዚህ የታሪክ ሀቅ ጋር በተያያዘም የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (/) የሩሲያ ጉብኝት፣ በፖለቲካውና በዲፕሎማሲው ዓለም ትልቅ አንድምታ እንዲኖረው አድርጓል፡፡

በሌላም በኩል ደግሞ ምዕራባውያንና አሜሪካ፣ በተቃራኒው ደግሞ ሩሲያ በዲፕሎማሲው መስክና በኃይል አሠላላፍ ረገድ አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት የተያያዙትን የገመድ ጉተታ አገሮችን ከጎናቸው ማሳለፍ ዋነኛ ጉዳያቸው በመሆኑ ነው፡፡ በዚህ ረገድም የአፍሪካ መዲና፣ የአፍሪካውያንና የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ዓርማ፣ የዓላማችን ታላላቅ ሃይማኖቶች ቤት፣ በአፍሪካና በአፍሪካ ቀንድ ወሳኝ የሆነ ጂኦ ፖለቲካዊ አቀማመጥን የያዘች እንደ ኢትዮጵያ ያለ አገርን ኃያላኑ አገሮች ከጎናቸው እንድትሆን/እንድትቆም ማድረግ ትልቅ ዲፕሎማሲያዊ ድል ከመሆኑ እውነታ ጋርም የሚያያዝ መሆኑ ነው፡፡

ይህን የኢትዮጵያንና የሩሲያን ታሪካዊ ግንኙነት አጠናክሮ ለማስቀጠል፣ ባለፈው ዓመት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ በአፍሪካ የአፍሪካ ኅብረት መገኛና መዲና በሆነችው በሆነችው አዲስ አበባ ይፋዊ ጉብኝት አድርገው ነበር፡፡ ይህን የላቭሮቭን ጉብኝት ተከትሎ መቀመጫውን በሩሲያ ያደረገው አሜሪካዊ የፖለቲካ ተንታኝ አንድሩ ኮሪብኮ ባወጣው ጽሑፍ፣ ‹‹የሩሲያ-ኢትዮጵያ ወዳጅነት የባለብዙ አቅጣጫ አጋርነት ማሳያ ሞዴል መሆኑንና የላቭሮቭ ጉብኝት ሩሲያ ከመላው የአፍሪካ አገሮች ጋር ያላትን የጋራና ሁለገብ ግንኙነት አጠናክራ ለመቀጠል ያላትን ፍላጎት ያሳየ መሆኑንም፤›› አትቶ ጽፎ ነበር፡፡


አንድሩ፣ ‹‹አዲስ አበባ የአፍሪካ ኅብረት መቀመጫ ብቻ ሳትሆን የመላው አፍሪካውያን የፀረ ቅኝ ግዛት ተጋድሎ ትእምርት/ሲምቦልና የፓን አፍሪካኒዝም ታሪካዊ መገኛ በመሆኗ የአኅጉሩ መንፈሳዊ መዲና ናት፤›› ብለው በርካቶች እንደሚያምኑም በጽሑፉ አውስቷል፡፡

ሩሲያና ኢትዮጵያ ለቀሪው ዓለም በተለይም ለአፍሪካ አገሮች እንዴት ከቅኝ ግዛት ነፃ መውጣት እንደሚቻል በማሳየት ረገድ ግንባር ቀደም ሆነዋልም ነው ያለው የፖለቲካ ተንታኙና ጸሐፊው አንድሪው፡፡ በጽሑፉ ማጠቃለያም፣ ‹‹ላቭሮቭ ወደ አዲስ አበባ ያደረጉት ጉዞ የሩሲያና የኢትዮጵያ መፃዒ ግንኙነት ጠንካራ እንደሚሆን ከወዲሁ የጠቆመ ነው፤›› ሲል ነበር የደመደመው፡፡

ሰላም ለኢትዮጵያ!

 


SOURCE:- https://www.ethiopianreporter.com/121093/

https://www.dw.com/am/%E1%8D%91%E1%89%B2%E1%8A%95%E1%8A%93-%E1%8A%A2%E1%89%B5%E1%8B%AE%E1%8C%B5%E1%8B%AB%E1%8B%89%E1%8B%AB%E1%8A%91-%E1%89%A0%E1%88%A9%E1%88%B5%E1%8B%AB/a-50043226



Monday, November 28, 2022

22ኛው የዓለም ዋንጫ በኳታር_2022

22ኛው የዓለም ዋንጫ ኳታር 


በባህረሰላጤዎች የተከከበች
ኳታር ልዩ መልክዓምድር ያላት አገር ናት።  በምዕራብ እስያ የምትገኝ ሲሆን በሰሜን ምስራቅ የኳታር ባህረሰላጤ፤ በደቡብ በኩል የሳውዲ አረቢያ ባህረሰላጤ፤ የተቀረው ግዛቷ በፋርስና በባህሬን ባህረሰላጤዎች  ተከብቧል። የዓለማችንን ረጅሙን የባህር ጠረፍ  በ534 ኪሜትር አስመዝግባለች፡፡ በ338 ጫማ ከፍታዋ ከዓለማችን ረባዳማ ስፍራዎች በሁለተኛ ደረጃ የምትጠቀስ ሲሆን አንደኛውን ደረጃ በ6 ጫማ ከፍታ የያዘችው ማልድቪስ ናት፡፡  ካ ሆር አልአዳይድ  Khor Al Adaid የተባለው ክልል ባህርና በረሐ ከሚገናኝባቸው የዓለማችን አስደናቂ ስፍራዎች አንዱ ሲሆን በዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ሆኖ እንዲመዘገብ ጥረት እየተደረገ ነው፡፡



የውጭ አገራት ዜጎች የበዙበት
የኳታር አጠቃላይ የህዝብ ብዛት ከ2.6 ሚሊዮን በላይ እንደሆነ የሚገመት ሲሆን የውጭ አገራት ዜጎች አብላጫውን ቁጥር ይይዛሉ። ከህዝቧ 12%  እስከ  315,000 ኳታራዊያን ሲሆኑ 88 በመቶው ከ2.3 ሚሊዮን በላይ ከተለያዩ አገራት የገቡ ስደተኞች ናቸው። በኳታር ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የውጭ ዜጎች ህንዳውያን ሲሆኑ እስከ 700ሺ ይደርሳሉ። 40% ከአረብ፤  36% ከደቡብ ኤስያ፤ 18% ከህንድ፤ 18% ከፓኪስታን፤ 10% ከኢራን እንዲሁም 14% ከተለያዩ የዓለም አገራት የመጡ ዜጎች ይገኙበታል፡፡


የቱሪዝም መስህብነቷ

ኳታር በቱሪዝም መስክ ፈጣን እድገት ካሳዩ አገራት አንዷ ነች። በየዓመቱ ከ2.3 ሚሊዮን በላይ አለም አቀፍ ቱሪስቶች ይጎበኟታል፡፡  በቅርቡ ባደረገችው የቪዛ ማሻሻያ የ88 ሀገራት ዜጎች ከቪዛ ነፃ እንዲገቡ አድርጋለች፡፡ ይህም በመካከለኛው ምስራቅ ካሉ የአረብ አገራት ተወዳጅ የቱሪስት መናሐርያ ያደረጋት ሆኗል። ከዓለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ የእግር ኳስ አፍቃሪዎችና ቱሪስቶች እንደሚጎበኟትም ይጠበቃል፡፡ ከኳታር የቱሪዝም መስህቦች መካከል የአርኪዮሎጂ ስፍራዎች፤ የባህር ዳርቻዎች፤ ወደቦች፤ ሙዚዬሞች፤ ብሄራዊ ፓርኮችና የገበያ ማዕከሎች ይጠቀሳሉ።


የአልታኒ ቤተሰብ

ከ1868 እኤአ ጀምሮ ኳታርን የሚያስተዳድረው መንግስት በአልታኒ ቤተሰብ የሚመራ ነው፡፡ የቤተሰቡ ልዩ አስተዳደር ስልጣን ላይ የወጣው ከኳታር እና ባህሬን ጦርነት በኋላ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የአገሪቱ ኢምር ወይም መሪ ታሚም ቢን ሃማድ አልታኒ የሚባሉ ሲሆኑ ከ203 እኤአ ጀምሮ በስልጣን ላይ ናቸው፡፡ የቤተሰቡ የሃብት መጠን ከ335 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ ይገመታል፡፡ የአልታኒ ቤተሰብ በዓለም በስነጥበብ ስራዎች ላይ ኢንቨስት በማድረግና በመግዛት ግንባር ቀደም ናት፡፡
የዓለም ስነጥበብ ዋና ሰብሳቢ
በኳታር የመንግስት አስተዳደር ላይ የሚገኙት የአልታኒ ቤተሰብ በእስልምናና ዘመናዊ ስነጥበብ ፍቅራቸውና አሰባሳቢነታቸው ይታወቃሉ፡፡ ከ14 ዓመታት በፊት በአረቡ ዓለም ምርጡን የእስልምና ጥበብ ሙዚየም The Museum of Islamic Art  መስርተዋል፡፡  በኳታር ሙዚየሞች ባለስልጣን ስር የሚተዳደሩ ሌሎች በርካታ ሙዚየሞች በዶሃ ከተማ ውስጥ የተገነቡ ሲሆን Arab Museum of Modern Art ይጠቀሳል፡፡ በመላው ዓለም ከ65 በላይ አገራትን የወከሉ ከ300 በላይ አርቲስቶችን የሚያስተናግደው ኳታር ኢንተርናሽናል አርት ፌስቲቫልም QIAF  አገሪቱ ለስነጥበብ የሰጠችውን ትኩረት ያመለክታል፡፡


ሙሉ ከተማ የሆነው ሃማድ

ሃማድ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በ2021 እኤአ ላይ ስካይትራክስ በሰጠው የዓለም አየር ማረፊያዎች አዋርድ ላይ የዓለም ምርጥ ተብሏል። ተመሳሳይ ሽልማትን ለ6 ጊዜያት በመውሰድም ከፍተኛውን ስኬት አስመዝግቧል፡፡ የአየር ማረፊያው የአውሮፕላን መንደርደርያ እስከ 4850 ሜትር ርዝማኔ በማስመዝገብ በምዕራብ ኤስያ ቀዳሚው ሲሆን በዓለም በ6ኛ ደረጃ የሚጠቀስ ነው፡፡ በሰባቱም አህጉራት የበረራ መስመሮችን በመዘርጋትም የሚታወቀው አየር ማረፊያው፤  በዓመት እስከ 50 ሚሊዮን ተጓዦችን ያስተናግዳል፡፡ ተመሳሳይ አቅም ያላቸው የአየር ማረፊያዎች የቶኪዮው ሃኔዳ፤ የሲንጋፑር ቻንጊ፤ ተዱባዩ ዲአየኤ እና የለንደኑ ሂትሮው ናቸው፡፡ የሃማድ ዓለም አቀፍ ማረፊያ 29 ስኩዌር ኪሎሜትር በመሸፈን  በግዝፈቱ ከዓለም በ9ኛ ደረጃ ይቀመጣል፡፡ ቅጥር ጊቢው ከ100 በላይ ህንፃዎች ፤ ከ100 በላይ ሱቆችና ሬስቶራንቶችን ይዟል፡፡


ኳታር ኤር ዌይስ


ኳታር ኤርዌይስ በዓለም ዙርያ ከ45 ሺ በላይ ሰራተኞችን ቀጥሮ የሚያስተዳድር ነው። ከዓለማችን ትልልቅ አየር መንገዶች አንዱ ሲሆን ከዶሃ በመነሳት  ከ150 በላይ ዓለምአቀፍ መዳረሻዎች አሉት፡፡


የአየር ማቀዠቀዣ ያላቸው ስታድዬሞች
22ኛው የዓለም ዋንጫው የሚካሄዱትን 64 ጨዋታዎች የሚያስተናግዱ 8 ስታድዬሞች ልዩ አየር የማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂ  ተገጥሞላቸዋል። በጨዋታ ሜዳ ላይ የሚያስፈለገውን የሙቀት መጠን ለማመጣጠን ተግባራዊ በሆነው ቴክኖሎጂ በየስታድዬሙ ያለውን የሙቀት መጠን  እስከ 26 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ እንዲሆን ማድረግ ተችሏል፡፡ የአየር ማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂው ዘላቂ እና ኃይል ቆጣቢ በሆነ መንገድ ከመስራቱም በላይ በየስታዲየሙ የሚገኘውን ተመልካች በመመርኮዝ የሙቀት መጠኑን መቆጣጠር የሚቻልበት ነው፡፡



የኤሌክትሪክ አውቶብሶች
22ኛው የዓለም ዋንጫ ላይ ተግባራዊ ከሚሆኑ አስደናቂ ቴክኖሎጂች መካከል በኤሌክትሪክ የሚሰሩ አውቶብሶች ይገኙበታል። ደጋፊዎችን ወደ ስታዲየሞችና ወደ የተለያዩ የዶሃ ከተማ ስፍራዎች የሚያመላልሱ ናቸው፡፡  በዓለም ዋንጫ ታሪክ የኤሌክትሪክ አውቶቡሶች ለትራንስፖርት አገልግሎት ሲውሉ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን በከፍተኛ የቴክኖሎጂ የመረጃ መሳሪያዎች የሚታገዙ የትራንስፖርት አገልግሎት ናቸው።


ከጨዋታ ውጭን የምትቆጣጠረው ኳስ
አል ሪሃላ Al Rihla ለ22ኛው የዓለም ዋንጫ በአዲዳስ የተሰራች ኳስ ናት፡፡ የዓለም ዋንጫዋ ኳስ  እውነተኛ መረጃን ለVAR ባለሙያዎች የምታስተላልፍ፤ ፊፋ ለመጀመርያ ጊዜ ተግባራዊ ከሚያደርገውና በከፊል አውቶሜትድ ከሆነ የኦፍሳይድ መቆጣጠርያ ቴክኖሎጂ ጋር በመናበብ የምትሰራም ነች፡፡ በሜዳው ዙርያ የሚገጠሙ  12 ካሜራዎችን ከኳሷ እንቅስቃሴ ጋር በማዋሃድ  የሚሰራ ቴክኖሎጂ ተለጥፎባታል፡፡ከጨዋታ ውጭ የሆኑ ኳሶችን ለመቆጣጠር ፊፋ ተግባራዊ የሚሆነው አዲስ ቴክኖሎጂ ዳኞች ትክክለኛ ውሳኔዎችን እንዲሰጡ ያግዛቸዋል፡፡



ረጅሙ የብስክሌት ጎዳና

ኳታር የዓለማችንን ረጅሙን የብስክሌት ጎዳናም ገንብታለች፡፡ በዶሃ የሚገኘው የኦሎምፒክ ደረጃ ያለው የብስክሌት ጎዳና በ33 ኪሜ ርዝማኔው በጊነስ ሪከርድ ሬከርድ የተመዘገበ ነው፡፡ ከጎዳናው 25.3 ኪሜትር በአስፋልት ኮንክሪት መነጠፉም ክብረወሰን ላይ ሰፍሯል፡፡


ከዓለም ሃብታም አገሮች ተርታ
ኳታር በድፍድፍ ነዳጅ ና ተፈጥሮ ጋዝ በተገነባው ኢኮኖሚዋ ከዓለማችን ሃብታም አገራት ተርታ ትሰለፋለች፡፡    ነዳጅ የኢኮኖሚ ዋልታዋ ሲሆን በጥልቀት ከተቆፈሩ ጉድጓዶች አንዱ 12290 ሜትር ተለክቷል፡፡ ኳታር ከሉክሰምበርግ፣ ስዊዘርላንድና ሲንጋፖር በመቀጠል አራተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ የዓለም ሃብታም አገር ናት፡፡  አንድ የኳታር ዜጋ የነፍስ ወከፍ ገቢ እስከ 100ሺ ዶላር ይደርሳል፡፡


አረቢያን አጋዘን
አረቢያን አጋዘን የኳታር ብሄራዊ እንስሳ ሆኖ ይታወቃል፡፡ ይሄው አጋዘን  መሰል እንስሳ የኳታር ኤርዌይስ ሎጎ ሆኖ ያገለግላል፡፡ በ1972 እኤአ ላይ ከዱር የጠፋው እንስሳ ከ10 ዓመት በኋላ እንደገና ወደ ዱር እንዲመለስ በማድረግ በማድረግ የኳታር መንግስት ከምድር ገጽ እንዳይጠፋ ተረባርቧል፡፡



በዓለም ዋንጫ ታሪክ ከፍተኛው የገንዘብ ሽልማት
በዓለም ዋንጫው ታሪክ ከፍተኛ የሽልማት ገንዘብ የተመደበ ሲሆን አጠቃላይ መጠኑ 440 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ ከ4 ዓመታት በፊት ራሽያ ካስተናገደችው 19ኛው የዓለም ዋንጫ በ40 ሚሊየን ዶላር ጭማሪ አሳይቷል፡፡ የዓለም ዋንጫው አሸናፊ 46 ሚሊዮን ዶላር የሚያገኝ ያገኛል፡፡ በ21ኛው ራሽያ ላይ 38 ሚሊዮን ዶላር፤ በ20ኛው ብራዚል ላይ 35 ፤ በ19ኛው ደቡብ አፍሪካ ላይ 30፤ በ18ኛው ጀርመን ላይ 20  እንዲሁም በ17ኛው በጃፓንና ደቡብ ኮርያ ላይ 8 ሚሊዮን ዶላር ለዋንጫው አሸናፊዎች ተሸልሞ ነበር፡፡



ሌሎች ተሳታፊዎች የሚሸለሙት
በ22ኛው የዓለም ዋንጫ ለሁለተኛ ደረጃ 30 ሚሊዮን ዶላር፤ ለሶስተኛ ደረጃ 27 ሚሊዮን ዶላር፤ ለአራተኛ ደረጃ 25 ሚሊዮን ዶላር፤ ከአምስት እስከ 8ኛ ደረጃ ለሚያገኙት 17 ሚሊዮን ዶላር፤ ከ9 እስከ 16ኛ ደረጃ ለሚያገኙት 13 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ከ17 እስከ 32ኛ ደረጃ ለሚኖራቸው 9 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ የሚከፈል ይሆናል፡፡


የጭልፊት አደንና በረራ ስፖርት
በኳታር ጭልፊት ማልመድ፤ ልዩ የአደንና የበራራ ውድድር ማካሄድ የእግር ኳስን ያህል  አድናቂዎች እያፈራ ነው፡፡  የአየር ሙቀቱ ለጭልፊቶቹ ተስማሚ በሚሆንበት ጊዜ  ለአሸናፊዎች ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማቶች እየተዘጋጀ ልዩ ስፖርታዊ ውድድሮች ይካሄዳሉ። ጭልፊቶች ከኳታራዊያን የእለት ኑሮ  ፈጽሞ የራቁ አይደሉም፡፡ በዶሃ ከተማ ያሉ የጭልፊት መሸጫ ሱቆች የቅንጦት መኪና ከሚሸጥባቸው ማዕከሎች ደረጃቸው ይስተካከላል፡፡ ዋጋቸው ከ2000 ፓውንድ ጀምሮ እስከ 200ሺ ፓውንድ ይደርሳል፡፡



የግምሎች ሽቅድምድም

በኳታር ተወዳጅ ከሆኑ ስፖርቶች የግምሎች ሽቅድምድም ዋንኛው ነው፡፡ ስፖርቱ በዶሃ ከተማ ውስጥ አልሻሃንያ የሚባል ዘመናዊ የመወዳደርያ ትራክ ተሰርቶለት የኳታር ባህል መለያ ሆኗል፡፡  የስፖርት አይነቱ የቱሪስት መስህብ ሆኖ ቆይቷል። ከዶሃ መሃል ከተማ የአንድ ሰአት የመኪና መንገድ ርቆ የሚገኘው አልሻሃኒያ በግመሎች የሚካሄዱ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ውድድሮችን ያስተናግዳል፡፡ በአንድ አመት ውስጥ ከ6000 በላይ ግመሎች በዚህ ውድድር ይሳተፋሉ፡፡ ተወዳዳሪ ግመሎች በሰዓት እስከ 40 ማይል ይሮጣሉ፡፡


ቡርጃ ዶሃ
በዶሃ ከተማ ከሚገኙ አስደናቂ  ህንፃዎች ቡርጃ ዶሃ ታወር አንዱ ሲሆን በፈረንሳዊው አርክቴክት ጂን ኖቭል የተሰራው ባለ 48 ፎቅ ህንፃ ነው፡፡


 ማቻቡስ
ማቻቡስ የኳታር ተወዳጅ ብሄራዊ ምግብ ነው፡፡ ከሩዝ፤ ስጋ፤ ሽንኩርት፤ ቲማቲም እና ከጀተለያዩ ቅመማ ቅመሞች ጋር ተዋህዶ ይሰራል፡፡


ስፖርት አዘጋጅነት በኳታር
በ22ኛው የዓለም ዋንጫ መስተንግዶ ኳታር ከዓለማችን ታላላቅ የስፖርት መድረኮች የመጀመርያውን ማዘጋጀቷ ነው፡፡  በ2006 እኤአ ላይ ያዘጋጀችውን የኤስያ ኦሎምፒክ በ2030 እኤአ ላይም እንድታስተናግድ ተመርጣለች፡፡


አዳዲስ ታሪኮች የበዙበት የዓለም ዋንጫ
22ኛው ዓለም ዋንጫ  በታሪክ ትንሿ አገር የምታዘጋጀው፤ በፈረንጆች አዲስ አመት ዋዜማ ለመጀመርያ ጊዜ የሚካሄድ፤ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ እግር ኳስ አፍቃሪዎችና ቱሪስቶች የሚሳተፉበት፤ በድምሩ እስከ  5 ቢሊዮን ተመልካች እንደሚያገኝም የተገመተ ፤ እስከ 7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ሊያስገኝ እንደሚችል የተጠበቀ ነው፡፡



የምንግዜም ውዱ የዓለም ዋንጫ

በ220 ቢሊዮን ዶላር ወጭው የምንግዜም ውዱ ዓለም ዋንጫ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ከብራዚልና ከራስያ ዓለም ዋንጫዎች በ10 እጥፍ፤ ከደቡብ አፍሪካ ዋንጫ በ64 እጥፍ የሚልቅ በጀት ወጥቶበታል፡፡



*********

ግሩም ሠይፉ_ አዲስ አድማስ ጋዜጣ 

https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=30194:%E1%8B%93%E1%88%88%E1%88%9D-%E1%89%A0%E1%8C%89%E1%8C%89%E1%89%B5-%E1%8B%A8%E1%88%9A%E1%8C%A0%E1%89%A5%E1%89%80%E1%8B%8D-%E1%8B%A8%E1%8B%93%E1%88%88%E1%88%9D-%E1%8B%8B%E1%8A%95%E1%8C%AB-%E1%8A%90%E1%8C%88-%E1%89%A0%E1%8A%B3%E1%89%B3%E1%88%AD-%E1%8B%AD%E1%8C%80%E1%88%98%E1%88%AB%E1%88%8D&Itemid=101

https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=30164:%E1%8B%A8%E1%88%B0%E1%8B%93%E1%88%8A-%E1%89%B0%E1%88%B0%E1%88%9B-%E1%88%A5%E1%8A%90%E1%8C%A5%E1%89%A0%E1%89%A3%E1%8B%8A-%E1%8B%B2%E1%8D%95%E1%88%8E%E1%88%9B%E1%88%B2-%E1%89%A0%E1%8A%B3%E1%89%B3%E1%88%AD&Itemid=276


ዶሃ:- የባሕረ ሰላጤዋ ዕንቁ
(ከመኩሪያ መካሻ)

***************
የባብ ኤል ባህር ዳርቻ ነው። መሻሽቷል። ሂልተን ዶሃ ስምንተኛው ፎቅ ላይ ነው ያለሁት። ቁጥር 81ዐ። ከዚያ ፎቅ ላይ የዶሃ ከተማን ዙሪያ ገባ መመልከት ይቻላል። በቀን ብርሃን ዶሃን በወፍ በረር ከመቃኘት ይልቅ አመሻሹን መመልከት የልብ ሃሴትን ይሰጣል። ዶሃ የካጣር ዋና ከተማ ናት።


በመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢተ ኢሳይያስ የተጠቀሰውን ምዕራፍ 21ን መለስ ብዬ አነበብኩ። ‹‹ዐውሎ ነፋስ ከደቡብ እንደሚመጣ፣ እንዲሁ ከሚያስፈራ አገር ከምድረ በዳ ይወጣል›› ይላል። አዎን! Qatar ካጣር፣ (አንዳንዶች ኳታር ይሏታል) ምድረ በዳ ናት። ዳሩ ግን የምታስፈራ ምድረ በዳ አይደለችም። እንዲያውም ‹‹ማርና ወተት የሚፈልቅባት›› ቢባል ያንሳታል እንጂ አይበዛባትም። ይህች ትንሽዬ የባህረ-ሰላጤ ሀገር በዕንቁና በጥቁር ወርቅ ሀብቷ መትረፍረፍ ሰማይ ጥግ ደርሳለች።
የዛሬዋ ካጣር (Qatar) ከመመሥረቷ በፊት ጥንታዊቷ ካጣር የዕንቁ ንግድ የሚካሄድባት ነበረች። ከቻይና፣ ከአውሮፓ፣ ከአፍሪካውያን ጋር ስትነግድ ኖራለች። በ2ዐኛው ክፍለ ዘመን በእንግሊዝ የበላይ ጠባቂነት ሥር ስትተዳደር ቆይታለች። በ1971 (እ.ኤ.አ.) ነው ነፃነቷን የተጐናፀፈችው። ነፃነቷን ከማግኘቷ በፊት እንግሊዞች ባወጡት የነዳጅ ሀብት ትንሽየዋ ሀገር ፈረጠመች። ነፃነቷን ከመጐናፀፏ አንድ ዓመት በፊት ደግሞ የተፈጥሮ ጋዝ አገኘች። ከዚህ በኋላማ ማን ይድረስባት። ሀብት፣ በሀብት ሆነች። ተድላና ደስታ በእያንዳንዱ ካጣሪ ቤት ውስጥ ገባ። በነገራችን ላይ የዜጋው አማካይ የገቢ መጠን ከ9,5ዐዐ ዶላር በላይ ሁኗል። እስቲ ይህን ገቢ ከኢትዮጵያውያን ገቢ ጋር አስሉት፣ ከ14 እጥፍ በላይ ነው። ይህ የሀገሪቱ ሀብት ለ3ዐዐሺ ዜጐቿ ይከፋፈላል። በካጣር አስገራሚው ነገር የውጭ ሀገር ዜጋ ከሀገሬው ዜጋ በአሥር እጥፍ መብለጡ ነው። በየስፍራው የፓኪስታንን፣ የህንድን፣ የሲሪላንካን፣ የኔፖልን፣ የፊሊፒንስን፣ የዩክሬይን ወዘተ. ዜጐች የሀገሪቱን ህይወት ወደፊት ይመራሉ። ለአንድ ካጣሪ አሥር የውጭ ዜጋ ይደርሰዋል እንደማለት ነው።
ሳውዲን ከሳውዲ ቤተሰብ (House of Saud) የወጡት እንደሚመሯት ሁሉ ካጣርን የአል-ታኒ ቤተሰቦች (House of Thani) ይመሯታል። የዶሃን የዘንድሮውን ዓለማቀፍ ፎረም (Doha Forum) በንግግር የከፈቱት ዘንካታው ሼህ አልታኒ (ታማም ቢን ሃማድ አልታኒ) ነበሩ። ዛሬ በዓለማችን ታዋቂውን የአልጀዚራ የቴሌቪዥን ጣቢያ 15ዐ ሚሊዮን ዶላራቸውን ሆጭ አድርገው ያቋቋሙት እኚሁ ሰው ናቸው። በካጣር ከሌላው የዐረብ ዓለም የተሻለ ዘመናዊነትና የሴቶች መብት ይከበራል። በዶሃ ጐዳናዎች ረጃጅም ሌክሰስና ጂኤምሲ (GMC) መኪናዎችን ሴቶቹ በነፃነት ያሽከረክራሉ። የእኛ ሴቶች የሚያዘወትሯት ቪትዝ ትኖር ይሆን? ብዬ ነበር፤ አንድም ለዓይን የለችም። የካጣር ሴቶች ተነግሮ የማያልቅ ውበት አላቸው። ከጥቁሩ ሂጃብ ውስጥ ለተመለከታቸው የዕንቁ ፈርጦች ናቸው። ከነዚሁ ሴቶች አንደኛዋና ወደ ዶሃ የጠሩኝ ወይዘሮ ሎልዋህ ራሽድ አልካጠር ነበሩ። አዲስ አበባ ሲመጡ የካጣር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሆነው ሲሆን፣ አሁን ዶሃ ፎረም ላይ ሳገኛቸው በስልጣናቸው ጨምረው ጠበቁኝ። በሚፍለቀለቅ ፈገግታቸው ተቀበሉኝ። ‹‹ሹመት ያዳብር!›› አልኳቸው። ‹‹በናንተ መጀን የኢትዮጵያ ምልኪ (Omen) መልካም ነበር፣ ይኸው ለዚህ በቃሁ›› አሉኝ። በሉ፣ ይበርቱ!›› ብያቸው ተለያየን።
ከፊት ለፊት በሻይ ጠረጴዛ ዙሪያ ወ/ሮ ሙፈሪያት፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ከባለቤታቸው ጋር፣ አምባሳደሯ ወ/ሮ ሳሚያ ያወራሉ። ጠጋ ብዬ ተወወቅሁ። አለፍ ስል ወርቅነህ ገበየሁን ተመለከትኩ። ለሠላምታ እጄን ስሰነዝር በቁመታቸው ልክ የሞቀ ሠላምታ ሰጡኝ። ከዐቢይ መንግሥት ወዲህ የባለስልጣኖቻችንን የባህርይ ለውጥ ተመለከትኩ። ከመጀነን ይልቅ ሠላምተኛ ሆነዋል። ከእኔ ትይዩ የፍልስጤሟ የፖለቲካ ሰውና ቃል አቀባይ ሃናን አሽራዊ ተከበው ያወራሉ። እሳቸውንማ መተዋወቅ አለብኝ ብዬ ተጠጋሁ። ተዋወቅኳቸው። ‹‹ኢትዮጵያዊ ነኝ፣ ኦሪያና ፋላቺ የፃፈችውን የአቡ አማርን (የያሲር አረፋት የሽምቅ ስም) ቃለምልልስ ወደ ሃገሬ ቋንቋ ተርጉሜ አስነብቤያለሁ›› አልኳቸው። ፊታቸው ደስታን ረጨ። ፎቶ ራስ-ገጭ (ሰልፊ) ተነስተን ተለያየን። ሃናን ደስ አላቸው፤ እኔም ውስጤ ደስታን አዝሎ ተሰናበትኳቸው።
አለፍ እንዳልኩ በግራንድ ሸራተን መስተናገጃ ስፍራ ቡና ማፍያና ማቅረቢያ ስኒዎች የደረደረ ሰው ተመለከትኩ። ዕጣንም አጠገቡ እያጨሰ ሀድራው ሞቅ ብሏል። የቡና ሱሴ ውል አለብኝ። የሊሙ ኢናሪያን ቡና ሲለቅምና ሲጠጣ ላደገ ለእኔ ዓይነቱ ሰው ቡና ሁሉም ነገር ነው። የግራንድ ሸራተኑ ቡና ከእኛ ሀገሩ ቡና ጋር አይመሳሰልም። ልዩ አቀራረብና መልክ አለው። እንደኛው ዓይነት የፈረስ ጭራ የመሰለ ቡና አለመሆኑ ደንቆኛል። ጠጋ ብዬ ቡና ቀጂውን ሰዒድ አቡበከርን ‹‹ይቻላል?›› አልኩት። ግማሽ ፍንጃል ለቅምሻ የሚሆን ቀዳልኝ። ስመለከተው ጠጅ ሊያስቀምሰኝ የቀዳልኝ እንጂ ቡና አይመስልም። ለመጀመሪያ ጊዜ ብጫ ቡና ልጠጣ ነው። ፉት ስላት አለቀች። ፍንጃሉን መለስኩለት። ደገመኝና ቴምር ሰጠኝ፤ የሚገርም ቴምር፣ የሚገመጥ ቴምር ነበር።
የካጣር ቡና አይቆላም። ጥሬው ተጨምቆ ነው የሚፈላው። ለዚህም ነው መልኩ ብጫ የሚመስለው። ፍፁም አርኪ ቡና ነበር። ወዲያው ሱሴን አበረደልኝ። ‹‹ሹክረን›› ብዬ ሰዒድን ተሰናበትኩና ወደ ማረፊያዬ ተመለስኩ። የኤሌክትሮኒክ ቁልፉን ለበሩ አሸተትኩት። ተበረገደ። ለዓይን ያዝ ማድረግ ጀምሯል። የቁጥር 81ዐን መስኮት ከፍቼ ቀዝቃዛውን አየር ማግ፣ ማግ አደረኩ። የተለየ ጠረን አወደኝ። የቱስካኖ ሲጋራም፣ የሺሻም ሺታ መሰለኝ። ለማንኛውም ወደ ባህሩ ዳርቻ ልውጣ ብዬ ወደዚያው አመራሁ። የባብ ኤል ባህር ሰርጥ ዳርቻ አሸብርቋል። ከቡና ቤቱ የሚፈሰው ሙዚቃ ይንቆረቆራል። የሪታ ኦራ ‹‹Let you Love me›› ሙዚቃ ነው። የዌስት ቤይ የባህር ወጀብ ፋልማውን ተጠግቶ ይገማሸራል። ከባህሩ ወጀብ ጋር የቀዘቀዘ አየር እየማጉ ጊዜያቸውን ያሳልፋሉ። ነጫጭ ጀለቢያቸውን የለበሱ አሚሮች፣ ሼኮች፣ የዶሃ እመቤቶች ተቀምጠው የሺሻቸውን ኵርቢት ይምጋሉ። ስለ ቢዝነስ ያወራሉ። ስለፍቅርም ሊሆን ይችላል የሚያወሩት። አንዱ ሼህ ከኋላዬ ከሎንደን የቢዝነስ አጋሩ ጋር በሞባይሉ ያወራል። ጆሮዬን ጣልኩበት። በዶሃ 2ዐ22 በሚዘጋጀው የዓለም ዋንጫ ውድድር ስለሚያስገባው ዕቃ ነበር ድርድሩ። ‹‹ሦስት ቢሊዮን ነው?›› አለው። ጆሮዬን አላመንኩም። ሦስት ቢሊዮን! ‹‹ከሎንደን ወገን ከ2.6 እስከ 3 ቢሊዮን ዶላር ቢሆን ነው›› ይለዋል። ‹‹ችግር የለም ቶሎ እንዲገባ ይሁን!››። ‹‹Let you love me›› ሙዚቃን በዓይን የማዬት ያህል በኦራ ድምጽ ሲንቆረቆር ወደ ሌላ ትዝታ ይዞ ይነጉዳል። ሺሻ ይጨሳል፣ ድርድር ይካሄዳል። የዶሃ ወይዛዝርት ለሁለት፣ ለሦስት፣ ሆነው በሺሻ ማጨሺያ ክፍሎች ሺሻውን ይምጉታል። የዶሃ ምሽት እንዲህ እየተንተከተከች ከሺሻው ጭስ ጋር የዶሃ ወይዛዝርትና አሚሮች ሃሳባቸውን አራግፈው ከዶሃ ሂልተን ወደየቤታቸው ይለያያሉ።
ከባህሩ ፋልማ ላይ ተቀምጨ ስቆዝም ባህሩ ላይ ቱሪስቶች ምሽቱን ተጠግተው በፈጣን ጀልባ ይንሸራሸራሉ። እኔን ባደረገኝ ያሰኛል። መልካም ያበሻ ቅናት። በመሃሉ ጨረቃዋ ሰማዩን ቀዳ ከባህሩ ስትወለድ ታየችኝ። እኔ ከልምዴ ጨረቃን ሰማይ ሲያዋልድ ነው የማውቀው። በገልፍ ሀገሮች ግን ባህር ቀዳ የምትወጣ ነበር የምትመስለው። ከዚያም ባህሩ ላይ ባውዛዋን ረጨች። ለካስ ዐረቦች ከጨረቃ ጋር ያላቸው ቁርኝት ከምንም ተነስቶ እንዳልሆነ ገባኝ። ድምቀቷ ጤፍ የሚያስለቅም ነበር። ‹‹Let you love me›› ቀጥሏል።
ፋታ ሳገኝ ‹‹መቀመጥ-መቆመጥ›› በሚለው መርህ መሠረት ወጣ ማለት ፈለግሁ። የሆቴሉን አስተናጋጅ ግብፃዊ መሀመድን ‹‹ዬት ሄጄ ታሪካዊ ነገር ብቃኝ ትመክረኛለህ?›› ስል ጠየኩት። ‹‹ወደ ሱቅ ዋቂፍ ሂድ!›› ሲል መከረኝ። መቼም ዶሃና የዶሃ ፎቆች የሚጠገቡ አይደሉም። ሁሉም ፎቆች ትናንት አልቀው ርክክብ የተደረጉ የሚመስሉ ጥርትና ልቅም ያሉ ናቸው። የፎቆች ዝናብ በዶሃ የዘነበ ይመስላል። ዲዛይናቸው ምርጥ የተባሉና አስደማሚ ናቸው። የዶሃ ዘንባባዎች እንደ ክብር ዘብ በሰልፍ ቆመው ይዘናፈላሉ። ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ፈጥረዋል። አንዱን አይተው ሳይጨርሱ ሌላኛው ፎቅ ይማርካል። የከተሜነት አዋሲስ (illusion) ሰቅዞ ባለ በሌለ ሀይሉ ይይዛችኋል። ምናለ የእኛ አርክቴክቶች ለአንዲት ቀን ዕድል አግኝተው ቢያዩዋት ያሰኛል። የአል-ታኒ ቤተሰቦች ገንዘባቸውን በሀገራቸው ግንባታ ላይ ማዋላቸውን መመስከር ይቻላል። ከቤጂንግ፣ ወይም ከኒውዮርክ ፎቆች በላይ የጐብኚን ዓይን መማረክ የሚችሉ ናቸው። ፎቆች ላይ የሚለጣጠፉ ማስታወቂያዎች ዓይን አይረብሹም። ምናለ የእኛዎቹ የከተማ አስተዳዳሪዎች ዶሃን በጐበኙ ያሰኛል። የኢቢሲው አብዱል ጀሊል በህንፃዎቹ ከመማረኩ የተነሳ ቀንም ማታም ህንፃዎቹን ፎቶ ያነሳል። ‹‹ምን ዓይነት ተአምር ነው?›› እያለ መልስ የሌለው ጥያቄ ይጠይቃል።
እስቲ የዶሃን ታላቅ ሱቅ ልጐብኝ ብዬ ወደ ሱቅ ዋቂፍ (Waqif) አመራሁ። ሱቅ ዋቂፍ ከዶሃ ዘመናዊነት መንጥቆ ወደ ቀድሞ የዶሃ ጥንታዊነት የሚወስድ ቋሚ ገበያ ነው። ይህ የደራ ገበያ አልባሳት፣ ቅመማ-ቅመሞች፣ ዕጣኖች፣ ሽቱዎች፣ የዐረብ ጣፋጮች፣ የስጦታ ዕቃዎችና ስዕሎች ይገኙበታል። ከካጣር ዘመናዊነት ዓለም አውጥቶ የካጣር ጥንታዊነትን ለመጎብኘት ትክከለኛው ሥፍራ ሱቅ ዋቂፍ ለመሆኑ ጥርጥር የለውም። ባለእጆችና ባህላዊ ልብስ ሰፊዎች ይታዩበታል። የሶሪያ፣ የሊባኖስ መመገቢያ ሥፍራዎችና የሺሻ ማጨሻዎች ዓይንና ልብን ሰቅዘው ይይዛሉ። ዋጋቸው ግን ለአበሻ ኪስ የሚሆኑ አይደሉም። በዓይን ጠግቦ መውጣት የሚቻልበት ሥፍራ ሱቅ ዋቂፍ ብቻ ይመስለኛል።
ከጣርን ከገልፍ ሀገሮች ሁሉ እጅግ ተፈላጊ ያደረጋት ስትራቴጂካዊ አቀማመጧ ነው። የአሜሪካና የእንግሊዝ የአየርና የህዋ ኦፕሬሽን ማዕከል የሚገኘው እዚያ ነው፤ በአል ኡዴድ የአየር ምድብ። ይህ የኃያላን ሀገራት የዕዝና ቁጥጥር ማዕከል ከኢራን እስከ አፋጋኒስታን ዘልቆ 17 ሀገራትን ይቆጣጠራል። ስለዚህ ካጣር ዋና ስትራቴጂካዊ ማዕከልና ለአሜሪካኖቹ እጅግ አስፈላጊ ሀገር ናት። በዚህ ልዩ ቦታዋ ዓለማቀፋዊ ኮንፈረንሶችን ታዘጋጃለች። የዘንድሮው የዶሃ ፎረም እንኳ 4ዐዐዐ ሰዎችን ከ1ዐዐ ሀገራት አስተናግዷል። በዚህ ሸብ-ረብ ውስጥ ዋነኛውን ሚና የሚወጣው አልጀዚራ ሲሆን፣ የአልጀዚራ ጋዜጠኞች በአስተባባሪነት፣ በመድረክ መሪነት፣ በጠያቂነት፣ ሪኮርድ በማድረግ ይሳተፋሉ። የእኛን የኢትዮጵያውያንን ጉዞ ያደራጀልን ወዳጄ፣ ዕውቁ ጋዜጠኛና የአልጀዚራ የኢትዮጵያ የቢሮ ሃላፊ መሀመድ ጠሃ ተወከል በዚህ አጋጣሚ ሊመሰገን ይገባል። ሀገር ቤት ገብቼ ኢ-ሜሌን ስከፍት ሙሉ ዶክመንቱ ደረሰኝ። ደስም አለኝ።
የዶሃ ፎረም ስብሰባ እንደተጠናቀቀ ጉብኝቴን የቀጠልኩት በአልጀዚራ ጣቢያና የሚዲያ ማሠልጠኛ ተቋም ጉብኝት ነበር። አልጀዚራ ሚዲያ ከሥራውና ካለበት ህንፃ ጋር ሲወዳደር ‹‹አልጀዚራ እዚህ ሆኖ ነው እንዴ ዓለምን የሚያነጋግር ሥራ የሚሠራው?›› ያሰኛል። የተቋሙ አባል የሆነውና አስጐብኚያችን ሙንታሲር ሙራይ እንደነገረኝ ‹‹ለሚዲያ ጥንካሬ ዋናው ህንፃና ዕቃ ሳይሆን የያዘው ሙያተኛ ነው ወሳኙ›› ሲል ነበር የሰው ኃይልን ወሳኝነት የገለፀልኝ።
*****
የመጨረሻው የዶሃ አዳሬ ዶሃን ብቻ ሳይሆን ሀገሬን እንዳስብ አደረገኝ። አንዲት የባህረ-ሰላጤ ትንሽ ሀገር 3 ሚሊዮን ለሚበልጡ የውጭ ሀገር ዜጐች የሥራ ዕድል ፈጥራ ስታሰራ ስመለከት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ዬት ነን? እላለሁ። ቅናት አይሉት የውድድር አባዜ ብቻ በእዝነ-ልቡናዬ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ተመላለሱብኝ። ዛሬ የሚታየው የኢትዮጵያውያን እርስ በርስ መናከስ፣ መበላላትና የሰው ልጅ ሊፈጽመው ይችላል ተብሎ የማይታሰብ የአውሬነት ባህርይ ከየት መጣ? ስል ጠየቅኩ። ይህች የባህረ-ሰላጤ ዕንቁ ከተማና የእኛ ከተሞች ህይወት በንጽጽር በዓይኔ እየተደቀኑ በማይጐረብጠው፣ እጅግ ምቾት - በምቾት በሆነው 81ዐ ክፍል ውስጥ ዕንቅልፍ በዓይኔ ሳይዞር ነቃሁ። ለካስ ምቾትም እንቅልፍ ይነሳል?
ወለል ብሎ የዶሃ ሰማይ በርቷል። በመስኮት ስመለከት የባብ ኤል ባህር ዳርቻ ህይወት እያንሰራራ ነው። የባህረ-ሰላጤው ባህር ፋልማውን እየገጨ ይፎክራል። የዶሃ-ህይወት መንተክተኳን ቀጥላለች። በስሱ የተለቀቀ የEasy Listening ሙዚቃ ጆሮ ሰርስሮ ይገባል። የልብ ሀሴትን ይሰጣል። ‹‹Lake of Peace›› ሙዚቃ ነበር የሚንቆረቆረው።
አሁን ሰዓቱ ደረሰ። በፍቅር የጣለችኝን ዶሃ ለቅቄ መብረሬ ነው። ከኢትዮጵያ ከመጣነው የቡድን አባላት ጋር የሃማድ አለማቀፍ አይሮፕላን ማረፊያን መንገድ ተያያዝነው። የዶሃን ልዩ ከተማነት፣ የህዝቡን ሥርዓትና እንግዳ አክባሪነት እያደነቅን ሃማድ አለማቀፍ አይሮፕላን ማረፊያ ደረስን። በአይሮፕላን ጣቢያው ልክ እንደ ግራንድ ሸራተኑ የካጣር ቡና (ቃዋ ነው እነሱም የሚሉት) ተፈልቶ ጠበቀን። አንድ ፍንጃል ቃዋዬን አወራርጄና ቴምር ቀምሸበት ዶሃን ተለየሁ። ዶሃ የባህረ-ሰላጤዋ ዕንቁ ከተማ ሁሌም ከአእምሮዬ የምትጠፋ አትሆንም። የሪታ ኦራ ‹‹Let you love me›› አሁንም በውስጤ ይሞዝቃል።



https://www.facebook.com/photo/?fbid=5979201378771420&set=a.100394486652168

https://www.youtube.com/watch?v=TiTg-op7yc0

2፡የዓለም ዋንጫ 2022፡

የዓለም ዋንጫ 2022

የዓለም ዋንጫ 2022

የዓለም ዋንጫ 2022

የዓለም ዋንጫ 2022